
"ሁሉም ስላጠፉ የእኔም ጥፋት ችላ ሊባል ይገባል ወይም እኔ ብቻ ሳልሆን ሁሉም ነው የሳቱት" የሚለው እና ለራስ የመማር ዕድልን መንፈግ ፍጹም የሆነ ስንፍና ነው። ይሄ ነገ ተመሳሳይ ጥፋት ለማጥፋት የሚሰጥ ማረጋገጫ ነው። እንዲህ የሚል ሰው ነገ በተመሳሳይ ወይም በባሰ ጥፋት ላይ ታገኙታላችሁ።
ለምሳሌ ሁሉም ሰው "ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ያሻግረናል" ብሎ ስላመነ፤ "የኔም በሰዓቱ እንዲህ ብሎ መቀበል እና ማመን ችግር የለውም" የሚል ሰው፤ ነገም ተመሳሳይ ጥፋት የሚያጠፋ ሰው ነው።
ይሄ ልጆች ያላቹ ወላጆች ዘወትር የሚገጥማችሁ የስንፍና መልስ እኮ ነው። "ስልክ አይቻልም፣ አይሰጣችሁም!" ስትሏቸው ለልጆቻችሁ ፥ ስልክ ጎበዝ ተማሪ ለመሆን እንዴት አስፈላጊ እና ጠቃሚ እንደሆነ አይደለም የሚያብራሩላችሁ። ይልቁንስ የሚሏቹ አንድ ነገር ነው። "ሁሉም ተማሪዎች ትምህርት ቤት ውስጥ ስልክ አላቸው፤ ሁሉም ናቸው እንደዛ የሚያደርጉት ስለዚህ እኔም እንደ ሁሉም ልሁን።" ይሄን የልጆች መልስ ነው ዛሬ አዋቂ ስንሆን የምንመልሰው።
በሕይወት መንጋነትን ከሰዎች ልታስቀሩ አትችሉም። ማስቀረት የምትችሉት እናንተ መንጋ አለመሆንን ብቻ ነው። ሕዝብ አለመሆንን ግን ማስቀረት እንችላለን። ልጆቻችንም ገና ልጅ እያሉ መማር ያለባቸው ብቻቸውን የመቆም ብቃትን ነው። ሁሉም ስለተሳሳቱ የኛን ጥፋት፤ ለጥፋቱም የምንቀበለውን ቅጣት ዝቅ አያደርገውም። ተፈጥሮ ለዚህ ዓይነት የጅልነት ምክንያት ቦታ የላትም። ሁሉም ርቃኑን ነው ብሎ ዝናብ ከመዝነብ አያቆምም። ማንም መጠለያ የለውም ብሎ የተፈጥሮ ዑደት አይታጎልም። ስለዚህ ይሄ ሰበብ እራሳችንን ለማጽናናት የስነልቦና ጥገጋ ብቻ ነው የሚያደርገው። መማር የሚፈልግ ሰው ደግሞ ከእንደዚህ ዓይነት የስነልቦና ሕክምና ራሱን ያርቃል። መማርን የሚወድ ሰው ርቃኑን የመቆም ድፍረት አለው። "ጠቢብን ተቸው ይወድሃል" እንዳለው ጠቢበኛው ሰሎሞን "ሰነፍን ደግሞ ተቸው ይጠላሃል" ነው መልሱ።
ለመማር እና ለመለወጥ የሚፈልግ ሰው ከብዙ ሰዎች ጋርም ይሁን ብቻውን ጥፋት ካጠፋ ኋላፊነት ከመውሰድ ፈጽሞ አይቆጠብም። ከጥፋቱ ለመማር እንጂ የሚቸኩለው ፥ ስለሚሰማው ስሜት አይደለም። በጓደኝነትም ሆነ በማንኛውም አጋርነት ውስጥ ፈጽሞ ማራቅ ያለብን (ዕድሉ ካለን እና ከቻልን) ስለምንሰጣቸው ትችት ከጥፋታቸው በላይ እንድንጨነቅ የሚያደርጉን ሰዎችን ነው። እነዚህ ለለውጥ እና ለዕድገት ጸር ናቸው። ቁስላቸው ከመዳኑ በላይ የሚጨነቁት ፥ ቁስሉን እንድናሻሽላቸው ነው።
ስንናገር በነጻነት እንድንናገር የማይፈቅዱልን እና ያን safety (ደኅንነት) የማይሰጡን ሰዎች ሕይወታችንን በመጨረሻ ሲዖል ያደርጓታል። በሕይወት (በተለይ ግብ ላለው ተልዕኮ) ከፍትፍቱ በላይ ስለፊቱ መጨነቅ የለብንም። እርሱ የቢዝነስ ደንበኛ ለማያዝ እንጂ ለሕይወት አጋር አይሆንም።
Comentários