- Mulualem Getachew

- 2 days ago
- 3 min read

አንዳንድ ቃላት ወይም አባባሎች ወይም ጥቅሶች ከመደጋገማቸው የተነሳ የምናውቃቸው ይመስለናል። ወይም በውስጣቸው ያለውን ቁም ነገር ለመመርመር ድግግሞሹ ያዘናጋናል።
አንድ በስራው ስኬታማ የሆነ ወዳጅ አለኝ። “ቀንህ እንዴት ነው?” ስለው፣ “የዕለት እንጀራዬን ለማብሰል እየሮጥኩኝ ነበር” ይለኛል። እኔም በመቀለድ ሥራው ከዕለት እንጀራ በላይ እንደሆነ እና ስኬቱም የብዙዎች የዕለት እንጀራ መሆን እንደሚችል እነግረዋለሁ። “አንተ እኮ የዕለት እንጀራዬን ስጠኝ የሚለው ክፍል ላይ ስትደርስ መዝለል አለብህ” እለዋለሁ፣ ያለውን ሀብት እያሰብኩ።
ነገር ግን ይሄ ቃል ከዕለት ምግብ፣ ከቁርስ፣ ምሳ እና እራት በላይ ትርጉም ሊኖረው ይገባል። ይሄ የሰው ልጆች ሁሉ ጸሎት እንዲሆን ያዘዘው አምላካችን፣ የዕለት ምግባቸውን ከገበታቸው ላይ ማኖር ጨንቋቸው ለማያውቁ ሰዎችም ጭምር ነው። የዕለት እንጀራችንን ስጠን ማለት የዕለት ቁርስን ከመጠየቅ በላይ ከሆነ ምንድነው ትርጉሙ?
ለእኔ ትርጉሙ መታመን ነው። ከእግዚአብሔር በቀር በየትኛውም ነገር ላይ መደገፍ ከእግዚአብሔር በተቃራኒ መቆም ነው። በሚገርም ሁኔታ የሰው ልጅ ሁልጊዜ እንዳከማቸ ነው። ታሪክ ከተጻፈበት ቀን ጀምሮ የምንረዳው ነገር ሰው ለነገ ብሎ ያከማቻል። የነገን ምግብ ማከማቸት ደግሞ በጣም ዝቅተኛው የጥበብ ደረጃ ነው። ጥበበኛው ሰሎሞን ይሄ ጥበብ ለገብረ ጉንዳን ሳይቀር ያላት ጥበብ መሆኑን ይነግረናል። ስለዚህ ማከማቸት፣ ለነገ መቆጠብ እና ማኖር ከስነፍጥረት ጥበብ ጋር የተያያዘ ጭምር ነው። በደመ ነፍስ ያሉ ፍጥረታት ሳይቀር ይሄን የሚያደርጉ አሉና። ይሄን በማድረጋቸውም ተመስግነዋል። ጥበበኞች ተብለው በጥበብ መጽሐፍ ተጠቅሰዋል።
ስለዚህ ሰው ከዕለት ምግብ የዘለለ ማከማቸቱ ነውር አይደለም፤ እንደውም የጥበብ አካል ነው። ይሄ የዮሴፍ ጥበብ ነው። በጥጋብ ዘመን ለሰባት ዓመት ለሚሆን የራብ ዘመን አከማቸ። በዚህም ጥበቡ በባዕድ ሀገር ገዢ ተደርጎ በፈርዖን ተሾመ። ጌታችን ስለ ዕለት እንጀራ እንድንጸልይ የጠየቀን፣ ሁላችንም የዕለት እንጀራ ችግር ሊገጥመን ይችላል ብሎ አይደለም፤ የሚገጥማቸው ቢኖሩም። ይሄ ጸሎት ግን ለሰው ልጆች ሁሉ ነው። ሁሉ እንዲለምን የታዘዘው ይሄ የዕለት እንጀራ ምንድን ነው?
የዕለት እንጀራ፣ የኛን እውነተኛ አቅም የሚገልጽ እና የፈጣሪን ቦታ የሚያሳይ ነው። ያከማቸነውን ሳይቀር ለመብላት አለመቻል ይኖራልና፤ “ነገ ምሳ ይሆናል” ያልነው ሊጠፋ ይችላል፣ በጥበብ የተቋጠረ ቢሆን እንኳን። ይሄ ከአምላካችን ጋር በየቀኑ የምናደርገው ውል ነው። በየቀኑ።
ነቢዩ ዳንኤል ተራ ግለሰብ ሳለ በቀን ሦስት ጊዜ በአምላኩ ፊት ይጸልይ ነበር። ናቡከደነፆር በሁሉም ላይ በሾመው ሰዓትም፣ ይሄ አስደናቂ እውቀት የነበረው ዳንኤል በእግዚአብሔር ፊት በቀን ሦስት ጊዜ ይጸልይ ነበር፤ ስለ ዕለት እንጀራ በመሶቡ እንጀራ ተርፎም ፀሎቱን አላስታጎለም። መደገፋችን አሁንም በአንተ ነው፤ በየቀኑ፣ በየሰዓቱ፣ በሰረገላ አይደለም በፈረስም አይደለም በአንተ እንጂ እያልን።
ባለፈው ሳምንት በJuly 11፣ 2026 የአሜሪካ ሴናተር የሆነው ሊንዚ ግራም ሞተ። ለመጀመሪያ ጊዜ በዚህ ሁለት ዓመት ውስጥ ፕሬዝዳንት ትረምፕ ሲደነግጥ የሰማሁት እና ያየሁት በግራም ሞት መርዶ ነው። ገና የሪፖብሊካንን ምርጫ አሸንፎ ለቀጣይ ስድስት ዓመታት ተወካይ ሆኜ እቀጥላለሁ ብሎ ሲዘጋጅ ሞት ወሰደው። ከወር በፊት የምርጫውን ፕራይመሪ ሲያሸንፍ እንዲህ ብሎ ነበር፦ “በመጀመሪያ የማመሰግነው እግዚአብሔርን ነው። ቀጥሎ ግን ከእግዚአብሔር ሩቅ ያልሆነውን ትረምፕን ነው” ብሎ ነበር። ይሄ ንግግር ብዙዎችን አስደንግጦ እና አስቆጥቶ ነበር፤ ፕሬዝዳንቱን ከእግዚአብሔር ጋር ማስተካከሉ፣ 'ሩቅ ያልሆነው' በማለቱ።
ከዛ ከዩክሬን ጉብኝት እንደተመለሰ ወደ ቢሮው ሄደ። በነጋታው ትልቅ የፕሬስ ዝግጅት ነበረው። ሰኞ በጁላይ አስራ ሦስት ደግሞ ሩሲያ ላይ ማዕቀብ ለማስጣል ረቂቅ ሕግ ያቀርብ ነበር። ሞቱን ተከትሉ የተደረገው የFBI ምርመራ እንደሚያሳየው ደረቱ ታመመ፣ በዛው ቅዳሜ ዕለት። ስልክ አንስቶ ሌላ የሴናተር ኦፊስ ደውሎ ይሄን አለ፦
“I can’t die now. I still need to do the Russia sanctions, get Iran sorted out and do Israeli-Saudi normalization,” (መሞት አልችልም። የራሺያን ማዕቀብ ማዘጋጀት፣ የኢራንን ጉዳይ ፈር ማስያዝ፣ የእስራኤል እና ሳውዲ ኖርማላይዜሽንን መስራት ይኖርብኛል። ገና ብዙ የምሰራው አለ።) ከዚህ በኋላ ለሰዓታት አልቆየም። ሊንዚ ግራም ሞተ።
መሞት የለብኝም ቢልም፣ ሞተ። ይሄን የምታነቡ ሰዎች የሊዮ ቶልስቶይን “የኢቫን ሞት” የሚለውን ድርሰት የምታስታውሱ ይመስለኛል፤ ያላነበባችሁት እንድታነቡ እጋብዛለሁ። ቶልስቶይ የግራምን ሞት ቀድሞ የነገረን ነው የሚመስለው።
ይሄ ሞት በምን ይሁን በምን በእርግጥ አናውቅም፤ አንድ ነገር ግን እንረዳለን፦ ግራም መሞት ሳይፈልግ እና ብዙ ለመስራት እና ለመኖር እየጓጓ እንደሞተ። ይሄ “ልሄድ ከክርስቶስ ጋር ልኖር እናፍቃለሁ” የሚሉት ዓይነት የጻድቅ ሰው ሞት እንዳልሆነ እንገምታለን።
ሐዋርያው ያዕቆብ፦ “አሁንም፦ ዛሬ ወይም ነገ ወደዚህ ከተማ እንሄዳለን በዚያም ዓመት እንኖራለን እንነግድማለን እናተርፍማለን የምትሉ እናንተ፣ ተመልከቱ፣ ነገ የሚሆነውን አታውቁምና። ሕይወታችሁ ምንድር ነው? ጥቂት ጊዜ ታይቶ ኋላ እንደሚጠፋ እንፍዋለት ናችሁና። በዚህ ፈንታ፦ ጌታ ቢፈቅድ ብንኖርም ይህን ወይም ያን እናደርጋለን ማለት ይገባችኋል።” ይለናል። ያዕቆብ 4፥13።
የዕለት እንጀራ ይህ ነው፤ ከጌታችን ጋር፣ ከእግዚአብሔር ጋር ያለን የየዕለት የትስስር ገመድ ነው። ምንም ብናከማች የኛ አይደለም። መሥራት ስላለብን እንሰራለን። ብትፈቅድ ለሌችም ለማካፈል እናከማቻለን፤ ግን የኛ አይደለም። ያንተ ነው፤ አንተ ለወደድከው እንድትሰጠው። የእኔንም በየዕለቱ እጠይቅሃለሁ። በየዕለቱ እየመጣሁ ሳገኝም ሥጦታህ እንደሆነ አምናለሁ፣ ካንተ እና ያንተ እንደሆነ። በደስታ ነው የምመጣው፣ የዕለቱን ልጠይቅህ።
አብርሃም “ውጣ” ነው የተባለው። የት እንደሚሄድ ሳይነገረው በእምነት ወጣ። በዚህም የሁሉም አባት አደረገው። እኛም ዛሬ በተሰጠን ቀን በጥበብ እንሰራለን፣ እናከማቻለን። ነገን ባጠራቀምነው ስለምናልፍ አይደለም። በበጎ ቀን ያጠራቀሙት ሁሉ በክፉ ቀን መውጫ ቢሆን፣ ክፉ ቀን የሚባል ባልኖረ ነበር። የዛሬም፣ የነገም መደገፊያችን አባታችን ነው። ስለዚህ “አባታችን ሆይ” ብለን በየዕለቱ እንጠራዋለን። በተደገፍንበት ዕለት እርሱ እንጀራችን ነው፣ እርሱ እረኛችን ነው፣ እርሱ በዛ ዕለት መደገፊያችን ነው።

