top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • 4 hours ago
  • 2 min read


አመጽ አንድን ነገር የማሳኪያው አጭሩ መንገድ ሊመስለን ይችላል። በሕይወት ውስጥ ወለፈንዲ (paradox) ከሆኑ ነገሮች ውስጥ አንዱ ስኬትን በአጭር ማግኘት እና በረጅሙ እና እውነተኛው መንገድ ማግኘት ነው። በየቀን ሕይወታችን ውስጥ በጣም ትልቁ ግፊት የምንፈልገው ነገር ጋር በአጭር ጊዜ ውስጥ መድረስ የሚለው ስሜት ነው። ሕይወት አጭር ናት ግን ከተሳሳትን ደግሞ የዛ ስህተትን ፍሬ የማጨዲያው ወራት ከሕይወት ርዝማኔ በላይ ረዥም ነው የሚሆንብን። ሁላችንም በሃያዎቹ መጀመሪያ ይሄ አብዮታዊ የመሆን ፍላጎታችን እና ለውጥን በቶሎ የማምጣት መሻታችን ጅል የሆኑ ስህተቶችን አሰርቶናል። ማምጣት የምንፈልገው ለውጥ የግድ ሀገራዊ ብቻ ላይሆን ይችላል። በሕይወታችንም ሊሆን ይችላል።



ለብዙ ዘመን ስለመታገስ ሰምቻለሁ። ግን ትግስት ሲባል ቃሉን እንደመጥራት ቀላል አይደለም። መታገስ ምንአልባትም ከትህትና ቀጥሎ በጣም ከባዱ ባህሪ ሊሆን ይችላል። መታገስ የምንፈልገውን ነገር መርሳት እና በመጣ ጊዜ ይምጣ ማለት አይደለም። መታገስ የምንፈልገው ነገር እንዲሆን በመስራት ግን ያንን ነገር ሕጋዊ ባልሆነ ሁኔታ እና ብዙዎችን በሚጎዳ መልኩ ላለማግኘት መስራት ነው። መታገስ የምንፈልገውን ነገር ባለመርሳት ፥ መሻታችን በራሱ ብቻ የመጠበቅ ጊዜውን እንዳያሳጥረው መጠንቀቅ ነው።



ለምሳሌ ፕሬዝዳንቱ እንዲቀየር የሚፈልግ ሰው ብዙ ሕጋዊ መንገዶች አሉት። ለዛ መስራት ይችላል። ሕጋዊ መንገዶች ተጓዳኝ ጉዳቶችን ለመቀነስ የተቀመጡ ናቸው። እንደ አሜሪካ ባለ ሀገር ውስጥ ደግሞ ፕሬዝዳንቶች በዓመታት ይቀያየራሉ። ሕዝብ አንድን ፕሬዝዳንት ሲመርጥ እኛ ላንስማማ ብንችል እንኳ የሌሎችን መራጮች መብት ግን ማክበር አንዱ የትግስት መገለጫ ነው። ከዛም በላይ ትህትና ነው። እነሱም በአመክንዮ ሂደት (reasoning process) አስበው እና አውጥተው አውርደው እንዳደረጉት ማመን ያስፈልጋል። ሕጋዊ መንገዶችን የሚከተል ማንም እነዛን የማሳመን ሸከም ስለሚኖርበት ፥ እነሱን ለመረዳት ብዙ ርቀት ይሄዳል። በዚህ መኃል እርስ በእርስ መነጋገር፣ የልዩነትን ክፍተቶች የማጥበብ ሥራዎች ይሰራሉ። ትግስት ባላንስድ (balanced) የሆነ ውጤት እንድናገኝ የሚያደርገን ለዛ ነው። በማህበራዊ እና ፖለቲካዊ ሕይወት ውስጥ እውነት ማናችንም ጋር ተጠቅልላ የለችም። የምንጠላው ወይም የምንቃወመው ቡድን ጋርም እውነት አለ። ለዚህ ነው በትግስት የሚራመድ ማንም ብዙ እውነቶችን ገንዘብ ማድረግ የሚችለው።



በጣም መጋፋት ካሉብን ፍላጎቶች ትልቁ ለውጥን በፍጥነት የማየት ውሳጣዊ ስሜትን ነው። ስንዴ ዘርታችሁ ይሄ ነገር እየበቀለ ነው እንዴ ብላችሁ ቆፍራችሁ አውጥታችሁ አታዩትም። አፈሩን አለስልሳችሁ፣ ወቅቱን ጠብቃችሁ እስከዘራችሁ ድረስ ያ ዘር አፈሩን ፈልቅቆ ቡቃያ ሆኖ እስኪወጣ መጠበቅ (መታገስ) ይኖርባችዋል። የብዙ ድንቅ ለውጦች ቁልፍ ያለው በመታገስ ላይ ነው።



አመጽ የትግስት እጦት ነው። አመጽ የምንፈልገው ነገር ጋር በአጭር የመድረስ ስሜታዊ ኃይል ነው። ውጤቱም የምንፈልገውን ነገር የበለጠ ማርዘም ነው። ጸጸት አንድን ነገር በአጭሩ የማግኘት ሩጫ ሽልማት ነው።



የምንፈልገው ነገር ላይ ውጤቱ ላይ ብቻ ዓይናችንን ከማድረግ ያን ለማግኘት የምንሄድበት ርቀት፣ ጉዞ ጭምር እንዲያስደስተን እና ያ ሂደት (process) የራሱ የሆነ ደስታ እንዳለው ማሰብ ትግስት እንዲኖረን ይረዳል። አቋራጮችን የሚጠቀም ማንም የሚፈልገው ነገር ጋር ቢደርስ ራሱ ያገኘው ነገር ምን እንደሆነ እና ዋጋው የቱን ያህል እንደሆነ አይገነዘብም። ያገኘውን የማጣት ዕድሉ እንደ መጣበት መንገድ ፈጣን ነው። የጥድፊያ ስሜት ከስንፍና ከሚመጣ የመዘግየት ስሜት በላይ አደገኛ ነው። የዘገየ ሰው ያለውን ላያጣ ይችላል። የሚጣደፍ ግን ያለውንም ያጣል። ትግስት ግን ማንቀላፋትም አይደለም። ትግስት ወደ ምትፈልጉበት ቦታ በየቀኑ መሄድ ማለት ነው። ትግስት የማያቋረጥ ፥ ጨርግዶም እንደማይሄድ ወንዝ ነው። ትግስት የሚፈልገውን ነገር ብቻ ሳይሆን ወደ ሚፈልገው ቦታ የመሄጃው መንገድንም የሚፈልገውን ነገር በመጨረሻ እንዲደሰትበት የማድረግ አቅም እንዳለው ይገነዘባል። የትግስት ዕጦት ውጤቱንም ይቀይረዋል።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Mar 15
  • 2 min read

በአሜሪካ ውስጥ የሚወለዱ ትውልደ ኢትዮጵያውያን ወጣቶች ራሳቸውን ማጥፋት አሁን አሁን የተለመደ ወሬ እየሆነ መጥቷል። ይሄ ለምን እየሆነ እንዳለ ጥናት የሚፈልግ ነገር ነው። ብድግ ብዬ ተነስቼ የዚህን ምክንያት መናገር አልፈልግም። ሰዎች ውስብስብ ፍጥረት ነን። ለመኖርም ሆነ ለመሞት የሚያነሳሳንም እንደዛው ዘርፈ ብዙ ነገሮች ናቸው። ግን ራስን ስለመግደል የሚሰሩ ጥናቶች ከሚያሳዩት አንዱ ራስን መግደል ባደጉ ሀገራት የበለጠ እንደሆነ ነው።



የዛሬ ዓመት ገደማ ሉዊዚያና የሚባል ስቴት ፍርዴ ቤት አንድ የአሳይለም ኬዝ ነበረን። አሳይለም ጠያቂዋ ኢትዮጵያዊት በድንበር የገባች እና በድንበር ከገባችበት ቀን ጀምሮ ለብዙ ወራት የታሰረች ነበረች። እኔ እና በኛ የጥብቅና ኦፊስ የምትሰራ የዚህ ሀገር ሰው የሆነች ጠበቃ ነበር የወከልናት። የታሰረችው ሉዊዚያና ሆኖእና፣ ዳኛው ግን አሳይለሟን አልፈቀደውም። ለዚህ ሁሉ ፕሮሰስ ከፍተኛ ገንዘብ ነበር ያወጣችው። ምንአልባት በሕይወቷ ያጠራቀመችውን ጥሪት ሁሉ ሊሆን ይችላል እዚህ ላይ ያዋለችው። ፍርዱ ሲሰጥ በለቅሶ ስላስቸገረች፣ ዳኛው በፖሊሶች ተይዛ እንድትወጣ ሁሉ አድርጎ ነበር።



ሁላችንም በእርሷ ሁኔታ በጣም አዝነን ነበር። በተለይ ባልደረባዬ ራሷን ታጠፋ ይሆን ብላ ጠየቀችኝ? ሁኔታዋ ስላስፈራት። በእንደዚህ ዓይነት መከራ ውስጥ የሚያልፉ ሰዎች መከራ ውስጥ ገብተው ከማያውቁ ሰዎች በላይ የመኖር እና ሕይወትን የመቀጠል አቅም አላቸው። የሚደንቀው ደንበኛችን በነጋታው በጣም ተጽናንታ ነበር ያናገረችን። ቀጣይ ሂደቾችን ከተነጋገርን በኋላ፣ ማንኛውንም ውጤት ለመቀበል እና ሕይወትን እንደገና በሌላ ቦታ ለመግፋት እንዳሰበች ነገረችን።



ይሄ ታሪክም ሆነ ሌሎች ክስተቶች አብዝቶ የሚጠቁመኝ ነገር የሰው ልጅን ከመከራ ይልቅ ምቾት እንደሚገለው ነው። የሰው ልጅ መከራ አይደለም የሚገለው። መከራን የመሸከም ውስጣዊ ጥንካሬ ማጣት ነው የሚያደቀው።



በአሜሪካ በምዞርበት ሁሉ የማየው፤ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ልጆችን ገና በልጅነት ለኃላፊነት አያዘጋጅም። ለደረሰበት ስኬት በመከራ ውስጥ ማለፉ ያለውን አስተዋጽኦ ፈጽሞ ዘንግቶ፣ ልጆችን ከሕይወት መከራ ለጊዜው በመከለል ፥ ሲያድጉ ሊኖራቸው የሚገባውን የውስጣዊ ጥንካሬ ያሳጣቸዋል። በጓደኞቻቸው ቡሊ መደረግ፣ ትንንሽ ውድቀቶች የሚሰብራሯቸው ይሆናሉ።



ብዙዎቻችን ያደግንበት መንገድ ፍጹም ላይሆን ይችላል። ግን አሁን ላለንበት ደረጃ እንዳደረሰን አንክድም። መጥፎ ደረጃ ላይ ካለን አስተዳደጋችን ለዛ ግብአት አለው። ጥሩ ባታ ላይ ካለንንም ደረጃው ቢለያይም ያደግንበት ሂደት ለዚህ ግብአት አለው። ስለዚህ በእኛ ላይ የተሞከረው አንዱ ጠንካራ የአስተዳደግ ሥርዓት እና ለውጥ ያመጣው በልጅነታችን ለብዙ ኃላፊነቶች መጋለጣችን ነበር። ዛሬ በአሜሪካ አስራዎቹ ውስጥ የምታገኟቸው ልጆች እጅግ ለስላሶች፣ ከቤት ውጪ መኖር የማይችሉ፣ ስሱዎች፣ ቶሎ የሚከፋቸው፣ ኃላፊነቶችን አምናችሁ የማሰጧቸው ናቸው። ይሄን ደግሞ በእነሱ ላይ ማሳበብ አይቻልም። ልጆች እንዳሳደግናቸው ናቸው።



በሉቃስ ወንጌል ላይ የምናገኘውን የጠፋውን ልጅ ታሪክ ተመልከቱ። ያ ፍቅር የሆነ አባት ታናሹ ልጅ ሀብቴን አካፍለኝ እና ልሂድ ሲለው፤ በልጁ ሕይወት ላይ ፈርዶ ነበር ሀብት ሰጥቶት የሸኘው። ልጁ ሊሞት እንደሚችል እያወቀ እንኳ ሊያግተው እና ሊያስቆመው እምብዛም አልሞከረም። ምክንያቱም የሰው ልጅ ከውድቀት የሚማር ፍጥረት ነው። ሰው የፍጽምና መለኪያ የሌለው ነው። ምን ጥሩ እና ምን መጥፎ እንደሆነ በማነጻጸሪያ ካልሆነ አይረዳም። ስለዚህ ምቾትን እና ጥሩ ሕይወትን እንዲያደንቅ ስቃይን እና መከራን መቅመስ እና በዛ ውስጥ ማለፍ አለበት። ያ ታናሽ ልጅ ገንዘቡን ሁሉ አባክኖ ጨርሶ፣ የአሳማ ምግብ ሳይቀር ተከልክሎ ረሀብን በደንብ እስከሚያይ ድረስ የአባቱ ፍቅር እና የቸርነት ቤት አልታየውም ነበር። ያን የሚያደንቅ አዕምሮ አልነበረውም።



ልጆቻችሁ ከመከራ እና ከኃላፊነት በማገድ የምታስቆሙት ሕይወታቸውን ነው። ሲያድጉ ለመጀመሪያ ጊዜ የሚያገኛቸው ያ ትንሹ መከራ ይገላቸዋል። የተኛበትን አልጋ እንዲያነጥፉ፣ ቤቱን እንዲያጸዳ፣ እቃ እንዲያጥብ፣ ለቤተሰቦቹ ምግብ እንዲያበስል፣ እንዲላላክ እና ከዛም ያለፉ ኃላፊነቶችን እንዲወስድ ያልተደረገ ልጅ፣ ነገ የትኛውንም ኃላፊነት የመወጣት አቅም አይኖረውም። ልጆቻንን ለሪስክ፣ ለመከራ እና ለአስቸጋሪ ሁኔታ ሆን ብለን ዛሬ ካላጋለጥናቸው ፥ አንድ ቀን ሕይወት ያንን ፊታቸው ስትደቅን መልሰው እኛኑ ነው የሚረግሙት። በዛ ሜዳ ተረተው እና ተሸንፈው ነው የሚቀሩት።ከሕይወት ወላፈንዲዎች ውስጥ አንዱ መከራ ነው። መከራ የሕይወት ጣዕም ነው። ችግር የመኖር ትርጉም ነው። ያንን መጋፈጥ፣ መረታት፣ መውደቅ፣ ለማሸነፍ መተናነቅ እና ማሸነፍ ነው በዚህ ዓለም ብዙ ርቀት የሚያስጉዘን። ለዛ ማይንድሴት የተዘጋጁ ናቸው የሕይወትን አውደ ውጊያዎች የሚሳተፉት እና የሚረቱት።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Feb 15
  • 2 min read

በሆመስ ኦድሲ መጽሐፍ አስራ ሁለተኛው ክፍል ላይ የኢቲካውን ንጉስ ኦዲሲየስን ከሁሉም የሚለየው ታሪክ ተጽፏል።


ኦዲሲየስ ማንም ያላደረገውን ድንቅ ሥራ ሊሰራ ነው። ሳይረን የተባሉ በድምጻቸው ውበት ማንም የማያልፋቸውን እነዛን ሴቶች ማድመጥ ግን ደግሞ ደሴቲቱንም መሻገር። ያን ደሴት የተሻገረ አንድም ንጉስ ወይም ኃያል ከዛ በፊት አልነበረም። ምክንያቱም የእነዛ ሳይረን ሴቶች ሙዚቃን ለመስማት ሁሉም እዛ ደሴት ላይ ሲቆሙ ይጠፉ ነበር። ያንን ድምጽ ሰምቶ ወደ እነሱ አለመሄድ ፥ ሄዶ ደግሞ በሕይወት መቆየት የማይታሰብ ነበር።



ኦዲሲየስ ግን ያን ለማድረግ ወሰነ።



ግን በጥበብ ነበር። ወታደሮቹ ከመርከቡ ጋር ጠፍረው እንዲያስሩት አዘዛቸው። በምንም ተዓምር ፍጻሜያቸው ጋር ሳይደርሱ እንዳይፈቱት አስጠነቀቃቸው። ፍቱኝ ብሎ በመኃል ቢያዛቸው እንኳ። ከዛ ወታደሮቹ ጆሮ ውስጥ ደግሞ ዋክስ ከቶ ደፈነው። ምንም እንዳይሰሙ። አንድም ያን ሙዚቃ ሰምተው እነሱም ማለፍ አይችሉም። አንድም የእሱንም ፍቱኝ የሚል የጭወት ትዕዛዝ ሰምተው እንዳይፈቱት በማሰብ ያንን አደረገ።



ኦዲሲየስ እዛ ደሴት ጋር ሲደርስ የእነዛን አሳሳች ሴቶች ሙዚቃ አደመጠ። ፍቱኝ እያለ ጮኸ። ግን የመጀመሪያ ትዕዛዙን ሰምተው ወታደሮቹ ይሄኛውን ዝም ብለው አለፉት። በሰማው ድምጽ ቢታወክም ግን የታሰረበትን አላቆ ወደዛ ደሴት መሄድ ተሳነው። ስለዚህ ኦዲሲየስ የሳይረኖችን ድምጽ ሰምቶ ያን ደሴት የተሻገረ የመጀመሪያው ንጉስ ሆነ።



ኦዲሲየስ ራሱን አላመነም። በራሱ ስሜትን የመግዛት አቅም አልተደገፈም። ይልቁንስ ከፈተና በፊት ራሱን ጠበቀ። ብዙ ሰዎች ያልገባቸውን ቁምነገር ኦዲሲየስ ገብቶታል። ስትራቴጂው ስሜትን እገዛለው የሚል ሳይሆን ስሜትን ያለማመን ነበር።



በዚህ ዓለም ትልቁ ጠላት ፈተና አይደለም። በራስ መተማመን ነው። በራሱ ስሜትን የመግዛት፣ በራሱ ጥበብ፣ በራሱ እውቀት፣ በራሱ ራሱን የመግራት ብቃት የሚተማመን ሁሉ ይሸነፋል። ራሱን የሚጠራጠር እና ለዛም ከፈተናው በፊት አጥርን የሚያበጅ ሰው ፈተናዎችን ይሻገራል።



ዲሴምበር ላይ ሚኒሶታ ላይ የICE ሰዎች ሲመጡ አንዱ ደንበኛዬ ጥሎ ከሀገር ሊወጣ ነበር። ይሄ ነገር መቼ ነው የሚያበቃው ሲለኝ አላቅም አልኩት። እንደሚያቆም ግን ነገርኩት። አምስት ስድስት ወራት ወይም ሁለት እና ሦስት ወራት። ወይም ከዛ በላይ። ግን ያበቃል። ምን ትመክረኛለህ ሲለኝ በተቻለ መጠን ከዚህ የረብሻ ዜና ራስህን መጠበቅ ነው የምመክርህ አልኩት። ብዙ ሰዎች ከሚገጥማቸው መከራ በፊት በመከራው ዜና አስቀድመው ይሞታሉ።



ኦዲሲየስ ድምጹን ሰምቼ አልፋለሁ ብሎ በራሱ አልተመካም። ከዚህ በፊት የነበሩት ሁሉ ያን ብለው እንዳልቻሉ ያውቃል እና። ግን ራሱን በገመድ አሰረ። በወታደሮቹም አልተመካም። የእነሱንም ጆሮ በዋክስ ደፈነ። በፈተና ወቅት ነጻነት የባርነት በር እንደሆነ ገብቶታል። ገደብ በፈተና ፊት ነጻነት ነው።



ጥበበኞች ፈተናን እንጂ የሚያርቁት በፈተና ፊት ዲሲፕሊን ለመሆን አይደለም የሚጥሩት። ስሜታዊው ሰው ምክንያታዊውን ሰው ሁልጊዜ በፈተና ፊት ያሸንፈዋል። እውቀት ያላቸው ሰዎች ለዚህ ነው በውጥረት ወቅት የጅልነት ጭቃ ውስጥ የምናገኛቸው። መጪው ባልታወቀ መጠን ብዙ ገደቦች በዙሪያችን ያስፈልገናል። ጠንካራው ሰው ፈተናን የሚጋፈጠው አይደለም። መጋፈጥን አላስፈላጊ የሚያደርገው እንጂ።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page