- Mulualem Getachew

- 4 hours ago
- 4 min read

ከምቸገርበት ነገር አንዱ ባህሪዬ ነው። የሆነ ሰሞን በፈጣሪ አምናለሁ። ፈጽሞ ከእርሱ ውጪ ልሰጠው በማልችለው ማዳን ከራሴ ጉድጓድ ጎትቶ ያወጣኛል። በዛ ሰሞን እንደእኔ በእርሱ የሚያምን የሌለ እስኪመስል ድረስ በእርሱ እደገፋለሁ። የሌሎችን ጥርጣሬ እና እንደ እኔ የእርሱን የማዳን እጅ ያላዩትን መኮነን ጭምር ያምረኛል። የሰከረ ሰው ዓይነት ባህሪ።
ከዛ ደግሞ ይመጣል። ኖርማል ቀኖች። አሁን አይምሮዬ ምክንያት ይፈልጋል። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያነበብኳቸው ዓይነት ተአምሮችን አለማየቴን በማሰብ የእርሱን መኖር እጠራጠራለሁ። በዚህ ዓለም በእኔ ዓይን ክፋት እና አደጋ ሊደርስባቸው አይገባም በምላቸው ላይ የሚደርሰውን ግፍ እና ግፈኛ ላይ በእኔ የጊዜ ሰሌዳ ምንም እርምጃ አለመወሰዱን ስመለከት ደግሞ እምነቴ ተንሸራቶ ለጥርጥር እጅ ይሰጣል። ምንም እንኳን እንደ ሙሴ ባህር በበትር ተከፍሎ ባላይም ዝንጀሮ በዝግመተ ለውጥ ሰው ሲሆን ባላየውበት የዳርዊን ሳይንስ ለማመን ይቃጠኛል። በሁለቱ መካከል በማየት ዙሪያ ለውጥ ባይኖረውም።
ይሄ ነኝ እኔ። ምን አልባት ብዙዎቻችን።
መጽሐፉ ቅዱስ ግን አንድ አስገራሚ ነገር ይነግረናል። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለመረጣቸው ሐዋርያት። በዚህ ውስጥ ጴጥሮስ አለ። በዚህ ውስጥ ቶማስ አለ። በዚህ ውስጥ ይሁዳ አለ። በዚህ ውስጥ ያዕቆብ እና ዩሐንስ አሉ። በዚህ ውስጥ ፊልጶስ አለ። በዚህ ውስጥ ናትናኤል አለ። በዚህ ውስጥ ቀራጩ ማቲዎስ አለ። ቀናተኛው ስምዖን በዚህ ውስጥ አለ።
ከአስቆሮቱ ይሁዳ በቀር በእነዚህ መሠረቶች ላይ ነው ክርስቶስ ቤተክርስቲያንን የገነባው። የሁሉም አለቃን ደግሞ ሐዋርያው ጴጥሮስን አደረገ።
ሐዋርያው ጴጥሮስ የክርስቶስን ዋነኛ ሰው የመሆን ዓላማ የተቃወመ በዚህም ሰይጣን የተባለ፣ ለማመንም ለመካድም የሚቸኩል፣ ከማሰቡ በፊት የሚናገር፣ ሰይፍ አንስቶ የሰው ጆሮ የቆረጠ የነበረ ነው። ከሁሉም ግን ክርስቶስን ሁሉም ቢክድህ እንኳ እኔ አልክድህም ባለበት አንደበቱ ፥ ጌታችን በእርኩሶች እጅ ምራቅ እየተተፋበት እያየ ሦስት ጊዜ አላውቀውም ያለ ሐዋርያ ነበር። እነዚህን ተራ ክህደት አድርጋችሁ አትዩት። ቅዱስ ጴጥሮስ ውሃ በእንስራ ሞልቶ ወይን ሲሆን ያየ ነው። ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታችን በውሃ ላይ ሲራመድ አይቶ እርሱም የተራመደ ነው። ቅዱስ ጴጥሮስ በደብረ ታቦር ተራራ ላይ ሙሴ እና ኤልያስ መጥተው አብ ከሰማያት ስለ ጌታችን ሲመሰክሩ የተመለከተ ነው። ቅዱስ ጴጥሮስ በሰይፍ የቆረጠው ጆሮ በሰከንዶች በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተመልሶ ተተክቶ እንደ ድሮ ያለ ጆሮ ሲሆን ያየ ነው። ዓይን ከጭቃ እንደገና ጌታችን ሲሰራ ያየ ነው። የሞተው አልአዛር ሲነሳ ያየ ነው።
ይሄን ሁሉ ያየ ሐዋርያው ጴጥሮስ ነው የካደው።
ግን በመጨረሻ የቤተክርስቲያን አለቃ ተደረገ። ማናችንም ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ያየውን ያህል አላየንም። ጌታችን የሰራቸው ሥራዎች ባህር ቀለም ቢሆን ምድር ብራና አይበቃውም ብሎ ሐዋርያው ዮሐንስ የተናገረለት ነው። ያንን ሁሉ ተዓምራት አይቶ ነው ፍርሃቱን ማሸነፍ አቅቶት የካደው። የፍቅርን ጌታ በመሰቃያው ሰዓት አላውቅህም አለው። ሐዋርያውን ለመክሰስ አይደለም። ይልቁንስ ይሄን ሁሉ ድካም የጻፈለን ራሱ መጽሐፍ ቅዱስ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ አንዱ አስደናቂ ባህሪው የሰዎችን ድካም ላለመጻፍ መጠንቀቁ ነው።
ለምሳሌ ዩሐንስ ወንጌል ምዕራፍ አራት ላይ ያለችው ሴት ብዙ ድካም ያላት ሴት እንደሆነች ይጠቁመናል። ግን ከመጠቆም ውጪ ድካሞቿን ዘርዝሮ አልነገረንም። እርሷ እና ጌታዋ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን መግባባታቸውን ከመንገር ውጪ። ይሄ እጅግ ብዙ ቦታ መጽሐፍ ቅዱስ ላይ የምታዩት መገለጫ (feature) ነው። የመረጣቸውን ሰዎች ድካም ግን በግልጽ ይዘረዝራል። እነሱን በአደባባይ ያሰጣቸዋል። ምክንያቱም ማንም ሊደርስበት ከማይችለው የክብር ማማ ላይ አስቀምጧቸዋልና። ከዛ በላይ እነሱ ለእኛ የመዳን ምልክቶች ናቸው። የሐዋርያው ጴጥሮስ ታሪክ እኔ ነኝ። ብዙዎቻችን ነን።
ኑ አይዟችሁ። የቤቴን መሠረት ይሄን ሁሉ በፈጸመ ግን በመጨረሻ በተመለሰ ላይ ነው የገነባውት እያለን ነው።
ትላንት ድንቅ ተደርጎልን፣ ከምንም አንስቶን ዛሬ ግን በሰው ፊት በአደባባይ እንክደዋለን። ዛሬ አዋቂ ስንባል እርሱ ማፈሪያችን ይሆናል። ዛሬ ምክንያታዊ ስንባል እርሱ እንደ ተረት ዝቅ አለብን። ቅዱስ ጴጥሮስ ግን ኑ ይለናል። ጌታችን ዛሬ በስም እየጠራ “ትወደኛለህ ወይ?” ይለናል። ምክንያቱም እርሱ ፍቅር ነው።
ሐዋርያው ቶማስንም ተመልከቱ። ሌላ የቤተክርስቲያን መሠረትን። ቶማስ መጠራጠር ሃይማኖቱ ጭምር ነበር። የአልአዛርን ከአራት ቀን በኋላ ከሞት መነሳት ያየ ሐዋርያው ቶማስ አልአዛርን ከሞት ያስነሳው ጌታን ትንሳኤ ግን አላምንም አለ። ባይም አላምንም አለ። መንካት መዳሰስ አለብኝ አለ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን በተዘጋ ቤት ውስጥ እርሱ እና ሌሎች ባሉበት ተገኝቶ “አሁንስ አታምንም?” አላለውም። ይልቁንስ ቶማስ እንደፈለገው “ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣና በጎኔ አግባው፤ ያመንህ እንጂ ያላመንህ አትሁን አለው።” ዮሐ 20፥27።
እኛ እንደዚህ ዓይነቱን ተጠራጣሪ የመታገስ አቅም ይኖረን ይሆን?
እጅግ ብዙዎቻችን ወይም ሁላችንም ሐዋርያው ቶማስ ካየው አንድ ፐርሰንቱን ተዓምር እስከዛሬ አላየንም። ይሄን ሁሉ ያየ ሐዋርያው ቶማስ ግን አስሩ የነገሩትን ትንሳኤ አላምንም አለ። ነገር በሁለት ምስክር ይጸናል ይባላል። እርሱ ግን የአስር ሐዋርያ ምስክር አልቀበልም አለ። የሚነገረው ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ቢሆን እንኳ። የጠራን፣ እንድንከተለው ያዘዘን ሐዋርያው ቶማስን ለቤተክርስቲያን መሠረትነት የመረጠው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።
ከዚህ በላይ የሚያጽናና ምን ነገር ይኖር ይሆን?
መጠራጠራችን እርሱ ለእኛ ያለውን ፍቅር አይረታውም።
ሐዋርያው ያዕቆብ እና ዮሐንስንም ነጎድጓዶች ይላቸዋል መጽሐፍ ቅዱስ። ምክንያቱም የእነርሱን አለማመን የታገሰውን ጌታችንን ሳያስተውሉ ፥ የእነርሱን ስለ ጌታችን ትምህርት ያላመኑትን ሰዎች ከሰማይ እሳት ወርዶ እንዲያጠፋቸው በቅናት ስለጠየቁ ነበር። እነርሱ እኮ ጌታ በምድር ሊነግስ ይችላል ብለው በእናታቸው በኩል በቀኝ እና በግራ ለመንገስ ያስጠየቁ ሐዋርያት ነበሩ። እነዚህ ደመ ቁጦዎች ሐዋርያት ናቸው ብዙዎችን ወደ ጌታ እንዲስቡ የተመረጡት።
ቀራጩ ሐዋርያው ማቲዎስስ። ከሮማውያን ጋር የሚተባበር እና በአይሁድ ማህበረሰብ የክፋት፣ የስግብግብነት መጠሪያ የሆነ የታክስ ቀራጭነት ሥራን የሚሰራ ሰው ነው ለቤተክርስቲያን መሠረትነት የተመረጠው። ይሄ ቀላል ከመሰላችሁ ፥ “ዛሬ ቤተክርስቲያን ኮሚቴ ሥራ ውስጥ እነዚህ ሰዎች በሰው ቢጠቆሙ ማነው የሚመርጣቸው?” የሚለውን ብቻ አስቡት። እነዚህን አይደለም ለቤተክርስቲያን ሐዋርያነት ለተራ አገልግሎት የሚመርጥ ክርስቲያን ይኖራል? በፍጹም።
ጭፈራ ቤት ያለው ሰው መጥቶ ቀን ቀን ቤተክርስቲያንን ላገልግል ቢል ብዙ ምዕመን አያጉረመርምም? ማነው ይሄን ግለሰብ የሚታገሰው? ጭፈራ ቤትህን ሳትዘጋ አትችልም አይደል የምንለው?
ቅዱስ ጳውሎስንም ተመልከቱ። እስጢፋኖስን በማስገደል የተባበረ፣ ክርስቲያኖችን ያሳደደ ነበር። ቢያንስ የቅዱስ ጳውሎስ የሚለየው ለሐዋርያነት ከመጠራቱ በፊት ያደረጋቸው ተግባሮች ስለሆኑ ነው። ግን ደግሞ ሐዋርያ ከሆነ በኋላ ሳይቀር በትዕቢት እንዳይቸገር የወገብ ከባድ ውጋት ተሰጠው። በዚህም ከትዕቢት ነጻ እንዳልሆነ ራሱ ነገረን። ጥላው ሌሎች በሽተኞችን የሚፈውሰው ቅዱስ ጳውሎስ ፥ እርሱ ግን በከፍተኛ የወገብ ውጋት በሽተኛ ነበር። ፈውስም አይደረግልህም ተባለ።
በመጨረሻ የምትረዱት ነገር ቢኖር ክርስትና የየዕለት ሕይወት እውነት ነው። ጌታችን ያቀናል። ደካሞች እንደሆንን ያቀናል። እኛ በራሳችን እንደምናፍር እርሱ ልጆቼ ብሎን በመጥራቱ አያፍርም። እግዚአብሔር ሆን ብሎ ነው እኛ ደካሞቹን የጠራን።
ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለ “ጥበበኞችን እንዲያሳፍር የዓለምን ሞኝ ነገር መረጠ፤ ብርቱንም ነገር እንዲያሳፍር እግዚአብሔር የዓለምን ደካማ ነገር መረጠ፤” 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 1፥27። የኛ ድካም የእርሱን ቸርነት አያስቆመውም። ትላንት ወድቀን ለምነነው ከተቀበልን በኋላ ዛሬ ከርሱ ርቀን ብንሄድም እርሱ እንደ ሰው አይደለም። እርሱ እንደ እኛም አይደለም። ለእኛ እራሱ ይሄ ባህሪያችን አሳፋሪ እና ራሳችንን ይቅር ለማለት ልንቸገር እንችላለን። እርሱ ግን ተጎሳቁለን መምጣታችንን አይቶ ከሩቅ ሮጦ ይቀበለናል። በዚህ እርግጠኛ ሁኑ።
የይሁዳም የሚነግረን ነገር አለ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነገ በሠላሳ ብር አሳልፎ እንደሚሸጠው እያወቀ ነው ይሁዳን የመረጠው። ከክህደቱም እንደማይመለስ እያወቀ ነው ከአስራ ሁለቱ አንዱ ያደረገው። እግሩን ያጠበው። ከማዕዱ አንስቶ ያጎረሰው። ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እጅግ የቀረብን የመሰለን ሰዎች ይሁዳን እናስብ። ከይሁዳ በላይ ማናችንም አልቀረብንም። የይሁዳን ያህል ጌታችንን አናውቀውም። በሁሉም ረገደ እርሱ ቅርብ ነበር። ቅርበቱ ግን ጌታችንን በገንዘብ አሳልፎ ላለመስጠት አልጠበቀውም። ቅርበቱ ከመጥፋት አላዳነውም።
ያልጠፋነው በምህረቱ ብዛት መሆኑን እናስተውል። በኃይለኛው በእግዚአብሔር እጅ እንዳንወድቅ ምህረቱን አናሹፍበት። ግን ደግሞ ኃጢአታችንም ወደ እርሱ ላለመምጣት እንቅፋት እንዲሆንብን አንፍቀድለት። እርሱ በድካማችን የሚሰራ ኃያል ነውና።

