top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jan 5
  • 3 min read


ree



ጥንታውያን የቼዝ ጨዋታን እንደ ጦር ስትራቴጂ እና የሕይወት ትምህርት ለመቅሰም ይጠቀሙበት ነበር። በቼዝ ጨዋታ የሁለቱም ተጫዎቾች ዓላማ ንጉሱን መጠበቅ ነው። (በአንዳንድ ሀገሮች ንግስቲቱን ሚኒስትር ንጉሱን ደግሞ ንግስቲቱ ብለው ይጠራሉ)። ወታደሮች፣ ፈረሶች፣ ቢሾፖች፣ ዘቦች እና ንግስቲቱ ዓላማቸው የራሳቸውን ንጉስ ጠብቀው የሌላኛውን ንጉስ መፈናፈኛ ማሳጣት ነው። ከዚህ ውጪ ሌላ ተልዕኮ የላቸውም። የራስን ንጉስ ከጥቃት መጠበቅ፤ የሌላኛውን ንጉስ በማጥቃት መሄጃ ማሳጣት።


ከዚህ ውጪ ያለው ሁሉ የጌሙ (የጫወታው) ውበት እንጂ ዓላማ አይደለም። በዚህ ጫወታ ውስጥ ሁሉንም ነገር አጥተህ ንጉስህን አስጠብቀህ ማሸነፍ ከቻልክ ድል ነው። ወታደሮች፣ ፈረሶችህ፣ ካህናትህ ሳይነኩብህ ንጉስህ ጥቃት ደርሶበት ልትሸነፍ ትችላለህ። ከሩቅ ለሚያየው ሁሉ ነገር ስላለህ የተሸነፈክ ላይመስል ይችላል። ከቅርብ ለሚያየው እና የጌሙን ሕግ ለሚረዳ ግን የንጉስህን ሁኔታ ተመልክቶ እንዳለቀልህ ሊገባው ይችላል። ስለዚህ ብዙ ፍሬዎች (pieces) አሉ ወይም የሉህም አይደለም ቁምነገሩ፤ ዋናው ነገር “ንጉስህ እንዴት ነው?” ነው



ልክ እንደቼዝ የትኛውም ሕይወት አንድ ንጉስ ነው ያለው። ሕይወታችን በጫወታው የሕግ ብዛት፣ በውስብስብ ማህበረሰባዊ ጥልፍልፍ መዋቅሮች እና መጠብቆች (expectations) ንጉሱ ካልተሰወረበት በቀር ንጉሱ አንድ ነው። የሰው ልጅ የዚህ ምድር ግብ ደስተኛ መሆን ነው። በግለሰብም ሆነ በቡድን የምናደርጋቸው ትግሎች መሠረታዊው ምሰሶ ደስታ ነው። ልክ እንደ ቼዝ የማሸነፊያ መንገዶች ሺ ዓይነት እንደሆኑ ሁሉ፣ በሕይወትም ሰዎች ደስተኛ የሚሆኑበት እሱም በዘላቂነት ደስተኛ የሚሆኑበት መንገድ ለየቅል ነው።



ለምሳሌ በጎግል በአንደኛ ደረጃ በዓለም ዙሪያ የተጠየቀ ጥያቄ “ምን ልመልከት?” (what to watch) የሚል ነው። ይሄ ሰዎች ራሳቸውን ለማዝናናት (ደስተኛ ለመሆን) የሚያነሱት ጥያቄ ነው። ሲ ኤስ ሉዊስ ሕመም ትልቁ “የእውነት ገላጭ መሳሪያ ነው” “Pain exposes reality” ይላል። ሰው ሲታመም ከምንም ነገር በላይ ምን ወሳኝ እንደሆነ ይገባዋል። በዛ የሕመም ወቅት የሕይወት ጥያቄ ሁሉ ተሰብስቦ አንድ ብቻ ይሆናል። እሱም ከዛ ሕመም ለጥቂት ጊዜ እንኳ ረፍት ማግኘት።


ይሄ ማለት ግን ምቾት እና ድሎት ነው ሰውን ደስተኛ የሚያደርገው ማለት ላይሆን ይችላል። ሰዎች ትርጉም የምንፈልግ ፍጥረት ነን። ይሄ ማለት ሌሎች እንስሳት ትርጉም አይፈልጉም ማለት ላይሆን ይችላል። እኛ በብዙ መንገድ በዓይናችን ከምናያቸው ፍጥረታት በላይ ውስብስብ ነን። ከዛ በተጨማሪም ነገሮችን የምንረዳበት መንገድም ደስተኛ በመሆን ላይ የራሱ ገጽታ አለው። በተለይ ሕይወትን በንጽጽር ብቻ መገንዘብ መቻላችን፤ ምቾትን፣ ጤናን፣ ረፍትን፣ እፎይታን ያለ ድካም፣ ሕመም እና ተግዳሮት ማጣጣም እንዳንችል አድርጎናል።



ቅዱስ ቶማስ አኩዋይነስ እንዳለው “ልክ ጸጥታ የዝማሬያችን ውበት እንደሆነው ፥ መከራ ነው፣ ስቃይ ነው፣ ክፋት ነው የበጎ ነገርን እውቀት የሰጠን።” ያለ ክፋት በጎነት ለሰው ልጆች አዕምሮ ግልጽ አይደለም። ያለ ሕመም ጤናን የሚረዳው አይኖርም ነበር። ደስተኛ ለመሆን ከደስታ ተቃራኒ የሆኑ የሕይወት ክፍሎች የግድ ያስፈልጉናል። ረፍትን ያለ ድካም ማጣጣም አይቻልም። የጤና ትርጉም ከሕመም ነው የሚመነጨው።


ይሄን የምዘረዝረው “የሰው ልጅ ንጉስ የሆነው ደስታ እንዲው በቀላሉ የሚጠበቅ አይደለም” የሚለውን ለማሳየት ነው። እሱ ብቻ ሳይሆን ለመከራ እና ስቃይ ያልተጋለጠ ሕይወት ደስታን ማግኘት አይቻለውም። በምቾት ውስጥ ካለ ሰው ይልቅ ከመከራ ወደ ምቾት የመጣ ሰው በሕይወት የበለጠ ደስተኛ ነው። ለዚህም ይመስላል እንደ ፊንላንድ ያሉ በHappiness Index እንዴክስ እና በምቾት ከፍተኛ ደረጃ ያስመዘገቡ ሀገሮች በተመሳሳይ ራስን በማጥፋትም (suicide rate) ከፍተኛ ቁጥር ያስመዘገቡት።



በቼዝ ውስጥ ከሁሉም በላይ ደካማው ንጉሱ ነው። ግን ደግሞ ንጉስ ነው። ከሁሉም በላይ ራሱን መጠበቅ የማይችለው ንጉሱ ነው። ከሁሉም በላይ ቀርፋፋው ንጉሱ ነው። በኛ ሕይወትም በሁሉም አቅጣጫ በቀላሉ ሊጠቃ የሚችለው ደስታችን ነው። መቼም ርግጠኛ የማንሆንበት ነገርም ደስታችን ነው። ከደቂቃዎች በፊት እየሳቀ የነበረ ሰው ሊያለቅስ ይችላል። ይሄን ከመፍራት የምስራቁ ዓለም ደስታን መግለጥ ላይ ገደብ ያኖራል። የምስራቁ ዓለም ማህበረሰባዊ ስለሆነ (በንጽጽር ለማስቀመጥ እንጂ ሁሉም ማህበረሰባዊ ነው)፤ ደስታው በቀላሉ ሊታጠፍ እንደሚችል ስለሚገባው የሚያስፈነድቀው ነገር ሲኖር ራሱ ያን በገደብ ነው የሚገልጸው። በዚህም በኋላ ከሚመጣ ማህበረሰባዊ ሀሜት ራሱን ይጠብቃል።



በቼዝ ሁሉም ፍሬዎች (pieces) እያሉህ፤ ንጉስህ ቼክ ተብሎ ከጫወታ ልትወጣ ትችላለህ። በተመሳሳይ በሕይወት ሁሉም ነገር እያላቸው ግን ፍጹም የሆነ ስቃይ ውስጥ የሚኖሩ አሉ። በተቃራኒው አብዛኛውን ፍሬዎች (pieces) አጥተው የቼዝን ጫወታ የሚያሸንፉ አሉ። ልክ እንደ ቼዙ ብዙ የቁስ ክምችት ያላፈናቸው ሰዎች ግን አስገራሚ ደስታ እና ርካታ ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች አሉ። እነዚህ የሕይወት ስትራቴጂስቶች ናቸው። በሕይወት ውስጥ ንጉሳቸውን እንዴት አድርገው መጠበቅ እንዳለባቸው የተረዱ እና ለራሳቸው የሚስማማ እና ራሳቸውን የሚመስል የጌም ፕላን አውጥተው የሚጫወቱ ሰዎች ናቸው። እስቲ ሪፍሌክት አድርጉ። እያደረጋችሁት ያለው ነገር በረዥም ጊዜ ውስጥ ደስተኛ ሕይወትን እንድትመሩ የሚያደርጋችሁ ነው? ወይስ ምንን በዚህ ሕይወት መጠበቅ እንዳለብን አስበንበት አናውቅም።

 
 
 

ree


1.  ለራሳችሁ ሥራ አስኪያጅ ተደርጋችሁ ብትሾሙ ምንድነው የምታደርጉት?



ራስሽን እንደ አንድ ለትርፍ እንደተቋቋመ ድርጅት ተመልከቺ። ስምሽ ምህረት ነው እንበል። ምህረት ለምትባት ትርፍ ማምጣት ግዴታዋ ለሆነ ድርጅት፤ የድርጅቱ ቦርድ ሥራ አስኪያጅ አድርጎ ሾመሽ። አሁን ሥራሽ የሚሆነው በመስሪያ ቤቱ ውስጥ የማይሰራን ነገር ማሶገድ ፥ ትርፍ ሊያመጡ የሚችሉ ነገሮችን ማብዛት ነው። መስሪያ ቤት ስለሚሆን ስሜት የለውም። ትርፍ እና ኪሳራን መለካት በጣም ቀላል ነው። ስለዚህ ውሳኔዎችሽ በሜትሪክስ የተለኩ ናቸው። በእኔ አስተዳደር ይሄን መስሪያ ቤት ትርፍ በትርፍ አደርገዋለሁ ብለሽ ተነሳሽ። ግን ደግሞ የረጅም ጊዜ ትርፍ እንጂ የምትፈልጊው ለጊዜው ብቻ ትርፍ አግኝተሽ የአንድ ዓመት ድርጅት ማድረግ አትፈልጊም። ስለዚህ ጠንካራ ሠራተኞችሽን ትንከባከቢያለሽ። ደካማ ሠራተኞሽን በቶሎ ትቀንሺያለሽ። እስቲ ራስሽን እንደዛ ብታስቢ ምንድነው ፈጥነሽ የምታሶግጂው? ምንድነው በብዛት የምታደርጊው? የቱ ነገሮች ናቸው ለረዥም ጊዜ ስኬትሽ ዋጋ ያላቸው?




2. ትኩረትን መጨመር



ልህቀት ማሶገድን ይፈልጋል።



ብዙ ሰዎች በሕይወት ውስጥ የማይገቡበት የቢዝነስ እና የፕሮፌሽን መዓት የለም። ራሳቸውን በሁሉም ዘርፍ መለጠጥ ይወዳሉ። ሁሉም ነገር ትኩረት የሚፈልግ ሲሆን ምንም ነገር ትኩረት አያገኝም። ስኬታችን እሺ ከምንለው ነገሮች በላይ እንቢ በምንላቸው ጉዳዮች የተወሰነ ነው። አስር ነገሮችን ዘርዝሩ። በጣም ለእናንተ ወሳኝ የሆኑ ጉዳዮች። ከዛ ውስጥ ሦስቱ ላይ ብቻ አተኩሩ። ሦስቱ ነገሮችን ብቻ ከዛ ውስጥ ለማተኮር ሞክሩ።



3. መዘውሩን አታቁሙት



ማስተላለፍ ሕልምን በጸጥታ የሚገድል ነው።



የምናስተላልፈው ሁሉንም ደረጃዎች አሁኑኑ መውጣት አለብን ብለን ስለምናስብ ነው። ሥራችንን ሁሉ በደረጃ እንክፈለው። አንድ ደረጃ ከዛ ደግሞ ሌላኛውን ደረጃ ለመውጣት እናስብ። ማራቶኑን ሥራ በአንድ እና በሁለት ኪሎ ሜትሮች ከፋፍሉት። ስኬት የሚጀምሩ ሰዎችን ነው የሚሸልመው የሚጠብቁ ሰዎች ሳይሆን።



4. የማንነት ሰርክል



አንተ በዙሪያ የከበቡህ ሰዎች አቭሬጅ ነህ። እኔ ሰዎችን የምለካው ከሚውሉበት አካባቢ በመነሳት ነው። እኛ ማለት ጊዜያችንን የምናሳልፍበት ነን። አካባቢህ ወደፊት መሆን የማትፈልገው ሰዎች ጥርቅም ካልሆነ በፍጥነት ያን ቦታ ለመልቀቅ ሞክር።



ጊዜዬን የምሰጣቸው ሰዎች እጅግ የማክብራቸው ወይም ሊታገዙ የሚችሉ ሰዎች ብቻ ናቸው። ጊዜዬን እንደማቃጠል የሚቆጨኝ ነገር የለም። አዕምሮዬን እና መንፈሴን የማያንጹ ቦታዎች እና ሰዎች ከእኔ ሕይወት ውስጥ በፍጥነት እንዲወጡ ነው የምፈልገው። በዚህ የሚመጣብኝን የወቀሳ ድንጋይ እንደ ሰማዕቱ እስጢፋኖስ በደስታ ነው የምቀበለው።



አስተውሉ፦ ምንም ጥቅም የሌላቸውን ወዳጅነቶች ማሶገድ የዕድገት ሀ ሁ ነው።


5.  አታካብድ



ስኬታማ ሰዎች ነገሮችን ማቅለል የሚወዱ ናቸው። በርግጥ አንዳንድ ነገሮች መቅለል ከሚገባው በላይ አይቀሉም። ራሳችሁን ይሄን ጠይቁ፦ ሕይወትን በማክበድ ነው ወይስ በማቅለል ነው እየኖርኩት ያለውት? ለምሳሌ ሰው ምክር ሳይጠይቀን መምከር ሕይወትን በማክበድ መኖር ማለት ነው። ለዚህ ሰውዬ እኛ ጥቅም ነው ያልነውን ነገር እየጋትነው ነው! በተመሳሳይ በጣም ደክሞን ከባድ ውሳኔዎችን መወሰን ወይም ጠንካራ ውይይቶችን ከፍቅር አጋራችን ወይም ከወዳጆቻችን ጋር ማድረግ ሕይወትን በከባድ ሁኔታ መኖር ማለት ነው። በየቀኑ ቢያንስ ለሰላሳ ደቂቃ ስፖርት መስራት ቀላል ሕይወትን ለረዥም ዘመን ለመኖር መወሰን ነው። አምሽቶ መተኛት የነገውን ቀን መጥፎ በማድረግ ሕይወትን በነጋታው አክብዶ ለመኖር እንደመወሰን ነው።



እስቲ አንድ ነገር ዛሬ ብትቀይሩ ነገን የተሻለ ሊያደርግ የሚችለው ምንድነው?



6. የተግባር ዕቅድ



የጊዜ ገደብ የሌለው ዕቅድ ተራ ሕልም ነው።



ማስፈጸም የማይችል ሰው ሕልመኛ ነው። መፈጸም የሚችሉ ሁሉ የቻሉት ለተግባራቸው የጊዜ ገደብ ስላበጁለት ነው።



7. ማወቅ የምፈልገው የምሞትበትን ቦታ ነው ፥ ወደዚያ ላለመሄድ።



ሁላችንም የሆነ መጥፎ ዝንባሌ አለን። አንዳንድ ሰው ለገንዘብ በጣም ስሱ ልብ አለው። አንዳንድ ሰው ለሴሰኝነት። አንዳንድ ሰው ለክብሩ። አንዳንድ ሰው ለመጠጥ እና ለሱስ። እነዚህ ሰዎች ይሄን ደካማ ጎናቸውን በቶሎ ተረድተው፤ ገደብ ካላበጁለት የሚሞቱበት ቦታ ያ ነው። እንደ ቶሎስቶይ የመሬት ነጋዴ ፥ በቃኝ ማለት አቅቶት መሬት ለመሰብሰብ ሲዳክር ሞተ። አንዳንድ ሰዎች ገንዘብ ያለበት ቦታ ሁሉ ይገባሉ። ለጥቂት ትርፍ ብለው የሞት ቀጠና ውስጥ ይደንሳሉ። አንዳንድ ሰዎች ለክብራቸው ሲሉ የውርደት ሞት ይሞታሉ። አንዳንድ ሰዎች ሴሰኝነት ድካማቸው ስለሆነ፤ ሴቶች ይጫወቱባቸዋል። የት ነው የምሞተው ብሎ መጠየቅ ወሳኝ ነው። የቱ ነው ደካማ ጎኔ? ስሱ ብልቴ። ወደ ዛ እንዳልሄድ።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Dec 22, 2024
  • 3 min read

ree

ከውድ ጓደኛዬ ጋር በቅርብ በስልክ ስናወራ አንዱ ርዕሳችን ሰዎች ማጣትን እና መተውን የሚወስዱበት መንገድ ነበር። ሰው በተፈጥሮ ማጣት ከማግኘት በላይ ይሰማዋል። አስር ሺ ብር ያጣ ሰው እና 12 ሺ ብር ያገኘ ሰው የሀዘን እና የደስታ መጠናቸው በጣም የተለያየ ነው። ያጣው ሰው የሚያዝነው ካገኘው ሰው ደስታ ይልቅ በብዙ እጥፍ ነው። ለምሳሌ ጠዋት ላይ 10 ሺ ብር አግኝተን ከሰዓት 5 ሺ ብር ብናጣ ፥ እጦታችን ሁሉመናችንን ይቆጣጠረዋል። በዚህም የተነሳ ሰዎች ብዙ ጊዜ በከሰረ ነገር ላይ ተጨማሪ ጊዜያቸውን ማጥፋት ይቀላቸዋል፤ ያ ነገር ላይ ተስፋ ከመቁረጥ ይልቅ።

 

የዚህ አንዱ ማሳያ በመጥፎ ግንኙነቶች ውስጥ የምናጠፋው ጊዜ ነው። ቀላል የማይባሉ ሰዎች ብዙ ጊዜ ከጎዷቸውሰዎች ጋር ወዳጅነታቸውን ይቀጥላሉ። እየጠቀማቸው ካለ ወዳጅነት ይልቅ፣ የተጣመመን ለማቅናት የሚወስዱት ጊዜ ይበልጣል። ስኬት ማለት ግን የሚሰራን ነገር በብዛት ማድረግ ፥ የማይሰራን ነገር በቶሎ መተው ነው። ለዚህ ደግሞ መጨከን ያስፈልጋል። ግራ የሚያጋቡንን ሰዎች፣ ፍላጎታቸውን በግልጽ ማኖር የከበዳቸውን እና ለወዳጅነታችን ያላቸው አክብሮት እምብዛም የሆኑ ግለሰቦችን መቁረጥ ፥ ስሜታችንን ከመጥቀሙ ባሻግር ለጥሩ ግንኙነቶች የበለጠ ጊዜ እና ዕድል እንድንሰጥ ያደርገናል። ይሄን ማድረግ ግን ቀላል አይደለም። ምክንያቱም ተፈጥሮአችን ማጣትን ከማግኘት በላይ ይፈራል። ስለዚህ ከተፈጥሮ ተቃራኒ መቆምን ይጠይቃል።

 

በኢኮኖሚክስ opportunity cost የሚባል ጽንሰ ሀሳብ አለ። ይሄ ማለት እያንዳንዱ ድርጊታችን እና ምርጫችን opportunity cost አለው። ከመጥፎ ወይም አሉታዊ ወዳጅነት ጋር የማሳለፍ opportunity cost ከጥሩ ወዳጅነት ጋር የማሳለፍ ነው። ከዛ ሰው ጋር የምናሳልፈው ሰዓት opportunity costቱ ጥሩ መጽሐፍ የማንበብ፣ ስሜታችንን የሚጠግኑ ነገሮችን የመስራት ሊሆን ይችላል። ግን ይሄን በማግኘት አናስበውም። በማክበር፣ በፍቅር፣ በታማኝነት እና በመልካም ቃላት ከጎናችን ሊሆኑ የማይችሉ ሰዎችን መተው (መቁረጥ) አለመቻል የሚያሳጣንን ነገር ማሰብ ለተፈጥሮአችን የተመቸ አስተሳሰብ ይሆናል። በመጥፎ ወዳጅነት ላይ የሚጠፉ እያንዳንዱ ደቂቃዎች ከጥሩ ወዳጅነት ጋር ልናሳልፋቸው የምንችላቸው ሰዓቶች እንደሆኑ ካሰባችሁ ፥ ለውሳኔ አሰጣጥ ይቀለናል።

 

ማቋረጥ፣ መተው፣ መልቀቅ፣ ተስፋ መቁረጥ የሚሉ ቃላት አሉታዊ (negative) ስሜት ብቻ ነው ያላቸው ብዙ ጊዜ። ለዚህ ነው አብረውን የሚሰሩ ሰዎችን፣ ወዳጆቻችንን ወይም የቅርብ ሰዎቻችን መተው እና ከእነሱ ጋር ማቆም የሚያስፈራን። ግን ለጥሩ ነገር ጅማሮ መጥፎ ነገር መቋረጥ ይኖርበታል። የበጎ ነገር መንደርደሪያ የመጥፎ ነገር ማብቂያ ነው። መጥፎ ነገር ወይም ለእነሱ የማይሰራን ነገር መተው ያልቻሉ ሰዎች ለእነሱ የሚሰራ እና በጎ የሚሆንላቸውን ለመጀመር አይችሉም። ቅድም እንዳልኩት በምንም መስክ ያለ ስኬት ማለት የሚሰራን ነገር አብዝቶ መስራት እና የማይሰራን ነገር መተው ነው።

 

በማይሰራ ነገር ላይ የምናጠፋው ጊዜ ከሚሰራ ነገር ላይ እየተቀነሰ እንደሆነ ካልገባን፤ ስለ አለን ውስን ሰዓቶች እና ሪሶርሶች ብዙ ግንዛቤ የለንም ማለት ነው። ሌላው ሰብአዊ ባህሪያችን የታዳጊነት እና ሰዎችን የመቀየር ስነልቦና እንዲኖር አድርጓል። እውነታው ግን ይሄን አስተሳሰብ የምንጠቀመው ሰዎች ከኛ የዓለም እይታ ጋር የሰመረ ባህሪ እንዲኖራቸው ነው። ወዳጆቻችን በራሳቸው ለራሳቸው የሚሆን ባህሪ ይዘው ይሆናል። ጥሩ ጓደኛ፣ ጥሩ ሚስት ወይም ጥሩ ቤተሰብ ላይሆኑ ይችላሉ። ግን እንደዛ የመሆን መብት እንዳላቸው መዘንጋት የለብንም። ብቸኛው ምርጫችን ያ ሰው ለኛ የሚሆን nurturing (ጠጋኝ) ባህሪ እንደሌላቸው መወሰን እና ያን ወዳጅነት ማብቃት ነው። ያ ሰው መጥፎ ስለሆነ ላይሆን ይችላል። ከኛ ጋር የሚስማማ ማንነት ግን እንዲኖረው ስላልመረጠ፤ የታዳጊነት እና ነገ ይሻሻላል የሚለው ባህሪያችን ያን ሰው ከኛ ጋር እንዲስማማ በማድረግ ጊዜያችንን በከንቱ እናጠፋለን።

 

በሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ 15 ከቁጥር 11 ጀምሮ ያለው አፍቃሪው አባት ታሪክ ብዙ አስተማሪ የሕይወት ምክሮች አሉት። አንዱ ትምህርት ልጁ ወደ ሞት ቀጠና እንደሚሄድ እያወቀ ገንዘቡን ከፍሎ ሰጥቶ መሸኘቱ ነው። እኛ ብንሆን የምናደርገውን ተመልከቱ። ፈጽሞ ልጃችንን አደጋ ውስጥ አንከተውም። በሽማግሌ ማስመከር፣ ማሳፈር፣ በጭቅጭቅ እና በኃይል ፍላጎቱን እንዲተው ማድረግ ነው። ያ ምን ያህል ልቡ የከጀለን ሰው ያስቆመዋል? መቼም የሚሰራ ስትራቴጂ ግን አይደለም።


ሲ ኤስ ሉዊስ እንዲህ ይላል “እየሰመጠ ያለን ሰው ለመርዳት እስከሚሰምጥ መታገስ ያስፈልጋል። ያለመስመጥ ትግሉን ሳይጨርስ የእርዳታ እጅ መዘርጋት ፥ ራስን ለአደጋ ማጋለጥ ነው።” በተመሳሳይ ሰዎች የውሳኔያቸውን ክፉ ውጤት በአግባቡ ተመልክተው፣ ሪፍሌክት አድርገው፣ የኛን እርዳታ ለመቀበል እጃቸውን እስከሚዘረጉ ድረስ ለመርዳት እና ለመታደግ መጣር የመማርን እና ፍጹም የመቀየርን ዕድል ነው የሚዘጋው። ለዚህ ነው የታዳጊነት ፓራሹታችንን ያለ ሰዓቱ ላለመክፈት መጠንቀቅ ያለብን።

 

ሰዎች ለምርጫቸው ኃላፊነት የሚወስዱ እና ከዛ የሚማሩ ካልሆኑ፤ ከእነዚህ ሰዎች ጋር የምናሳልፈው ጊዜ ጉዳቱ ለኛ ብቻ አይደለም፤ ለእነዛም ሰዎች የመማርን እና የመለወጥን ዕድል ነው የሚነሳው።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page