top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jan 19, 2025
  • 1 min read



ጎርጎሪዮስ ዘኑሲስ ነው ይሄ ሩጫ የፍጽምና ሩጫ ነው ያለው። መጨረሻው የሌላ ነገር መጀመሪያ እንጂ በርግጥም መጨረሻ አይደለም ያለው። በዚህ ሕይወት እስካለን ድረስ እያንዳንዱ ግብ ፥ የሌላ ሕይወት መጀመሪያ ነው። እያንዳንዱ መጨረሻ ፥ የሌላ ሕይወት መነሻ ነው።

 

ቻርልስ ቢኮወስኪ “ይሄ ሕይወት፦ ያሁኑ፤ ያለፈው ሁሉ ያንተ ነው” ሲል ፥ በዚህ ሕይወት ለውድቀትህም ሆነ ለድልህ ከአንተ በላይ ተጠያቂ የለም እያለህ ነው። ያንተ እና ያንተ ብቻ ነው። ያነሰ ኃላፊነት አትውሰድ። ለዚህ ነው በዚህ ሕይወት በሌሎች ፍልስፍና፣ በሌሎች አረዳድ እና በሌሎች የመገንዘብ ችሎታ የራስን ሕይወት መምራት ሕይወትን ማባከን ነው። ሰው ምን ይለኛል ብለህ ይሄን አንድ ሕይወት፣ ይሄን ያንተ የሆነውን ስጦታ ሕይወት ለማህበረሰብ አትስጥ። “ለምን ይሉኛል” ባርነት አትንበርከክ። በዚህ ዓለም  የመኖሪያ ማብቂያ ሰዓት ላይ እንዴት ያለ ጅል እንደነበርክ የሚገባህ ፥ ስለራሱ እንጂ ስለአንተ ግድ ስለማይሰጠው ዓለም ስትጨነቅ ህልምህን አለመኖርህ ሲገለጥልህ ነው።

 

ቆም ብለህ አስብ። የትኛው ኢንዶክትርኔሽን ነው ጨፍልቆህ ያለው? ደስተኛ ያልሆነ ሕይወት እና ኑሮ ውስጥ የነከረ? ለምን? ምንአልባት ያለህበትን ሁኔታ መቀየር አትችል ይሆናል። በርግጠኝነት ግን ላለህበት ሁኔታ ባሪያ አለመሆን ትችላለህ። በሚዲያ፣ በማጉያ፣ በቲዎሎጂ፣ በፖለቲካ፣ በቡና ወሬ አንተን የስብስባቸው ቁጥር፣ የእነርሱ ህልውና ማስረጃ፣ የእንጀራቸው ማብሰያ ከሚያደርጉህ ተላቀ፤ በማፈር እና በፍርሃት የሸመቀቃትን ነፍስ ነጻ ስታወጣት ብቻ ፥ የፍልስፍናቸው ኦናነት ይገለጥልሃል። ለራስህ እውነተኛ ስትሆን ፥ ብዙዎችን ትማርካለህ። ከዘመንህም መሻገር ትችላለህ።

 

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jan 12, 2025
  • 3 min read



“ስለ ምን ኃጢአተኞች በሕይወት ይኖራሉ? ስለ ምንስ ያረጃሉ? በባለጠግነትስ ስለ ምን ይበረታሉ?


ዘራቸው ከእነርሱ ጋር ጸንቶ ይኖራል፥ ልጆቻቸውም በዓይናቸው ፊት ናቸው።


ቤታቸው ከፍርሃት ወጥቶ የታመነ ነው፥ የእግዚአብሔርም በትር የለባቸውም።”

መጽሐፈ ኢዮብ 21፥7



ይሄ የኢዮብ ቃል። ኢዮብ ለዚህ ምክንያት እና መልስ አልተሰጠውም። አንድ ነገር ግን ተደረገለት። ተፈጥሮን እንዲያይ ተደረገ። እግዚአብሔር ለኢዮብ የነገረው ነገር ፥ ስለፍጥረቱ ነው። ፍትህ እና የሰጥቶ መቀበል ሕግ የዚህ ሥርዓት ምሰሶ አልነበረም። አይደለምም።



ብዙ ሰዎች በየቀኑ የሚሉት ነው።


ለምን እኔ?


ይሄ ፌር አይደለም (This is not fair)?


ለምን ይሄ ሁሉ ስቃይ በእኔ ላይ?


ሌሎች በዚህ መጠን አልተሰቃዩም ወይም ወዳጆቼ ሲደሰቱ ለምን ይሄ በእኔ ላይ ደረሰ?


ዙሪያችን ያሉትን በማየት እና የሌሎችን ሕይወት አጮልቀን በመመልከት ፥ ይሄን ሕይወት እናማራለን። ሃይማኖተኛ ካልሆንን ደግሞ እንደ Luigi Mangione የካፒታሊዝም መሪዎችን በአደባባይ በሽጉጥ እንዘርራለን። የዚህ ሁሉ ምክንያቱ ሕይወት እንደ እኛ የፍትሕ መስፈርት ስለማትሰራ ነው። በየቀኑ የማያማርን ሰው አለመስማት በጣም ከባድ ነው። ከዛ ለዚህ ምራሬ የሃይማኖት ደጅ መጥናት፤ የጸናበት ደግሞ ይሄን የሚረሳበት ማደንዘዣ መውሰድ የተለመደ ነው።



ግን አንድ መራራ ሀቅ አለ። እርሱም ይሄ ሕይወት ፈጽሞ ፍትሐዊ መሆን እንደማይችል ማወቅ ነው። በተገነባ፣ በተሰራ እና በሚንቀሳቀስ ዓለም ላይ ነው የተፈጠርነው። ብዕራችንን አንስተን ከምንም ዲዛይን ሰርተን የምንገነባው ዓለም ላይ አይደለም ያለነው። በሃይማኖት ለምናምን ይሄ ዓለም ድንቅ በሆነ ሠሪ ከብዙ ሺ ዓመት በፊት የተገነባ ነው። በሃይማኖት ለማናምን ይሄ ዓለም ከብዙ ሚሊዮን ዓመታት በፊት በዝግመታዊ ለውጥ ሂደት አሁን ያለንበት ደረጃ የደረሰ ነው። በሁለቱም ብንሄድ የኛ ድርሻ ኢምንት ነው። በኛ አቅም ወይም በአንድ ትውልድ ዘመን የሚፈርስ ሆነ የሚገነባ ምንም ነገር የለም። የሚለወጥም መሠረታዊ አሰራር አይኖርም።



ማንንም የማታውቁበት ሰዎች ወደ ተሰበሰቡበት ታላቅ ድግስ ተጠራችሁ እንበል። ስለ ድግሱ ዓላማማ ሆነ የመርሐ-ግብር ይዘት እምብዛም እውቀት የላችሁም። መቅረት አትችሉም። ስለዚህ በዚህ ድግስ መኃል ራሳችሁን ብታገኙ ምንድነው የምታደርጉት? አቅማችሁ በፈቀደ መጠን ስለድግሱ ለማወቅ ነው የምትጥሩት። በድግሱ ስላሉት ሰዎች፣ ስለመርሐግቡር ይዘት፣ ስለምግቡ እና ስለእናንተ ቦታ፣ ምን ማድረግ እንዳለባችሁ እና በዛ ድግስ ውስጥ ስለሚኖራችሁ ዕድል ነው አብዝታችሁ የምትጨነቁት።



ሕይወትም እንደዛ ናት። ራሳችንን በዚህ የሕይወት ድግስ መኃል አግኝተነዋል። ድግሱ እንዲህ መሆን አለበት ማለት ሳይሆን ይሄ ድግስ እንዴት ነው የሚሰራው የሚለው ነው ታላቁ ጥያቄ።



ፍልስፍና ይዘን፣ ሕይወት እንዲህ እና እንዲያ መሆን አለበት በማለት ወደዚህ ሕይወት ወደ ተባለ ውቅያኖስ መግባት ብዙም አዋጪ አይደለም። ይሄ የማርክሲስት ውድቀት ነው። ሕይወትን ፍትሐዊ እናደርጋለን ብለው ሁሉን ድሃ አደረጉት። ካፒታሊዝም ከገደለው እና ካሰቃየው በላይ ብዙ ገደሉ አሰቃዩ። ስለ ፍትሕ እጨነቃለሁ የሚለውም Luigi Mangione ሦስት ልጆችን ያለ አባት አስቀረ። ሶሻሊዝምን ድጋሚ እና ድጋሚ ብትሞክሩትም ፥ ፍትሕ እኛ በምንለው መልኩ ሊመጣ አይችልም።


ከክርስቶስ ልደት አራት መቶ አመት በፊት የነበረው ዲሞስትኒስ “ሰው የሚመኘውን ነገር ያምነዋል” ይላል። በሌላ አነጋገር እውነት እንዲሆን ስለምንፈልግ ፥ እውነት ነው ብለን እናምናለን።



ማን ነው በዚህ እንቅፋት ያልተመታ? ማማረር ማለት ይሄ ነው። ምኞታችን እውነት ሳይሆን ሲቀር ፥ የሚመጣ ንጭንጭ ነው።



በየቀኑ የምሰማው ይሄ ፌር (fair) አይደለም የሚል ማማረርን ነው። ግን ማነው ፌር (fari) ይሆናል ብሎ ቃል የገባልን? ማነው ፍትሐዊ ሕይወት እንደምናገኝ ቃል የሰጠን? ማንም ዋስትና የሰጠን የለም። በሆነ በሚሰራ እና የራሱ አሰራር ባለው ዓለም ውስጥ ተወርውረናል። ስለዚህ ያን ተቀብሎ እና እንዴት እንደሚሰራ አጥንቶ መጓዝ እንጂ ዓለም ያልሆነውን እንዲሆን መመኘት ቅዠት ነው።


እንደ ፍቺ የሕግ ጠበቃ ፥ የትዳር መፍረስ መሠረቱ ይሄ ነው። ሲጋቡ አንዱ አንዱን ለመቀየር ይጋባሉ። ሁለቱም ግን በልባቸው ሌላኛው ሰው እንደ ሆኑት እንዲቀበሏቸው ነው የሚመኙት። ሁሉም ጋብቻ በሚባል መልኩ የሚፈርሱት ጋብቻው ሲመሰረት በነበረ ባህሪ ነው። ሁለቱም ያን ባህሪ ገና ወደ ጋብቻ ውስጥ ሲገቡ ያውቁታል። ግን እለውጠዋለሁ ብለው አመኑ።



በተመሳሳይ ከዚህ ሕይወት ጋር ያለን ትግል ይሄ ነው። መሬት ላይ የተቀበረ ድንጋይ እንቅፋት ቢመታን ፥ ሕጻን ካልሆንን በቀር እንቅፋት ከመታን ድንጋይ ጋር ድብድብ አንገጥምም። ይልቁንስ ድንጋዩን ባለማየታችን ራሳችንን እንወቅሳለን። በዚህ ሕይወት ከጠበቅነው ውጪ ስናገኝ ፥ ያላየነው እና ያልተረዳነው ነገር እንዳለ ነው ማወቅ ያለብን እንጂ የምናማር ከሆነ ከድንጋዩ ጋር እየተደባደብን መሆኑን ማወቅ አለብን።



ራሳችሁን ይሄን ጠይቁ። ይሄን ነገር የማምነው ምኞቴ ያ ስለሆነ ነው ወይስ በርግጥም እውነት እንደዛ ስለሆነ ነው? እንደዚህ እየሰራው እና እየሆንኩኝ ያለሁት ምኞቴ ስለሆነ ነው ወይስ እውነቱ እንደዛ ስለሆነ ነው? የማታውቁ ከሆነ አላውቅም በሉ። እዛ አቁሙ። ይሄ ሁሉ ፍልስፍና እና እምነት እንደ እንጉዳይ ዓለምን የሞላው ዓለም አላውቅም ማለት ፈርቶ እና አፍሮ ነው። ስለዚህ እውቀት አልባነትን ከምኞት በሚመጣ ፍልስፍና ሞላው። የትንትኔ እና የዲስኩር መዓት የከደነን ፥ አላውቅም የሚሉ ሰዎች ስለሌሉን ነው።



ዓለም ግን እርሷን ለማወቅ የሚጥርን እና ከማማረር ይልቅ ነገሮች እንዴት እንደሚሰሩ አውቆ ራሱን ከዛ ጋር ለማስማማት የሚጥርን ሁልጊዜ ትሸልማለች። ቢያንስ የሚያማርበት ጊዜ አይኖረውም።


 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jan 5, 2025
  • 3 min read





ጥንታውያን የቼዝ ጨዋታን እንደ ጦር ስትራቴጂ እና የሕይወት ትምህርት ለመቅሰም ይጠቀሙበት ነበር። በቼዝ ጨዋታ የሁለቱም ተጫዎቾች ዓላማ ንጉሱን መጠበቅ ነው። (በአንዳንድ ሀገሮች ንግስቲቱን ሚኒስትር ንጉሱን ደግሞ ንግስቲቱ ብለው ይጠራሉ)። ወታደሮች፣ ፈረሶች፣ ቢሾፖች፣ ዘቦች እና ንግስቲቱ ዓላማቸው የራሳቸውን ንጉስ ጠብቀው የሌላኛውን ንጉስ መፈናፈኛ ማሳጣት ነው። ከዚህ ውጪ ሌላ ተልዕኮ የላቸውም። የራስን ንጉስ ከጥቃት መጠበቅ፤ የሌላኛውን ንጉስ በማጥቃት መሄጃ ማሳጣት።


ከዚህ ውጪ ያለው ሁሉ የጌሙ (የጫወታው) ውበት እንጂ ዓላማ አይደለም። በዚህ ጫወታ ውስጥ ሁሉንም ነገር አጥተህ ንጉስህን አስጠብቀህ ማሸነፍ ከቻልክ ድል ነው። ወታደሮች፣ ፈረሶችህ፣ ካህናትህ ሳይነኩብህ ንጉስህ ጥቃት ደርሶበት ልትሸነፍ ትችላለህ። ከሩቅ ለሚያየው ሁሉ ነገር ስላለህ የተሸነፈክ ላይመስል ይችላል። ከቅርብ ለሚያየው እና የጌሙን ሕግ ለሚረዳ ግን የንጉስህን ሁኔታ ተመልክቶ እንዳለቀልህ ሊገባው ይችላል። ስለዚህ ብዙ ፍሬዎች (pieces) አሉ ወይም የሉህም አይደለም ቁምነገሩ፤ ዋናው ነገር “ንጉስህ እንዴት ነው?” ነው



ልክ እንደቼዝ የትኛውም ሕይወት አንድ ንጉስ ነው ያለው። ሕይወታችን በጫወታው የሕግ ብዛት፣ በውስብስብ ማህበረሰባዊ ጥልፍልፍ መዋቅሮች እና መጠብቆች (expectations) ንጉሱ ካልተሰወረበት በቀር ንጉሱ አንድ ነው። የሰው ልጅ የዚህ ምድር ግብ ደስተኛ መሆን ነው። በግለሰብም ሆነ በቡድን የምናደርጋቸው ትግሎች መሠረታዊው ምሰሶ ደስታ ነው። ልክ እንደ ቼዝ የማሸነፊያ መንገዶች ሺ ዓይነት እንደሆኑ ሁሉ፣ በሕይወትም ሰዎች ደስተኛ የሚሆኑበት እሱም በዘላቂነት ደስተኛ የሚሆኑበት መንገድ ለየቅል ነው።



ለምሳሌ በጎግል በአንደኛ ደረጃ በዓለም ዙሪያ የተጠየቀ ጥያቄ “ምን ልመልከት?” (what to watch) የሚል ነው። ይሄ ሰዎች ራሳቸውን ለማዝናናት (ደስተኛ ለመሆን) የሚያነሱት ጥያቄ ነው። ሲ ኤስ ሉዊስ ሕመም ትልቁ “የእውነት ገላጭ መሳሪያ ነው” “Pain exposes reality” ይላል። ሰው ሲታመም ከምንም ነገር በላይ ምን ወሳኝ እንደሆነ ይገባዋል። በዛ የሕመም ወቅት የሕይወት ጥያቄ ሁሉ ተሰብስቦ አንድ ብቻ ይሆናል። እሱም ከዛ ሕመም ለጥቂት ጊዜ እንኳ ረፍት ማግኘት።


ይሄ ማለት ግን ምቾት እና ድሎት ነው ሰውን ደስተኛ የሚያደርገው ማለት ላይሆን ይችላል። ሰዎች ትርጉም የምንፈልግ ፍጥረት ነን። ይሄ ማለት ሌሎች እንስሳት ትርጉም አይፈልጉም ማለት ላይሆን ይችላል። እኛ በብዙ መንገድ በዓይናችን ከምናያቸው ፍጥረታት በላይ ውስብስብ ነን። ከዛ በተጨማሪም ነገሮችን የምንረዳበት መንገድም ደስተኛ በመሆን ላይ የራሱ ገጽታ አለው። በተለይ ሕይወትን በንጽጽር ብቻ መገንዘብ መቻላችን፤ ምቾትን፣ ጤናን፣ ረፍትን፣ እፎይታን ያለ ድካም፣ ሕመም እና ተግዳሮት ማጣጣም እንዳንችል አድርጎናል።



ቅዱስ ቶማስ አኩዋይነስ እንዳለው “ልክ ጸጥታ የዝማሬያችን ውበት እንደሆነው ፥ መከራ ነው፣ ስቃይ ነው፣ ክፋት ነው የበጎ ነገርን እውቀት የሰጠን።” ያለ ክፋት በጎነት ለሰው ልጆች አዕምሮ ግልጽ አይደለም። ያለ ሕመም ጤናን የሚረዳው አይኖርም ነበር። ደስተኛ ለመሆን ከደስታ ተቃራኒ የሆኑ የሕይወት ክፍሎች የግድ ያስፈልጉናል። ረፍትን ያለ ድካም ማጣጣም አይቻልም። የጤና ትርጉም ከሕመም ነው የሚመነጨው።


ይሄን የምዘረዝረው “የሰው ልጅ ንጉስ የሆነው ደስታ እንዲው በቀላሉ የሚጠበቅ አይደለም” የሚለውን ለማሳየት ነው። እሱ ብቻ ሳይሆን ለመከራ እና ስቃይ ያልተጋለጠ ሕይወት ደስታን ማግኘት አይቻለውም። በምቾት ውስጥ ካለ ሰው ይልቅ ከመከራ ወደ ምቾት የመጣ ሰው በሕይወት የበለጠ ደስተኛ ነው። ለዚህም ይመስላል እንደ ፊንላንድ ያሉ በHappiness Index እንዴክስ እና በምቾት ከፍተኛ ደረጃ ያስመዘገቡ ሀገሮች በተመሳሳይ ራስን በማጥፋትም (suicide rate) ከፍተኛ ቁጥር ያስመዘገቡት።



በቼዝ ውስጥ ከሁሉም በላይ ደካማው ንጉሱ ነው። ግን ደግሞ ንጉስ ነው። ከሁሉም በላይ ራሱን መጠበቅ የማይችለው ንጉሱ ነው። ከሁሉም በላይ ቀርፋፋው ንጉሱ ነው። በኛ ሕይወትም በሁሉም አቅጣጫ በቀላሉ ሊጠቃ የሚችለው ደስታችን ነው። መቼም ርግጠኛ የማንሆንበት ነገርም ደስታችን ነው። ከደቂቃዎች በፊት እየሳቀ የነበረ ሰው ሊያለቅስ ይችላል። ይሄን ከመፍራት የምስራቁ ዓለም ደስታን መግለጥ ላይ ገደብ ያኖራል። የምስራቁ ዓለም ማህበረሰባዊ ስለሆነ (በንጽጽር ለማስቀመጥ እንጂ ሁሉም ማህበረሰባዊ ነው)፤ ደስታው በቀላሉ ሊታጠፍ እንደሚችል ስለሚገባው የሚያስፈነድቀው ነገር ሲኖር ራሱ ያን በገደብ ነው የሚገልጸው። በዚህም በኋላ ከሚመጣ ማህበረሰባዊ ሀሜት ራሱን ይጠብቃል።



በቼዝ ሁሉም ፍሬዎች (pieces) እያሉህ፤ ንጉስህ ቼክ ተብሎ ከጫወታ ልትወጣ ትችላለህ። በተመሳሳይ በሕይወት ሁሉም ነገር እያላቸው ግን ፍጹም የሆነ ስቃይ ውስጥ የሚኖሩ አሉ። በተቃራኒው አብዛኛውን ፍሬዎች (pieces) አጥተው የቼዝን ጫወታ የሚያሸንፉ አሉ። ልክ እንደ ቼዙ ብዙ የቁስ ክምችት ያላፈናቸው ሰዎች ግን አስገራሚ ደስታ እና ርካታ ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች አሉ። እነዚህ የሕይወት ስትራቴጂስቶች ናቸው። በሕይወት ውስጥ ንጉሳቸውን እንዴት አድርገው መጠበቅ እንዳለባቸው የተረዱ እና ለራሳቸው የሚስማማ እና ራሳቸውን የሚመስል የጌም ፕላን አውጥተው የሚጫወቱ ሰዎች ናቸው። እስቲ ሪፍሌክት አድርጉ። እያደረጋችሁት ያለው ነገር በረዥም ጊዜ ውስጥ ደስተኛ ሕይወትን እንድትመሩ የሚያደርጋችሁ ነው? ወይስ ምንን በዚህ ሕይወት መጠበቅ እንዳለብን አስበንበት አናውቅም።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page