top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • 2 days ago
  • 3 min read


አንዳንድ ቃላት ወይም አባባሎች ወይም ጥቅሶች ከመደጋገማቸው የተነሳ የምናውቃቸው ይመስለናል። ወይም በውስጣቸው ያለውን ቁም ነገር ለመመርመር ድግግሞሹ ያዘናጋናል።



አንድ በስራው ስኬታማ የሆነ ወዳጅ አለኝ። “ቀንህ እንዴት ነው?” ስለው፣ “የዕለት እንጀራዬን ለማብሰል እየሮጥኩኝ ነበር” ይለኛል። እኔም በመቀለድ ሥራው ከዕለት እንጀራ በላይ እንደሆነ እና ስኬቱም የብዙዎች የዕለት እንጀራ መሆን እንደሚችል እነግረዋለሁ። “አንተ እኮ የዕለት እንጀራዬን ስጠኝ የሚለው ክፍል ላይ ስትደርስ መዝለል አለብህ” እለዋለሁ፣ ያለውን ሀብት እያሰብኩ።



ነገር ግን ይሄ ቃል ከዕለት ምግብ፣ ከቁርስ፣ ምሳ እና እራት በላይ ትርጉም ሊኖረው ይገባል። ይሄ የሰው ልጆች ሁሉ ጸሎት እንዲሆን ያዘዘው አምላካችን፣ የዕለት ምግባቸውን ከገበታቸው ላይ ማኖር ጨንቋቸው ለማያው ሰዎችም ጭምር ነው። የዕለት እንጀራችንን ስጠን ማለት የዕለት ቁርስን ከመጠየቅ በላይ ከሆነ ምንድነው ትርጉሙ?



ለእኔ ትርጉሙ መታመን ነው። ከእግዚአብሔር በቀር በየትኛውም ነገር ላይ መደገፍ ከእግዚአብሔር በተቃራኒ መቆም ነው። በሚገርም ሁኔታ የሰው ልጅ ሁልጊዜ እንዳከማቸ ነው። ታሪክ ከተጻፈበት ቀን ጀምሮ የምንረዳው ነገር ሰው ለነገ ብሎ ያከማቻል። የነገን ምግብ ማከማቸት ደግሞ በጣም ዝቅተኛው የጥበብ ደረጃ ነው። ጥበበኛው ሰሎሞን ይሄ ጥበብ ለገብረ ጉንዳን ሳይቀር ያላት ጥበብ መሆኑን ይነግረናል። ስለዚህ ማከማቸት፣ ለነገ መቆጠብ እና ማኖር ከስነፍጥረት ጥበብ ጋር የተያያዘ ጭምር ነው። በደመ ነፍስ ያሉ ፍጥረታት ሳይቀር ይሄን የሚያደርጉ አሉና። ይሄን በማድረጋቸውም ተመስግነዋል። ጥበበኞች ተብለው በጥበብ መጽሐፍ ተጠቅሰዋል።



ስለዚህ ሰው ከዕለት ምግብ የዘለለ ማከማቸቱ ነውር አይደለም፤ እንደውም የጥበብ አካል ነው። ይሄ የዮሴፍ ጥበብ ነው። በጥጋብ ዘመን ለሰባት ዓመት ለሚሆን የራብ ዘመን አከማቸ። በዚህም ጥበቡ በባዕድ ሀገር ገዢ ተደርጎ በፈርዖን ተሾመ። ጌታችን ስለ ዕለት እንጀራ እንድንጸልይ የጠየቀን፣ ሁላችንም የዕለት እንጀራ ችግር ሊገጥመን ይችላል ብሎ አይደለም፤ የሚገጥማቸው ቢኖሩም። ይሄ ጸሎት ግን ለሰው ልጆች ሁሉ ነው። ሁሉ እንዲለምን የታዘዘው ይሄ የዕለት እንጀራ ምንድን ነው?



የዕለት እንጀራ፣ የኛን እውነተኛ አቅም የሚገልጽ እና የፈጣሪን ቦታ የሚያሳይ ነው። ያከማቸነውን ሳይቀር ለመብላት አለመቻል ይኖራልና፤ “ነገ ምሳ ይሆናል” ያልነው ሊጠፋ ይችላል፣ በጥበብ የተቋጠረ ቢሆን እንኳን። ይሄ ከአምላካችን ጋር በየቀኑ የምናደርገው ውል ነው። በየቀኑ።



ነቢዩ ዳንኤል ተራ ግለሰብ ሳለ በቀን ሦስት ጊዜ በአምላኩ ፊት ይጸልይ ነበር። ናቡከደነፆር በሁሉም ላይ በሾመው ሰዓትም፣ ይሄ አስደናቂ እውቀት የነበረው ዳንኤል በእግዚአብሔር ፊት በቀን ሦስት ጊዜ ይጸልይ ነበር፤ ስለ ዕለት እንጀራ በመሶቡ እንጀራ ተርፎም ፀሎቱን አላስታጎለም። መደገፋችን አሁንም በአንተ ነው፤ በየቀኑ፣ በየሰዓቱ፣ በሰረገላ አይደለም በፈረስም አይደለም በአንተ እንጂ እያልን።



ባለፈው ሳምንት በJuly 11፣ 2026 የአሜሪካ ሴናተር የሆነው ሊንዚ ግራም ሞተ። ለመጀመሪያ ጊዜ በዚህ ሁለት ዓመት ውስጥ ፕሬዝዳንት ትረምፕ ሲደነግጥ የሰማሁት እና ያየሁት በግራም ሞት መርዶ ነው። ገና የሪፖብሊካንን ምርጫ አሸንፎ ለቀጣይ ስድስት ዓመታት ተወካይ ሆኜ እቀጥላለሁ ብሎ ሲዘጋጅ ሞት ወሰደው። ከወር በፊት የምርጫውን ፕራይመሪ ሲያሸንፍ እንዲህ ብሎ ነበር፦ “በመጀመሪያ የማመሰግነው እግዚአብሔርን ነው። ቀጥሎ ግን ከእግዚአብሔር ሩቅ ያልሆነውን ትረምፕን ነው” ብሎ ነበር። ይሄ ንግግር ብዙዎችን አስደንግጦ እና አስቆጥቶ ነበር፤ ፕሬዝዳንቱን ከእግዚአብሔር ጋር ማስተካከሉ፣ 'ሩቅ ያልሆነው' በማለቱ።



ከዛ ከዩክሬን ጉብኝት እንደተመለሰ ወደ ቢሮው ሄደ። በነጋታው ትልቅ የፕሬስ ዝግጅት ነበረው። ሰኞ በጁላይ አስራ ሦስት ደግሞ ሩሲያ ላይ ማዕቀብ ለማስጣል ረቂቅ ሕግ ያቀርብ ነበር። ሞቱን ተከትሉ የተደረገው የFBI ምርመራ እንደሚያሳየው ደረቱ ታመመ፣ በዛው ቅዳሜ ዕለት። ስልክ አንስቶ ሌላ የሴናተር ኦፊስ ደውሎ ይሄን አለ፦



“I can’t die now. I still need to do the Russia sanctions, get Iran sorted out and do Israeli-Saudi normalization,” (መሞት አልችልም። የራሺያን ማዕቀብ ማዘጋጀት፣ የኢራንን ጉዳይ ፈር ማስያዝ፣ የእስራኤል እና ሳውዲ ኖርማላይዜሽንን መስራት ይኖርብኛል። ገና ብዙ የምሰራው አለ።) ከዚህ በኋላ ለሰዓታት አልቆየም። ሊንዚ ግራም ሞተ።



መሞት የለብኝም ቢልም፣ ሞተ። ይሄን የምታነቡ ሰዎች የሊዮ ቶልስቶይን “የኢቫን ሞት” የሚለውን ድርሰት የምታስታውሱ ይመስለኛል፤ ያላነበባችሁት እንድታነቡ እጋብዛለሁ። ቶልስቶይ የግራምን ሞት ቀድሞ የነገረን ነው የሚመስለው።



ይሄ ሞት በምን ይሁን በምን በእርግጥ አናውቅም፤ አንድ ነገር ግን እንረዳለን፦ ግራም መሞት ሳይፈልግ እና ብዙ ለመስራት እና ለመኖር እየጓጓ እንደሞተ። ይሄ “ልሄድ ከክርስቶስ ጋር ልኖር እናፍቃለሁ” የሚሉት ዓይነት የጻድቅ ሰው ሞት እንዳልሆነ እንገምታለን።



ሐዋርያው ያዕቆብ፦ “አሁንም፦ ዛሬ ወይም ነገ ወደዚህ ከተማ እንሄዳለን በዚያም ዓመት እንኖራለን እንነግድማለን እናተርፍማለን የምትሉ እናንተ፣ ተመልከቱ፣ ነገ የሚሆነውን አታውቁምና። ሕይወታችሁ ምንድር ነው? ጥቂት ጊዜ ታይቶ ኋላ እንደሚጠፋ እንፍዋለት ናችሁና። በዚህ ፈንታ፦ ጌታ ቢፈቅድ ብንኖርም ይህን ወይም ያን እናደርጋለን ማለት ይገባችኋል።” ይለናል። ያዕቆብ 4፥13።



የዕለት እንጀራ ይህ ነው፤ ከጌታችን ጋር፣ ከእግዚአብሔር ጋር ያለን የየዕለት የትስስር ገመድ ነው። ምንም ብናከማች የኛ አይደለም። መሥራት ስላለብን እንሰራለን። ብትፈቅድ ለሌችም ለማካፈል እናከማቻለን፤ ግን የኛ አይደለም። ያንተ ነው፤ አንተ ለወደድከው እንድትሰጠው። የእኔንም በየዕለቱ እጠይቅሃለሁ። በየዕለቱ እየመጣሁ ሳገኝም ሥጦታህ እንደሆነ አምናለሁ፣ ካንተ እና ያንተ እንደሆነ። በደስታ ነው የምመጣው፣ የዕለቱን ልጠይቅህ።



አብርሃም “ውጣ” ነው የተባለው። የት እንደሚሄድ ሳይነገረው በእምነት ወጣ። በዚህም የሁሉም አባት አደረገው። እኛም ዛሬ በተሰጠን ቀን በጥበብ እንሰራለን፣ እናከማቻለን። ነገን ባጠራቀምነው ስለምናልፍ አይደለም። በበጎ ቀን ያጠራቀሙት ሁሉ በክፉ ቀን መውጫ ቢሆን፣ ክፉ ቀን የሚባል ባልኖረ ነበር። የዛሬም፣ የነገም መደገፊያችን አባታችን ነው። ስለዚህ “አባታችን ሆይ” ብለን በየዕለቱ እንጠራዋለን። በተደገፍንበት ዕለት እርሱ እንጀራችን ነው፣ እርሱ እረኛችን ነው፣ እርሱ በዛ ዕለት መደገፊያችን ነው።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jun 28
  • 3 min read



 


“መልካም ስም ከብዙ ባለጠግነት ይሻላል፥ መልካምም ሞገስ ከብርና ከወርቅ ይበልጣል።” ምሳሌ 22፥1



ማህበራዊ ሚዲያ ላይ መንግስትን ደግፋችሁም ይሁን ተቃውማችሁ ወይም የሆነ ግለሰብ ወይም ተቋም ላይ የሀሳብ ልዩነት ስታነሱ መጥተው በነውረኛ ስድብ የሚያጥለቀልቋችሁ ሰዎች ተፈጥረዋል። የሚገርመው ደግሞ የእነዚህ ሰዎችን የፕሮፋይል ፎቶ ስታዩ የክርስቶስ፣ ወይም የማርያም ስዕል ወይም ደግሞ የሃይማኖት ተቋም ምልክት ወይም አላህን ወይም ፈጣሪን የሚጠራ ጥቅስ ያዘለ ሆነው ታገኛላችሁ ሁሉም ባይሆኑም እንኳ አብዛኞቹ እንደዛ ናቸው።



የቅዱሳን ወይም የፈጣሪ ወዳጅ ነን ብለው ፕሮፋይል ፎቶ ቀይረዋል ግን የስድብ አፍ አላቸው። ሰዎችን ከማዋረድ፣ ከመስደብ፣ ከመዝለፍ ውጪ ምንም ጨዋነት የተሞላው ክርክር እና ውይይት አያደርጉም። በሀሳብ ለመሞገት አይችሉም። ግን ጸያፍ የስድብ አፍ አላቸው። በዮሐንስ ራዕይ ላይ “ለአውሬው የስድብ አፍ ተሰጠው” ይላል። መቼስ የሚሳደብ አውሬ እስካሁን አላየንም። አውሬው ልንባል የምንችለው ተሳዳቢዎቹ እኛው ነን።



እኔ በወገኔቼ ላይ የማየው ይሄ አስነዋሪ ምግባር የምር ያሳስበኛል። በመጀመሪያ ከፈጣሪ ጋር ያጣላል እግዚአብሔር እርስ በእርሳችን እንድንከባበር አዞናልና በተጨማሪም ልዩነት ማለትም የሀሳብ ልዩነት የብዙ መልካም ነገሮች ውጤት ነው። የተሰበሰው ህዝብ ሁሉ ንጉሱ ራቁቱን ሆኖ እያየው ከፍርሃት የተነሳ ያልለበሰውን ልብስ “ዋው! እንዴት ያምራል!” ሲል ፥ አንድ ልጅ ናት “ንጉሱኮ ራቆቱን ነው!” ያለችው። ይሄ ምሳሌ የሚነግረን ሀሳብን ማፈን የማህበረሰብን ውድቀት እንደሚያፋጥን ነው።



ስንት ድንቅ እውቀት እና ሀሳብ ያላቸው ሰዎች የአውሬዎችን የስድብ አፍ ተፀይፈው ከሀሳብ መለዋወጫ መድረክ ራቁ?! ይሄ ደግሞ ዋልጌዎች ልጆቻችን ላይ ተጽዕኖ እንዲያሳድሩ ፥ እውቀት አልባ ሰዎች መድረኩን እንዲይዙ ዕድል ይፈጥራል።



ዛሬ አንድ ከምደነቅበት የአዲስ ኪዳን ታሪክ ላጋራቹ። በሉቃስ ወንጌል 16:19 ጀምሮ ያለ ብዙ ትምህርት ያለው ታሪክ ነው። እኔ ግን ከጨዋነት አንጻር ብቻ ለትምህርት ይሆነን ዘንድ ልጥቀስ።



ታሪኩ ስለ አንድ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ደስተኛ ስለነበረ ባለጸጋ እና አልአዛር ስለተባለ ድሃ ነው። ድሃው አልአዛር ሲሞት ወደ አብርሃም እቅፍ በመላእክት ተወሰደ። ሃብታሙ ግን ወደ ሲዖል። ከሲዖል ሆኖ ወደ አብርሃም እየተመለከተ “አብርሃም አባት ሆይ ማረኝ፥” እያለ ምህረት እና ውሃ ለመነ። ለእኔ አስደናቂው የአብርሃም መልስ ነበር። ይሄ በሃጢአቱ ምክንያት ወደ ሲዖል የወረደ፣ ለደሃው አልአዛር ፍርፋሪ ለመስጠት እንቢ ያለ ንፉግ ባለጸጋ አሁን በድፍረት ምህረት እና ውሃ ሲለምን፤ አብርሃም ብዙ ማለት በቻለ ነበር። አብርሐም በደሉን አስታውሶ ሊያሳፍረው ወይም ሊሰድበው አልወደደም ይልቁንስ “ልጄ ሆይ” ብሎ መለሰለት እንጂ። ይሄን የተፈረደበት ኃጢአተኛ ልጄ ለማለት አብርሐም አልተጠየፈም።



በዚህ ባለጸጋ የተበደለው ህያው ምስክር ሆኖ በአብርሃም እቅፍ መኖሩ ፥ ለአብርሃም ያልተገባ ንግግር ለመናገር ምክንያትም ሆነ ሰበብ ሊሆን አልቻለም ፥ ይልቁንስ ለሚጠይቀው ጥያቄ ሁሉ ሳይሰለች በአክብሮት መለሰለት እንጂ። ድሃውን አልአዛርን ለማየት ያልፈቀደ ይሄ ባለጸጋ ፥ የአብርሃምን የክብር መልስ ግን አገኘ። በሰው ሳይሆን በእግዚአብሔር ቢፈረድበት እንኳ አብርሃም ግን ልጄ ብሎ በክብር ጠርቶት ምህረት እንደማይደረግለት ነገረው።



ክፉ ዜና ለመንገር እንኳ አንደበቱን ማቆሸሽ አላስፈለገውም። ያንን በክብር ነገረው እንጂ። የመልካምነት ማማ አብርሃም ፥ ከሲዖል ለሚያናግሩት እንደዚህ ካለ ፥ እኛ ገና በዚህ ምድር የመጨረሻ ፍርድ ሳይቀበሉ ላሉት የምናሳየው ርህራሔ ምንኛ መተለቅ ነበረበት።



የአብርሃምን አሉታዊ የሆነ መልስ የሰማው ባለጸጋውም ፥ ከዚህ በኋላ ምን ሊቀርብኝ ብሎ አንደበቱን አላጎደፈም። እስከመጨረሻው “አባት ሆይ” እያለ ነበር አብርሃምን ያናገረው። ወደ ገነት የመግባት ምንም ተስፋ እንደሌለው ቢነገረውም አሁን ግን ከሞት በኋላ ባየው ነገር ይሁን ወይም ያለፈው ዘመኑ ሕይወት ከንቱነት ገብቶት ተስፋ የለህም ሲባል እንኳ አንደበቱ ጨዋነት አልተለየውም ነበር።



ወገኖቼ ቅዱስ ጳውሎስ የሚለን ነገር አለው። “እግዚአብሔር አይዘበትበትም። ሰው ሁሉ የዘራውን ያጭዳል።” ስድብን የሚዘራ ነውርን ያጭዳል። ጨዋነትን የሚዘራ ክብርን ያጭዳል።



መልካም ስም፣ መልካም አንደበት ከምንም ሃብት በላይ ነው። ብዙ እውቀት የማያስከፍተውን በሮች መልካም ምግባር ያስከፍታል። አንደበታችንን፣ አዕምሮአችንን መግራት ያስፈልጋል። ለሰዎች በክብር ለመመለስ እንጣር። እኛ መከበርን እንደምንፈልግ ሁሉ ሌሎችን እናክብር።



ስድቡን ኪቦርድ ላይ ስንፅፈው ሄዶ የሚያርፈው ሰው ልብ ላይ መሆኑን እናስታውስ፥ ተጎጂዎቹና ጉዳቱ ሩቅ ሆኖ ካልታየን እኛ ላይ ሲደርስ ያለውን ህመም እናስታውስ:: ማዋረድ የሰይጣን ባህሪ ነው፥ ዳይብሎስ ነው አዋራጅ:: እኛ ግን በክብር ጌታ ምሳሌ የተፈጠርን ነን እና ለምንናገረው እንጠንቀቅ።



አንደበታችንን መግራት የማንፈልግ ተናዳጅ እና ቁጡ፣ ተሳዳቢ ለመሆን ከወሰንን ደግሞ ቢያንስ የፈጣሪን፣ የቅዱሳንን ስዕል እና ጥቅስ ከፕሮፋይል ፎቶ እንቀይር። ይሄ ሌላ በደል ይሆንብናልና።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • May 31
  • 4 min read


በየቀኑ ስለ መጪው ግምት እንሰጣለን። በተለይ ሙያተኛ ስትሆኑ ደግሞ ሰዎችም ስለ መጪው ይጠይቋችዋል። አላውቅም ካላችሁ ወይ እየዋሻቹ ነው የሚመስላቸው ወይም እውቀት የሌላቹ። ግን ደግሞ ሁላችንም ስለ መጪው ገምተን ውሳኔ እንሰጣለን።



ሕይወቴ እንዲሰምር ማንን ላግባ?


ምን ባጠና ይሻላል?


ምን ሙያ ልምረጥ ወደፊት የሚያበላ?


ብሰደድ ወይስ ሀገሬ ብቀር?


ዓብይ አህመድ ለሚቀጥሉት ዓምስት አመታት ይቀጥላል ወይስ ይወድቃል?


ዲሞክራቶች ይመረጣሉ ወይስ የአሁኑ አስተዳደር ይቀጥላል?



የመሳሰሉት መጪው ጊዜ ላይ ያተኮሩ ትንበያዎችን በየቀኑ እንሰጣለን። ያን ተመስርተን ሕይወታችንን በዛ መንገድ እንመራለን።



ግን ከዚህ በፊት ያደረግናቸውን ትንበያዎች ብንመለከት ብዙዎቹ አሰቃቂ ናቸው። በአንድ ወቅት የDepartment of Homeland Security ምክትል የነበረ አንድ የሕግ ፕሮፌሰር ነበረኝ። ፕሬዝዳንት ትረምፕ ሲመረጥ ትረምፕ የሚሰራቸውን ታሪኮች፣ ስለሚገነባው አዲስ የፌዴራል ከተማ፣ ስለሚቀነሱ በጀቶች እና የአሜሪካ የበጀት ጉድለትን እንዴት እንደሚፈታ በማብራራት በኢሜል ያልጻፈልኝ ጉድ የለም። እኔም የእርሱን እምነት ሳይ ትረምፕ ሊያደርገው ይችላል ብዬ አስቤ ነበር።



ከሁለት ዓመት በኋላስ ምን ሆነ? በቅርብ ኢሜል አደረኩለት። ትረምፕ ክዶናል አለኝ። ጦርነት ጀመረ። የፌዴራል በጀት ጉድለት በጥቂት ወራት ውስጥ 39 ትሪሊዮን ዶላር ደረሰ። አሜሪካ በዓመት ከምትሰበስበው በላይ ለዕዳ የምትከፍለው በለጠ። የተገነባ የፌዴራል ከተማ የለም። ትረምፕ በብዙ ሙስና እየታማ ነው። ያ ሁሉ ግምት ውሃ በላው። ያ ሁሉ ትንበያ (በጣም አዋቂ በሚባል ሰው የተሰጠ) የተገላቢጦሽ ሆነ።




ዛሬ ከአጎቴ ጋር ስናወራ፣ ስለ ኢትዮጵያ ምርጫ አነሳን። ከዛ ዓብይ አህመድ ወደ ስልጣን ሲመጣ የተናገራቸውን ንግግሮች፣ ስለዲሞክራሲ የገባቸውን ቃሎች፣ ስለ ፖለቲካ ምህዳሩ የገለጸልን ተስፋዎችን እና እኛ ደግሞ በምን ደረጃ አምነን ኢትዮጵያችን ተቀየረች ፥ ትንሣኤዋ ደረሰ ብለን ተቀብለን እንደነበረ ራሳችንን ገመገምን። ከስምንት ዓመት በኋላ ከአዲስ አበባ ልዩ ማማር በቀር ሀገራችን እንዳልነበረች ሆና አገኘናት። የቱንም አልገመትንም ነበር። የቱም አልታየንም ነበር። የኢትዮጵያ ሕዝብ ነገ ለምርጫ የቀረበለትን ዓብይ አህመድን ብቻ ሊመርጥ እየወጣ ነው። ይሄን ማየት አልቻልንም ነበር።



ነገስ? ከዛሬ ስምንት ዓመት በኋላስ ምን ይሆናል? ከዛሬ ሁለት ዓመት በኋላስ? AI በሁሉም ቦታ እየመጣ ነው። ምንድነው የሚሆነው ነገር?






አላውቅም።






ግን ስለ አንድ መሳጭ ታሪክ ልንገራቹ። ዓለምን ስለወረሰ ሰው። እንዲሁም ለዓለም ጥፋት ምሳሌ ስለሆነ ሰው።



ዘፍጥረት ምክራፍ 13 ላይ ነው ያለው።




የወንድማማች ጦርነት። የታላቅ እና የታናሽ ወንድሞች ጥል።




የአብርሃም እና የሎጥ የእረኛ ሠራዊት በግጦሽ መሬቶች ተጣሉ። ጥንታዊ ጦርነትም ሆነ ዘመናዊ ጦርነት በሪሶርስ መቆጣጠር ላይ ያለ ነው።




አብርሃም ይሄ የእረኞች ጥል ወደ እርሱ እና ወንድሙ ሎጥ ጋር መምጣቱ እንደማይቀር አወቀ። ስለዚህ ወደ ሎጥ ሄዶ እንዲህ አለው። "እኛ ወንድማማች ነንና በእኔና በአንተ በእረኞቼና በእረኞችህ መካከል ጠብ እንዳይሆን እለምንሃለሁ። ምድር ሁሉ በፊት ህ አይደለችምን፧ ከእኔ ትለይ ዘንድ እለምንሃለሁ፤ አንተ ግራውን ብትወስድ እኔ ወደ ቀኝ እሄዳለሁ፤ አንተም ቀኙን ብትወስድ እኔ ወደ ግራ እሄዳለሁ።" ዘፍ ምዕ 13፥8።



አብርሃም ምን ያህል የወደፊቱን መገመት የሚችል ሰው መሆኑን እወቁ። ሁሉን ነገር ግን አይደለም። የሰውን ባህሪ ነው የገመተው። ሰው ይጣላል። ጻድቅ ነን ስለዚህ ከጥል ነጻ ነን አላለም። ሁለት ሰዎች ተመሳሳይ ነገር የሚፈልጉ ከሆነ መጣላታቸው አይቀርም። አንዳች በመኃላቸው ይሄን የሚያስቆም ጠንካራ ሥርዓት ከሌለ በቀር። አቻዎች ይጣላሉ። አብርሃም ታላቅ ቢሆንም ሎጥን ግን በትህትና እና በልመና ቀረበው። እንለያይ ብሎ ለመነው። አሁንም ታላቅ ቢሆንም የመምረጥን ቅድሚያ ለሎጥ ሰጠው። አንተ ምረጥ እኔ እከተላለሁ አለው።



ሎጥ የእርሱ እና የአብርሃም እረኞች ጥል ሰላም እንደነሳው የሚገልጽ ምንም ነገር የለም። ምንአልባትም ሁልጊዜ አሁን ያለው የወንድማማች ፍቅር ይቀጥላል የሚል የዋህ እይታ አለው ማለት ነው። ምክንያቱም ይሄ ነገር አሳስቦት የመጣው አብርሃም እንጂ ሎጥ አይደለም። አብርሃም ጠብን ከሩቅ አይቶ መጪውን ተነበያ። ለዛም መጠበቂያ ሊያደርግ ተነሳ።



መጠበቂያውንም ሲዘረጋ የእኔ የሚለውን እና የራሱን ጥቅም ለማስጠበቅ ቅድሚያ አልሰጠም። ግን መልካም የሆነውን ለወንድሙ፣ ለታናሽ ወንድሙ በማስቀደም አንተ ምረጥ አለው። በስግብግብነት የሚጸና ዘላቂ ሰላም እንደሌለ አውቋልና። ሎጥ አሁንም "አንተ ታላቅ ነህ። አንተን መከተል ነው ያለብኝ" አላለውም።



እሺ ብሎ የወደፊቱን መኖሪያውን ለመምረጥ ተነሳ። የምርጫ መስፈርቱንም ዓይኑን አደረገ። መጽሐፉ ቅዱስ ሎጥ ዓይኑን አነሳ። ለዓይኑም እንደ እግዚአብሔር ገነት የምትመስለውን፣ በግብጽ አምሳያ የተሰራችውን ሰዶምን መረጠ ይለናል። ውበት። እርሱም የዓይን ውበት ነበር መለኪያው።



የወደፊቱን ተነበየ። በትንበያውም መሰረት መረጠ። የዛ ትንበያ ፎርሙላ የዓይን ውበት ነበር። ሳየው ደስ ይለኛል። ሳየው ያምራል። የሚል።



አብርሃም ወደ ምርጫ እና የወደፊቱን መኖሪያ ለመምረጥ አልተጣደፈም። ተረጋጋ። ሎጥ ግን በፍጥነት ተለየው። ይልቁንስ አብርሃም እግዚአብሔር መጥቶ ዓይኑን እስኪያበራለት ድረስ ታገሰ። በመጨረሻም የመረጠው ቦታ ድንጋያማውን ኬብሮን ነበር። ግን ጸሎት እንዳደረገ እና በእምነትም በመደገፍ ያን ምርጫ እንዳደረገ እናነባለን። ግን የዓይን ውበት አልነበረውም ፥ ቤተሰብ ለመመስረት፣ ተረጋግቶ ለመኖር፣ አምላኩን ለማምለክ የሚያስችል ስፍራ ግን ነበር።



በአብርሃም የወደፊት ትንበያ ውስጥ የምንማራቸው በጣም አስገራሚ እውቀቶች አሉ።



የመጀመሪያው ስግብግብነት የለበትም። ለራሱ ቅድሚያ ያልሰጠ ምርጫ ነበር። ታናሽ ወንድሙን አስቀደመ። ምን አልባት ሌሎችን መስማት፣ ታናሽ ቢሆኑ እንኳን ሌሎችን ለማድመጥ መሞከር ስለ ወደፊቱ ለመገመት ይረዳል። ከሁሉ በላይ ሰው ስግብግብ በሆነበት ነገሮች ላይ ጥራት ያለው እይታ አይኖረውም። የቸኮላችሁበት፣ የተስገበገባችሁበት ነገሮች ላይ ግልጽ እና ጥርት ያለው እይታ የላችሁም። ስለዚህ ተረጋጉ። ሌሎች ሊቀሟቹ ከመሰላቹ ተውሏቸው። ይውሰዱት።



ሁለተኛ አብርሃም ዓይኑን አላመነም። ዓይናችን እውነትን የመግለጥ ተልዕኮ ብቻ የለውም። የመጋረድም እንጂ። ሎጥ መጥፊያውን ከተማ መረጠ። ሚስቱን አጣበት። ልጆቹ አስነወሩት። ሎጥ የብዙ መጥፎ ምስሌ እንዲሆን አደረገው ዓይኑ። ፍጻሜውም ጉስቁልና ሆነ። የእርሱ ንጽህና ነፍሱን ቢታደግለትም ደስታ እና ርካታ ግን አልሰጠውም። ምክንያቱም የወደፊቱን በዓይኑ ብቻ መርጧልና።



አብርሃም በእምነት እና በጸሎት ጭምር ተደገፈ። መሰረታዊ የሆኑ የወደፊት ሕይወታችን ላይ ልዩነት የሚፈጥሩ ጉዳዮች ላይ እንረጋጋ። ጸሎት ማድረግ ከቻልን እናድርግ። የማናምን ካለን ደግሞ ቢያንስ የተረጋጉ እና የሰከኑ፣ ታማኝ ሰዎችን እናውራ። ከዛም በእምነት ይሁን ምርጫችን።



አብርሃም የመሬቱ ውበት ሳይሆን የእምነቱ ጥንካሬን መሠረት አደረገ። ብዙ ሰዎች ነገ የሚያበላው ምንድነው ብለው ሙያ እና ትምህርታቸውን ይመርጣሉ። ከዛ ይልቅ ጠንካራ የሆንበትን፣ ጎበዝ የሆንበትን ነገር የምርጫ መሠረታችን ብናደርግ ስኬት ይቀርበናል።



ሎጥ የምርጫውን አካባቢ እና ሁኔታ ለማጥናት ጊዜ አልወሰደም። ቢወስድም በዛ ያሉት ሕዝቦች ምን እንደሚመስሉ፣ ለልጆቹ እንዴት ያለ አካባቢ መሆኑ፣ ሰው አነዋወሩ እንዴት እንደሆነ ግድ አልሰጠውም። አንድን ነገር ስንመርጥ እና የወደፊቱን ስንተነብይ ይሄ ዓለም ውስብስብ መሆኑን አንርሳ። ምርጫችን እና ትንበያችን በብዙ ዙሪያው ባሉ ጉዳዮች ይጠቃል። በብዙ የተያያዙ ጉዳዮች ተጽዕኖ ውስጥ ይወድቃል። ለምሳሌ ይሄን ግለሰብ አምነዋለሁ ብለን ልንመርጠው እንችላለን። ግን ግለሰቡ ምን ዓይነት ጓደኞች አሉት፣ የት ያዘወትራል፣ አብረው እነማን ይሰራሉ፣ ቤተሰቡ ምን ይመስላል እና የመሰሉ ሁኔታዎች ያ ግለሰብ መልካም ቢሆን እንኳ ሊቀይሩት ይችላሉ። ስለዚህ ብዙ ጉዳዮችን ትንታኔያችን ውስጥ ማስገባት ተገቢ ነው።



በመጨረሻም ለምርጫችን ጊዜ እንስጠው። የሎጥ ምርጫ መጥፎ እንደሆነ የአብርሃም ምርጫ ደግሞ ትክክል እንደነበረ ለማየት ጊዜ አስፈልጎታል።


 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page