top of page
Search

ችግራችንን እንዴት ነው የምንፈታው?

Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew



የሁሉም ሰው የሕይወት ተልዕኮ ውስጥ የሰዎችን መከራ ማቅለል አንዱ ነው። ብዙዎቻችን ግን ለችግራችን የምንሰጠው መፍትሔ የበለጠ ችግር ይዞብን ይመጣል። እንግሊዝ ሕንድን ቅኝ በገዛችበት ወቅት ተናዳፊ እባብ ቀኝ ገዚዎችን አስጨነቀ። ለዚህ ቀላሉ መፍትሔ እባቦቹን አድኖ መግደል ነበር። ይሄን ለማበረታት ደግሞ ለሕንዶቹ ተናዳፊ ኮብራ እባቦቹን አጥምደው ባመጡ ሰዓት ማበረታቻ ገንዘብ ቃል ተገባላቸው። ሕንዶቹ ግን ማበረታቸውን ለማግኘት ሲሉ ጭራሽ ኮብራ እባቦቹን ማርባት ተያያዙት። እባቦቹን ለመቀነስ የወጣው ሕግ እባቦቹን በብዙ እጥፍ አበዛቸው።



በየቀኑ የሰዎችን ችግር ስሰማ እና ያን መፍትሔ ለመስጠት መጣር ነው ሥራዬ እና ኑሮዬ። ሰዎች ለብዙ ችግራቸው መፍትሔው ቀላል እና ርካሽ እንደሆነ ሲነገራቸው ደስ ይላቸዋል። መፍትሔው ረዥም መንገድ ሊወስድ እንደሚችል ማንም መስማት አይፈልግም፤ በጥልቀት ከሚያስተውሉ ሰዎች በቀር።



ዛሬ በአማራ ክልል የተነሳው ጦርነት ልክ እንግሊዝ እባቦቹን ለማጥፋት እንደሄደችበት ያለ መፍትሔ የሞከሩ ሰዎች የፈጠሩት መከራ ነው። ፋኖን ትጥቅ ማስፈታት አጭሩ የማስገበሪያ መንገድ መስሎ ታያቸው። ይሄው ሀገሪቷን ረዥም የእርስ በእርስ ጦርነት ውስጥ ነከራት። አንድ ቦታ ቶሎ የመድረሻው መንገድ ረዥሙ መንገድ እንደሆነ ብዙዎቻችን የሚገባን አጭሩን መንገድ ከሞከርን በኋላ ነው። እንዴት ነው ግን ችግሮቻችንን የምንፈታው? እንዴት ነው በሕይወታችን ውስጥ ያሉትን ችግሮች የፈታነው ፥ ፈተን የምናውቅ ከሆነ!



መቼስ አንድ ችግር በሕይወታችን ፈተን እናውቃለን። እንዴት ነው ያን ችግር የፈታነው? እንዴት ነው ዘላቂ መፍትሔ የሰጠነው? ያን የመገምገም እድል አግኝታችዋል? በርግጥ ለብዙ ችግራችን ሌሎች ችግሮችን ስንፈጥር ነው የኖርነው። ለዚህም ይመስላል፤ ሀብት ያለው ሰው ልጆቹ እና ቤተሰቦቹ ያልተሳኩለት የሚሆነው። የድኅነትን ችግር ፈቷል፤ ግን ልጆቹን አጥቷል። ወይም ትዳሩን አጥቷል። ወይም ወዳጆቹን። በዚህም ደስታን አጉድሏል። ሌሎች ደግሞ የቤተሰብ ፍቅር አላቸው ግን ጠኔ ፍቅራቸውን ይፈታተነዋል። አንዳንዶች ልጆቻቸውን ጨዋ ማድረግ ችለዋል ግን ፈጣን አዕምሮ እና በራሳቸው የሚቆሙ ልጆች አይደሉም።



ስዊዘርላንድ እያለው የሰማውት ነው። የስዊዝ መንግስት በስልሳዎቹ ከሁለተኛው ጦርነት በኋላ የገጠመውን የቤት እጥረት ለመቅረፍ ባለአንድ ክፍል ጠባብ አፓርትመንቶችን አብዝቶ ገነባ። ከሠላሳ እና አርባ ዓመት በኋላ ግን ሲዊዘርላንድ ውስጥ ከፍተኛ ብቸኝነት ተስፋፋ። አንዱ ምክንያት በእነዚህ ጠባብ አፓርትመንቶች ውስጥ ከአንድ ግለሰብ በላይ መኖር ከባድ ስለሆነ ነበር። ቤተሰባዊ እና የጋሪዮሽ ሕይወት የሚያበረታታ አልነበረም። የቤት እጥረት መፍትሔ ብቸኝነትን በማሕበረሰብ ውስጥ አዋለደ። ቤተሰብን አፈረሰ።



ለችግሮቻችን እንዴት ነው መፍትሔ የምንሰጠው? ግን መጀመሪያ ለችግሮቻችን መፍትሔ እንዴት መስጠት እንደሌለብን ልግለጽ።



1) መለኮታዊ ሰበብ አለመፈለግ፤



ይሄ ከማመን እና አለማመን ጋር አይገናኝም። ግን ራስን ከማወቅ ጋር እንጂ። የብዙዎቻችን ሕይወት ከዚህ የመመረጥ እና የፈተና መንገድ በብቃት የተነሳ የተወገደ ነው። ግን ብዙዎቻችን ራሳችንን አንድ ፐርሰንቱ ውስጥ እንጂ 99 ፐርሰንቱ ውስጥ ከተን ማየት አንሻም። የኛ ሕይወት ውስብስብ በሆኑ የመንስኤ እና ውጤት ጥምረቶች የሚመተር እና የሚጓዝ ነው። ምርጫችን ነው አሁን ላለንበት ውጤት የዳረገን። ችግር ሲፈጠርም ሮጠን የመለኮት እጅ የኛን የኃላፊነት ድርሻ እንዲተካ አንሩጥ። በርግጥ ማስተዋል እና ርጋታን መለመን አንድ ነገር ነው። ግን ማስተዋል እና ርጋታ እየለመኑ መተኛት ካልቻልን ማስተዋል እና ርጋት ወደ እኛ አይመጣም። ለምሳሌ አንድ ነገር አቅደን መፈጸም ሲሳነን ፥ ሰይጣን ሊያሰናክለን ወጥኖ ያደረገው ነው ከሚል እምነትም ሆነ ቃሎች እንራቅ። ከዛ ይልቅ የኛ ሕይወት ለዚህ ዓይነት ፈተና ገና ብቁ እንዳልሆነ በመገንዘብ የራሳችንን ድርሻ ላይ በማተኮር ያን ለመቅረፍ እንጣር።



2) ጊዜ ይፈታዋል በሚል ራሳችንን አናታል፤



ብዙ ነገሮች ስሜት የላቸውም። ማለትም ፍርድ የላቸውም። ኒውትራል ናቸው። ለምሳሌ ስለሞት ስናወራ ፥ ሞትን ልክ እንደ አንድ ግለሰብ አድርገን ነው የምናወራው። ከሞት ጋር ተፋጥጬ፣ ሞት መጥቶብኝ ወይም ከሞት ጋር ተናንቄ የሚል እና ሞትን ግዝፈተ አካል ሰጥተነው ነው የምንናገረው። ከቋንቋ ውበት እና ንግግር አንጻር ከሆነ መልካም። ይሄ ግን አስተሳሰብ ከሆነ የመረዳት አቅማችንን ያሽመደምደዋል። ሞት ከአንድ ሁኔታ ወደ ሌላ የምንሻገርበት ነው። ሽግግር (state) ነው። ልክ ጊዜም ኒውትራል ነው። ምንም ዓይነት የፍርድ ዝንባሌ የሌለው ኒውትራል ሂደት ነው። ጊዜ የመፍትሔ ዘለላዎች የሉትም። በራሱ የሚፈታልን ወይም የሚያባብሰው አንዳች ነገር የለም። ጀግናም አይደለም ፈሪም አይደለም። ታጋሽም አይደለም አይናደድምም። ስለዚህ ለጊዜ ችግራችንን አሳልፈን አንሰጠውም። መታገስም የጊዜ ሳይሆን የኛ ነው። መናደድም የኛ ውሉድ እንጂ የጊዜ አይደለም። ስለዚህ ለጊዜ ችግራችንን በመስጠት የሚገኝ ምንም ነገር የለም። በዕድል እና በክስተት ለመመራት ከመፍቀድ ውጪ።



ይቀጥላል።

460 views0 comments

Recent Posts

See All

የሰንበት ዕይታ - 16

እንቢ ማለትን በምግብ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አከራካሪ ከሆኑ ነገሮች አንዱ እና የተለያዩ ሊቃውንትም ግራ ከሚጋቡበት ነገሮች ውስጥ ንጹሁ የሆኑ እና ንጹሁ ያልሆኑ ተብለው እንስሳት ለምግበ እስራኤል መለየታቸው ነው።...

የሰንበት ዕይታ - 14. የኢዮብ መጽሐፍ እንቆቅልሾች

January 20, 2024 ዊሊያም ብሌክ እንዳለው “በሞኝነቱ የጸና ሞኝ ጠቢብ ይሆናል።” “ያለጽናት አይደለም ጥሩ አማኝ፤ ጥሩ ኢአማኒም መሆን አይቻልም” እንደሚባለው ማለት ነው። አንዴ ያየኸውን ነገር አውቃለሁ...

Comments


  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page