top of page
Search

ሕመም

Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew




ድሮ የምሰራበት የስፖርት ቦታ በትልቁ “NO PAIN NO GAIN ወይም ካለሕመም ምንም የምታገኘው ነገር የለም!” የሚል የተጻፈ መፈክር ነበረው። አንዳንዴ ወደ ኋላ በመሄድ በሕይወቴ ያሳለፉኳቸውን ከባባድ ጊዜዎችን ለማስታወስ እጥርና “ምናለ እንደ ዛ ባልሆን” ልል ይቃጣኛል ፥ ሕመሙን በማስታወስ። ግን ያ ሀሳብ ከአንዱ የአዕምሮ ክፍሌ ሳያልፍ ነው ያን የመስቀል ጉዞ “እሰይ ሆነ ፥ እሰይ ደረሰብኝ” ብዬ በድጋሚ የማፈቅረው። ብዙዎቻችን ያለ መስቀል ትንሣኤ ፈጽሞ እንደማይኖር አይገለጽልንም። እሁድን የሚናፍቅ ቢኖር አርብን መታገስ ይጠበቅበታል።


ሕመምን የምንታገሰው ጀግና  ፥ ስለሆንን ወይም የተለየ ፍጡር ስለሆንን አይደለም።


እንደሚሞት፣ ለዛውም የመስቀል ሞትን እንደሚሞት ራሱ ጭምር እየተናገረ የመጣው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሳይቀር መስቀሉን በቅርብ ርቀት ሲያየው ፥ “ይሄ ጽዋ ፈቃድህ ቢሆን ከእኔ ይራቅ” ብሎ ጸልዪል። የጌታችን ያልተሰማ ጸሎት ይሄ ብቻ ነበር። “ዋጠው፣ ይሄን ጽዋ ጠጣው” ብሎ አባቱ ጨከነበት። አጽናኞችን ግን ላከለት። እውነተኛ አባት የሚያደርገው ይሄን ነው። የሕመምን ጽዋ ለልጆቹ ያስጎነጫል። እውነተኛም እናት ከዚህ የአባት ጭካኔ ጋር ትስማማለች። ምክንያቱም የልጇን ትንሣኤ ትፈልጋለች እና። ልጇ ሁልጊዜ ልጅ ሆኖ እንዲቀር አትፈልግም። ለዚህ ነው እመቤታችን ድንግል ማርያም አንድም ጊዜ ጌታን ከመስቀል ሞት እንደ ሐዋርያው ጴጥሮስ “ልጄ ሆይ ፥ አትሙትብኝ” ብላ ስትከላከል ያልታየችው። ያልተሰማችው። ያ ሞት ያለጊዜው ሲመጣ ብቻ ልጇን ካለጊዜው ከሆነ ሕመም ጠበቀችው እንጂ ፥ በዕድሜው ለሆነው አርብ ግን ድንጋል ማርያም ተባባሪ ነበረች። ይሄ ትንሣኤን ለራሱ ለሚሻ ፥ ለልጆቹ ለሚመኝ ሰው ሁሉ የተጻፈ ታሪክ ነው።



አሁን አሁን ሕይወትን ካለብዙ ነገሮች ማሰብ እያቃተን ነው። በተለይ በምዕራቡ ሀገራት። መብራት፣ ኮምፒውተር፣ ጉግል፣ ፍርጅ፣ መኝታ ቤት የተቀመጠ መጸዳጃ ቤት ፥ ሕይወትን ካለእነዚህ የማያውቅ ትውልድ ነው ያለው። አንዱ ለልጄ “በኛ ጊዜ ጉግል (Google) አልነበረም ስለው አላመነኝም” ብሏል። ምክንያቱም ካለ ጉግል የሰው ልጅ ምን ያህል መረጃን ለማግኘት እንደሚደክም ይሄ ልጅ ፈጽሞ የማይረዳበት ዘመን ነው።



አሁን አሁን ወደ ሕክምና ስፍራ ብትሄዱ የመጀመሪያው የሚሰጣችሁ ነገር ሕመም ማስታገሻ ነው። በየቤቱ የተለያዩ ዓይነት የሕመም ማስታገሻዎች አሉ። መውሰድ ባንፈልግ እንኳ ቢያንስ ከራስ ምታት ማስታገሻ እስከ ተለያዩ ኦፒዎዶች ቤታችን አሉ። እንቅልፍ እንቢ ካለንም ብዙ መጨናነቅ አሁን አያስፈልገንም። በተለያዩ መልኮች የእንቅልፍ ማስተኛ ሽሮፖች እና ክኒን ሞልተውልናል። የሰው ልጅ ብዙ ታሪኩ ግን እንዲህ አልነበረም። እስከ አስራዘጠነኛው ክፍለዘመን መጨረሻ ድረስ የሕመም ብቸኛ ምርጫ ጥርስን ነክሶ መቻል ነበር። ምን አልባት ትንሽ ማደንዘዣ አልኮል ይሰጥሃል ወይም የምትነክሰው ነገር ያቀብሉህና ፥ የሰውነትህ አካል ሳይቀር ያለማደንዘዣ ይቆረጥ ነበር። ልክ እንደ ክርስቶስ አጠገብህ የሚያጽናኑህ ይኖሩ ይሆናል እንጂ ያን ሕመም ስለ ሕመሙ ብቻ ተብሎ የሚያስቀረው አልነበረም። ምክንያቱም ለረዥሙ የሰው ልጅ ታሪክ ሕመም የሰው ታሪክ አካል ነበር። የሕክምና ባለሙያዎች እና ተመራማሪዎች ሳይቀር ፥ ሕመምን ለማስቀረት ያደረጉት ጥረት የረዥም ጊዜ ታሪክ አልነበረም። ትልቁም የሳይንስ ትኩረት አልነበረም።



ጆናን በርክ በStory of Pain በሚለው መጽሐፉ እንደጻፈው ኬሚስት ሀምፍሬ ዴቪይ የLaughing Gasን (ላፊንግ ጋዝን) የሕመም የማስታገሻ ባህሪውን ካገኘ በኋላ እንኳ በሕክምናው እና በሳይንሱ ዓለም እንደ ትልቅ ግኝት ተቆጥሮ በቶሎ ወደ ተግባር አልተገባም። ለሕመም ማስታገሻነት በስፋት ጥቅም ላይ እስኪውል መቶ ዓመታት ፈጅቷል ። ሌሎችም የሕመም ማስታገሻዎች፣ ለምሳሌ እንደ ኒትረስ ኦክሳይድ ሲገኝም የሕክምናው ዘረፍ እንደ ዛሬው ተሯርጦ ወደ መጠቀም አልገባም። ጆናን በርክ እንደሚለው የሕመም ትርክት ለብዙ ሰዎች ለመቀበል የሚቸገሩት አልነበረም። ሕመም ለዶክተሮችም ሆነ ለታካሚዎች የሕክምናው እና የመዳን ሂደት አካል ነበር። እንደውም አንዳንድ ሰርጅኖች ያለ ታካሚው የስሜት እንቅስቃሴዎች እና ጩኸት ሕክምናውን ማድረግ አይፈልጉም ነበር።



ከሁሉም በላይ ግን ለብዙ ሰዎች ለብዙ የታሪክ ዘመን ሕመምን ራስን በመቆጣጠር፣ በመግዛት እና በክብር ጨክኖ ማለፍ የማንነት መገለጫቸው እና የጀግንነት ጌጣቸው ነበር። ሕመም የጀግንነት፣ የወንድነት እና የታላቅ ስብዕና መገለጫ ነበር። ሕመምን ሳይመጣ ይለማመዱት ነበር። በሚበሉት ነገር ሳይቀር የሚያቃጥል፣ የሚለበልብ እና ጎምዛዛ ነገር በማብዛት የሕመም የመታገስ ሐሞታቸውን ያጠነክሩ ነበር። በእኔ ዕድሜ ሳይቀር የሚያቃጥል ቃሪያ በምግብ ጠቅልሎ አባቴ ያጎርሰኝ ነበር። ፈጽሞ ያን እንድተፋው አይፈቀድልኝም ነበር። ጨክኜ አኝኬ እድውጠው እንጂ። ከዛ የሚብስ ነገር ሊመጣ ስለሚችል ያን ቃጠሎ ቃሪያ አኝኬ እውጠዋለሁ። የአባትነት ሥራ ልጅን ከሕመም መጠበቅ አልነበረም። ይልቁንስ በየደረጃው ለሕመም ማጋለጥ እንጂ።



ዛሬ ግን የሕክምናው ዘርፍም ተለውጧል። በአሜሪካ ዶክተሮች የሚገመገሙት ታካሚዎች የሕክምናው ፕሮሲጀር ሲካሄድ በተሰማቸው የሕመም መጠን ሆኗል። ምንም ሕመም ካልተሰማቸው ያ ዶክተር ትልቅ እና በጎ ሬቲንግ ያገኛል። ያም ለደሞዝ እና ለእርከን ዕድገት አስተዋጽኦ አለው። ስለዚህ ዶክተሮች ምን ያደርጋሉ? ሱስ እንደሚያሲዝ እያወቁ የተለያዩ የሕመም ማስታገሻዎችን ለታካሚዎቻቸው ያስቅማሉ። ዛሬ አሜሪካ ውስጥ መጨነቅ መድኃኒት አለው። መወፈር መድኃኒት አለው። ትኩረት ማጣት የሚቃም መድኃኒት አለው። ያለመድኃኒት የማይንቀሳቀሱ ጥቂት መጤዎች ብቻ ቢሆኑ ነው። ከ1980ዎች ጀምሮ የዓለም የጤና ድርጅት ሳይቀር እነዚህ የሕመም ማስታገሻ ኦፒዶዎች በስፋት እንዲመረቱ እና ጥቅም ላይ እንዲውሉ መግፋት እና ማበረታታት ጀምረዋል።



የሚገርመው ግን የሕመም ማስታገሻዎች የረዥም ጊዜ ጥቅም እንዳላቸው የሚያሳይ ምንም ሳይንቲፊክ የሪሰርች ውጤቶች አለመኖሩ ነው። ያ ብቻ ሳይሆን አሁን በስፋት እየወጡ ያሉ ጥናቶች እንደሚያሳዩት የሕመም ማስታገሻዎች የቁስሎች የመዳንን ሂደት በጣም እንደሚያዘገዩት ነው። ልክ ነው አንዳንድ የቀዶ ጥገና ሕክምናዎች የግድ የሕመም ማስታገሻዎች (anesthesia) ያስፈልጋቸው ይሆናል። ግን ከየት ወዴት እንደመጣን ብቻ እዩት?



የሰው ልጅ ትልቁ ሀብቱ ለራሱ የሚነግረው ትርክት ነው። ብዙ ጊዜ እንደጻፉኩት የደስተኛ ሕይወት ምንጭ ትርጉም ያለው ሥራ መሥራት እንጅ ምቾት አይደለም። ደሃ ራሱን አጠፋ ሲባል መስማት በጣም ዝቅተኛ ነው። ራስን ማጥፋት እንደ ፊንላንድ፣ ደቡብ ኮሪያ እና መሰል የምቾት መጠናቸው ከፍ ባሉ ሀገራት ላይ ነው የሚብሰው። የሰው ልጅ ሕመምን እና መከራን ለማለፍ የሚታገለው ትግል እና በዚህ ወቅት ለራሱ የሚነግረው ትርክት ነው የደስታው መሠረት። ትርጉም ያለው ሕይወት ማለት ይሄን ሕመም ጥርስ ነክሶ ሲታለፍ ነው። ይሄ ሕመም የትውስታ ማህደራችን (memory) ውስጥ ካልተቀበረ ፥ የምናገኘው ጥሩ ነገሮች እና ምቾቶች ሁሉ አያስደስቱንም። መስቀሉ ነው የትንሣኤው ውበት። ያ ትንሣኤ ውበት የሚኖረው ፥ ልብሳችንን ተከፋፍለው፣ በጦራቸው አይነሳም ብለው ወጋግተው፣ በተሳለቁብን እና ባሾፉብን መኃል ከዛ ሕመም በላይ ሆነን ፥ ከቀናት መሰወር በኋላ ላያስቆሙን ብድግ ስንል ነው። እነዛ ሕመሞች የትንሣኤው ዘላለማዊ ጌጦች ናቸው። ኢዮብ ያለ ሕመሙ እና ጥርሱን ነክሶ ራሱን ሳያዋርድ ሕመሙን መታገሱ ነበር ዖፅ ከምትባል መንደር በላይ ለዘላለም ገዝፎ እንዲታይ፣ እንዲተረክለት ያደረገው። ሰው እንዴት ነው ጌጦቹን የሚርቀው? እንዴት ይሄን የደስታ ምንጭ ከልጆቻችን እናርቃለን?

417 views0 comments

Recent Posts

See All

የሰንበት ዕይታ - 16

እንቢ ማለትን በምግብ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አከራካሪ ከሆኑ ነገሮች አንዱ እና የተለያዩ ሊቃውንትም ግራ ከሚጋቡበት ነገሮች ውስጥ ንጹሁ የሆኑ እና ንጹሁ ያልሆኑ ተብለው እንስሳት ለምግበ እስራኤል መለየታቸው ነው።...

የሰንበት ዕይታ - 14. የኢዮብ መጽሐፍ እንቆቅልሾች

January 20, 2024 ዊሊያም ብሌክ እንዳለው “በሞኝነቱ የጸና ሞኝ ጠቢብ ይሆናል።” “ያለጽናት አይደለም ጥሩ አማኝ፤ ጥሩ ኢአማኒም መሆን አይቻልም” እንደሚባለው ማለት ነው። አንዴ ያየኸውን ነገር አውቃለሁ...

Comments


  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page