top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • 4 days ago
  • 3 min read
ree

አንዳንድ ጊዜ እውነተኛ ትምህርት በምቾት ውስጥ ካለፉ ወይም ከስቃይ ውስጥ ከወጡ ሰዎች ነው መማር የምንችለው የሚለውን እርግጠኛ መሆን እቸገራለሁ። ምክንያቱም ብዙ በችግር ውስጥ የሚያልፉ ሰዎች አያለሁ፤ ምቾት ግን የሚገላቸው። ቢሆንም "ሁላችንም ይሄን እንዴት አልፈዋለሁ?" ብለን የምንጨነቀው ችግር ሲመጣ ነው። የዛሬ የሰንበት ጹሁፌ በፍጹም መከራ ውስጥ ያለፈውን ቪክተር ፍራንክል ምክሮች ላይ ያተኮረ ነው። ይሄ ድንቅ ሰው ከመጀመሪያው ግልጽ የሚያደርገው ችግር አንጻራዊ እንደሆነ ነው። በአሜሪካ በሶፋው ላይ ቁጭ ብሎ ያለ ሰው እና በሱዳን የእርስ በርስ ጦርነት መካከል ያለ ሰው እኩል ሊቸገሩ ይችላሉ። ምክንያቱም የመከራ ከባዱ ክፍል ብዙ ጊዜ አካላዊ ሳይሆን ስነ ልቦናዊ ስቃዩ ነው። “መከራ እንደ ጋዝ ነው” ይላል። “አንድ ጠብታ ጋዝ በበርሜል ውስጥ ቢከተትም ሆነ በአንድ ትልቅ ክፍል ውስጥ የሚቆጣጠረው ክፍት ቦታ ተመሳሳይ ነው።” ያ ጠብታ ጋዝ ክፍሉን ሁሉ መቆጣጠር ይችላል። በተመሳሳይ በበርሜል ውስጥም ቢገባ በርሜሉን ሁሉ ይቆጣጠራል። መከራም ትልቅነቱ እና ትንሽነቱ አይደለም። የዛን ሰው አዕምሮ ትንሽም ይሁን ትልቅ በምልአት ነው የሚቆጣጠረው።



ለዚህ ነው ፍራንክል በናዚ ካምፖች ውስጥ ስላለው እና እርሱ ራሱ ስላለፈበት ሕይወት ሲናገር “ማንም አካሉ ጠንካራ ስለነበረ ያን መከራ አላለፈውም። ይልቁንስ ያን መከራ ያለፉት ሰዎች የመኖር ምክንያት (meaning) የነበራቸው ናቸው” ይላል። “ለምን የሚለውን የመለሰ ሰው የትኛውንም እንዴት ያልፈዋል” ይላል። የተረፉ ሰዎች ከዛ ካምፕ የሚወጡበት ምክንያት ነበራቸው። ሕይወታቸው አሁንም ያላለቀ እና የሚያሳኩት ትርጉም እንዳላት ያምናሉ። ከዛም የተነሳ መከራን እንደ ቅጣት ሳይሆን እንደ ፈተና ብቻ ነው የሚያዩት። ፍራንክል ሳይቀር ከኦሽዊትዝ ካምፕ ወጥቶ ይሄን ስቃዩን ሌክቸር ሲያደርግ እና የሕይወትን ትርጉም ሲያስተምር ራሱን ይስለው ነበር።



ይሄን ያለፉ ሰዎች ባብዛኛው “ይሄ ግን በእኔ ላይ ለምን ሆነ?” ሲሉ አይጠይቁም። “ለዚህ መከራ የሚስማማ ስብዕና ምንድነው? ብለው ነው የሚጠይቁት።



ፋራንክል “ብዙ ጊዜ በሕይወት ምርጫ ላይኖረን ይችላል። መቼም የማንነጠቀው ነጻነት ግን አለን? ይላል። ያም አመለካከታችን ላይ ያለን ነጻነት ነው። በሆነ ሁኔታ ውስጥ ስንሆን በዛ ሰዓት ሊኖረን የሚችለውን አመለካከት የመምረጥ ነጻነት ግን አለን።



ተስፋ ከመቁረጥ አዕምሮአችንን መመለስ፣ የውስጥ ሰላምን ለመጠበቅ ራሳችንን ከክፋት ማራቅ፣ እጅ ላለመስጠት መወሰን፣ በሌሎች ላይ ላለመፍረድ መጠንቀቅ እና ክብርን በትንንሽ ነገሮች ሳይቀር መጠበቅ።



“በሚገርም ሁኔታ በናዚ ካምፖች ውስጥ የሰዎችን መልካምነት ብቻ ተመልክቶ ማን ሊተርፍ እንደሚችል መገመት ይቻል ነበር” ላል ፍራንክል። ቁራሽ ዳቦዎቻቸውን ለሌሎች ያጋሩ፣ በራብ ወቅት ሳይቀር ክብራቸውን የጠበቁ፣ ሌሎች እስረኞችን ያልዱ ሰዎች የመትረፍ ዕድላቸው ሰፍቶ እና ከእነዛ ካምፖች በሕይወት ቆይተው ሲወጡ አይቻለሁ። ይላል።



እዚህ ጋር ዳዊት ወልደጊዮርጊስ በጻፈው መጽሐፍ ላይ ያለ የወሎ ረሀብ ታሪክ ትዝ ይለኛል። የአሜሪካው ሴናተር ኬኔዲ ረሀብተኞቹን ጎብኝቶ ተመልሶ ሆቴሉ መተኛት ያቅተዋል። በተመለከተው የተራቡ ሰዎች ብቻ ግን አይደለም። እነዛ የተራቡ ሰዎች ሰልፍ ጠብቀው፣ ዳቦ አየን ብለው ሳይጋፉ እና ሳይደባደቡ የተሰጣቸውን አመስግነው ተቀብለው መሄዳቸው እና በዛ ሁኔታ ውስጥ እንኳ ክብራቸውን መጠበቃቸው ነበር ያስደነቀው።



ብዙዎቻችን እንደዚህ ሥርዓት መያዝ እና አለመስገብገብ ሕይወትን ለማስቀጠል ትርጉም ያለው ላይመስለን ይችላል። ይሄ ማንነት ግን በመከራ ውስጥ ቅስምን ከመሰበር ይጠብቀዋል። ቅስም ከአጥንት ውስጥ ያለ አጥንት ነው። የተሰበረ ቅስም ያለው ሰው ጠንካራ አጥንት ቢኖረው እንኳ ቆሞ አይሄድም። የቅስም ጽናቱ ደግሞ ሞራል ነው።




ፋራንክል “አዕምሮ እውነትን መቀበል ሲክድ ይሰበራል” ይላል። የአዕምሮ ጥንካሬ አሁን ያለውን እውነት በመቀበል የሚመጣ ነው። ጽናት መሸሽ ለማንችለው መከራ ትርጉም በመስጠት የሚገኝ ነው። መቀበል ማለት እጅ መስጠት አይደለም። አለመካድ እንጂ። የሚታየውን ነገር ኮስሞቲክስ እና ሊፒስቲክ አለመቀባት እንጂ።



ጽናተ ቅስም ያላቸው ሰዎች ፍርሃትን ካልገሩት ፥ ፍርሃትን እንዲሁ ከፈቀዱለት አሳስሮ እንደሚያስቀምጥ ያውቁታል። ተስፋቸው ህልም አይደለም። ማለትም የዛሬ ሦስት ወር ወይም ከዓመት በኋላ ይለወጣል ብለው አይደለም የሚያምኑት። ይሄ እብደት፣ ይሄ ክፋት፣ ይሄ መከራ ግን እንደሚያልፍ ያምናሉ።



የመከራው ፍጻሜ በግልጽ አልታየው ያለው ጻዲቁ ኢዮብ በወዳጆቹ ወቀሳ ፊት እና በተሸከመው የስቃይ ሰውነት መካከል ቆሞ እንዲህ ነበር ያለው “እኔን ግን የሚቤዠኝ ሕያው እንደ ሆነ፥ በመጨረሻም ዘመን በምድር ላይ እንዲቆም፥ ይህ ቁርበቴም ከጠፋ በኋላ፥ በዚያን ጊዜ ከሥጋዬ ተለይቼ እግዚአብሔርን እንዳይ አውቃለሁ።” ኢዮ 19፥25። ቻርሊ መንገር እንዲህ ይላል “የሚደርስበት የፕሬዠር ደረጃ እንጂ የማይሰበር ሰው የለም።” ምን ያህል ግፊት ይፈልጋል ነው እንጂ ሰው ሁሉ ይሰበራል። ለዚህ ነው ብርቱ ኢዮብ ሳይቀር “ጕልበቴ የድንጋይ ጕልበት ነውን? ሥጋዬስ እንደ ናስ ነውን?” ያለው። ኢዮ 6፥12። በመከራቸው ወቅት “ከዚህ መከራ አንድ ቀን ይታለፋል። በዚህ መከራ ውስጥ የሕይወት ትርጉም አገኛለሁ።” ያሉ ሰዎች የገጠማቸውን የመሻገር አቅም ያገኛሉ።



መከራን ማለፍ የሚችሉ ሰዎች በመከራቸው ሰዓት ሳይቀር ትንንሽ ደስታዎችን ይፈልጋሉ። በሚያዩት የተፈጥሮ ውበት ይደሰታሉ። በዛ መከራ መካከል ከከዷቸው እና ከተዎቸው ሰዎች ላይ ዓይናቸውን አንስተው ባልጠበቁት ሰዓት የደረሱላቸውን ሰዎች ደግነት እያዩ ያመሰግናሉ። በዛ መከራ ውስጥ ሳይቀር በቀልዶች እና በራሳቸው ባህሪ ይስቃሉ። ይሄ ሕይወት ከዚ ውጪ መሆን አይችልም። በዚህ መካከል ማለፍ ነው ስብዕና።




ሕይወት ትርጉም የሚኖራት በመከራ ውስጥ ማለፍ ለፈቀዱ ነው። በዚህ ውስጥ እንኳ እያለፉ ራስ ወዳድነት ሳያሸንፋቸው በመስጠት ሲያምኑ፣ ለእነሱ በቂ ያልነበረውን ለመጋራት ሲፈቅዱ፣ ነውር ሳይነካቸው ወደ መታረጃው ቦታ ሲገቡ ግን ደግሞ ትንሣኤ እንዳለ ፥ ክፋት በመጨረሻ እንደሚሸነፍ ሲያምኑ ፥ የዛኔ የእነርሱ ታሪክ ለማስተማሪያነት እንደሚውል ሲያውቁ ፥ ቅስማቸው እንደ ጸና ፥ አንገታቸው እንደ ቀና ይሻገራሉ።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Nov 23
  • 5 min read
ree


በቅርብ እህቴን ስለ አዶናይ ጠየቀኳት። ተደንቃ “አንተ ደግሞ ምን ስትሰራ አወቅከው?” አለችኝ፤ ማህበራዊ ሚዲያ ላይ እንዳየውት ነግሬያት፤ አሁንም ምን ታስቤያልሽ ስላት ፥ “እኔ ምን አገባኝ፤ አንተስ ደግሞ ስለዚህ ሰው ምን ይጨንቀሃል” ብላኝ በዚህ ዘጋነው።



አዶናይ ግን የዚህ አሁን ያለንበት ዘመን መገለጫ ይመስለኛል። አዶናይ ዝም ብሎ የሚተው ሰው አይመስለኝም። ስለዚህ የሰንበት ዕይታዬን በእርሱ ዙሪያ ላደርግ ነው።



ትላንት አስተሳሰቡን የምወድለት ፈላስፋውን አላን ዶ ቦቶን ስሰማ እንዲህ አለ በመኃል፤ “የጨዋ እና ጥሩ ቤተሰብ አንዱ መገለጫ ልጆቻቸው ምንም የታዋቂነት ፍላጎት ሳይኖራቸው ሲቀር ነው።” አለ። ሲያብራራ “በልጅነቱ ለቤተሰቡ ዓለማቸው እና ሁሉመናቸው እንደሆነ ተሰምቶት ያደገ ልጅ፤ ሲያድግ በማያውቃቸው ሰዎች መወደድን አይናፍቅም። የማያውቃቸው ሰዎች አወቁት፣ አላወቁት፣ ወደዱት ጠሉት ለእርሱ ምኑም አይደለም። በልጅነቱ መታየት፣ መወደድ ያልቻለ ሰው ነው ካደገ በኋላ ይሄን ከሌሎች ለማግኘት የሚጥረው። ልክ የዘጠና ፐርሰን ኮሜዲያንን የልጅነት አስተዳደግ ታሪክ ስታጠኑ፤ በልጅነታቸው ሁሉም የሰዎችን ትኩረት ለማግኘት የሚቸገሩ ነበሩ። ለዚህ ነው ሌሎችን ለማሳቅ ተምረው እና አጥንተው ወደ ዛ ፕሮፌሽን የተሳቡት።”



ይሄን በማህበራዊ ሚዲያ አጋርቼው፤ አንድ ወዳጄ ኮሜንት እስከሚሰጥበት ድረስ እውነት ለመናገር ከአዶናይ ጋር የሚገናኝ አልመሰለኝም ነበር። በኋላ ግን ሰግጥ፤ ፈምስ ትዝ አለኝ።



አዶናይ የዚህ ዘመን ብቻ መገለጫ ሳይሆን፤ የብዙዎቻችንም መገለጫ መሆኑ የገባኝ ለዛ ነው። አብዛኞቻችን በሌሎች መደነቅ፣ መታወቅ እና ምርጥነታችን በሰዎች ሁሉ እንዲመሰከርልን እንፈልጋለን። የኛነታችን Value (ቦታ) ራሱ በተከተሉን እና ባደነቁን ሰዎች ብዛት የሚወሰን ነው። ምክንያቱም ጎስቋላ ልጅነት ነበረን። ልጆችን ደግሞ የሚያሳድገው ቤተሰብ ብቻ ሳይሆን ማህበረሰብም ጭምር ነው።


እኔ እውነት ለመናገር አዶናይን በተለየ መውቀስ አልፈልግም። መጀመሪያ አዶናይ ታናሽ ወንድሜ ቢሆን ኖሮ የምመኝለት እንዲሳካለት ብቻ ነው። ቶልስቶይ ጠላት አድርጋችሁ የምታዩት ሰው የምትወደው እናት፣ የምታዝንለት እህት እንዳለችው ስትመለከቱ፤ ያን ሰው እንደ ሰው ማየት ትችላላችሁ የሚል ዓይነት ፍልስፍና አለው። ለዚህ ነው ወንበዴውን ዶሎኮቭ ስለ እህቱ እና ስለ እናቱ በሞቱ ጫፍ ሰዓት ላይ ሲጨነቅ ያሳየን።ወንበዴውን በወንበዴነት ብቻ ሳይሆን እናቱን እና እህቱን በሞቱ ሰዓት ሳይቀር በሚያስብ አፍቃሪ ወንድምም እንደሆነ እንድናይ ነው የጋበዘን።


የመጀመሪያው አዶናይ ከሌሎቹ በላይ በፍጥነት መታወቅ ቻለ እንጂ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በሁሉም ዓለም የሚታየው ይሄ አይደለምን? በኛ እንኳ ዮኒ ማኛ፣ ሞጣ፣ ጂጂ፣ ዘመድኩን አልነበሩ መድረኩን የያዙት። እነዚህ ሁሉ ሰዎች ጆሮን ጭው የሚያደርግ ነገር የሚናገሩ፣ ታላላቆችን የሚያዋርዱ፣ ለባህል እና ለሞራል ያልተገዙ አልነበሩምን? እነዚህ ሰዎችን ስንቶቻችን በይፋም ሆነ በድብቅ ሰማናቸው?!



በአሜሪካ ውስጥስ ብሔራዊ ጀግና የተባለውን ቻርሊ ከርክን ተመልከቱ። ለኮሚኒቲ ኮሌጅ እንኳ ብቁ ያልሆነ፣ ከየትኛውም ኮሌጅ ያልተመረቀ፣ አንዳች ለማህበረሰብ የሚጠቅም ነገር ያልፈጠረ ግን የሀርቫርድ የሕግ ትምህርት ቤትን ወርቅ የወሰደች የጠቅላይ ፍርድ ቤትን ዳኛ “ጥቁር በመሆኗ ነው እንጂ ለዛ የሚበቃ እውቀት የላትም” ብሎ በድፍረት የተናገረ፣ “ጥቁሮች አይሮፕላን አብራሪ ሆነው ካየው ያ ሰው እውነትም ብቃት አለው ብዬ አስባለው” ያለ፣ ስለ ባርነት በጎ ነገርን የተናገረ ሰው አልነበረም አሜሪካ እንደ ጀግና የቀበረው? ጀግና ያደረገው! ይሄን ልጅ ማህበራዊ ሚዲያ አገነነው እንጂ የትኛው እውቀቱ እና የፈጣራ ችሎታው ነበር እዚህ ያደረሰው? ዛሬ በማህበራዊ ሚዲያ ታዋቂ የሆኑትን ባብዛኛው ተመልከቱ? የትምህርት ደረጃቸውን ተመልከቱ ከዛ ደግሞ ለምን ታዋቂ እንደሆኑ እዩ የምታገኙት ሁሉ እኮ ተመሳሳይ ነው። በትምህርት ደረጃቸው የወረዱ፣ የኮንስፓይረሲ ንደፈ ሀሳብ የሚያራምዱ፣ ትልልቅ የተባሉትን የሚዘረጥጡ እና የሚያዋርዱ ሰዎች ናቸው የተከታይ መዓት ያላቸው።



የእነሱን የተከታይ እና የታዋቂነት መጠን እያዩ ደግሞ ብዙዎች ያን መንገድ እየተከተሉ ነው። ምክንያቱም እብድ የሆነ ነገር ማድረግ፣ ማህበረሰብ ያከበረውን ነገር ለጆሮ ጭው በሚል መልኩ አዋርዶ እና ፈንቅሎ መውጣት ነው የሚያስፈልገው። ከዛ በብዙዎች መታየት፣ የላይክ ብዛት እና የሺዎች እና የሚሊዮኖች ተከታዮች ብዛትን ማሳየት ወይም መሰብሰብ። ፎቶ ትለጥፋላችሁ፣ ጹሁፍ ትለጥፋላችሁ የሚሊዮን ተከታዮች እና ላይኮችን መቁጠር ነው።



አላን ዶ ቦቶን ይሄን ነው የጥሩ አስተዳደግ ማሳያው ልጆቻችሁ ታዋቂ መሆንን ሳይፈልጉ ሲቀር ነው ያለው። ወላጅ ታዋቂ ለመሆን በሚጥርበት ዓለም ውስጥ፣ ልጆች አይፓድ እና ስልክ በሚያሳድጋቸው ዓለም ውስጥ ምን ዓይነት ትውልድ ነው የሚፈጠረው? ይሄን እንጠይቅ አላን ዶ ቦቶን የጥሩ አስተዳደግ አለ እንጂ የትኛው ወላጅ ነው ከዚህ ደዌ የተፈወሰው ቀድሞስ?



የአላን ዶ ቦቶንን ንግግር እየሰማው በተመሳሳይ በጣም ቀዝቃዛ በሆነው የሚሲሲፒ ወንዝ ሥር ረጅም የእግር ዋክ (walk) እያደረኩኝ ነበር። ሁለት ነገሮች መጡልኝ። የመጀመሪያው ሰላማዊ እና ጸጥ ያለ ሕይወት ያለውን ደስታ። የምር በዛ ወንዝ ዳር ያለው የዝምታ ውበት ወደር አልነበረውም። በዛ ውስጥ ምንም ዋክ የሚያደርግም ሰው አልነበረም። ያ እራሱ ገረመኝ። ከዚህ ዝምታ በላይ ውበት የት ኖሮ ነው ሰው የጠፋው? ይሄን የመሰለ ኦርዲነሪ (ተራ) ሕይወት። ማንም የማይሻማችሁ ሕይወት። ተራ ሰው ሆኖ የመኖር ውበት። በዚህ ተፈጥሮ ውስጥ፣ በዚህ ዝምታ ውስጥ ፥ ምንም ሆኖ የመኖር ሕይወት። ግን በሕይወት ሚሊዮን ሰዎች ተክትለዋችሁ ፥ የውስጥ ሰላም ከሌላችሁ ምንድነው? ለጉድ ፈምሳችሁ ፥ ውስጣችሁ ግን ርጋታ ከሌላው፣ የቁስ ክምችት እንዲያፍናችሁ አሁንም አሁንም የምትጥሩ ከሆነ ፥ ምንድነው ረቡ? የሆነ ቀን አሁን ያደነቃችሁ ሰው ሁሉ ሟች ነው። የተደነቃችሁት እናንተም ማንም የማያስታውሳችሁ ቀን ይመጣል። ከዛስ? ፥ ለዚህ ነበር? ያ ሁሉ ትግል!



ሁለተኛው ሀሳብ ሃይማኖት ነው። ምንድነው ሰዎች በሃይማኖት ውስጥ የሚያገኙት? በሃይማኖት ውስጥ ሰዎች የሚያገኙት ፍቅርን ነው። አንድ እስከ ሁለመናቸው የሚወዳቸው አምላክ እንዳለ ነው የሚያውቁት። አንድ ምንም ቢሆኑ፣ ምንም በኃጢአት ቢቆሽሹ፣ መልከ ጥፉ ቢሆኑ፣ ወይም ሰዎች ገበናቸውን ቢያውቁ መቀበሪያ የሚያጡ የሚመስላቸው ሰዎች ሳይቀር ፥ “ፈጣሪ ግን ይወደኛል!” ፣ የሚል ስሜትን ነው የሚያገኙት።



ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰዎች የእርሱ መሆናችንን እንዴት እንዲያውቁ እንደፈለገ ሲናገር ሰምታችሁታል? “በመጨረሻም ካሸነፋችሁ የእኔ መሆናችሁ ይታወቃል” አላለም። “የእኔ መሆናችሁ የሚታወቀው በዓለም ዙሪያ ተበትናችሁ፣ የእኔ ወንጌል መቀበር ካልቻለ እና አሸናፊ ከሆነ ነው እውነተኛ መሆናችሁ የሚታወቀው” አላለም። "ለብዙ ዘመናት ወንጌሌ ከቀጠለ የዛኔ እውነተኛ እንደሆነ እወቁም" አላለም። ይሄ የአይሁዱ  ገማልያል ትምህርት እንጂ የክርስቶስ ትምህርት አይደለም። እውነትን ልክ እንደ "ሽል ከሆነ ይገፋል ቦርጭ ከሆነ ይጠፋል" በሚል ንግግር የለካው ገማልያል እንጂ ክርስቶስ አልነበረም። ክርስቶስ እውነትን የለካው በፍቅር ነው።



የክርስቶስ ትምህርት ይሄ ነው “እርስ በእርስ ከተፋቀራችሁ የዛኔ የእኔ መሆናችሁ ይታወቃል።” ይሄ ነው ሃይማኖት የሰጠን። የፈጣሪያችን የፍቅር ዓይን በኛ ላይ እንዳረፈ ማመን። የአላን ዶ ቦቶንን የጥሩ አስተዳደግ መለኪያ የሚያሟላ ወላጅ ማግኘት በጣም ከባድ ነው። በሰው መደነቅ እና የሰው ዓይንን መናፈቅ አዶናያዊ ናፍቆት የሌለበት ሰው ማግኘት ከባድ ነው። ምክንያቱም የእውነተኛ ፍቅር እጦት ስላለብን።



የተርዕዮን ኃይል ያሸነፉ ሰዎች በፈጣሪያቸው የፍቅር ዓይን እንደታዩ የገባቸው ወይም ያንን የዝምታ ውበት ፥ ያን ኦርዲነሪ ሆኖ የመኖርን ፥ የሰው ኳኳታ እና ጋጋታ የሌለበትን የውበት ዓለም የተረዱ ሰዎች ብቻ ናቸው።



ጌታዬን ኢየሱስ ክርስቶስን ሳስብ እኔ ከማንም በላይ የምትመጣብኝ ያቺ ከወንዝ ዳር ውሃ ልትቀዳ የመጣችው የሰማርያዋ ሴት ነች። የዝች ሴት ታሪክ የምር የገባው ፍጹም የፍቅር ሰው የነበረው ዮሐንስ ነበር። ሕዝብ ሊያስተምር ነው የመጣው ብለው ያሰቡት ደቀመዛሙርቱ ይሄ ታሪክ ወዲያው አልገባቸውም። እርሱ ግን የአንዲት ሴት ሕይወት ግድ አለው።


“በሰማርያም ሊያልፍ ግድ ሆነበት።” ይላል ታሪኩ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ አራት ሲጀምር። የአንዲት ሴት ሕይወት ግድ አለው። የአንዲት። በጠራራ ፀሐይ ለሰዓታት ጠበቀ። ለእርሱ፣ ለዚህ ጌታ እርሷ ልጁ ናትና። ዓለሙ ናት። ሁሉመናው ናት። ስለዚህ ግድ አለው። ፍቅሩ።


ከአንዲት በኃጢአት ከደከመች ግን ደግሞ የውስጧን ድክመት ከዓለሙ ሁሉ ከሰወረች ሴት ጋር ንግግር አደረገ። ብቻዋን አገኛት። “እኔ የምሰጥሽ ውሃ” አላት። ማህበራዊ ሚዲያ ላይ ለላይክ ቆጠራ የማያመላልስ፣ ለሰብስክሪፕሽን ልመና የማያንቆራጥጥ፣ ለወደዱልኝ እና ምን ተባልኩ ስጋት እዚህም እዛም የማያስብል ፥ “እኔ የምሰጥሽ ውሃ" አላት። አልገባትም። ከዚህ ጥማት፣ ከዚህ የመወደድ ፍላጎት ራብ፣ ከዚህ የመታየት ናፍቆት ውጣውረድ የሚገላግላት የሚያናግራት ፥ ውዷ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑ አልገባትም።



“መቅጃ የለህም እኮ አለችው።” የእርሱ ውሃ ዘወትር መቀዳት የሚያስፈልገው መስሏት። ይሄን ውሃ ግን አንዴ እስከምትጠጪው ነው ከዛ በኋላ አይጠማሽም። እንደዚህ ዓለም ውሃ በጠጣሽው መጠን የበለጠ የሚያስመኝሽ አይደለም። ከጠጣሽው በኋላ እስከ ዘላለም የምትረኪበት እንጂ።



 በዛ ወንዝ ብቻዬን እየሄድኩኝ ነበር። ስለ ሰማርያዊቷ ሴት እና ስለ ጌታዋ ሳስብ እና ያ ስሜት የፈጠረብኝ የውስጥ አስገራሚ ንዳድ ከየትም ቦታ ያላገኘውት ረፍት ነበር የሰጠኝ። በዛ ሰዓት ልክ ሐዋርያው ጴጥሮስ “እባክህ ከዚህ ተራራ አንውረድ” እንዳለው ከዚህ የመገለጥ ፍንጣቂ ወደ ፈምስ ጨለማ እንዳልወርድ ተማጸንኩኝ። ግን ባህሪዬ እዛ ለመርጋት የሚያስችለው ልምምድ አልነበረውም።



የምርጥ አስተዳደግ መለኪያ ልጆቻችን ታዋቂ የመሆን ምኞት ሳይኖራቸው ሲቀር ነው። ላይክ የሚናፍቅ እና የእርሱን እና የሰውን (value) በላይክ ብዛት የሚመዝን ልጅ ካሳደግን ፥ አዎ እንደ ሰማራዊቷ ሴት ከዚህ ድካም ፈጣሪያችን እንዲገላግለን እመኛለሁ። ይሄን ውሃ የቀመስን ቀን ቅንጣት ታክል በሰው መወደድ እና መጠላት ለኛ ግድ አይሰጠንም። ይሄን በጥቂት፣ እጅግ በጥቂት ሰዎች ሕይወት አይቸዋለሁ።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Nov 16
  • 3 min read
ree


የጠቢበኛው የጥበብ መዝሙር ላይ እንዲህ ይላል “ወይናችን አብቦአልና የወይናችንን ቦታ የሚያጠፉትን ቀበሮች፥ ጥቃቅኑን ቀበሮች አጥምዳችሁ ያዙልን።” መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን 2፥15።



ለመውደቅም ለመነሳትም የጥቃቅን ሕግ ወሳኝ ነው። የጥቃቅን ሕግን የሚያውቅ ሰው፣ በአግባቡ የገባው ሰው በዚህ ምድር ብዙ ርቀት ይጓዛል። የጥቃቅን ሕግ የሰው ልጅን ተፈጥሮ የስንፍናም ሆነ የውንብድና፣ የጉብዝናም ሆነ የዝናን ተፈጥሮ ያገናዘበ ነው።



ሰው ትንሣኤውም ሆነ ሞቱ በጥቃቅን ሕግ ነው።



ስናድግ በወላጆቻችን የሚነገረን ተረት ነበር። በሬ ሰሮቆ የተያዘው ልጅ። ያ ልጅ በበሬ ስርቆትን አልጀመረም ነበር። አንድ ቀን መርፌ ሰርቆ መጣ። ዝም አለችው እናቱ። ከዛ ዳቦ፣ ከዛ የሆኑ ተራ እቃዎችን፣ ከዛ እያደገ ሄደ። በበሬ ግን ተያዘ። ያኔ ወደ እናቱ ዞሮ “በመርፌ ብታቆሚኝ!” አላት። የጥቃቅን ሕግ ማለት ይሄ ነው።



አንዳንድ ጊዜ በመንገድ ስሄድ ቤት አልባ የሆኑ እና በሱስ የወደቁ ሰዎችን አያለሁ። እነዚህ ሰዎች መንገድ ላይ ከሆነ ጊዜ በኋላ ነው የወጡት። እዛው አልተፈጠሩም። ግን የትኛው ሱስ ነበር ለዚህ ያደረሳቸው? የመጀመሪያ ቀን የሳቡት፣ ሁለተኛው ቀን የሳቡት ወይስ ከሳምንት በኋላ የሳቡት ሲሻ ወይም ኮኬን ነው እዚህ ላይ ያደረሳቸው? አላውቅም። የማውቀው ግን ያን መሳብ የጀመሩ ቀን ዛሬ እዚህ ላይ እንደሚድርሱ ማናቸውም አልገመቱም ነበር።



አባት ልጁን ሌላ ከተማ ወዳለሁ እርሻው ላከው። የላከው እርሻውን እንዲያርም ነው። ልጅ ወደ እርሻው ሲደርስ ፥ የእርሻው ግዙፍነት እና መላው እርሻው በአረም መዋጡ የሥራ ቅስሙን ሰበረው። ስለዚህ ማረሙን ትቶ ተኛ። አባት ከሆነ ጊዜ በኋላ ሲመጣ ልጅ ተኝቷል። ለምን እንዳላረመ ሲጠይቀው፤ ይሄን ሁሉ እርሻ ብቻውን ማረም ከአቅሙ በላይ እንደሆነ ነገረው። የጥቃቅን ሕግ የገባው አባት ነበርና፤ ልጁን ሳይቆጣ እንዲህ አለው። “በየቀኑ በቁመትህ ልክ ብቻ አርም። ከዛ ተኛ።” ልጅ እያንገራገረ ጀመረ። ቀስ እያለ ማረሙን ወደደው፣ ከቁመቱ በላይ፣ ሁለት እና ሦስት እጥፍ ማረም ጀመረ። በጥቂት ጊዜያት ውስጥ እርሻውን ሁሉ አርሞ ጨረሰ። የጥቃቅን ሕግ በሬ ብቻ አይደለም የሚያሰርቀው። ጋሻ የሚያክልን እርሻም ያሳርማል። የርግማን ብቻ ሳይሆን የበረከትም ሕግ ነው።



በሕይወታችሁ ተኝታችሁ ካላችሁ እና ሰማይ ምድሩ በላያችሁ ላይ የተጫነ ከመሰላችሁ፤ ሰማዩን ከላያችሁ ለማንሳት ከመታገል ፥ ማንሳት ከምትችሉት ቀላል ነገር ጀምሩ። ምንም ስፖርት ከማይሰራ ሰው ይልቅ አራት ፑሽ አፕ ብቻ በየቀኑ ሰራለሁ ብሎ የተነሳ ሰው በዓመቱ መጨረሻ የተሻለ ጤነኛ ሆኖ ራሱን ያገኘዋል። ብዙ ሰው ስለቢዝነስ፣ ስለ ስኬት እና ስለሥራ ሲያስብ ዓይኑ ላይ ድቅን የሚለው የትልልቅ ሕግ እንጂ የጥቃቅን ሕግ አይደለም።



የሆነ ነገር ሥራ የምትሉት አብዛኛው ሰው ትልቅ ብር ይጠራላችዋል። ወይም ይሄን ያህል ገንዘብ ያስፈልጋል ይላል። ግን ትልልቅ ብር ያላቸው ሰዎች ሁሉ ከዛ አልጀመሩም። ይልቁንስ በእጃቸው የነበሩ ጥቂቶችን ዘሩ። ከዛ ያጨዱትን መልሰው እየዘሩ ፥ ዛሬ ጋሻው የእነሱ ሆነ። ከትንሽ ለመጀመር ያልፈቀደ ሰው ትልቅ ሆኖ መቀጠል አይችልም።



ብዙ ሰው ስለ ስርቆት፣ ሌብነት፣ ማጭበርበር ሲያስብ ፥ የሚያስበው ስለ ሳንቲሞች እና መርፌዎች አይደለም። ግን የጥቃቅን ሕግ የሚነግረን ወደ ገሀነም የሚወስደው መንገድ በቅን ልቦና የተጠረገ መሆኑን ነው። “ምንም አይደል” ብለን ዛሬ የሰበርናት ትንሽዬ ሕግ ነገ ገሀነም ላይ ታደርሰናለች።



አብይ አህመድ በአንድ ቀን አንባገነን አልሆነም። ደራሲ ሀዲስ አለማየው ስለ መንግስቱ ኃይለማርያም መለወጥ ለቪኦኤ በተናገሩበት ወቅት እንዲህ ነበር ያሉት። መንግስቱን እዚህ አውሬነት ላይ ያደረሱት ዙሪያው ያሉ ጓዶቹ ናቸው። “አንተ እኮ ነብር ነህ” አሉት። መጀመሪያ “ጓዶች እኔ እንደናንተው ነኝ” አላቸው። ግን ደገመቱ። “ነብር ነህ” አሉት አሁንም። ተቃወመ። በትህትና “እንደናንተው ነኝ” አላቸው። ቀስ እያለ ግን እርሱም ተቃውሞውን ቀነሰ። በመጨረሻ ነብር ሳልሆን አልቀርም ብሎ መጠራጠር ጀመር። በመጨረሻ ጭራሽ ነብር ነህ ካላሉት መግደል ጀመረ። ከዛ ነብር ሆኖ ፈጃቸው። ኢትዮጵያ ትቅደም ያለምንም ደም ብሎ የተጀመረ አብዮት፣ በአንዱ ሰው ጄኔራል አማን አንዶም መገደል ቀስ እያለ ስልሳዎችን ፈጀ። ከዛ ስልሳ ሺ ሕዝብ ፈጀ። አብይ አህመድም ዛሬ ላይ ለመድረስ የጥቃቅን ሕግን ተከትሏል።



ራሳችሁን በመጥፎ ባህሪ እና በማትፈልጉት አስተሳሰብ ውስጥ ካገኛችሁት፣ የጥቃቅን ሕግን ፍልስፍና ተከተሉ። ችላ ያላችሁት ደካማ ወይም መጥፎ ባህሪ ካላችሁ ፥ ነገ የሞት አፋፍ ላይ ራሳችሁን ከማግኘታችሁ በፊት ዛሬ ንቁ።



ብዙ ትዳሮች ፍጹም በሆነ ፍቅር ይጀምራሉ። ልነጠፍልሽ ያልተባባሉ፣ በሕልምም በቁምም ያልተነፋፈቁ ፍቅረኛሞችን ማግኘት ከባድ ነው። ከዛ ከዓመታት በኋላ ወደ ዛ ትዳር ተመለሱ። የጥቃቅን ሕግ ወይ ፍቺ ላይ አድርሷቸዋል ወይም ፍቅር የሞተበት ቤት አስታቅፎአቸዋል። መቼ ነው ግን እንደዚህ መሆን የጀመሩት? አንድ ቀን!!! ያ ችላ ያሏት አለመግባባት፣ በቶሎ ያልፈቱት ልዩነት፣ ያዳፈኑት እና ከውይይት አርቀው የቀበሩት ያ አጀንዳ ነው የጥቃቅን ሕግን ተከትሎ የትዳራቸው ካንሰር ወደ መሆን ያደገው።



ወይናችሁ እንዲያብብ የምትፈልጉ ሰዎች ፥ ጥቃቅን ነገር ማድረግ ጀምሩ። ወይናችሁ ያበበም ሰዎች ወይናችሁ እንዳይጠፋ ጥቃቅን ነገሮችን በቶሎ ፈልጋችሁ ፥ እነሱን ነቅላችሁ አሶግዱ። ትልልቁን ነገር ችላ ብትሉት ይሻላል፤ ጥቃቅኑን ችላ ከምትሉ።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page