top of page
ree


አላን ዋትስ ስለ ካርል ዩንግ በጻፈው መጣጥፍ ላይ ከራሱ ጋር የታረቀ ሰው በዚህ ዓለም ላይ ካርል ዩንግ ነበረ ይላል። ዩንግ ራሱ ላይ ያሉትን ሕጸጾች እና ድካሞች በይሁንታ ያለማፈር የተቀበለ ሰው ነበር። በተለይ በ1950ዎቹ ሲዊዘርላንድ ላይ ለቀሳውስት ያደረገው ንግግሩ ዩንግ የሰውን ተፈጥሮ በጥልቀት መረዳቱን የሚያሳይ ነበር።



ሰዎች ለራሳቸው ጥቅም እንደሆነ እስካወቁ ድረስ ምንም ክፋትን በሰዎች ላይ የማድረግ አቅም አላቸው። የሰው ልጆች በጎ ላደረገላቸው እና መልካሙን ነገር ለሰጣቸው ሳይቀር የእነሱ ሕይወት የሚሰምር ከመሰላቸው ወይም በጣም የሚፈልጉት ነገር እንዲሆንላቸው የወደዱ እንደሆነ ክፋትን ለማድረግ ፈቃደኛ ናቸው። ለዚህ ነው ለክርስቲያኖች የክርስቶስ ሕይወት አስገራሚ የሆነው። ምክንያቱም በበርባን ምትክ ንጹሁ ክርስቶስ ለመሞት ፈቅዷልና። በቅርብ አንድ ወዳጄ ስለ ልጁ ነገረኝ። ልጁ ገና አራት እና አምስት ዓመቷ ነው። በቤቱ ውስጥ እርሷ ነበረች እንደ እንቁ የምትታየው። ነገር ግን አዲስ ልጅ ሲወለድ የቤተሰቡ ትኩረት ሁሉ ወደ ሕጻኑ ሆነ። ከዛ ይህች ሕጻን ልጅ አዲስ የተወለደውን ልጅ ጠላችው። መምታት ጭምር ፈለገች። እኔን በጣም የገረመኝ የአንዲት ነፍስ ያላወቀች ልጅ ሪያክሽን ራሱ ከፍቅር ይልቅ ቅናት መሆኑ ነው። በዚህ ዓለም ላይ ገና ክፍትን ያልተማረች ሕጻን ልጅ ተፈጥሮዋ የነገራት አዲስ የመጣው ልጅ ትኩረቱን ስለወሰደ ጠላትሽ ነው የሚል ነው። ይሄ የሚነግረን የሰው ልጅ ጠባዩ እንስሳዊነት ሲሆን፤ ተፈጥሮውም እስካልተገራ ድረስ ከበጎነት ይልቅ ለክፋት የተመቸ መሆኑን ነው።



ለዚህ ነው ሰው የራሱን ጥቅም ከሚያጣ፤ ሰዎችን አሳልፎ መስጠት እና መጉዳት ምርጫው የሚሆነው። ይሄን ለክፋት የተመቸን ማንነታችንን እውቅና ካልሰጠነው እና በፍጹም ሰብአዊ አስተሳሰቦች እና ክርስትናዊ ፍቅር ካልገራነው በቀር ሰው አውሬ ነው። ክርስቶስን የተለየ የሚያደርገውም ይሄ ነው። ተፈጥሮ ለመልካም ነገሮች ያደላ ነው። ፍጹም ስለራሱ ሕመም ብቻ ማሰብ በሚገባው የመስቀል ሰዓት ያሰበው ከራሱ ይልቅ ስለ ሰቀሉት ምህረትን ነበር። ከዛም ለሚወዳት እናቱ ልጅ እና ተንከባካቢን መስጠት ነበር። ከዛም በዛ መራራ ሰዓት አንተም እንደኛው ወንጀለኛ ነህ እያለ በሚከሰው አላዋቂ ከመናደድ እና ከመራገም ይልቅ በሌላኛው ጎኑ ሆኖ አንተ ልዩ ነህ ያለውን ያን ሰው የገነት ቁልፍን መስጠት ነበር ሥራው ያደረገው። ለክፋት ፈጽሞ አልመለሰም። ከክፋት ጋር ድርድር ውስጥ አልገባም። ፍርድን ሊሰጥ ከማይችል ከጲላጦስ ፊት አለፈለፈም። ሦስቴ የከሰሰውን ሰው ከሰስከኝ ብሎ አላወራውም። ይሄ ሁሉ ክፋት ምንም አላስደነቀውም።



የበሰሉ ሰዎች የሚደርሱበት ደረጃ ያ ይመስለኛል። በሰው ክፋት አለመደነቅ። ከሰው ልጆች ሞራል እና ከፍታን አለመጠበቅ። የሰው ልጅ ተፈጥሮ በሆኑ ጉዳዮች ጉድ አለማለት። ያ ብቻ ሳይሆን እነርሱም ለዛ ክፋት ብቁ መሆናቸውን ማወቅ። ለጴጥሮስ መመለስ ትልቁ አስተዋጽኦ ክርስቶስ በርሱ መክዳት አለመደነቁ ነው። የሰው ልጅ የሚድን ከመሰለው ሁሉን ትቶ የተከተለውን መልሶ ይክደዋል።



ተመልከቱ አሜሪካ ውስጥ እየተካሄደ ያለውን ጉድ። በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ክርስትናን የሚያራምድ ነው። አሜሪካ ውስጥ በባለፉት ሃምሳ ዓመታት ውስጥ እንደዚህ ጊዜ ስደተኞች ባይተዋርነት ተሰምቷቸው አያውቅም። ጥቁር እና ስደተኛ ፍጹም ወደ ሆነ ባይተዋርነት እየተገፉ ያለበት ዘመን ላይ ነን። አንገታቸው ላይ መስቀል ያደረጉ እና የቻርሊ ከርክን መገደ አስመልክቶ ወደ ቤተክርስቲያን እየጎረፈ ያለ የትረምፕ ደጋፊዎች ናቸው ስልጣን ላይ ያሉት። ከክርስትና በላይ ለስደተኞች መጨነቅ ያለበት ሃይማኖት መኖር ያለበት አይመስለኝም። ምክንያቱም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰደደ ነበር። ለስደተኞች ፍጹም ርህራሄ እንድናሳይ የተጋበዝንበት ሃይማኖት ነበር። ክርስትና መሠረቱ፣ ምሰሶው፣ ጣሪያው ሁሉ ምስኪኖችን እና መሄጃ የሌላቸውን በመቀበል ላይ የተመሰረተ ነው። ቤተክርስቲያን ለዚህ ነው የስደተኞች ቤት የምትባለው። ተሰደው የመጡ ሰዎች የሚጠለዩት የክርስቶስ ቤት ውስጥ ነው።



አሁን ግን ክርስትና የሰው ክፋትን ሊገራው ይቅርና የመጨቆኛ መሳሪያ ሆኖ መጥቷል። ኃጢያተኞች ቤት እየሄደ በአመንዝራዋ እንባ እግሮቹ የታጠበ፣ በቀራጩ ቤት እራት የበላ፣ ከወንበዴው ጋር ንግግር ያደረገ፣ ባል እየቀያየረ ከኖረች ሴት ጋር ለማውራት በጠራራ ፀሐይ ወንዝ ዳር ቁጭ ብሎ የጠበቀን አምላክ የምናመልክ እና የምንከተል ሰዎች ፈጽሞ ልንሆን አንችልም፤ አሁን የምናደርገውን እያደረግን። ይሄ የክርስትና ተቃራኒ ነው። ይሄ ፖለቲካ እንጂ ክርስትና፣ ሃይማኖት ሊሆን አይችልም። ለባህሪያችን የሚስማማ ነገር እያደረግን ክርስቲያን ተብለን ልንጠራ አንችልም።



ለዚህ ነው ዩንግ በዚህ ስብከቱ ለእነዛ ቀሳውስት የክርስትና መሠረቱ በራሳችን ውስጥ ያለውን በርባንን፣ ያን ወንበዴ፣ ያን ዘረኛ የሆነውን እና ቡድነኝነት የሚስማማውን ተፈጥሮአችንን መቀበል ነው ያለው። በርሱ ማፈር ሳይሆን መቀበል፣ በውስጣችን እንደሚኖር ማወቅ ነው ያለብን። ምክንያቱም ሰዎች እንደዛ ነን። ያንን በውስጣችን ያለው የክፋት ጥግ ስናውቅ ሌላው ላይ የመፍረድ አቅም አይኖረንም። ሌሎችንም ከፍ ወዳለ ስብዕና እና እርከን ማውጣት እንችላለን። ያኔ ብቻ ራሳችንን ወደ ማወቅ እና ክርስቶሳዊ ፍቅርን ወደ መላበስ ማደግ እንችላለን።


አረመኔያዊ ነገሮች ሊደርሱብን የፈቀድን ካልሆንን የክርስቶስን ፍቅር መሸከም የምንችል አይመስለኝም። ምክንያቱም መልካም ካልሆንን የሰዎች ክፋትን መቋቋም እንችላለን። የሰዎች ክፋትን ስናውቅ ነው ደግሞ እውነተኛ መልካም መሆን የምንችለው። ምክንያቱም በጎ እንደሚሰጠን እያመንን መልካም ካደረግን’ማ ከተፈጥሮአችን ተቃራኒ የሆነን እምነት አልተከተልም። ክፋት እና መከዳት እንደሚጠብቀን አምነን መልካምነትን የመረጥን ከሆንን ብቻ ነው በመርህ እየተጓዝን ያለነው። በሰው ልጆች እንደምንጎዳ አውቀን ነው ፍቅርን የመረጥነው። ባጎረስን እንደምንነከስ በፍጹም ጠብቀን ነው እጃችንን በክፋት አፍ ውስጥ የከተትነው። ለምን? ይሄ ምርጫ ነው። ምርጫችን በጨለማው ዓለም ውስጥ ጨለማ ላለመሆን ነው። በጨለማው ዓለም ውስጥ ላለመታየት የፈለገ ሰው እርሱም ጨለማ ነው መሆን ያለበት። ከጨለማው ጋር የተባበረ በጨለማው አይጎዳም። የጨለማውን ጨለማነት በመልካም ባህሪ እና በፍቅር ለመለወጥ የፈለጉ ሰዎች ብቻ በዚህ ዓለም ክርስቲያን ተብለው ይጠራሉ። ከዓለም እና ከተፈጥሮአችን ግብዣ ውጪ ክፋትን በክፋት ላለመመለስ ወስነዋልና። እንደሚጠቁ እና እንደሚከሰሱ እያወቁ ራሳቸውን ለሚበልጠው የስብዕና ማማ አሳልፈው ሰጥተዋል። ከርሱ የመከዳት የውስጥ ሕመም እና የሀሰት ክስ ስቅላት ቁስል ጋር አሁን ተባብረው ፥ ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ለመተባበር የመርህ ውሳኔ አድርገዋል። በስም ሳይሆን በተግባር ክርስቶስን ለመምሰል መጣር የእነዚህ ራስን እና ሰውን የመረዳት ጉዞ እና ከዛ ተፈጥሮአችን በተቃራኒ የመጓዝ ውሳኔ ነው።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Sep 28
  • 5 min read

ree


Written on April 7, 2023 and you can find the original post with this link. (https://www.facebook.com/profile/100002335758452/search/?q=ጄኔራል%20አበባው)



እኔ አንተን የትላንት ታሪክህን ጠቅሼ መክሰስ አልፈልግም። ስለኢትዮጵያም ያለህን እምነትህን እና ፍቅርህን መጠየቅ አልሻም። የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ውስጥ ሆነህ ፥ ሀገራችንን ለማገልገል መፍቀድህ በራሱ ለእኔ ትልቅ ቁምነገር ነው። ነገር ግን ባለፉት 5 ዓመታት ሁላችንን ብዙ ነገር አስተምሯል ፥ “ኢትዮጵያ ሱስ ናት” ብለው በቃላቸው ፥ በተግባር ግን አንዱን ብሔር ነጥለው የሚመቱ ፥ 3 መቶ አማሮች በየቀኑ ሲረግፉ ፥ መንገድ ዳር ከተከሉት እና ለጠወለገባቸው አበባ ያሳዩትን ብስጭት ለአማሮች ሞት መግለጽ ያልቻሉ መሪዎችን ነው ያየነው። “አዲስ አበባ ውስጥ የኦሮሞ ጥላቻ አለ” ብሎ ጠረጼዛ እየደበደበ የተናገረ ጠቅላይ ሚኒስትር ፥ 3 መቶ አማሮች በቀን ሲታረዱ ግን ድግስ እየደገሰ ሲደሰት ለህዝብ ያሳያል። ወገኔ ላለው ተጠላ ብሎ በፓርላማ ያዙኝ ልቀቁኝ ሲል ፥ ከመጠላት አልፎ ሕጻን አዛውንት ሳይቀር በገፍ ለታረዱበት የአማራ ሕዝብ ግን የውሸት ሐዘናቸውን እንኳ ሊያሳዩት አልፈቀዱም። ጄኔራል አበባው ፥ ንግግር ሰምተን እና አምነን እማ ፥ ዐብይ አህመድን ልባችን እስኪወልቅ ደግፈነው ፥ ሞቱን ሳይቀር ለመሞት መርጠን ነበር። የዛሬ 5 ዓመት ለዐብይ አህመድ የድጋፍ ሠልፍ ሲወጣበት የነበረው የአማራ ከተሞች እና መንደሮች ነበሩ።ለምን?



 (የዛኔ ከጥቂት የኦሮሚያ ከተሞች በቀር ለዐብይ የተደረገ ሠልፍ አላስታውስም።ከ5 ዓመት በኋላ ቃሉን ሳይሆን ተግባሩን ያዩ ሰዎች ለድጋፍ የወጡት በኦሮሚያ ነው።)

 አማራ ዐብይ አህመድ “መደመር ይሻለናል ፥ አንድነት ይሻለናል” ስላለ እንጂ ፥ ዐብይ ኦህዴድ መሆኑ ጠፍቶት አልነበረም የደገፈው። አማራንም ጠቅማለው ስላለው አልነበረም። ይልቁስ ጄኔራል ፥ ዐብይ አህመድ ያለን ዛሬ ልክ አንተ ያልከንን ነበር። “አንድነት ይሻላለና ፥ ስንደመር ነው ኃያል የምንሆነው” ነበር ያለን። ዛሬ እሱን የሚያምነው ስለሌለ አንተ እነዚህን ቃላቶች እንድትናገር ላከክ። አንተም የዛሬ 5 ዓመት እሱ የተናገረውን ሳትቀንስ እና ሳትደምር ፥ “በጋራ አድርገን አንድ ጠንካራ ኃይል ልንገነባ ነው” አልከን። ጄኔራል አንተ ሰው አማኝ ምንአልባትም እንዳልከው ፖለቲካ ብዙ የማትወድ ትሆናለህ። እኔም ብችል እንዳንተ ብሆን እና ለዚህ ሕዝብ የተደገሰለት ግፍ ባይገባኝ እመርጥ ነበር። ግን ትምህርቴ እና የሥራ ልምዴ ዓይኖቼን ከፍቶታል። ማኪያቬሌ እንዳለው ፥ ሕይወት ሰዎች የሚናገሩትን ሳይሆን የሚሰሩትን እንድመለከት አስተምራኛለች።

ለዚህ ነው ውድ ጄኔራል አበባው ፥ የምትናገረው ነገር ከሚሰራው ጋር ፈጽሞ አይገናኝም የምልህ። በርግጥ አንተም የምትናገረውን ብዙ ያመንክበት አይመስልም ፥ ምክንያቱም ባንድ በኩል ትልቅ አቅም እንደተገነባ እየፎከርክ ታወራለህ በሌላ በኩል ደግሞ “ዛሬ ባለችው ኢትዮጵያ አይደለም ሰው በነጻነት ሰላም ተሰምቶት ከክልል ክልል ሊሄድ ከቤቱ ወጥቶ ማምሸት እንደማይችል” ትገልጻለህ። ደግሞ መልሰህ ትፎክራለህ። አንድ አባት በአንድ ወቅት ሲናገሩ እንደሰማውት የተሸነፈ ሠራዊት ፉከራ ያበዛል ፥ አንተም አቅማችን ኃይል ነው ብለህ ሳትጨርስ ሰው ከቤቱ ወጥቶ ማምሸት የማይችልበት ኢትዮጵያ እንደተፈጠረች ትነግረናለህ።



የሕዝብ አመጽን ማፈን የሚችል ኃይል ተገንብቷል ፥ ማንም ምንም የማምጣት አቅም የለውም በተደጋጋሚ ትላለህ። ጄኔራል ፥ አንተ የውጭ ፖለቲካ አትከታተል ይሆናል። አይደለም ኢትዮጵያ ውስጥ ፥ አሜሪካ ውስጥ ራሱ የእርስ በእርስ ጦርነት ሊነሳ ይችላል አይችልም የሚሉ ክርክሮች በስፋት በሙሁሩ ዘንድ እየተካሄደ ነው። ይሄ ማለት በኃይል ስልጣን ሊይዝ የሚያስብ አለ ማለት ነው። የማይቻል ነገር ደግሞ አይታሰብም። በአሜሪካ እንኳ ሊሞከር የሚችልን ነገር ነው እርሶ ገና እየተገነባ ያለ ሠራዊትን ይዘው እንዲህ የሚፎክሩት።



 እሱ ብቻ ግን አይደለም ፥ አንት እንዳልከው ኃይል ስልጣን የመያዣ መንገድ ብቻ ሳይሆን ፥ በስልጣን ላይ ያለን የማስገደጃም ነው። ለምሳሌ በሕዝብ ከተመረጠ የወራት ዕድሜ ያለው የቢቢ ናታኒሆን (የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር) መንግስት ፥ የጠቅላይ ፍርድ ቤቱን የመወሰን እና ህገ-መንግስታዊ ጉዳዮችን የማየት አቅም የሚያሽመደምድ ረቂቅ ሕግ ለፓራላማው አቅርቦ ሊያጸድቅ ነበር። እስራኤሎች ግን ገና ከመረጡት ወራት ባስቆጠረው ጠቅላይ ሚኒስትራቸው ላይ ሕዝባዊ አመጽ ጠሩ። ምክንያቱም የእስራኤል ብቸኛ ነጻ ተቋም ፍርድ ቤቱ ነበር። ይሄን አጡት ማለት ዲሞክራሲ በእስራኤል አበቃለት ማለት ነው። ቢቢ ናታኒሆን እስራኤልን በመውደድ አቻ የሚገኝለት ሰው አይደለም። ግን ፖለቲከኛ ነው። ፖለቲከኛ ስልጣንን ከምንም ነገር በላይ ይወዳለ። እሱ ብቻ ግን አይደለም። ፖለቲከኛ ብዙ ጊዜ እጁ ቆሻሻ ነው ፥ ስለዚህ ተጠያቂነትን ማስቀረት ይሻል። ለዚህ ነው ከራስ በላይ ንፋስ ብሎ ፥ በእስራኤል የዲሞክራሲ ምሰሶ ላይ የዘመተው። ሕዝብ ግን አደባባዩን አጥለቀለቀው። መንገዶችን ዘጋ። ቢቢ ናታኒሆን በቅርብ ተመርጬ ይሄ እንዴት ተደርጎ ብሎ ያዙኝ ልቀቁኝ አላለም። ምክንያቱም ምርጫ ማለት ኮንትራት ነው። ኮንትራት ማለት ውል ነው። ከአንድ ድርጅት ጋር ለ5 ዓመት ውል ገባህ ማለት ፥ ድርጅቱ ሊጠግንልህ የቀጠርከውን ቤትህን ሲያፈርስ የ5 ዓመት ውሉ እስከሚያልቅ ዝም ብለህ ታየዋለህ ማለት አይደለም። ከውል ውጪ እየፈጸመ ብቻ ሳይሆን ፥ ውሉ ያስፈለገበትን ዋነኛ መሠረት እየናደ ስለሆነ ውሉን የመሰረዝ መብት የትኛውም የአራዊት ሕግ የሌለበት ሀገር ሕግ ይፈቅዳል። የሕግ ባለሙያ ስለሆንኩ የምናገረውን አውቃለው።

በተመሳሳይ የዐብይ አስተዳደር አንድነትን የመፍጠር ቃልኪዳኑ ቀርቶብን እንደ ድሮ ተከፋፍለን እንኳ መኖር እንዳንችል እያደረገን ነው። ክቡር ጄኔራል አንተ ለኢትዮጵያዊ የምታዝን ከሆንክ ፥ በአዲስ አበባ ዙሪያ ከ10 ዓመት በላይ ከኖሩበት ቤት ኢትዮጵያኖች ሲፈናቀሉ ፥ ምን አደረክህ? እውነት ነው ያደረከውን ነገር በአደባባይ ትነግረኛለህ ብዬ ጠብቄ አይደለም ፥ ግን ኢትዮጵያኖች ቤታቸው በላያቸው መፍረሱ ሊቆም ይቅርና ፥ ራሳቸው አፍርሰው ጣሪያና በራቸውን እንኳ መውሰድ አትችሉም ነው የተባሉት። አንተ በውስጥ ስለዚህ ጉዳይ ተናግረሃል ብለን እንመን። አንተ ጄኔራሉ ማስቆም ያቀተህን የዛሬ ግፍ ፥ አማራው ነገ ስለተደገሰለት መከራ ግድ የላችሁም እኔን እመኑኝ ስትል ትንሽ ለህሊናዎ አይከብዶትም።


ጄኔራል ከስልጣን ተባሮ መኖር እንደሚቻል እኮ እርሶ በተግባር ያውቁታል። ግፍ እና ውንብድና ሰርቶ ግን መኖር ቀላል እንዳልሆነ ፥ እርሶም ከቀድሞ የትግል አጋሮቾ ለምን አይማሩም? (በቃለመጠይቁ "ከትግራይ ጦርነት ተማሩ" የሚለውን በብዛት ስለተጠቀሙ ነው። እርሶም ከቀድሞ ጓዶቾ የሚማሩት ብዙ አለ የሚለውን ለማስታወስ ነው።)

ልጠይቆትማ ጄኔራል። ከአማራ ልዩ ኃይል አባላት ጋር አብረን ጎን ለጎን ተዋግተናል። ቆስለናል ፥ ደምተናል አሉን ልበል። እንግዲያውስ ይሄን ይመልሱ። ሕወኃት ቆቦን ስትይዝ ፥ ለምናቹ የጠራችሁት ጄኔራል ፥ በዚህም ምክንያት ከ 10 በላይ ጥይቶችን በእግሩ ውስጥ የተሸከመን ባለውለታ ፥ ለአስቸኳይ ሕክምና ከአገር አትወጣም ብላችሁት እየተሰቃየ ነው። ሲሆን ሲሆን ወጪውን ችላችሁ ማሳከም ሲገባ ፥ ይሄን ምስኪን ጄኔራል ቀስ እያለ እንዲሞት ፈረዳችሁበት። ከጎንህ ሲዋጋ ለቆሰለው ፥ ለሀገሩ ዋጋ ለከፈለው ጄኔራል ተፈራ ያልቆምከውን አንተ ፥ ለሱ መሆን ያልቻልከውን አንተ ፥ በሚሊዮን ሕዝብ ደህንነት ጉዳይ እመኑኝ ነው የምትለን? ክቡር ጄኔራል ፥ እኔ በመጽሐፉ ቅዱስ አምናለው። በመጽሐፉ ቅዱስ ላይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶ ፥ አደራ የሰጠውን ባለሟሉን ጠርቶ ያለው እንዲህ ነው ፥ “አንተ በጥቂት ታምነሃል እና በብዙ ትሾማለህ ፥ ያልታመነውን ደግሞ ያለው “አንተ በጥቂት አልታመንክም እና ያለህም ይወሰድብሃል።” ስለዚህ ክቡር ጄኔራል ፥ አይደለም በብዙ ሚሊዮን ምስኪን የአማራ ወገኔ ጉዳይ ላምንህ ይቅርና ፥ ከዛ ባነሱ ጉዳዮች ሳይቀር እምነቴ መሉ አይደለም።


በመጨረሻ የመንግስት ትዕዛዝን በሰላም የማትቀበሉ ከሆነ ፥ እንጠርጋችሃለን ብለሃል። አሁን የቀደመው ፥ ማስታወስ የማልሻው ማንነትህ ተገለጠ። ግን ክቡር ጄኔራል አንተ እንዳልከው እኛን የማጥፋት ኃይል ቢኖርህ እንኳ ፥ የሕዝባችንን መጥፋት ዓይናችን እያየ ዝም ከምንል ፥ ሁሉን መሆንን እንመርጣለን። ኔልሰን ማንዴላ እንዳለው “ሁሉም ነገር እስከሚሆን ድረስ የማይቻል ነበር።” እግዚአብሔርን የማመሰግነው ፥ “የምንሸነፍ አይደለንም ፥ ጦርነት ባህላዊ ጫዎታችን ነው” ያሉትን ሕወኃቶች ሳይቀር ፥ በእንብርክክ ይቅርታ ጠይቀው መሸነፍ የተፈጥሮ ግዴታ መሆኑን በዕድሜዬ ማየቴ ነው። የአማራ ሕዝብም እንዲህ ባለህ መታበይ ፥ እንዲገጥማችሁ አልሻም። ምክንያቱም ኃይል የእግዚአብሔር መሆኑን ከአንዴም ብዙ ጊዜ አይቻለው እና። የአማራ ሕዝብ ካሸነፈም የሚያሸንፈው የመገፋቱን መጠን ፥ የደረሰበትን ግፍ እና ስቃይ አምላክ ስለቆጠረለት ነው። አዎ ፥ ለምስኪኖች ተስፋቸው ማነው? ፥ እግዚአብሔር አይደለምን?


በዚህ ጥበዓት የአማራ ሕዝብ ለህልውናው ይቆማል ፥ ዳግም በአፈ ሞላጮች ላይሸወደ በአንድነት ይነሳል። ለራሱ ብቻ ሳይሆን ፥ በኢትዮጵያ ምድር ለሚጎሳቆሉ ሁሉ ፥ ለሚጠሉት ሁሉ ፥ የተመቸች የጋራ ቤት ፥ የእኩልነት ቤት ለማቆም ይሰራል። በመጨረሻ የዐብይ ፖለቲካ ግር ለሚላችሁ ይሄን የማኪያቬሊ ምሳሌያዊ ታሪክ ፥ መርህ ይሁናችሁ።


ማኪያቬሊ ሰውን በዓይንህ በምታየው ሳይሆን በእጁ በሚሰራው ፍረድ የሚለውን አስደናቂ ጥበብ ያገኘው በሱ ዘመን ከነበረ አንድ መጽሐፍ ነው ፥ መጽሐፉ ውስጥ የትልቋ እና የትንሻ ወፍ ወግ ይላል። ታሪኩ እንዲህ ነው። አንድ ሰውዬ ወፎችን ሰብስቦ በብረት ወጥመድ (cage) ውስጥ ያስቀምጣቸዋል። የሆነ ቀን እየጠበቀ ፥ ከወጥመዱ እያወጣ እነዚህን ወፎች አንድ በአንድ ያርዳል። ከሁሉ ሕጻን የሆነችው እና ልምድ የሌላት ወፍ ለትልቋ ወፍ ፥ “ዓይኖቹን ተመልከቺ ፥ ጓደኞቻችንን ሲያርድ እኰ አዝኖ እያለቀሰ ነው” ትላለች። ትልቋ ወፍም “ሰውዬውን በዓይኑ ሳይሆን በእጆቹ በሚሰራው ፍረጂ” አለቻት (“Judge by the hands, not by the eyes”)።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Sep 28
  • 3 min read
ree

እምነት የእውቀት ጉድለት ክፍተት መሙያ ነው። ከስሜት የአዕምሮአችን ክፍል ጋር የተያያዘ ነው። ማሰላሰል የሚካሄድባቸው የአዕምሮአችን ክፍል ሂፒካምፐስ እና ፕሪ ፍሮንታላ ኮርቴክስ እኛን የመቆጣጠር አቅማቸው በጣም አነስተኛ ነው። በተቀራኒው የስሜት ክፍላችን የሆነው አሚግደላ ልክ እንደ ዝሆን ጠንካራው እና መሪው ነው። እምነት ሰዎች በአንድ ጉዳይ ላይ የተሟላ እውቀት ሳይኖራቸው ሲቀር የሚደገፉበት ምርኩዝ ነው። ማናችንም ስለፈጣሪ ሙሉ እውቀት የለንም። ወይም ስለዚህ ዓለም አመጣጥ። ሁለት አማራጮች ብቻ ነው ያሉን። ማመን፦ ይሄ ዓለም እንዲህ ነው የተፈጠረው ብለን። ወይም መላምቶችን መዘርዘር። መላምቶችንም የምንቀበልበት መንገድ ሁለት ነው። ማመን ወይም ይሄ መላምት ነው። ፍጹም ውሸት ሊሆን ይችላል። ስለዚህ አላውቅም። ባለማወቄም ሳልሸማቀቅ እኖራለሁ ብሎ መቁረጥ።

 

ልክ ከእውቀት በላይ እምነት በዚህ ዓለም ላይ ጠንካራ የሰዎችን ባህሪ ለዋጭ ጉዳይ እንደሆነ ሁሉ፤ ከእውነት በላይ ፕሮፖጋንዳ ሰዎችን ይቆጣጠራል። አንድ ነገር እውነት ተብሎ በሰዎች ቅቡልነት እንዲኖረው ኦብጀክቲቭሊ (objectively)  መታወቅ አለበት። ለምሳሌ ግራቪቲ እውነት ነው። ምክንያቱም ኦብጀክቲቭሊ ይታወቃል። ይሄ ማለት ሁላችን እናውቀዋለን ማለት አይደለም። ግን በአግባቡ ምርምር እና ጥናት ካደረግን እናውቀዋለን። ፀሐይ በምስራቅ ነው የምትወጣው። ሁሉም ሰው ይሄን ላያውቅ ይችላል። ግን የፀሐይን በምስራቅ መውጣት አይቀይረውም። እነዚህ አይነት እውቀቶች ናቸው ሌሎች እውቀቶችን እየጨመሩልን እንድንሄድ የሚያደርጉን። ብዙ ጊዜ ሰዎች ከእነዚህ ዓይነት እውነቶች ይልቅ በእምነት የሚገኝ እና በድግግሞሽ የሚደመጥን ትርክት የበለጠ የመቀበል እና ለዛ ዋጋ የመክፈል ዝንባሌ አላቸው።

 

ሁላችንም የሆነ የምናምነው ነገር ውሸት ነው። አሁን ላይ ከምናምናቸው ነገሮች ውስጥ ቢያንስ አንዱ ውሸት ነው።የብዙዎቻችን ደግሞ ብዙ የምናምናቸው ነገሮች ውሸቶች ናቸው። ለምሳሌ የቁልቋል ተክል ፈሳሹ ከሰገራ ጋርተቀላቅሎ የሚፈጥረውን ኬሚካል ብንቀባው መላጣነትን ያስቀራል ብዬ ብጽፍ፤ ለመጀመሪያ ጊዜ የሚያነበው ሰው ስቆ ሊያልፍ ይችላል። ከዛ ሌላ የሕክምና ሰው ይሄንኑ የሆነ ቦታ አስፍቶ ጽፎ ብታዩት። ከዛ ሌሎች ሰዎችም እየተቀባበሉ ጽፈው ብትመለከቱት። የዛኔ ለመሞከር ልትነሳሱ ትችላላችሁ። ከዛ የሆነ ሰው “ይሄው የእኔ ጸጉር ሞልቶ ተመልከቱ” ብሎ ቢያሳያችሁስ። አሁን ጭራሽ ከማመን አልፋችሁ እናንተም ወሬውን ማሰራጨት ትጀምራላችሁ። ሰዎች ለአንድ ሀሳብ በተደጋጋሚ ከተጋለጡ ያንን የማመን ዝንባሌ አላቸው። አንድን ነገር በተደጋጋሚ ከሰማነው እውነት እየመሰለን ይሄዳል።ለዚህ ነው ፕሮፖጋንዳ በጣም አዋጭ የሆነው።

 

ለፕሮፓጋንዳ ምርጡ ምሳሌ ፕሬዝዳንት ትረምፕ ነው። ፕሬዝዳንት ትረምፕ የተዋጣለት ኮሚኒኬተር ነው። ማንም የሚረዳውን ቋንቋ ይናገራል። ስለሚናገረው ነገር እውነትነት ተጨንቆ አያውቅም። ግን በተደጋጋሚ ያንን ለመናገር አያመነታም። በዚህም ብዙ ሰዎች በመጨረሻ እርሱ የሚናገረውን ያምናሉ። ኢኮኖሚው እየወደቀ ፕሬዝዳንት ትረምፕ በከፍተኛ ደረጃ ኢኮኖሚው እያደገ ነው ለማለት ምንም ችግር የለበትም። በተመሳሳይ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይን ተመልከቱ። መደመር መደመር እያለ ይሰብካል። በተቃራኒው እርሱን የሚቃወም ሰው ለደቂቃ አጠገቡ አይታገስም።ትላንት አብረውት ወደ ስልጣን የመጡት ሁሉ ዛሬ ሀገር ጥለው ወጥተዋል ወይም ተገድለዋል። ሌሎች ደግሞ ፍጹም ገብረዋል። ግን አሁንም መደመር የሚል መጽሐፍ አጽፎ ያስመርቃል። አብይ ምስኪን እና ስሱ ሆኖ ለመታየት ነው በሚዲያ የሚጥረው። በድርጊቱ ግን ጨካኝ እና ለሰው ልጆች ሕይወት ምንም ደንታ የሌለው ሰው ነው። ግን የእርሱን ምስኪንነት፣ እጅ ሳሚነት፣ ትከሻ ዳባሽነት፣ ጺም ነካኪነት፣ የእናቶችን እጅ ሳሚነት ሚዲያው በማሳየት ፥ምስኪን የመሰለ ስዕል ስለእርሱ አሁን ሳይቀር (ይሄን ሁሉ ካየን በኋላ) ይመጣብናል። ምክንያቱም ሰው አብዝቶ የሚያየውን ነገር የማመን ዝንባሌ አለውና።

 

ሌላኛው ጉዳይ እውነት ደባሪ ነው። እስቲ ተመልከቱ ብዙ የሃይማኖት መጽሐፎችን። ከፍታችሁ አንብቧቸው። ከዛ ደግሞ የተረት መጽሐፎችን አንብቧቸው። በሚደንቅ ሁኔታ በሃይማኖት መጽሐፎች ላይ የምታገኟቸውን ታሪኮች ከሃይማኖት ጋር በማይገናኙ መጽሐፎች ብታገኟቸው ኖሮ ፈጽሞ አምናችሁ አትቀበሏቸውም። ስለዚህ ታሪኮቹን ለማንበብ ራሱ በስሜት መዘጋጀት እና በሆነ መጠን የውስጥ መሻታችሁ አንዳች ከፍ ያለ በስሜት ከፍታ አንድን ነገ ርለማግኘት መዘጋጀት አለባችሁ።


እውነት ግን በተቃራኒው በጣም ደባሪ ነው። ማነው ሒሳብን እንደ ስብከት የሚማረው? ማነው ውስብስብ ማክሮ ኢኮኖሚን ወይም አልጀብራን ወይም ሴሉላር እና ሞሎኪውላር ባይሎጂን ተመስጦ የሚሰማ? በተቃራኒው ታሪክን ስንሰማ ያለንን መመሰጥ እዩ ምክንያቱም ታሪክ ብዙ ነገሩ ግነት እና የሰው ድራማቲክ ትረካ ነው።

 

ለዚህ ነው ፕሮፖጋንዳ መሳጭ የሚሆነው። አንደኛው የፕሮፓጋንዳ መለያው ቀልድ፣ ሳቅ እና ፈገግ ማስባል ነው። ፕሬዝዳንት ትረምፕን ተመልከቱ አሁንም። እርሱ ሲናገር የሚጠሉት ሰዎች ሳይቀር ይስቃሉ። ሰውዬው ብዙዎች አፍረው የማይናገሩትን ነገር ያለምንም ጥንቃቄ ያወጣዋል፣ ከዛ ያንን የሚሰማ ሁሉ ይስቃል። በመሳቅ ሳናውቀው ወደ እርሱ ቀስ እያልን እንሳባለን። ምናአልባትም ለዚህ ይሆናል ታላቁ ሰባኪ ዮሐንስ አፈወርቅ ሳቅን ይጸየፍ የነበረውበእርሱ እምነት ጤነኛ የሆነ ሰው ይሄ ሁሉ ግፍ በሚፈጸምበት ዓለም ላይ ሊስቅ አይችልም ብሎ ያስባል።ለዚህም ይመስላል የእርሱን ስብከት ብዙዎች በዘመናቸው የሚታገሱት ያልነበረው። ማስታወቂያዎች ለዚህ ነው የሚያስቁ ሰዎችን እና ታሪኮችን ለእቃቸው ማስታወቂያነት የሚጠቀሙት። ቀስ እያልን ለፕሮዳክታቸው ፍቅር ያድርብናል።

 

ከፕሮፓጋንዳ ይልቅ ለእውነት እንዴት እንገዛ?

 

መጀመሪያ የምንሰማው ነገር በኛ ላይ ምንም የሚያመጣው ለውጥ የለም ብለን አናስብ። ስለሁሉም ጉዳይ ደግሞ እውቀትላይኖራችሁ እንደሚችል ብቻ ሳይሆን ለማጣራትም ጊዜም እንደሌላችሁ እወቁ። በሆነ ነገር ፍላጎት ካደረባችሁ፤ ከዜና ተቋማት ያንን እውቀት ከማግኘት ይልቅ፤ ጊዜ ስጡት እና ጥናት አድርጉበት። ሁሉንም ነገር ማጥናት ስለማትችሉ፤ በብዙ ጉዳይ ላይ አቋም አይኑራችሁ። አቋም ባለመያዝ ምቾት ይሰማችሁ።


ባስ ላይ፣ መኪና ውስጥ ወይም ስልካችሁ ላይ ዝም ብሎ የሚመጣላችሁን ዜና አትቃርሙ። አዕምሮአችን ያስገባውን መረጃ ልክ እንደ ምግብ ነው የሚመለከተው። ያስገባውን ያላምጠዋል። ከዛ ውሳኔ ለመወሰን ይጠቀምበታል።መጨነቅ፣ መፍራት፣ መረበሽ ውሳኔዎች ናቸው። መደሰት፣ ጽንፈኛ መሆን፣ መጥላት፣ መውደድም ውሳኔዎች ናቸው። መደገፍ እና መቃወምም ውሳኔዎች ናቸው። እነዚህ ሁሉ አዕምሮአችን ውስጥ በገቡ ብዙ ውሸቶች (ፕሮፖጋንዳዎች) የሚሰጡ ውሳኔዎች ናቸው። ለዚህ ነው ወደ አዕምሮአችን ውስጥ በማንኛውም ጊዜ ስለምናስገባቸው መረጃዎች መጨነቅ ያለብን። ነጻ የሚመስሉን መረጃዎች ሁሉ በመጨረሻ ከፍተኛ ወጪ ያሶጡናል።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page