top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Dec 15, 2024
  • 3 min read

ree



ጥንታዊ መጽሐፎች የሚነግሩን ይሄ ሕይወት ጦርነት እንደሆነ ነው። እስቲ በደንብ ይሄን ለመረዳት አሁን እየተካሄደ ያለ ጦርነት እንመልከት። ለምሳሌ ሩሲያ እና ዩክሬን ጦርነት ውስጥ ናቸው። ጦርነቱ ገና አልተጠናቀቀም። እምብዛም የተገመተው ውጤት አልተገኘም። በጦርነቱ እስካሁን በሁለቱም ወገን ያሉት የጠበቁት አልሆነም። ብዙ ውጊያዎች እስካሁን ተካሂደዋል። ለምሳሌ በአንቶኖቭ ውጊያ፣ በካርኪቪ ውጊያ፣ በኬርሰን ውጊያ፣ በሉናስክ ውጊያ እና ሌሎች ሩሲያ ስታሸንፍ ፥ በቮዝነሰስኪ ውጊያ፣ በሚካሪ ውጊያ፣ በኢርፒን ውጊያ፣ በሰሚ ውጊያ እና ሌሎች ዩክሬን አሸንፋለች። ውጤታቸው ገና ያልታወቁ ውጊያዎች አሉ። እንደቀጠሉ ያሉ። ጦርነቱ በመጨረሻ እንደሁሉም ጦርነቶች አንዱ በአንዱ ላይ የበላይ ሆኖ ይጠናቀቃል። ግን አሸናፊው የሚፈልገውን በመጨረሻ ላያገኝ ይችላል።



ሕይወትም ልክ እንደዚ ጦርነት ናት። ዩክሬን ከሩሲያ ጎረቤት መሆኗ ተፈጥሮአዊ ሁኔታ ነው። ጎረቤት ሀገርህን መምረጥ አትችልም። በሕይወትም ብዙ ማንመርጣቸው ነገሮች አሉ። ዕድል ብቻ የሆኑ፣ ከኛ ቁጥጥር ውጪ ያሉ ክስተቶች አሉ። በሚገርም ሁኔታ ግን የሕይወትን ደስታ እና ስኬት የሚወስነው ከማንመርጣቸው ነገሮች በላይ የምንመርጣቸው ጉዳዮች ናቸው።


የመጀመሪያው የሆነውን ነገር እንደሆነ የመቀበል ምርጫ ነው። ሪያሊቲን (ነባራዊ እውነታን) እንዳለ የማየት ምርጫ።



ምንም ሩሲያ ኃያል ብትሆን ሁሉንም ውጊያዎች ማሸነፍ አትችልም። ከሩሲያ አንጻር ዩኩሬን ምንም ትንሽ ብትሆን ሁሉንም ውጊያዎች አትሸነፍም። በኛም ሕይወት ሁሉንም አውደ ውጊያዎች አናሸንፍም። ይሄ ሕይወት የልጅ አውደ ውጊያ አለው፣ የገንዘብ አውደ ውጊያ አለው፣ የጓደኝነት አውደ ውጊያ አለው፣ የጤና አውደ ውጊያ አለው፣ የመንፈሳዊነት አውደ ውጊያ አለው፣ የታዋቂነት እና የማህበረሰባዊ ክብር አውደ ውጊያ አለው፣ የውበት አውደ ውጊያ አለው፣ የጥበብ እና የእውቀት አውደ ውጊያ አሉት፣ የትዳር እና የፍቅር አውደ ውጊያ አሉት፣ የጥሩ ቤተሰብ አውደ ውጊያ አለው፣ የሥራ እና የሙያ አውደ ውጊያ አሉት፣ የመኖሪያ አከባቢ አውደ ውጊያ አለው። እነዚህ እና ሌሎች የውጊያ አውዶች ናቸው በሕይወት ጦርነት ውስጥ ያሉት። ስኬታማ ሕይወት ማለት ሁሉንም አውደ ውጊያዎች ማሸነፍ ማለት አይደለም። እንደዛ የሚያስብ ሁሉ በዚህ የሕይወት ፍልሚያ በፍጥነት ከጫወታ ውጪ የሚሆን ነው። የመጀመሪያው እውነት ሁሉንም ውጊያዎች እንደማናሸንፍ ማወቅ ነው። ሁለተኛው ትልቁ ጥበብ ግን የትኛው ውጊያ ወገብ ሰባሪ እንደሆነ መረዳት ነው። ማለትም በፍጹም መሸነፍ የሌለብን ውጊያ የትኛው ነው የሚለውን ማወቅ። ያን ውጊያ የተሸነፈ ሁሉንም አውደ ውጊያዎች ቢያሸንፍ እንኳ ጦርነቱን ይሸነፋል።



ታላቁ የጦር አዋቂ ሰን ዙ እንዳለው የምርጥ ጄኔራል መለያው ይሄን አውደ ውጊያ ማወቅ ነው። ምርጥ ጄኔራል ብዙ ውጊያዎችን ተሸንፎ እንኳ ጦርነቱን ግን ያሸንፋል። ሁሉም ውጊያዎች ላይ ያለንን አቅም በእኩል መጠን ማፍሰስ አንችልም። ስለዚህ አንዳንዶቹን ለመሸነፍ መተው አለብን። ለአንዳንዶቹ ውጊያዎች ተፈጥሮ ሳይቀር ለሽንፈት የሚሆን ማንነት ሰጥታናለች። ስለዚህ ያንን መቀበል ያስፈልጋል። ዩኩሬን ምርጫዋ ቢሆን ከሩሲያ አጠገብ ጎረቤት ባትሆን ይሻላት ነበር። ግን አንዳንድ ምርጫዎች በዚህ ዓለም ዝግ ናቸው። የመቀበል እና የለውጥ ሚዛን ነው በጦርነቱ አሸናፊ የሚያደርገን።



የሆነን ግለሰብ ሕይወት አይታችሁ የእናንተ ሕይወት እንደዛ ሰው እንዲሆን መመኘት የመጀመሪያው የሽንፈት ፕሮፓጋንዳ ሰለባ መሆኛ መንገድ ነው። ሰን ዙ እንደሚለው ጦርነትን ሳትዋጋ ማሸነፍ ከቻልክ የምንጊዜም ምርጥ ጄኔራል ነህ። እንዴት ነው ሳትዋጋ የምትሸነፈው? (ለጊዜው ሳንዋጋ ማሸነፉን እንተወው እና!)። እንደ ሌሎች እኛም እንድንሆን በመመኘት። የሕይወት ምርጫችን እኛን ብቻ ነው ሊመስል የሚገባው። ተመሳሳይ መጽሐፍ እያነበቡ፣ ተመሳሳይ ምግብ እየበሉ፣ በተመሳሳይ ቤተሰብ እና በተመሳሳይ አካባቢ ያደጉ ሁለት መንትያ ልጆች ሳይቀር በዚህ ምድር ላይ ለሚገጥማቸው ነገር የሚሰጡት ግብረ መልስ ለየቅል ነው። ልጆች እንደእነ እከሌ ልጆች እንዲሆኑ መመኘት ልጆችን ለሽንፈት ማሰልጠን ነው። ያ ልክ ለጠላት ፕሮፓጋንዳ ተላልፎ እንደመሰጠት ነው። እውነት ነው ሰው በመሆናችን ከሌሎች ጋር የምንጋራቸው ብዙ ጉዳዮች አሉ። ግን በዚህ ሕይወት ያለን ጥልቅ ደስታ እና ሀዘንን አስመልክቶ ከማንም ጋር አንጋራም። በጦርነት መኃል አሰቃቂን መከራ ተቀብሎ የሚስቅ እንዳለ ሁሉ ፥ ፌሽታ በበዛበት መኃል የሚቆዝም አለ። “ለምን?” ካልን መልሱ ያን ሰው ብቻ ነው የሚመስለው። ሕይወትን በሌሎች መነጽር ብቻ ለማየት የሚደክም ማንም ምንም ነገርን አጥርቶ የማየት እርከን ላይ አይደርስም።



በመጨረሻም የሰው ልጅ ትልቁ ሀብቱ የማሰብ እና የማሰላሰል አቅሙ ነው። ያም አውደ ውጊያ ነው። በነጻነት የማሰብ እና ነገሮችን በጥልቀት የማየት አቅምን ማዳበር የሕይወትን ጦርነት ለኛ በሚስማማ መልኩ ለማጠናቀቅ ጥቅም አለው። ይሄ ሕይወት የኛ ሕይወት ነው። ባንተ ሕይወት መዝገብ ውስጥ ያለፈው እና ያለው ያንተ ነው። ስለዚህ ኃላፊነት እንውሰድ። ሁሉን ልታሸንፍ አትችልም። ዓላማህ በጦርነቱ ማብቂያ ጫፍ ላይ ስትደርስ ፥ የአንድ ደቂቃ ዕድል ብታገኝ ፥ ይሄ ሕይወት ውብ ነበር ለማለት ነው። በስንፍና ያለፍከው ነገር እንደሌለ በማየት፣ የራስህን ጀርባ እየመታህ "በራሴ ሕይወት ላይ ምርጥ ጄኔራል ነበርኩኝ" ለማለት መብቃት ነው። ምክንያቱም ይሄ ሕይወት ያንተ ሕይወት ነው። ሽንፈቱም ድሉም ያንተ ነው።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Dec 1, 2024
  • 4 min read

ree



ድሮ የምሰራበት የስፖርት ቦታ በትልቁ “NO PAIN NO GAIN ወይም ካለሕመም ምንም የምታገኘው ነገር የለም!” የሚል የተጻፈ መፈክር ነበረው። አንዳንዴ ወደ ኋላ በመሄድ በሕይወቴ ያሳለፉኳቸውን ከባባድ ጊዜዎችን ለማስታወስ እጥርና “ምናለ እንደ ዛ ባልሆን” ልል ይቃጣኛል ፥ ሕመሙን በማስታወስ። ግን ያ ሀሳብ ከአንዱ የአዕምሮ ክፍሌ ሳያልፍ ነው ያን የመስቀል ጉዞ “እሰይ ሆነ ፥ እሰይ ደረሰብኝ” ብዬ በድጋሚ የማፈቅረው። ብዙዎቻችን ያለ መስቀል ትንሣኤ ፈጽሞ እንደማይኖር አይገለጽልንም። እሁድን የሚናፍቅ ቢኖር አርብን መታገስ ይጠበቅበታል።


ሕመምን የምንታገሰው ጀግና  ፥ ስለሆንን ወይም የተለየ ፍጡር ስለሆንን አይደለም።


እንደሚሞት፣ ለዛውም የመስቀል ሞትን እንደሚሞት ራሱ ጭምር እየተናገረ የመጣው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሳይቀር መስቀሉን በቅርብ ርቀት ሲያየው ፥ “ይሄ ጽዋ ፈቃድህ ቢሆን ከእኔ ይራቅ” ብሎ ጸልዪል። የጌታችን ያልተሰማ ጸሎት ይሄ ብቻ ነበር። “ዋጠው፣ ይሄን ጽዋ ጠጣው” ብሎ አባቱ ጨከነበት። አጽናኞችን ግን ላከለት። እውነተኛ አባት የሚያደርገው ይሄን ነው። የሕመምን ጽዋ ለልጆቹ ያስጎነጫል። እውነተኛም እናት ከዚህ የአባት ጭካኔ ጋር ትስማማለች። ምክንያቱም የልጇን ትንሣኤ ትፈልጋለች እና። ልጇ ሁልጊዜ ልጅ ሆኖ እንዲቀር አትፈልግም። ለዚህ ነው እመቤታችን ድንግል ማርያም አንድም ጊዜ ጌታን ከመስቀል ሞት እንደ ሐዋርያው ጴጥሮስ “ልጄ ሆይ ፥ አትሙትብኝ” ብላ ስትከላከል ያልታየችው። ያልተሰማችው። ያ ሞት ያለጊዜው ሲመጣ ብቻ ልጇን ካለጊዜው ከሆነ ሕመም ጠበቀችው እንጂ ፥ በዕድሜው ለሆነው አርብ ግን ድንጋል ማርያም ተባባሪ ነበረች። ይሄ ትንሣኤን ለራሱ ለሚሻ ፥ ለልጆቹ ለሚመኝ ሰው ሁሉ የተጻፈ ታሪክ ነው።



አሁን አሁን ሕይወትን ካለብዙ ነገሮች ማሰብ እያቃተን ነው። በተለይ በምዕራቡ ሀገራት። መብራት፣ ኮምፒውተር፣ ጉግል፣ ፍርጅ፣ መኝታ ቤት የተቀመጠ መጸዳጃ ቤት ፥ ሕይወትን ካለእነዚህ የማያውቅ ትውልድ ነው ያለው። አንዱ ለልጄ “በኛ ጊዜ ጉግል (Google) አልነበረም ስለው አላመነኝም” ብሏል። ምክንያቱም ካለ ጉግል የሰው ልጅ ምን ያህል መረጃን ለማግኘት እንደሚደክም ይሄ ልጅ ፈጽሞ የማይረዳበት ዘመን ነው።



አሁን አሁን ወደ ሕክምና ስፍራ ብትሄዱ የመጀመሪያው የሚሰጣችሁ ነገር ሕመም ማስታገሻ ነው። በየቤቱ የተለያዩ ዓይነት የሕመም ማስታገሻዎች አሉ። መውሰድ ባንፈልግ እንኳ ቢያንስ ከራስ ምታት ማስታገሻ እስከ ተለያዩ ኦፒዎዶች ቤታችን አሉ። እንቅልፍ እንቢ ካለንም ብዙ መጨናነቅ አሁን አያስፈልገንም። በተለያዩ መልኮች የእንቅልፍ ማስተኛ ሽሮፖች እና ክኒን ሞልተውልናል። የሰው ልጅ ብዙ ታሪኩ ግን እንዲህ አልነበረም። እስከ አስራዘጠነኛው ክፍለዘመን መጨረሻ ድረስ የሕመም ብቸኛ ምርጫ ጥርስን ነክሶ መቻል ነበር። ምን አልባት ትንሽ ማደንዘዣ አልኮል ይሰጥሃል ወይም የምትነክሰው ነገር ያቀብሉህና ፥ የሰውነትህ አካል ሳይቀር ያለማደንዘዣ ይቆረጥ ነበር። ልክ እንደ ክርስቶስ አጠገብህ የሚያጽናኑህ ይኖሩ ይሆናል እንጂ ያን ሕመም ስለ ሕመሙ ብቻ ተብሎ የሚያስቀረው አልነበረም። ምክንያቱም ለረዥሙ የሰው ልጅ ታሪክ ሕመም የሰው ታሪክ አካል ነበር። የሕክምና ባለሙያዎች እና ተመራማሪዎች ሳይቀር ፥ ሕመምን ለማስቀረት ያደረጉት ጥረት የረዥም ጊዜ ታሪክ አልነበረም። ትልቁም የሳይንስ ትኩረት አልነበረም።



ጆናን በርክ በStory of Pain በሚለው መጽሐፉ እንደጻፈው ኬሚስት ሀምፍሬ ዴቪይ የLaughing Gasን (ላፊንግ ጋዝን) የሕመም የማስታገሻ ባህሪውን ካገኘ በኋላ እንኳ በሕክምናው እና በሳይንሱ ዓለም እንደ ትልቅ ግኝት ተቆጥሮ በቶሎ ወደ ተግባር አልተገባም። ለሕመም ማስታገሻነት በስፋት ጥቅም ላይ እስኪውል መቶ ዓመታት ፈጅቷል ። ሌሎችም የሕመም ማስታገሻዎች፣ ለምሳሌ እንደ ኒትረስ ኦክሳይድ ሲገኝም የሕክምናው ዘረፍ እንደ ዛሬው ተሯርጦ ወደ መጠቀም አልገባም። ጆናን በርክ እንደሚለው የሕመም ትርክት ለብዙ ሰዎች ለመቀበል የሚቸገሩት አልነበረም። ሕመም ለዶክተሮችም ሆነ ለታካሚዎች የሕክምናው እና የመዳን ሂደት አካል ነበር። እንደውም አንዳንድ ሰርጅኖች ያለ ታካሚው የስሜት እንቅስቃሴዎች እና ጩኸት ሕክምናውን ማድረግ አይፈልጉም ነበር።



ከሁሉም በላይ ግን ለብዙ ሰዎች ለብዙ የታሪክ ዘመን ሕመምን ራስን በመቆጣጠር፣ በመግዛት እና በክብር ጨክኖ ማለፍ የማንነት መገለጫቸው እና የጀግንነት ጌጣቸው ነበር። ሕመም የጀግንነት፣ የወንድነት እና የታላቅ ስብዕና መገለጫ ነበር። ሕመምን ሳይመጣ ይለማመዱት ነበር። በሚበሉት ነገር ሳይቀር የሚያቃጥል፣ የሚለበልብ እና ጎምዛዛ ነገር በማብዛት የሕመም የመታገስ ሐሞታቸውን ያጠነክሩ ነበር። በእኔ ዕድሜ ሳይቀር የሚያቃጥል ቃሪያ በምግብ ጠቅልሎ አባቴ ያጎርሰኝ ነበር። ፈጽሞ ያን እንድተፋው አይፈቀድልኝም ነበር። ጨክኜ አኝኬ እድውጠው እንጂ። ከዛ የሚብስ ነገር ሊመጣ ስለሚችል ያን ቃጠሎ ቃሪያ አኝኬ እውጠዋለሁ። የአባትነት ሥራ ልጅን ከሕመም መጠበቅ አልነበረም። ይልቁንስ በየደረጃው ለሕመም ማጋለጥ እንጂ።



ዛሬ ግን የሕክምናው ዘርፍም ተለውጧል። በአሜሪካ ዶክተሮች የሚገመገሙት ታካሚዎች የሕክምናው ፕሮሲጀር ሲካሄድ በተሰማቸው የሕመም መጠን ሆኗል። ምንም ሕመም ካልተሰማቸው ያ ዶክተር ትልቅ እና በጎ ሬቲንግ ያገኛል። ያም ለደሞዝ እና ለእርከን ዕድገት አስተዋጽኦ አለው። ስለዚህ ዶክተሮች ምን ያደርጋሉ? ሱስ እንደሚያሲዝ እያወቁ የተለያዩ የሕመም ማስታገሻዎችን ለታካሚዎቻቸው ያስቅማሉ። ዛሬ አሜሪካ ውስጥ መጨነቅ መድኃኒት አለው። መወፈር መድኃኒት አለው። ትኩረት ማጣት የሚቃም መድኃኒት አለው። ያለመድኃኒት የማይንቀሳቀሱ ጥቂት መጤዎች ብቻ ቢሆኑ ነው። ከ1980ዎች ጀምሮ የዓለም የጤና ድርጅት ሳይቀር እነዚህ የሕመም ማስታገሻ ኦፒዶዎች በስፋት እንዲመረቱ እና ጥቅም ላይ እንዲውሉ መግፋት እና ማበረታታት ጀምረዋል።



የሚገርመው ግን የሕመም ማስታገሻዎች የረዥም ጊዜ ጥቅም እንዳላቸው የሚያሳይ ምንም ሳይንቲፊክ የሪሰርች ውጤቶች አለመኖሩ ነው። ያ ብቻ ሳይሆን አሁን በስፋት እየወጡ ያሉ ጥናቶች እንደሚያሳዩት የሕመም ማስታገሻዎች የቁስሎች የመዳንን ሂደት በጣም እንደሚያዘገዩት ነው። ልክ ነው አንዳንድ የቀዶ ጥገና ሕክምናዎች የግድ የሕመም ማስታገሻዎች (anesthesia) ያስፈልጋቸው ይሆናል። ግን ከየት ወዴት እንደመጣን ብቻ እዩት?



የሰው ልጅ ትልቁ ሀብቱ ለራሱ የሚነግረው ትርክት ነው። ብዙ ጊዜ እንደጻፉኩት የደስተኛ ሕይወት ምንጭ ትርጉም ያለው ሥራ መሥራት እንጅ ምቾት አይደለም። ደሃ ራሱን አጠፋ ሲባል መስማት በጣም ዝቅተኛ ነው። ራስን ማጥፋት እንደ ፊንላንድ፣ ደቡብ ኮሪያ እና መሰል የምቾት መጠናቸው ከፍ ባሉ ሀገራት ላይ ነው የሚብሰው። የሰው ልጅ ሕመምን እና መከራን ለማለፍ የሚታገለው ትግል እና በዚህ ወቅት ለራሱ የሚነግረው ትርክት ነው የደስታው መሠረት። ትርጉም ያለው ሕይወት ማለት ይሄን ሕመም ጥርስ ነክሶ ሲታለፍ ነው። ይሄ ሕመም የትውስታ ማህደራችን (memory) ውስጥ ካልተቀበረ ፥ የምናገኘው ጥሩ ነገሮች እና ምቾቶች ሁሉ አያስደስቱንም። መስቀሉ ነው የትንሣኤው ውበት። ያ ትንሣኤ ውበት የሚኖረው ፥ ልብሳችንን ተከፋፍለው፣ በጦራቸው አይነሳም ብለው ወጋግተው፣ በተሳለቁብን እና ባሾፉብን መኃል ከዛ ሕመም በላይ ሆነን ፥ ከቀናት መሰወር በኋላ ላያስቆሙን ብድግ ስንል ነው። እነዛ ሕመሞች የትንሣኤው ዘላለማዊ ጌጦች ናቸው። ኢዮብ ያለ ሕመሙ እና ጥርሱን ነክሶ ራሱን ሳያዋርድ ሕመሙን መታገሱ ነበር ዖፅ ከምትባል መንደር በላይ ለዘላለም ገዝፎ እንዲታይ፣ እንዲተረክለት ያደረገው። ሰው እንዴት ነው ጌጦቹን የሚርቀው? እንዴት ይሄን የደስታ ምንጭ ከልጆቻችን እናርቃለን?

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Nov 28, 2024
  • 4 min read

ree

September 2023


የሁለት ሺ ዓመት ታሪክን በሚደንቅ ውበት የሳለ፣ በታላቁ የስዕል ጠቢብ በቪንሰንት ቫን ጎ “ይሄን ስዕል መሳል የቻለ ሰው ብዙ ሞትን ራሱ የሞተ ነው” ተብሎ የተመሰከረለት ፥ በዚህ ምድር ሁሉን ነገር አግኝቶ ያጣ ፥ የ17ኛው ክፍለ ዘመን የደች የምን ጊዜም ምርጥ ሰዓሊ ራምበረንት እና የጠፋው ልጅ ታሪክ።



ራምበረንት በ17ኛው ክፍለ ዘመን የነበረ ታዋቂ ሰዓሊ ነበር። በጊዜው ሀብታም ሰው ሁሉ ለሱ ማንኛውንም ክፍያ ከፍሎ በሱ መሳልን ፥ የሱን የቡርሽ አሻራ በቤቱ ማኖር የሚፈልጉ ሁሉም ከበርቴዎች እና ባላባቶች ነበሩ። በዚህ ዝናው በሚመጣ ሀብት እና ክብር ራምበረንት የጉብዝናውን ወራት ፍጹም በተጋነነ የዝሙት እና የስካር ሕይወት ማሳለፍ ጀመረ። ደንበኞቹን መስደብ እና ማመናጨቅ፣ የጠመዳቸውን ሰዎች ከፍተኛ ገንዘብ ከፍሎ የሚያሳስር፣ የአዕምሮ ሕክምና ጣቢያ ውስጥ የሚያስጨምር ሆነ። ያን ረምበረንት ነበር ዓለም እስከመጨረሻው የሚያውቀው ፥ ለራሱ ክፋት ሁለተኛ ዕድል የሚሰጠው የሰው ልጅ ሌላ ሰው ሲሳሳት እና ሲበድል ቢያየው ግን የወደፊቱን ብቻ ሳይሆን የቀደመውንም ጽድቅ ነው የሚነሳው። ድሮም ሲያስመስል ነበር ይላል። ወደፊትም በጎ ይሰራል ብሎ አይቀበልም።



ራምበረንት ያን ፍርድ ነው ከዓለም ያገኘው። በሉቃስ ወንጌል (15፥12) የምናገኘው ታናሹ ልጅ ልክ እንደ ራምበረንት ከአባቱ ሀብት ተካፍሎ (ጸጋ ወስዶ) ወደ ሩቅ ሀገር ሄደ ይላል መጽሐፍ ቅዱስ። በዚህ የሉቃስ ወንጌል ላይ ጥናት የሰራው የሀርቫርዱ ሄነሪ ኖዌን በየትኛውም የዓለማችን ክፍል ባሉ ማህበረሰቦች ባህል አባት ሳይሞት ፥ ልጅ የአባቱን ንብረት አይጠይቅም ይላል። በሌላ አነጋገር ታናሹ ልጅ ያለው “አባቴ ሆይ አትሞትም እንዴ? የማትሞት ከሆነ ቆሜ አልጠብቅህም” ነው። ሞቱን ተመኝቶ ንብረቱን ተካፍሎት ርቆ ሄደ።



ራምበረንት ይሄን ልቅ ሕይወት ሲመራ የመጀመሪያ ወንድ ልጁን በ1635 በሞት ተነጠቀ። ከመቼውም ጊዜ በላይ ለቀሪ ልጆቹ መራራት እና ከሚስቱ ሳሲካ ጋር በሀዘኑ ምክንያት ቅርበትን ፈጠረ። ራምበረንት ግን የመጀመሪያ ሴት ልጁን በ1638 በሞት ተነጠቀ። ብዙም አልቆየም በ1640 ኮሪኒላ የተባለች ሴት ልጁ በሞት ተለየችው። በዚህ ጊዜ የራምበረንት ዝና እና ክብር ወርዶ ፥ ሕይወቱ መመሰቃቀል ጀመረ። የገንዘብ ዕዳ ውስጥ እየተነከረ መጣ። በዚህ ወቅት ነበር ሚስቱ ሳሲካ የዘጠኝ ወር ልጅ አሳቅፋው በ1642 በሞት የተለየችው። ከልጁ ሞግዚት ጋር ግንኙነት ቢመሰርትም ፥ በክስ እና በመጨረሻም እሷ በአዕምሮ ሕክምና ጣቢያ ውስጥ በሚያሳስር ፍርድ ተጠናቀቀ። ስቶፈል ከተባለች ሴት ጋር ተጋባ ፥ ሁለት ልጆች ወለደችለት። ነገር ግን አሁንም የወለደችለት ወንድ ልጁ በ1652 ሞተበት። በዚህ ወቅት ቤቱ እና ስዕሎቹ ሁሉ በሀራጅ ተሸጡበት። በዚህ ሰዓት የሳላቸው ስዕሎች በጣም ልዩ እንደሆኑ እና “ሰውን እና ተፈጥሮን በሚደንቅ መነጽር ማየት የጀመረበት፣ ከዚህ በፊት በስዕሉ የሚታዩ ውጪያዊ ጫጫታዎች የራቁት ነበሩ” ይላል ስለሱ የጻፈው ጃኮብ ሮዘንበርግ። ሁለተኛ ሚስቱ በ1663 ሞተችበት። ከዓምስት አመት ቆይታ በኋላ ራምበረንት ከመጀመሪያ ሚስቱ የወለደው ብቸኛ ወንድ ልጁ እና በጣም የሚወደው ቲተስ ሞተ። ራምበረንት በዚህ ወቅት ነበር ፥ ቡሩሹን አንስቶ ማንም ስሎት በማያውቀው ጥልቀት የጠፋውን ልጅ ታሪክ የሳለው።



የእርያዎችን አሰር መብላት ሲከለከል የአባቱ ቤት ሕይወት እንደታወሰው የጠፋው ልጅ ብቻ አይደለም ራምበረንት አሁን እግዚአብሔርን ያወቀው። ይልቁስ በጠፋው ልጅ ታሪክ የተሰወረውን የአባት ፍቅር ነበር ራምበረንት በስዕሉ አውጥቶ ያሳየው። የጠፋው ልጅ ልሂድ ሲል ፥ እንደ ወላጅ “አትሂድ አላለውም” ያ አባት። ታናሹ ልጅ ለመሄድ የሚያስፈልገውን ሁሉ ሰጠው እንጂ። ከዚህ ቤት ውጪ ደስታ እንደሌለ ቢያውቅም ፥ ደስታን ከአባቱ እቅፍ ውጪ ለፈለገች ነፍስ በዓለም የሚያስፈልጋትን ሁሉ ሰጥቶ ሸኛት። ያ ሀብት እንደሚያልቅ፣ መቁሰል እና መጎዳት እንዳለ ቢገነዘብም ፥ ያ አባት ግን አደጋን ለመጋፈጥ ለፈቀደች ነፍስ ነጻነትን ሰጣት። ራምበረንት “ታናሹ ልጅ ከአባቱ ቤት ሲሄድ ብቻ ሳይሆን ወደ አባቱ ቤት ሲመጣም አባቱን እንዳላወቀው ስለገባው” ነበር ፥ የጠፋውን ልጅ ጭንቅላት የሕጻን ልጅ ሰውነቱን የአዋቂ አድርጎ የሳለው። አባቱ ቤት ሲመለስ ንግግር እየተለማመደ፣ ምን መናገር እንዳለበት እያሰበ ነበር የመጣው። የሱ ንግግር የአባቱን ልብ የሚያራራ መስሎት። ከእግዚአብሔር ፍቅር በላይ የኛ ቃላት ፍቅር የተሸከሙ ይመስለናል። አባቱ ግን ገና ሩቅ ሳለ አዘነለት። ልጁ ንስሐውን ሳይጨርስ አባቱ ልጁን አለበሰው፣ እጁን በቀለበት እግሩን በጫማ አሳመረው።



ራምበረንት ወደ እግዚአብሔር መንግስት እንደ ልጅ ካሎናችሁ አትገቡም የሚለውንም አሳየን።የጠፋውን ልጅ ጭንቅላት ከማህፀን የወጣ ጭንቅላት አስመስሎ ስሎ። አባቱን ሁለት ዓይነት እጆች ያሉት፥ የሴት እና የወንድ አድርጎ ሳለው። እንደምንጎዳ እያወቀ ለነጻ ፍቃዳችን እሺታውን የሚሰጥ አባት (ልቤ ጨከነ እንዳለ ዳዊት)፥ ስንመለስ ደግሞ በፍቅር ሮጦ የሚቀበለን እናት ነው እግዚአብሔር። ራምበረንት ግን ታላቁንም ሳለው። በውስጥ ሳለ የጠፋውን ፥ ከጠፋው ይልቅ በውስጡ መራራነትን ያዘለውን። ከወንድሙ መዳን ይልቅ የሰባው ፍሪዳ መታረድ ያስጨነቀው ፥ መመለሱ ሳይታወቅ ታሪኩ የተጠናቀቀው ታላቁ ልጅ። ባለፈው ዓመት በሀገራችን ያየነው ይሄን የታላቁን ልጅ ማንነት ነበር።



ታላቁ ልጅ በልቡ በታናሹ ልብ ውሳኔ የሚደሰት ሰው ነበር። የሚጠብቀው አባቱ ሞቶ ታናሹን ማስቀናት፣ ከሱ የበላይ ሆኖ መኖር ነበር። ሁልጊዜ ከአባቱ ጋር መሆኑ አላስደሰተውም ፥ የሚጠባበቀው አንድ ቀን የአባቱን ሁሉን መውሰድ እንጂ። ስለዚህ ከአባቱ ምንም እንዳይጎድል በስስት ይጠብቅ ነበር። የክህነት ቀሚስ ገድቧቸው እንጂ እንደታናናሿቹ መጋደል ያማራቸው፣ ታናናሾቹ ሲታረቁ ሞተን እንገኛለን ብለው የአባታችንን ቤት ቆልፈው የሄዱ ታላላቆችንም ያየነው ባለፈው ዓመት ነበር።



ለምን እንደሆነ አላውቅም ፥ ስለራምበረንት እስከማውቅ ድረስ የጠፋው ልጅ ያባከነው ‘ገንዘብ እና ጸጋ’ ብቻ ነበር የሚመስለኝ። ለካ ሁሉም ነገር ስጦታ ነው። ማለትም ራምበረንት ልጆቹን እና ሚስቱን አጣ ፥ እነዚህ ሁሉ የእግዚአብሔር ስጦታ ነበሩ። ኢዮብ ልጆቹን እንዳጣ፣ ኑኃሚን ከባሏ እና ከሁለት ልጆቿ ጋር ከእስራኤል ወጥታ ፥ ባሏን እና ሁለት ልጇቿን አጥታ ባዶ እጇን እንደተመለሰች ፥ የሚወሰደብን ነገር ምን እንደሆነ አናውቀውም። ሁሉም ግን የሱ ስጦታ ነው። ከሱ በተለየን መጠን የሚጠፉ ፥ የሚባክኑ፣ የሚያልቁ ናቸው።



ራምበረንት የመጨረሻ ልጁን ባጣ በሁለት ዓመት ውስጥ እሱም ሞተ። በሉቃስ ወንጌል 2፥28 እንደምናገኘው ስምዖን “እርሱ ደግሞ ተቀብሎ አቀፈው እግዚአብሔርንም እየባረከ እንዲህ አለ። ጌታ ሆይ፥ አሁን እንደ ቃልህ ባሪያህን በሰላም ታሰናብተዋለህ”፤ ራምበረንት በክርስቶስ እቅፍ ውስጥ በመጨረሻ አረፈ። ከሩቅ ያየው አምላኩ ከሱ ብዙ አልጠበቀምና ወደራሱ ሰበሰበው። የራምበረንት የመጨረሻ ስዕልም የነበረው ይሄ የአዛውንቱ ስምዖን ነበር። "አሰናብተኝ ፥ ነፍሴ የተጠማችሁን በመጨረሻ አየውት" የሚለው የአዛውንቱ የስምዖን ስዕል ነበር የራምበረት ፍጻሜ።



አዲሱ ዓመት ወደ ልቦናችን የምንመጣበት ዓመት ይሁነን። የእግዚአብሔር ፍቅር ይግባን። እሱም ወንድምን ከፍሪዳዎች በላይ መውደድ እና አባታችን እኛን በፍጹም ፍቅሩ እንደሚወደን ማወቅ ነው። “ይሄ የምወደው ልጄ ነው” የሚለው ድምጽ ከእርሱ ጋር ሕብረት ቢኖረን ለኛም ነው። የፈረድንባቸው እና ከመጠን በላይ የምንጠላቸው ሰዎች ሁሉ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸው። የሰባውን ፍሪዳ የሚያርድላቸው፣ አንባር የሚያጠልቅላቸው ፥ ጫማ የሚያደርግላቸው አንገታቸውን አቅፎ የሚስማቸው ናቸው። ይሄን ስናውቅ በወንድሞቻችን ላይ ጥላቻ ሊኖረን እንደምን ይችላል? ይሄ ፍቅር ካለበትስ ቤት ወዴት እንሄዳለን?

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page