top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Feb 24
  • 4 min read

ree



ስትራቴጂ ጽንሰ ሀሳቡ የመጣው ከውትድርና ወይም ጦርነት ነው። ለዚህ ነው ስለስትራቴጂ ሲነሳ ሁልጊዜ በተቀናቃኝ ላይ ብልጫ ከመያዝ አንጻር የሚሆነው። ምክንያቱም በመሠረቱ ስትራቴጂ ማለት በተቀናቃኝ ላይ የመጨረሻውን የድል ብልጫ መውሰድ ማለት ነው። ነገር ግን ስለስትራቴጂ ማውራት እና ስትራቴጂ ቀርጾ በተግባር ላይ ማዋል ለየቅል ናቸው።



በዚህ ጹሁፍ ስለ ስትራቴጂ ዓምስት ጉዳዮችን እዳስሳለሁ፤



፩) ስትራቴጂ ለዘላቂ አሸናፊነት የግድ ያስፈልጋል፤



፪) ስትራቴጂ መሪነትን ይፈልጋል፤



፫) ስትራቴጂ እና ተጽዕኖ መፍጠር የማይነጣጠሉ ናቸው፤



፬) ታላላቅ ስትራቴጂዎች ግባቸውን እንዲመቱ የተከታዮች እና የመሪዎች ጽናት ምሰሶ ነው፤



፭) ስትራቴጂ በየጊዜው ራሱን ከሁኔታዎች ጋር ማስማማት መቻል አለበት፤



፩) ስትራቴጂ ለዘላቂ አሸናፊነት ወሳኝ ነው፤



በውትድርና መጥፎ ስትራቴጂ ወይም ስንኩል ስትራቴጂ ሲኖርህ ግልጽ ላልሆነ ፖለቲካዊ ግብ ትዋጋለህ፣ የአቅርቦት እና የሪሶርስ እጥረት በየጊዜው ያጋጥምሃል፣ ያለአቅምህ ትለጠጣለህ ከዛም “utopia” የሆነ ፈጽሞ የማይሳኩ ግቦች ይኖሩሃል። ይሄ የመጥፎ ስትራቴጂ ወይም የስንኩል ስትራቴጂ ውጤቶች ናቸው። በቢዝነስ ተቋሞችም ውስጥ ተመሳሳይ ነው። የቢዝነሱ ግብ እና አቅም እና ችሎታ ያላቸው ሠራተኞች የሚያጠፉት ጊዜ የተራራቀ ነው። ቢዝነሱ ያለአቅሙ ይለጠጣል፣ በሁሉ ነገር ይነከራል፣ ሁሉን ነገር ለማግበስበስ ይጥራል።



የስትራቴጂክ ስህተት እና የኦፕሬሽን ስህተቶች ውጤታቸው የተለያየ ነው። ስትራቴጂው ጥሩ ሆኖ ኦፕሬሽኑ ላይ ስህተት ቢሰራ ማረም በጣም ቀላል ነው። የተሳሳተ ስትራቴጂ ኖሮ ግን ኦፕሬሽኖችህ ቢሳኩ እንኳ እምብዛም ጥቅም የለውም። ስለዚህ ሳስብ ዘወትር እንደምሳሌ የሚመጣልኝ ጌታችን በስሙ አጋንንት ያወጡትን ሰዎች ያላቸው ነው። “ጌታ ሆይ፥ ጌታ ሆይ፥ በስምህ ትንቢት አልተናገርንምን ፥ በስምህስ አጋንንትን አላወጣንምን ፥ በስምህስ ብዙ ተአምራትን አላደረግንምን? ይሉኛል። የዚያን ጊዜም። ከቶ አላወቅኋችሁም፤ እናንተ ዓመፀኞች፥ ከእኔ ራቁ ብዬ እመሰክርባቸዋለሁ።” እነዚህ ሰባኪያን ኦፕሬሽን ሌቨል (level) ላይ የተሳካ ሥራ የሠሩ ነበሩ፣ ብዙዎች ማሳካት ያልቻሉትን ነገር የፈጸሙ ነበሩ። ነገር ግን ያ ሁሉ በተሳሳተ ዓላማ ላይ የቆመ ስለነበረ አላውቃችሁም ተባሉ።



እኔ ይሄን ለስትራቴጂ ጥሩ ምሳሌ አድርጌ የምወስደው በሕይወት ብዙዎቻችን እንደዛ ስለሆንን ነው። ገንዘብ ማግኘትን ስትራቴጂክ ግባቸው ያደርጉና በመጨረሻ ግን ቤተሰብ አልባ እና ጤና አልባ የሚሆኑ ሰዎች የስትራቴጂ ስንኩልነት የገጠማቸው ናቸው። በሀገር ደረጃ ደግሞ የትግራይ ጦርነት ትልቁ የስትራቴጂ ውድቀት የታየበት ነበር። መቀሌ መግባት ኦፕሬሽን ማሳካት እንጂ ስትራቴጂ አልነበረም፣ በዚህም ምክንያት ያ ጦርነት ሀገሪቷን ያደማ፣ ቤተክርስቲያንን የከፈለ፣ ማንም ያላተረፈበት ሆነ። መንግስት በአማራ ክልል የተከተለው የትጥቅ አስፈታለው ኦፕሬሽንን ተመልከቱ፦ ምን ነበር ስትራቴጂው? ከዛ ምን አስከተለ? ምን ላሳካ ብሎ ትጥቅ ካልፈታችሁ አለ? አሁን የተከሰተውን እና ማጠፊያ ያጣውን መዓት ተመልከቱ። ወደ ቤተክርስቲያን ስንመጣ ደግሞ በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ወጥቶ እና ከፍተኛ ጊዜ እና ገንዘብ ተርከፍክፎባቸው የሚደገሱ የመዝመሩ፣ የጉባኤ ድግሶች የስትራቴጂ አለመኖር ወይም የመጥፎ ስትራቴጂ ውጤቶች መሆናቸውን ለማወቅ ብዙ ራሱ ሳንቆይ ከዛ በኋላ የሚከሰቱ ልዩነቶችን ማየት ብቻ ይበቃል። ምንድነው ያስገኙት ውጤት? የወጣባቸው ልፋት እና የተለወጠው ነገር ይመጣጠናል? ምንድነው የምር ያሳካነው? በመጨረሻ እነዚህን ሁሉ ከምን አንጻር መዝነናቸው ስትራቴጂው ልክ ነበር ወይም አይደለም እንበል? የማይመዘን፣ የማይገመገም እና የመመዘኛ እና የመገምገሚያ መስፈረት ያላስቀመጠ ስትራቴጂ ገና ከመነሻው ችግር ያለበት ነው።



መጥፎ ስትራቴጂ ኖሮን በኦፕሬሽ ጉዳዮች ላይ መከራከር ጊዜ ማጥፋት ነው። እኔ ብዙ ጊዜ ራሴን ከእንደዚህ ዓይነት ጉዳዮች ማራቅን ነው የምመርጠው ፥ ትልቁን ስዕል ለማየት ፍቃደኛ የሆነ አዕምሮአዊ ክህሎትን ማሽተት ካልቻልኩ። ምክንያቱም የተሳሳተ ስትራቴጂ ኖሮ ስለኦፕሬሽን ማውራት ፥ መኪና እንደሚያባርር ውሻ መሆን ነው። መኪናውን ቢደርስበትም ውሻው ምንም አያደርገውም። ነክሶ አያደማው፣ ቦጭቆ አይበላው።



ጥሩ ስትራቴጂ ዓላማን ከተግባር ጋር የሚያዋህድ ነው። ሁለቱን ማጋባት ሲችል ስትራቴጂው ጥሩ ነው ይባላል። ይሄ ማለት ካለን አቅም፣ የሰው ኃይል፣ ሪሶርስ እና ሁኔታ ጋር የተዛመደ ተግባሮችን ማሳካት ከምንፈልገው ዓላማ ጋር ስንቀርጽ ጥሩ ስትራቴጂ ይባላል።



በመነሻዬ እንዳልኩት ስትራቴጂ ተቀናቃኝ ባለበት ሁኔታ የሚቀረጽ እና መነሻውም ከጦርነት ነው።



ስለዚህ ስለስትራቴጂ ስናስብ የግድ ከግንዛቤ መውሰድ ያሉብን ሦስት ነጥቦች አሉ፤



1) የኛን መጎዳት ወይም መክሰር የሚፈልግ ጠላት ወይም ተቀናቃኝ እንዳለን ማመን ያስፈልጋል።


በዚህ ዓለም ላይ ጦርነት ፈጽሞ ሊቆም እንደማይችል ማመን ከሞኝነት የመላቀቂያ የመጀመሪያው ደረጃ ነው። በተመሳሳይ ዓላማ አንግበን፣ አንዳች ነገር ለማሳካት ስንነሳ በሁሉም አቅጣጫ ጠላቶች እንደሚነሱብን መቀብል የተግባራዊ አስተሳሰብ ጅማሮ ነው። የእኛ መነሳት ወደድንም ጠላንም የሚጎዳው አካል ይኖራል። ያ አካል በቻለው መጠን ይዋጋናል። የእርሱ የበታች አድርጎን ለማቆየት ወይም ለማጥፋት ይሰራል። ስለዚህ ስትራቴጂ ይሄን ሁልጊዜ ከግንዛቤ መውሰድ አለበት።



2) ስትራቴጂ የሚጸናባቸው ግምቶች ለጥሩ ስትራቴጂ እጅግ ወሳኝ ናቸው። ማንኛውም ስትራቴጂ ሲቀረጽ ስለራስም ሆነ ስለተቀናቃኝ ወይም ከኛ ውጪ ስላሉ ነገሮች ጠንቅቀን አናውቅም። ስለዚህ ስትራቴጂያችን ከሞላ ጎደል በግምቶች (assumptions) ላይ የተመሰረተ ነው። ስለዚህ የስትራቴጂያችን ጥራት በግምቶቻችን ጥራት ላይ ይመረኮዛል። በውትድርና ውስጥ እነዚህን ግምቶች በስለላ ተቋሞች በኩል ሲገኝ፣ በግለሰብ ሕይወትም ሆነ በተቋሞቻችን ስለተቀናቃኞቻችን ያለንን እውቀቶች የምንሞላበት መንገዶች ሊኖሩን ይገባል። አለበለዚያ የሚኖረን ስትራቴጂ ሳይሆን ህልም እና ርዕይ ነው።



3) ጥሩ ስትራቴጂ በአንድ ሀሳብ፣ መሳሪያ ወይም ግለሰብ ብቃት ወይም አቅም ላይ የተንጠለጠለ ፈጽሞ መሆን የለበትም። የትኛውም ጥሩ የውትድርና ስትራቴጂ ባሉት ጥቂት መሳሪያዎች (ከጠላት በሚሻሉ) ላይ ተንጠልጥሎ ተሳክቶ አያውቅም። ወይም በአንድ ግለሰብ ላይ ተመርኩዞም ዘላቂ አሸናፊነት አይገኝም። ከታዋቂ ጄኔራሎች እና የጦር መሪዎች ጀርባ ቀላል የማይባሉ ስትራቴጂክ አሳቢዎች እና የኦፕሬሽን አስፈጻሚዎች አሉ። ዓለም ልብወለድ እና ድራማ ስለሚወድ አንድ ናፖሊዮ፣ አንድ አሌክሳንደር፣ አንድ ምንሊክን ማድነቅ ይወዳል እንጂ ከእነዚህ ምርጥ የጦር ጄኔራሎች ጀርባ ከእነሱ የማይተናነሱ ሌሎች ምርጦች ነበሩ። በተመሳሳይ የሁለተኛው የዓለም ጦርነትም ሆነ ቀዝቃዛው ጦርነት አሜሪካ ከጀርመን ወይም ከራሺያ የሚልቁ ምርጥ መሳሪያዎች ስላሏት አይደለም ያሸነፈችው። ይልቁስ ብዙ ነገርን ታሳቢ ባደረገ እና ውህደት (synergy) በፈጠረ፣ በየጊዜው ራሱን እያሻሻለ እና እየተማረ በሚሄድ ስትራቴጂ እና መሪዎች ምክንያት ነው ያሸነፈችው። ተቀናቋኇቿ ደግሞ ይሄ አልነበራቸውም።



በግል ሕይወትም ከችግር ለመውጣት ገንዘብ የሚጠይቅ ሰው እምብዛም ከችግር እንደማይላቀቅ አምናለሁ። ለእንደዚህ ዓይነት ሰውም ሆነ ተቋሞች የሚሰጥ ገንዘብ ከብክነት ብዙ ለይቼ አላየውም። ምንም ጥርጥር የለውም ገንዘብ በኦፕሬሽን ላይ የሚያስፈልግ ትልቅ ሪሶርስ ነው። ነገር ግን ገንዝብ ስትራቴጂ ሆኖ አያውቅም። በጎስቋላ ሕይወት ውስጥ ያለ ግለሰብም ሆነ እንደ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ያሉ ተቋሞች የገንዘብ ችግር አይደለም ያለባቸው። እንደውም ገንዘቡ የችግሩ አካል ሆኖ እንጂ የምንመለከተው። እንደ ኮዳክ ካሜሬ እና ኖኪያ ስልክ የመሰሉ ኩባንያዎች መሪዎቻቸው እያለቀሱ ከገበያ የወጡት የገንዘብ እጥረት ስለነበረባቸው አልነበረም። ስለዚህ ስለጥሩ ስትራቴጂ ስናስብ ገንዘብ ስላለን፣ ወይም አንድ ምርጥ ሰው በመካከላችን ስላለ፣ ወይም ጥሩ መሳሪያዎች ስላሉን ስትራቴጂያችን ይሳካል ብለን ማሰብ የለብንም።




 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Feb 23
  • 3 min read

ree


በእኔ ዓይነት ሥራ ወይም የሰዎችን መከራ እና ስቃይ መስማት የየዕለት ሥራችሁ ሲሆን ፥ ሰውን የሚያሳዝን እና የሚያስለቅስ ታሪክ ልክ የፀሐይ በምስራቅ የመውጣት ያህል ኖርማል ይሆንባችዋል። በሂደት፣ ብዙ ሰዎች እንደሆኑት፣ ትደነድናላችሁ። በተለይ ይሄ ሥራዬ ነው ብላችሁ ከወሰዳችሁት ፥ ራሳችሁን እንዲረበሽ አትፈቅዱለትም። በዚህም ሰዎች ለእናንተ ቴክኒካል ችግር ይሆኑባችዋል። ልክ እንደ ማሽን መጠገን ከቻላችሁ የምትጠግኗቸው፣ አለበለዚያ ግን የምትተዎቸው።



በቅርብ ከአንድ የሕግ ትምህርት ቤት ፕሮፌሰሬ ጋር ምሳ ነበረን። በመኃል በቅርብ የመኪና አደጋ ደርሶባት ሆስፒታል ገብታ ስለነበረችው ሚስቱ በትካዜ ያወራኝ ጀመር። ስለሕክምናው ሲነግረኝ፤ ለዶክተሮቹ ሚስቴ ቴክኒካል ችግር (techinical problem) ነበረች። ለነርሶቹ ግን ሚስት፣ እናት፣ ሴት እና የእነሱን ርዳታ ፈልጋ በእጃቸው ላይ የወደቀች ተረጂ ነፍስ ነበረች። ዶክተሮቹ እንደ ማሽን ለመጠገን ዓይተዋት ሲወጡ ፥ ነርሶቹ ግን አጽናንተዋትም ጭምር ነበር የሚለዩን አለኝ።



ከሰዎች ጋር የሚያገናኝ ሥራ እንሰራ ይሆናል። እንጀራ የሚያመጣ። የሰዎች ችግር የገንዘብ ምንጫችን ሊሆን ይችላል። ግን እነዛ ሰዎች ሰውነታቸው ከተረሳን ፥ በመጨረሻ የራሳችንን ልብ ጭምር እናጣዋለን። ዋረን በፌት ለሼሬ ሆልደሮቹ ዛሬ በጻፈው ዓመታዊ ሪፖርት ፥ “ይሄን ሪፖርት ትላልቅ ኩባንያዎች በየዓመቱ እንደሚያዘጋጁት ዓይነት ሪፖርት ዓይደለም የምንጽፈው እና የምናዘጋጀው። ይልቁንስ እኛ ሼር ሆልደር ብንሆን ምን ዓይነት ሪፖርት ነው ማንበብ የምንፈልገው ብለን በማሰብ ነው የምናዘጋጀው። ገንዘባችሁን እኛን አምናችሁ ፥ በኛ ኩባንያ ላይ ኢንቨስት ካደረጋችሁ ፥ ልክ እኛ በእናንተ ቦታ ብንሆን ማንበብ የምትፈልጉትን በማሰብ ነው የምንጽፈው” ይላል። ለዚህም ነው የበፌት ዓመታዊ ሪፖርት እንደ ልብ አንጠልጣይ ፊልም በጉጉት የሚጠበቀው። የሚነበበው። ለምን? ምክንያቱም ራሱን በሌሎች ጫማ ውስጥ መክተት ችሏል። የሌሎችን ሰውነት የየቀን ዕለታዊ የሆነው ሥራው እንዲያስረሳው አልፈቀደም። ያን ነው ትልቅ ልብ የምለው። ያ ልብ በፈጣሪ የሚያምኑ ሰዎች ሁሉ ለፈጣሪያቸው የሚሰጡት ልብ ነው። ሁላችንም አምላካችንን ትልቅ ነው ብለን እናምናለን። ሺ ዘመናት ተደጋግሞ ቢሰማው ፥ ምንም የሱ ጉልበት ፍጹም ኃያል ቢሆን ፥ ፊት ለፊቱ ተንበርክኮ የሚለምነውን ፍጥረቱን ግን ለመስማት ያዘነብላል ብለን እናምናለን። የኛ ስቃይ ለሱ ትልቅ ወይም አዲስ ስለሆነበት ሳይሆን ፥ ትልቅ ልብ ስላለው እንጂ።



ትልቅ ልብ ያለው መሪ ሲኖረን ፥ ሕጻናት ተጨፍጭፈው የችግኝ ተከላ ድግስ ደግሶ የሰዎችን ለቅሶ ለርሱ የሁልጊዜ ሥራው እንደሆነ አያስመስልም። ብዙዎቻችን ይሄ የሚጠቅመው የኛን ተገልጋይ ብቻ ይመስለናል። በፍጹም። ራሳችንን እንጂ። ሥራችን ሌሎችን እንደ ማሽን አሳይቶ ፥ የሰውነት ልብን ሊነፍገን ካልቻለ ፥ በመጨረሻ ሰዎችን የመረዳት እና የመገንዘብ ታላቅ ልብ ገንዘብ እናደርጋለን። ሰውነትን በምላት የመጎናጸፍ ዕድል እናገኛለን። ከዚህ የሚገኝ ርካታ ደግሞ ወደር የለውም።



ትልቅ ልብ ማለት የኛን ርዳታ ፈልጎ ፊትለፊታችን የቆመው ሰውን እኔ ብሆን እንዴት ነው የሚሰማኝ ብሎ የሱ ቁስል እንዲሰማን የመፍቀድ ልምምድ ነው። ዛሬ አሜሪካ ውስጥ የምታዮቸው መሪዎች ፥ አቅም እና ጉልበት የሌላቸውን ምስኪን ስደተኞች በሰንሰለት አስረው ወደ ማጎሪያ ማዕከል በመጣል መደሰት የቻሉት ፥ “ሕገወጦች” የሚል ስም ስለሰጧቸው ነው። ያ ስደተኞችን ለማሰቃየት እና የእነሱን ታሪክ ለመስማት እንዳይችሉ አቅሙን ሰጣቸው። እኛም የተለየን አንሆንም። ቆም ብለን ፥ የሌላውን ሰው መከራ ወደ ራሳችን ለማስጠጋት ካልወሰንን። እኔ ብሆንስ ካላልን።



ቶሎስቶይ በ1500 ገጽ በከተበው "ዎር ኤንድ ፒስ" መጽሐፍ ውስጥ አስገራሚ ብቃቱን የገለጸበት ሦስት መስመር ጹሁፉ ይመስለኛል። ዶሎኮቭ የተበላ ቁማርተኛ፣ የሽጉጥ ፍልሚያን የሚያዘወትር፣ ቢጠጣ ቢጠጣ የማይጠረቃ እና ቤተሰብ እንዳላሳደገው የሚኖር ሰው ነበር። የተለያዩ የአውሮፓ አገራትን ትምህርት ቀምሶ ወደ ሩስያ የመጣ እና የአባቱን ግዙፍ ሃብት በመውረስ ሃብታም ከሆነው "ፒየር" ከሚባል ሰው ጋር ዶሎኮቭ ይጣላል። የሽጉጥ ፍልሚያ የጥሉ መቋጫ እንዲሆን ይስማማሉ። ሁሉም ዶሎኮቭ ካለው ፍጹም የልምድ ብልጫ በመነሳት ፒየርን እንደሚገለው ገመቱ። ከፍልሚያው በፊት ዶሎኮቭ ለወዳጁ ሮስቶቭ "ይኸውልህ ወደ እንደዚህ ዓይነት ግጥሚያ ስትሄድ እንደምትሞት አስበክ ኑዛዜ ጽፈክ፣ የመጨረሻ ቃልህን በሚያምር ቃላት ከትበኸ መጓዝ የለብህም። ግን እንደምትገድል ቅንጣቢ ጥርጣሬ ሳይኖርኽ ከገባህበት ሁሉም ነገር ይሰምራል። ልክ እንደ ድብ አዳኝ ፥ ፍርሃቱን ከገለጠ ድቡ ያንን በማሽተት እንደሚያከሽፍበት ሁሉ ፣ ፍርሃት ከተሰማክ ሁሉ ነገር እዛው ያከትማክ።" ሲያቀብጠው እዚህ ጉድ ውስጥ እንደገባ የገባው ፒየር ግን አንዴ ለግጥሚያው እሺ ብያለው እንግዲህ የፈሰሰ ውሃ አይታፈስ በሚል ፍልሚያው ሜዳ ላይ ቆመ። ፒየር ዶሎኮቭን ክፉኛ አቆሰለው። ዶሎኮቭ ፒየርን ሳተው። ሮስቶቭ ጓደኛውን አቃቅፎ ወደ እርዳታ ከነፈ። በመኃል ዶሎኮቭ እያቃሰተ እነዚህን ቃላት ይተፋል "ይሄን ከሰማች ትሞታለች፣ አትተርፍም፣ ለእኔስ ግድ የለኝም እሷ ግን ... እሷ ግን ቆማ መሄዷን እንጃ። ወይኔ ... ይሄን ጉድ ...ማየት የለባትም ... በሕይወት አትኖርም ..." ሮስቶቭ ግራ ገባው! "ስለ ማን ነው የምታወራው?" አለው። "ስለ ... እናቴ! .... ስለ እህቴ!" ከዚህ በኋላ ሮስቶቭ አዕምሮ ውስጥ የተመላለሰው ቃላቶች ናቸው ዘወትር የሚገርመኝ። "ዶሎኮቭ ወንበዴው፣ ዶሎኮቭ ቁማርተኛው፣ ዶሎኮቭ አጭበርባሪው ... አፍቃሪ ልጅ እና ወንድምም ነበር!"



በኢኮኖሚክስ የኖቤል ተሸላሚ የሆነው እና የሆሎኮስት ተራፊ Daniel Kahneman በደች ግዛት ውስጥ ከጀርመን ወታደሮች ቤተሰቦቹ ደብቀውት እያለ ከተደበቀበት ቦታ አፈትልኮ ይወጣል። "መንገዱ ኦና ነበር። ሰው አይታይም" ይላል ጊዜውን ሲያስታውስ። "ዞር ስል አንድ ወታደር ጋር ዓይን ለዓይን ተጋጠምን። ለመሸሽ ሞከርኩ። ጠራኝ። ሮጬ ማምለጥ እንደማልችል ስለገባኝ ወደ ወታደሩ ሄድኩ። የናዚ ጀርመን ወታደር ነበር። በሁለት እጆቹ ወደ ላይ ላጥ አርጎ አነሳኝ። ዓይኖቹ እንባ አቀረሩ። ስንት ዓመትህ ነው አለኝ። ነገርኩት። 'አንተን የሚያህል ልጅ አለኝ። በጣም ናፍቆኛል' ብሎ ሳመኝ እና ወደ መሬት መለሰኝ።" ዳኒ ስለ ሰው ያለው አመለካከት ከዛ ጊዜ ጀምሮ እንደተለወጠ ይናገራል።


ዳንኤል የእውቀት ልህቀቱ እና የሰውን ተፈጥሮ በማወቅ አቻ የማይገኝለት ሰው የነበረ ቢሆንም እስኪሞት ድረስ ግን ሰዎችን ነጭ ወይም ጥቁር ብቻ በሚል ፍረጃ (ማለትም ጥሩ ወይም መጥፎ) ወጥመድ ሳይወድቅ ቀረ። በክፉው እና በደካማው ሰው ውስጥ ሳይቀር የጽድቅን ልምላሜ ፥ የሰውነትን ዘር ማሽተት እንዲችል ሆነ። ትልቅ ልብ ማለት ያ ነው። ትልቅ ሆኖ ለመሞት ፈቀደ። ትልቅ ሰው ሆኖ ይሄን ትንሽ ሕይወት ፈጸመ።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Feb 4
  • 5 min read

እንቢ ማለትን በምግብ


በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አከራካሪ ከሆኑ ነገሮች አንዱ እና የተለያዩ ሊቃውንትም ግራ ከሚጋቡበት ነገሮች ውስጥ ንጹሁ የሆኑ እና ንጹሁ ያልሆኑ ተብለው እንስሳት ለምግበ እስራኤል መለየታቸው ነው። በተለይ በዘፍጥረት ምዕራፍ አንድ ላይ እግዚአብሔር የፈጠራቸው ፍጥረታት ሁሉ መልካም መሆናቸው በይፋ ተገልጾልን፣ ፍጥረቱን እንደሚወድ እና እንደሚመግባቸው በብዙ የመጽሐፍ ክፍል ተነግሮን ሳለ፣ እንደገና ንጹሁ የሆኑ እና ንጹሁ ያልሆኑ ተብለው መለየታቸው እስራኤሎችን ሳይቀር ግራ የሚያጋባ ነው።


ከክርስቶስ ልደት በፊት በግብጽ አሌክሳንደሪያ ብዙ ግብጾች ይኖሩ ነበር፤ በአይሁድ የአመጋገብ ምርጫ የሚደነቁ ሄለናዊያን እና ግሪኮች እነዚህን አይሁዶች ለምን ንጹሁ እና ንጹሁ ያልሆነ ምግቦች በማለት አንዳንድ እንስሳትን እንደማይበሉ ጠይቀዋቸው ነበር። ፋይሎ የሚባል ሊቅ በሰዓቱ ለዚህ ምክንያት ነው ያላቸውን ዘርዝሮ ጽፎ ነበር። የአርስጣጢለስ ደብዳቤ ለአሌክሳንደርም ይሄን ጉዳይ ያብራራል። እውነታው ግን በርግጠኝነት ማናቸውም ምክንያቱን እንደማያውቁት ነው የሚያሳየው።


ይሄ በዘሌዋውያን ምዕራፍ 11 እስራኤል እንዲበሉት ተብለው የተጠቀሱት እንስሶች አንዳንዶቹ በእንደዚህ ባህሪያት ተለይተዋል፤


፩) የተሰነጠቀ ሰኮና ያለውንና የሚያመሰኳውን እንስሳ ሁሉ ብሉ።

፪) በባሕሮችና በወንዞች ውስጥ ክንፍና ቅርፊት የሌላቸው ሁሉ በእናንተ ዘንድ የተጸየፉ ናቸው።

፫) በአራት እግሮቹ ከሚሄድ እንስሳ ሁሉ በመዳፎቹ ላይ የሚሄድ በእናንተ ዘንድ ርኩስ ነው፤

፬) በሆዱ የሚሳብ፥ በአራትም እግሮች የሚሳብ፥ ብዙ እግሮችም ያሉት፥ በምድርም ላይ የሚንቀሳቀሱ ተንቀሳቃሾች ሁሉ የተጸየፉ ናቸውና አትብሉአቸው።


ስለሚበሩ ወፎች የተነገረ መለያ ሕግ ባይኖርም፤ የማይበሉት እንደ ቁራ፣ ዳክዬ፣ ጥንብ አንሳ ተዘርዝረዋል።


በብሉይ ሕግ ስለንጽህና በምግብ ብቻ ሳይሆን በአልባሳትም ተጠቅሷል። ለምሳሌ ሁለት ዓይነት ቀለማት ያሉት ልብስ መልበስ ንጹሁ አይደለም። የሞተ እንስሳ መንካትም እንዲሁ ከንጽህና ያሶጣል። እነዚህን ነገሮች ማድረግ ኃጢአት ነው ሳይሆን፣ ወደ ተቀደሰው ቤት እና ወደ መቅደሱ ለመግባት ግን የመንጻት ሥርዓትን መፈጸም ያስፈልጋል።


አንዱ የሊቃውንት መከራከሪያ እነዚህ ንጹሁ አይደሉም የተባሉ እንስሶች በጣዖት በሚያመልኩ ሕዝቦች ዘንድ የአማልክቶቻቸው ወካይ ናቸው ተብሎ መጠቀሱ ነው ይላሉ። ለምሳሌ በዮሐንስ ራዕይ ሰይጣን በእንቁራሪት ተመስሏል፣ እንቁራሪት ደግሞ ንጹሁ አይደሉም ስለዚህ አትብሏቸው ከተባሉት ነው ወገኑ። ሌላኛው መከራከሪያ ደግሞ ንጹሁ የተባሉ እንስሳት የወገኖቻቸው ወካይ ናቸው፤ ለምሳሌ በውሃ ውስጥ የሚኖር እንስሳ ክንፍና ቅርፊት ከሌለው የአሣን መስፈረት አያሟላም ፥ ስለዚህ ያን ዘር (የአሣን) አጉዳይ ስለሆነ ንጹሁ እንዳልሆነ ይቆጠራል የሚል ነው።

በስፋት በሀገራችን ሊቃውንት ሳይቀር የምንሰማው መከራከሪያ ደግሞ ዝምድና ነው። ለምሳሌ አሳማ ሁሉን የሚበላ፣ የሚከረፋ፣ ሆዳም ስለሆነ ያንን እንደ ኃጢአተኛ እና ከክብሩ እንደተዋረደ ማንነት አድርጎ በምሳሌ በማቅረብ፤ ለመብላት ንጹሁ ያልተባለው ለዛ ነው የሚል ነው። ጥንብ አንሳም ከዚህ ምሳሌ የሚካተት ነው።


ሌሎች ደግሞ ንጹሁ የተባሉት እንስሳት ለፈጣሪ በመሥዋዕት መልክ የሚቀርቡ በመሆናቸው፤ የፈጣሪ ምግብ ናቸው፣ በዚህም ንጹሁ ተባሉ። በተቃራኒው አሳማ፣ ግመል ደግሞ ለመሥዋዕት ስለማይቀርቡ፣ የሰው ልጆችም መብላት የለባቸውም የሚል ነው።


ሌሎች ደግሞ እንደ ጠንካራ መከራከሪያ አድርገው የሚያነሱት ከጤና አንጻር ነው። እንደ እንቁራሪት፣ አሳማ ያሉ እንስሶች ከውሏቸው እና አመጋገባቸው አንጻር ለጤና አደገኛ ስለሆኑ (ሁሉን የሚያግበሰብሱ በመሆናቸው) ለዛ ነው አትብሉ የተባልነው ይላሉ።

እውነት ለመናገር ከላይ የተጠቀሱት ምሳሌዎች እምብዛም አሳማኝ አይደሉም። ለምሳሌ ቀላል የማይባሉ ንጹሁ የተባሉ እንስሶች የክፋት ምሳሌዎች፣ የባዕድ አምልኮ ምልክቶች ነበሩ። በንጽህናም ከወሰድን ፍየል እምብዛም ከአሳማ የሚለይ የአመጋገብ ሥርዓት የለውም። ዶሮም ሁሉን የሚመገብ ነው። ከጤናም አንጻር የሚነሳው ክርክር ውሃ የሚቋጥር አይደለም። አሳማ ከምግባር አንጻር በመጥፎ እና በሁሉ አግበስባሽነት ቢመሰልም፣ በምንም ክፋት የማይመሰሉ እንስሶችም ንጹሁ አይደሉም እና አትብሏቸው ተብሏል። ለምሳሌ ዳክዬ፣ ሎብሰተር፣ ፈረስ እና ሌሎችም። ስለዚህ የክፋት ምሳሌ ናቸው መባሉም አሳማኝ መከራከሪያ አይደለም። ለፈጣሪ ምግብነትም (ከመሥዋዕት አንጻር) ተብሎ የሚቀርበው ምክንያት መሻገር የማይችሏቸው ነጥቦች አሉት። ለምሳሌ ለመብላት ንጹሁ ሆነው ለእግዚአብሔር ግን በመሥዋዕትነት ማቅረብ የማይፈቀዱ እንስሶች ነበሩ። አጋዘን አንዱ ነው። ይበላል ግን አይሠዋም።


ከበሽታ እና ከንጽህና አንጻርም እስራኤሎች የተለየ ጤናማ ሕዝቦች አልነበሩም። ንጹሁ የተባሉ እንስሳትን ብቻ በመብላታቸው ያተረፉት የተለየ የጤና ጉዳይ የለም። ሌሎች በሚጠቁበት በሽታ ሁሉ ተጠቅተዋል። ረዥም ዕድሜ በመኖር በአርኬዎሎጂ ጥናት መሠረት ሩቅ ምስራቆች የተሻሉ ናቸው። እነዚህ ደግሞ በአመጋገብ ባህላቸው ከእስራኤሎች የተለዩ ነበሩ።

አንድ መገንዘብ ያለብን ነገር መጽሐፍ ቅዱስ ንጹሁ እንስሳት እና ንጹሁ ያልሆኑ ብሎ ለመብል ሲከፍላቸው ፈጽሞ ከሰውነት ጤና እና ከረዥም ዕድሜ ጋር እንዳላያያዛቸው ነው።

በዚህ ክርክር ውስጥ እግዚአብሔር ለእስራኤላውን ንጹሁ እና ንጹሁ ያልሆኑ እንስሳት፣ አዕዋፋት እና የባህር እንስሶች ብሎ ሲለይ በምን ምክንያት ነው የሚለውን ከዳሰሱ እና አሳማኝ ሆነው ያገኘውትን ነጥቦች ልዘርዝር፤


1) መገደብን፣ እንቢ ማለትን ማስተማር፤


ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፥ “ሁሉ ተፈቅዶልኛል፥ ሁሉ ግን አይጠቅምም። ሁሉ ተፈቅዶልኛል፥ በእኔ ላይ ግን አንድ ነገር እንኳ አይሠለጥንብኝም።” እግዚአብሔር ሁሉን መልካም አድርጎ ከፈጠረ በኋላ፣ በገነት ውስጥ መታዘዝን፣ የሰውን በፍጥረቱ ውስጥ ያለውን ቦታ እና ከእግዚአብሔር ጋር ያለውን ግንኙነት የምታሳይ ያለመብላት ሕግ አውጥቶ ነበር። ያ ፍሬ በገነት ውስጥ ከነበሩት ፍሬዎች የተለየ ውበት ወይም ማስቀየም እንዳለው የተነገረን ነገር የለም። ሔዋን ለመብላት ስታስብ ፍሬው ያማረ እንደሆነ ከማየቷ በቀር። ይሄ ግን ሌሎቹ የሚበሉ ፍሬዎች ከዛ ዛፍ ያነሰ ውበት ወይም አስጎምጅነት እንዳላቸው ምንም አልተገለጸም። አንድ ነገር ግን ተነግሮናል፣ ያ ዝፍ የሞት ፍሬ መሆኑ። ምክንያቱም እርሱን መብላት ያለመታዘዝ ምልክት ነው። የአመጽ ምሳሌ ነው። በተመሳሳይ ለእስራኤል ንጹሁ እንስሳት ተብለው የተዘረዘሩትን በመስመር ማስቀመጥ እና ሁሉንም በሆነ መስፈረት ማኖር አይቻልም (arbitrariness አለባቸው)። ይሄ የሚነግረን ጉዳዩ ከመብልነት እጅጉን የተሻገረ እንደሆነ ነው።


እስራኤል እንቢ ማለትን፣ ለእግዚአብሔር ሲል መተውን፣ በዚህም ራስን መግዛትን እንዲማር የወጡ ሕጎች ናቸው። የሥጋ ትልቁ ፍላጎት እና ፈተና የሆነውን መብላት በመገደብ ፥ እንቢ ማለትን እና የፍቃድ ጡንቻን ማጠንከርን ለእስራኤል አስተማረው። እስራኤል እነዚህ የኛ ምግቦች አይደሉም፣ ለኛ አይሆኑም በማለት በሕይወት ራስን መገደብን እና ኃጢአት እንኳ ባይሆን ለእኛ የተፈቀደ አይደለም በማለት እንቢ ማለትን በሕይወት እንዲማሩ የተተከለ የፍቃድ (will power) ጡንቻ ማጎልበቻ ናቸው። ለእግዚአብሔር ስንል ምክንያት እንኳ ባይኖረው እንቢ ማለትን እንዲማሩ አደረጋቸው። በዚህም በሕይወት ነገሮች ስላጓጓቸው እና ስሜታቸው ስላሻው ብቻ እንዳያደርጉ ፥ ለምኞታቸው እንቢ የማለትን ጡንቻ ገና በጊዜ እንዲያዳብሩ አደረጋቸው።


የአይሁድ ቤተሰቦች በዚህ ዘመን ሳይቀር ይሄን የምግብ ባህል በጥንቃቄ ይከተላሉ። ተመልከቱ ይሄ ራስን የመግዛት፣ በዚህም የሕይወት ስኬትን የመቆናጠጥ ማንነት ከአይሁድ ዘር በላይ በዚህ ዓለም ማን ምሳሌ ሊሆን ይችላል። የኖቤል ሽልማትን ብቻ ውሰዱ። እስከዛሬ ከ965 የኖቤል ተሸላሚዎች ውስጥ፣ 214 አይሁዶች ናቸው። በአሜሪካ ውስጥ የአይሁድ ቁጥር 2.4% ነው፤ በአሜሪካ ቢዝነስም ሆነ ፖለቲካ ግን 71% ከሚሆነው የነጩ ማህበረሰብ ምንም ያልተናነሰ ተጽዕኖ የአይሁድ ማህበረሰብ ነው ያለው። በዚህ ዓለም ላይ ከቁጥሩ አንጻር የአይሁዶችን ያህል ስኬት የተጎናጸፈ አንድ ዘር መጥራት የሚችል ይኖራል? የትኛውንም የስኬት ሜትሪክሶችን አምጡ እና የአይሁድን ማህበረሰብ አስቀምጡ፤ ይሄ ማህበረሰብ ካለው ቁጥር አንጻር እጅግ አስገራሚ ስኬት የተጎናጸፈ ሆኖ ታገኙታላችሁ።

ማንንም ጠይቁ ፥ ለጊዜያዊ ፍላጎቱ እንቢ ማለት የቻለ ሰው፣ ራሱን መቆጣጠር እና መግዛት የሚችል ሰው በምንም ዘርፍ በመጨረሻ ያሸንፋል። ይሄን ነበር በምግብ እግዚአብሔር ለእስራኤል ያስተማራቸው። በዚህ ሕግ ሕይወታቸውን ሁሉ አበራላቸው። እንቢ የማለትን ማንነት አጸናላቸው።


2) ሥርዓትን ያስተምራል ፦ መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን ላይ “ዓላማ ይዞ እንደ ተሰለፈ ሠራዊት የምታስፈራ ማን ናት?” እንዳለው ጠቢቡ፤ በሕይወት ሥርዓት ያለው ትንሽ ሠራዊት ሥርዓት የሌለውን እልፎች ይረታል። ዛሬም ስለእስራኤላውን ይሄ እውነት ነው። ጎረቤቶቻቸው በቁጥር በስንት እጥፍ እየበለጧቸው፣ ራሳቸውን የለዩ፣ በሥርዓት ማንነታቸውን ያሰለጠኑ በመሆናቸው በእልፍ የሚበልጧቸው በፊታቸው ይርዳሉ። (You develop an ordered soul that says no to certain things).


3) ማንነት ነው ፦ እነዚህን ምግብ እኛ እስራኤላውያን በመሆናችን አንበላም በማለታቸው ፥ ራሳቸውን ሁሉን ከሚበላው ዓለም ለዩ። በዚህም በቁጥር በብዙ እጥፍ ከሚበልጡአቸሁ ጎረቤቶቻቸሁ ማንነታቸውን ጠብቀው ማቆየት ቻሉ።


4) የእግዚአብሔርን ንጽሕ እና ቅድስና የሚያሳይ ነው። ለምሳሌ ሴቶች በወራዊ ልማዳቸው ወቅት ወደ ቅዱሱ ስፍራ ወንዶችም ዘራቸው የፈሰሰ እንደሆነ ወደ እግዚአብሔር መቅደስ እንዳይገቡ በብሉይ ሕግ ተደንግጎ ነበር። ሴቶች ወራዊ ልማዳቸውን ማስቀረት የሚችሉት ነገር አይደለም፤ ስለዚህም ኃጢአት አይደለም። ነገር ግን ወደ ቅድስናው ስፍራ በዚህ ወቅት መቅረብ አይችሉም፤ ለምን? ይሄ የእግዚአብሔርን ቅድስና እና ንጽህና የሚናገር ነው። “እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ነኝና፤ ሰውነታችሁን ቀድሱ፥ ቅዱሳንም ሁኑ፥ እኔ ቅዱስ ነኝና፤ በምድርም ላይ በሚሳብ ተንቀሳቃሽ ሁሉ ሰውነታችሁን አታርክሱ።” ዘሌዋውያን 11፥44። ኃጢአትን አለመስራት አንድን ሰው ቅዱስ አያደርገውም። ቅድስና የዓላማ ተግባር ነው (affirmative action)። ቅድስና መተግበርን ይሻል፣ መራቅን ብቻ አይደለም። አንድ ሰው ኃጢአት መሥራት እየቻለ፣ ስለእግዚአብሔር ብቻ ሲል ከተወ ያ ቅድስና ነው። ምክንያቱም የዓላማ ተግባር ነውና። ቤቱ ውስጥ ምግብ የሞላለት እና ምንም ያልጎደለበት ሰው ላይሰርቅ ይችላል። አለመስረቁ ቅዱስ አያደርገውም። ከመጸወተ ግን ያ ቅድስና ነው። ሰይጣን ስለኢዮብ ያለው ይሄን ነበር። “እርሱ ስለሞላለት፣ ምንም ስላልጎደለበት፣ ዙሪያውንም ከክፍ ስላጠርክለት እንጂ ምንም ጽድቅ የለውም” ነበር ያለው። ሰይጣን ሳይቀር ከኃጢአት መራቅ በራሱ የጽድቅ ምልክት እንዳልሆነ ያውቃል ማለት ነው። እነዚህ ምግቦች ለእግዚአብሔር ሲባል ብቻ መተውን፣ በዚህም መቀደስን የሚያስተምሩ ምልክቶች ናቸው።

በአዲስ ኪዳን እነዚህ ምግቦች ያላቸው ቦታ ግልጽ ነው። በቤተክርስቲያናችንም እንዴት እንደሚታዩ ብጹዑ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የቤተክርስቲያን ታሪክን በጻፉበት መጽሐፋቸው ዳሰውታል።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page