top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Oct 20, 2024
  • 5 min read

ree


አንድ እግዚአብሔርን እጅግ የሚወድ ወዳጅ አለኝ። ነገር ግን ስለሲዖል ሲያስብ ግራ ይገባዋል። እግዚአብሔር ምን ያህል ፍቅር እንደሆነ እያወቀ፣ ስለ ሲዖል የሚሰጠውን ትምህርት ደግሞ ለመቀበል ይቸገራል። ልጆች ስላሉት ለዘላለም እግዚአብሔር ልጆቹን በእሳት ያቃጥላል የሚለው ትምህርት አይዋጥለትም። በልጆቹ ፈጽሞ የማይጨክነው እርሱ፤ እግዚአብሔር ፍቅር ሆኖ ሳለ በእጆቹ ውብ ሥራ የሰው ልጆች ላይ ይጨክናል የሚለው ይጸንነዋል። በርግጥ ይሄ እኔንም የሚከብደኝ ትምህርት ነበር። ነገር ግን እግዚአብሔር ፍቅር ብቻ ሳይሆን ፍትሕ እና እውነትም እንደሆነ ስለምንዘነጋ እና ያን ደግሞ ፍቅሩን የተቀበሉት ከእርሱ የሚጠብቁት እንደሆነ ስለምንረሳ ነው። ማለትም እግዚአብሔርን ለማፍቀራቸው አንዱ የእርሱ ፍትሐዊነት እና እውነተኝነትም ነው።



 ይሄን በጥቂቱ ከማብራራቴ በፊት “የእኛስ ቅጣት ከእግዚአብሔር ይለያል ወይ?” የሚለውን ጥያቄ ልጠይቅ በመጀመሪያ፤ ሲዖል በዋናነት የሚከብደን ኃጢአተኛ በመቀጣቱ ሳይሆን ፥ በጥቂቱ የሕይወት ዕድሜው በሠራው ኃጢአት እንዴት ዘላለም ይቀጣል፤ ያውም በገሀነም እሳት የሚለው ነው። ማለትም ‘ኃጢአት የሠራበት ዘመን እና የመቀጣቱ ዘመን ርዝማኔ አይመጣጠንም’ ነው እያልን ያለነው እንጂ “የሰው ልጆችን በእሳት ቼምበር አቃጥሎ ሥጋቸውን ያስፈጨው ሂትለር ያለቅጣት በይቅርታ ይታለፉ፣ የሰረቀ እና ከድኋው በክፋት የነጠቀ፣ ወንድሙ የዕለት እንጀራ አጥቶ እየተቸገር ለብዙ ዓመት የሚያጠራቅመውን ለዛውም በእውነት እና በሀቅ ባልሆነ መንገድ ሲሞትም ደስታ እና ሀሴት ይጠብቀው” እያልን እንዳልሆነ አምናለሁ። ይልቁንስ እያልን ያለነው “የኃጢአት ዘመኑን የሚመጥን ቅጣት ይጠብቀው ነው።” ፍትሐዊ አባባል ነው።



የመጀመሪያው ጌታችን ወደ ቅፍርናሆም እና ቤተሳይዳ እያመለከተ ፥ ፍቅሩ እና የማዳን ሥራው እንደ ጊዮን ውሃ የፈሰሰላቸው እነዚህ ከተሞች ነገር ግን ጌታቸውን ያገለሉ እና ችላ ያሉ በፍርድ ቀን ከጢሮስ፣ ከሰዶም እና ከገሞራ ይልቅ የበለጠ ፍርድ እንደሚጠብቃቸው ነገሮናል። (ማቴ 10፥15፣ ማቴ 11፥22)። ምክንያቱም ሰዶም እና ገሞራ ለሰሩት ኃጢአት ፍርድን ወዲያው በምድር ላይ ተቀብለዋልና፣ በዘላለም ፍርድ ፍትሐዊው ፈራጃችን ያን እንደሚያስብላቸው ነገሮናል። በዚህም የቅጣት ፍርዱ ለሁሉም እኩል እንዳልሆነ አሳወቀን። ያነሰ ፍርድ የሚቀበሉ እንዳሉ ነግሮናል። የዘላለም የገሀነምን እሳት እንዳለ በቅጣት የሚቀበሉም እንዳሉ እንዲሁ። ከእነሱም ዋነኞቹ የመዳን ወንጌሉ ተሰብኮላቸው ፥ የፍቅሩ ተዓምር ተደርጎላቸው ያገለሉት ትልቁን ፍርድ እንደሚቀበሉ ነው የነገረን። ስለዚህ ፍርዱ በሚዛን እንደሚሆን ገልጦልናል። ያ ሚዛን ግን የእሱ ስለሆነ አሁን ላይ ምን እንደሚመስል ከዚህ በጠለቀ ሁኔታ አልተገለጸልንም። ይሄም ለእኛ ስለማይጠቅመን እንደሆነ አምናለሁ። ግን ትልቁን ጥያቄ መልሶልናል። ያም የቅጣቱ ፍርዱ እንደሚለያይ። እዚህ ጋር አንድ ማስመር የምፈልገው ጌታችን ከብሉይ ኪዳን በአሉታዊ መንገድ የጠቀሳት ብቸኛዋ ሴትን ነው። እሷም የሎጥ ሚስት ናት።(ሉቃ 17፥32)። ጌታችን ወደ ሐዋርያት ዞሮ የሎጥን ሚስት አስቧት ብሏቸዋል። ያቺ ከታላቁ የእምነት አባት አብርሃም ዘር የመቆጠርን ዕድል ያገኘችው፣ መላዕክት እጇን ይዘው የእሳትን ባህር የሚያሿግራት የሎጥ ሚስት። በመጨረሻም ፊትለፊቷ ካለው የጽድቅ ተራራ ይልቅ የሰዶም ውበት ትዝታ የሳባት እና ወደኋላ የዞረችው የሎጥ ሚስት። ይህችን ሴት ጌታ በተለየ ሁኔታ እንድናስባት አሳስቦናል። ጌታችን ይሄን ለሐዋርያት ነው የተናገረው። በዛ የፍርድ ቀን ለእናንተ ይብስባችኋል ሲል።



ሁለተኛው ጥያቄ የዘላለም ቅጣት ጉዳይ ነው። በዚህ ምድር ያለ የፍትሕ ፍርድ ቤት እንዴት እንደሚፈርድ ጠይቃችሁ ታውቃላችሁ? ለምሳሌ አንድ ሰው ተናዶ ወደ ቤቱ ሲመጣ ሚስቱ እና ልጆቹ የበለጠ ቢያናዱት እና በዛ የአንድ ደቂቃ ደም ፍላት ምክንያት ሽጉጡን አውጥቶ ሚስቱን እና ልጆቹን ቢገድል ፥ ይሄ ሰውዬ የሚጠብቀው ፍርድ ምን እንደሆነ አስባችኋል? ፍርድ ቤቱ የአንድ ደቂቃ የደም ፍላት ችግር ነው ብሎ እድሜ ልክ ከመፍረድ የሚቆጠብ ይመስላችኋል? የአንድ ደቂቃ ስህተት መሆኑ ለዛ ወንጀል የሚገባውን የእድሜ ልክ ፍርድ ከማሰጠት ያድነዋል? ብዙ ወንጀሎችስ በእውነት ቅጣታቸው ወንጀሉ ከተደረገበት የእድሜ ዘመን በላይ እንደሆነ አስባችሁ አታውቁምን? እነዚህ ቅጣቶች መቼ የፍትሕ ጥያቄ ይነሳባችኋል? ከወንጀል ድርጊቱስ በላይ የምንቀጣው የሰውዬውን የመግደል ፍላጎት እና የአዕምሮ ሁኔታ አይደለምን? ለመግደል ያነሳሳውን ፍላጎት እና ሁኔታ አይደለም ታሳቢ የምናደርገው? ለዛስ አይደለ ሰው የገደለ ሁሉ እኩል ቅጣት የማይከተልበት? ለምሳሌ በጦርነት ያለ ወታደር ምንም ሰው ቢገድል፤ ከአሸናፊው ወገን በመጨረሻ ከሆነ እንደ ገዳይ ሳይሆን እንደ ጀግና እና መልካም ሰው የምናየው የምንቀጣው ተግባሮችን ሳይሆን በዋነኝነት እነዛ ተግባሮች የቆሙበትን ፍላጎት፣ የማህበረሰብ ቀጣይ አኗኗር እና የሌሎች ሰዎችን ባህሪ እና መጠበቅ ታሳቢ በማድረግ አይደለምን? ይሄ የሚያሳየን ቅጣት ወንጀለኛው ለሠራው ክፋት ብቻ ሳይሆን፣ ሌላውንስ ከመውደድ፣ ማለትም በወንጀለኛው ክፋት የተጎዱትን እና የሚጎዱትን በማሰብም ጭምር እንደሆነ እንዴት እንዘነጋለን?



እግዚአብሔር ፍቅር ነው ብለን፣ ሁሉን ያለፍርድ የሚያልፍ፣ በፍቅሩ ታምነው ቃሉን ለጠበቁት ብቻ ሳይሆን፣ ሁሉንም በእርሱ እቅፍ የሚሰበስብ ከሆነ ... አምላካችን ስለዘላለማዊ ቅጣት የተናገረውን የእውነት ቃል አምነው፣ የዚህ ምድርን ጊዜያው ጥቅም እንደጉዳት የወሰዱ ሰዎችን ወዴት እናድርጋቸው? መከራን ስለመንግስቱ ሲሉ የተቀበሉትን ፥ መከራቸውስ ስለከንቱ ነውን?



ሰነፉን ተማሪ እና እንቅልፍ አጥቶ ያጠናውን ተማሪ ስለፍቅር ብሎ እኩል የሚሸልም እና የሚያሳልፍ መምህር ከሁሉ በላይ የጎዳው ፍቅርን አይደለምን? ምክንያቱም ፍቅሩን ከምር የወሰደው ተማሪ ሲጎዳ ፥ እርሱን ያላመነው ግን አላማመኑ እውነት እንደነበረ በውስጡ የተጠራጠረው ልክ አልነበረምን? የትኛውስ ፍቅር ያለፍትሕ ይቆማል? የትኛውስ ፍቅር ያለእምነት (እውነት) ይጸናል?



ብዙ የሚያጠራጥር ነገር በሞላበት ዓለም ውስጥ እየኖሩ፣ ለብዙ ጥያቄዎቻቸው መልስ ሳያገኙ፣ እሱን ግን አምነው ቃሉን የጠበቁት በከንቱ ነበርን? በእነሱ ላይ ያሾፉት እና በደካማው እና ምስኪኑ ላይ ፍርድን ያዛቡት፣ “የእናንተ እግዚአብሔር ቢኖር ይሄ ሁሉ ይፈጸማልን?” እያሉ ከደካማው ነጥቀው የሞላውን ጎተራቸውን የጠቀጠቁትን ፥ “እኔ ፍቅር ነኝ” በሚል ብቻ በመንግስቱ ስለእርሱ ሁሉን እያጡ መከራ ከተቀበሉት ጋር ከደመራቸው ፥ በዚህ ፍርድ አሸናፊው ማነው? ከእግዚአብሔርም ሆነ ከጻድቃን በላይ የዚህ የፍጻሜ ፍርድ አሸናፊዎች የክፋት ሰዎች አይደሉምን?



ቅዱስ ጳውሎስ “እግዚአብሔር አይዘበትበትም፣ ሰው ሁሉ የዘራውን ያጭዳል” ያለው ውሸቱን ነበርን?። (ገላ 6፥8)። ይሄንንስ አምነው መልካም ዘር የዘሩት፣ እግዚአብሔር ላይ ያልዘበቱት፣ ክርስቶስ በፍጻሜ ፍርዱ የዘላለም እሳት አለ ያልኳቹ “ውሸቴን ነው ወይም ትቼዋለሁ፣ እኔ ፍቅር ሆኜ ሳለ ሰውን በገሀነም እሳት እንደኃጢአቱ መጠን ላቃጥል አይገባኝም፤ ስለዚህ ሁላቹሁ የአባቴ ወገን ናችሁና ኑ” ቢል፤ እነዚህ ስለእርሱ ሁሉን ያጡት ስለፍቅሩ ምን ይሰማቸው? ይሄ ፍቅርስ ከእነሱ ይልቅ ለኃጢአተኞች አይደለምንም? ሰነፍ ተማሪዎች መውደቃቸውን አይቶ፤ የጎበዞቹን ልፋት እንደምንም ሳይቆጥር ፈተናው ተሰርዟል ሁላችሁም አልፋችኋል የሚል መምህር፣ ከሁሉም በላይ ፍትሕ የማያውቅ፣ ፍቅሩ ለሰነፎች ያደላ አይደለምን? ፍቅሩስ ለሁሉ ቢሆን መጀመሪያ ያን ለሁሉ አይነግርምን? ይሄ አድሎ ደግሞ በእግዚአብሔር ሲሆን የበለጠ እንደሆነ እንዴት ይጠፋናል፤ ምክንያቱም መምህሩ አስቀድሞ ያን ያላለው ይሄን ያህል ተማሪ እንደሚወድቅ ስለማያውቅ ነው ብለን ልንምረው እንችላለን፤ አላዋቂነቱን አስበን፤ እግዚአብሔር ግን ሁሉን እያወቀ፣ ፍጻሜውን እያወቀ፣ አስቀድሞ ያን ከተናገረ ውሸት ተናግሯል ማለት ነው፤ ለማታለል፣ ሙሉ ለሙሉ ሰዎች ክፍዎች እንዳይሆኑ ሕጻን ልጅን በከረሜላ እንደሚደልሉት፣ የእሱን ፍቅር ያመኑትን ደልሏል ማለት ነው!?



ይሄ ከእኛ ይራቅ። እርሱ በባህሪው ንጹሁ ነው። ውሸት ከእርሱ ጋር ፈጽሞ ሕብረት የለውም። ለቃሉም ተማኝ ነው። አዳምን ያን ፍሬ ከበላክ ትሞታለህ ብሎታል፤ በዚህም አራራለትም። ሞትን ለዘላለም አስጎነጨው እንጂ። የእጁ ሥራ ቢሆን እንኳ፤ እርሱ ለቃሉ ታማኝ ስለነበረ፣ ከገነት አባረረው። ወደ ሞት ዓለም ጣለው። ሊምረው ሲያዝንለት እንኳ ቃሉን ሳይሽረው አደረገው። ምህረቱ ፍርዱን አላሸነፈውም። ፍርዱም ምህረቱን አላጠፋውም። የትኛውም ኃጢአት ያለቅጣት እንደማያልፍ ነገረን እንጂ። በገሀነም የማይቀጣ ኃጢአት ካለ፣ ያ ኃጢአት በመስቀሉ በቀራንዮ ተቸንክሯል ማለት ነው። “የሞት ሞት ትሞታለህ ቃሌን የሻርክ ቀን” ላለው ቃሉ አንድያ ልጁን ኃጢአት አደረገው። (2ኛ ቆሮ 5፥21)። በዚህም በክርስቶስ ኢየሱስ የማይምኑት ሁሉ፣ ከልጁ ሞት ጋር አልተባበሩም እና የኃጢአት ደሞዝን ይቀበላሉ። በእርሱ ጭካኔ ግን አይደለም፣ በወላጆቻቸውም በደል አይደለም፣ በራሳቸው ኃጢአት እንጂ። እርሱማ አዳምን ለዘላለም ሞት ቢጥለው ያ ጭካኔው ሳይሆን ቃሉ እና ፍርዱ ነበር። አትብላ ብሎታል። በላ። ስለዚህ ሞተ። ማንም ባያድነን የሚከሰው የለም። ግዴታ የለበትም እና። ቃሉ እና ሕጉን ነው የፈጸመው። ነገር ግን እንዲሁ ወዶናልና፣ የእጆቹን ውብ ሥራ ለሞት ይተወው ዘንድ ፍቅሩ እና ክብሩ አልፈቀደሉትም። ቃሉን ይሽር ዘንድ ደግሞ እርሱ አይለዋወጥም። ስለዚህ ያን ሞት እርሱ ተሸከመ።



ቀንበሩ ከባድ የሆነን እቃ አጎንብሰን፣ ዝቅ ብለን ትከሻችን ላይ እንደምንጭነው፣ ከዛም ቀና ብለን፣ አሁን በትከሻችን ላይ ያለውን ያ መሬት ተቀምጦ የነበረውን ከራሳችን ጋር እንደምናነሳው፤ በቃሉ ሸክም መሬት የወደቀውን ለማንሳት ዝቅ አለ፣ በትከሻው ላይ በአባቱ ፈቃድ አኖረው፣ ከራሱ ጋር ያን መሬት የወደቀውን ይዞት ተነሳ። እርሱ ወዳለበት ቦታም ወሰደው። ፍርዱን ሳይሽር ፍቅር መሆኑን ገለጠልን። ራሱን ከወደቅነው በታች አድርጎ፣ በፍቅር ትከሻው ይዞን ተነሣ። በዚህም ፍቅሩ ካለ ፍርዱ ሙሉ እንደማይሆን በኛ በሰዎች የዕለት ሕይወት ውስጥ የተገለጠውን እውነት የበለጠ አሳየን።


 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Oct 14, 2024
  • 6 min read

ree


“የሃማስ አባል የሆነ ሁሉ ሞት ዒላማ አድርጎታል” ይሄን ያለው የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቢቢ ናታኔሁ ነው። በእስራኤሎች ላይ ባለፈው ቅዳሜ መስከረም ፳፯ ቀን በሃማስ የተፈጸመው ግፍ አረመኔያዊ ነው። ምንም ጥያቄ የለውም። ይሄን ሰብአዊነት የሚሰማው ሁሉ አምርሮ ማውገዝ አለበት። ጥያቄው ግን እንዴት ነው ሀዘናችንን የምንገልጸው የሚል ነው? ማለትም በሞተው የሰው ቁጥር ብዛት ነው ወይስ በአገዳደሉ ዓይነት ነው ወይስ ለሞት በዳረጋቸው ምክንያት ወይስ ገዳዮቹ የተነሱበትን ዓላማ በመፈተሽ ወይስ በራሳችን የአይዶሎጂ እና የማንነት ትስስር (ክርስቲያን እና ሙስሊም መሆናችንን ለማለት ነው)? ምንድነው ከፍልስጤማውያን የሚሞቱ ልጆች በላይ ለእስራኤሎች ሕጻናት ወይም ከእስራኤላውያን ሲቪሊያን በላይ ለፍልስጤማውያን ሲቪሊያን ለማዘን የዳረገን? ምንድነው የሰብአዊነትን እና የታሪክ እንዲሁም የመብት ጥሰት መከራከሪያ ጽንሰሀሳቦችን አስቀድሞ ፍርድ ለሰጠው ስሜታችን መደገፊያ አድርገን እንድናቀርብ ያደረገን? ምንድነው ለያዝነው አቋም መሰረት?


ለዚህ የሚኖረን መልስ ብዙ ሊሆን ይችላል። ትልቁ ግን ዝምድናችን ነው። ይሄ ዝምድና ያልኩት ምን እንደሆነ ከማስረዳቴ በፊት የጹሁፌን ጭብጥ ልናገር። ከላይ ያነሳውትን ጥያቄ የጠየኩት ለእስራኤሎች ወይም ለፍልስጤማውያን የምትከራከሩ ሰዎች ምን ያህል ምክንያታዊ እንዳልሆናችሁ ለማሳየት አይደለም። የኔ ፍላጎት ይሄን ጦርነት እንዴት ሰዎች እየተረጎሙት እንደሆነ እና ለሞቱት ሰዎች ያሳዩት ሐዘን ፥ የእስራኤል መንግስትም ሆነ ሀማስ የወሰዱት አጸፋ ምን ያህል ስለእኛ ሀገር ሁኔታ የበለጠ እንድገነዘብ ያደርገኛል የሚል ነው።


ይሄን ስለእስራኤላውያን አይደለም የምለው። ወይም ስለፍልስጤማውያንም አይደለም። ስለእኛ እና እየተካሄደ ካለው ጦርነት ጋር የአይዶሎጂ ወይም የሌሎች ተዛማጅ ግንኙነት ስላለን ሰዎች እንጂ። የፈረንሳይ የሕግ እና የታሪክ ሊቅ ፈርናንድ ብሮዴል በአንድ ወቅት እንዳለው “ወደ እንግሊዝ ሀገር ለአንድ ዓመት ሄደ ብትኖር፣ በዛ አንድ ዓመት ውስጥ ስለእንግሊዝ ማወቅ አትችልም። ነገር ግን ወደ ሀገርኽ ስትመለስ ከመልመድኽ የተነሳ የተሰወረብኽ ነገር ግልጥ ሆኖ ይታይሃል። በአዲስ ጮራ በልምድህ የተሰወረብህ ይገለጥልሃል” ይላል። በሌላ አነጋገር የሌሎችን ነገር የምታጠናው የበለጠ ስለራስሕ ለማወቅ ነው ማለት ነው። ያንተ ቆዳ በሌለበት ጦርነት (skin in the game) ውስጥ በዜና እና በንባብ (intellectually) ያገኘኸው ነገር ያን ጦርነት ወይም ሀገር ያሳወቀኸ ከመሰለህ ከትዕቢት ውጪ ያተረፍከው ምንም የለም። አንድን ነገር በእውቀት ማወቅ እና በዛ ውስጥ ራስኽ ማለፍ ምን ያህል ልዩነት እንዳለው ለማወቅ መከራ የገጠማቸውን ሰዎች ለማጽናናት ያነጎድከው ዲስኩር በአንተ መከራ ወቅት ከሸንበቆ የቀጠነ ደካማ ምርኩዝ እንደነበረ ማስታወስ ብቻ ይበቃኸል። ያ ዲስኩር ሊያጽናናኽ ይቅርና ተመሳሳይ ነገር ሊነግሩኽ እና ሊያጽናኑ የሚፈልጉትን እንኳ እንዴት እንደምትጠየፋቸው ታውቃለኸ። ቲኤስ ኤሊኦት እንዳለው “ስለሌሎች ለማወቅ መባዘናችንን ማቆም የለብንም። ነገር ግን የዚህ የማወቅ አሰሳ መጨረሻው መነሻችን ጋር መድረስ መሆን አለበት። የአሰሳው ፍጻሜ መነሻችንን ለመጀመሪያ ጊዜ አጥርተን ለማወቅ ነው።”

አሁን የድጋፎቻችን መሠረት ስለሆነው ዝምድና ለመናገር ልመለስ። የስጋ ዘመዱን በሞት የተነጠቀ ሰው ሀዘኑን በማሰብ ወይም በምክንያት እንዲያደርግ መጠየቅ ተገቢ ነው ብዬ አላምንም። እናቱ የሞተችበትን ሰው ፥ “ይሄ ሁሉ ሕጻን በግፍ በሚገደልበት ሀገር ምን ይሄን ያህል ለእናትህ ያስለቅሰሃል” ማለት ፥ ስለሀዘን የመረዳት አቅማችን ምን ያህል ደካም እንደሆነ ብቻ ነው የሚገልጸው። ሕይወት እንኳ በአልአዛር ሞት ለሞት እንባን አፍሷል። ስለዚህ የቅርብ ወገኑን የተነጠቀ ሰው እንዲያመዛዝን መጠበቅ ጅልነት ብቻ ነው።


ለምን?


ጅልነት የሚሆነው ማመዛዘንን ስለጠበቅንበት አይደለም። ይልቁንስ አንዱ ከአንዱ ጋር ተሳስሮ የሚኖረው ፥ እርስ በእርሳችን በፈጠርነው የዝምድና ገመድ እንጂ ፥ የሰው ልጅ የሰው ልጅን ሁሉ መውደድ አለበት በሚል ፍልስፍናዊ ትርክት ስላልሆነ ነው። ለወገንህ ያለህ ፍቅር እና ያ ፍቅርህ በሚወልደው ኃላፊነት ብቻ ነው ለሌላው የሚተርፍ ሰብአዊነት በውስጥኽ የሚያቆጠቁጠው።

ከዚህ ውጪ ለሀገርህ እና ለወገንሕ የተሻለ ነገር ለመመኘት እና ያን ወደ ድርጊት ለውጠኽ ስትንቀሳቀስ ለምን ስለራስኽ ብቻ ታስባለኽ፣ ለሌላውም መቆም አለብህ፤ ካለዛ ግን ዘረኛ ነህ ብሎ የሚከስኽ ፥ አንተ ለራስህ ወገን ያደረከውን ለዛ ሰው ወገን የራስህን ትተኽ ብታደርግለት ግን በዘረኝነት እና በጨካኝነት አይከስህም። ለምን? ምክንያቱም ከመጀመሪያው ያን ክስ ያቀረበብኽ እሱም ለራሱ ወገን የበለጠ ሳስቶ እንጂ አንተን ከከሰህ ለዝምድና ከማድላት ሰብአዊነት ተላቆ አይደለም።


ይልቁንስ እንዳልኩት እናቱ የሞተችበት ሰው ብዙ ሕጻናት ስለሚሞቱ እናቱን በማጣቱ የመረረ ሀዘኑን ከመግለጽ ከተቆጠበ የዛኔ ማህበረሰብ አደጋ ውስጥ ይገባል። ሰው ከሰውነት ጎራ ይወጣል። ኃላፊነት ላለመውሰድ እና ከተጠያቂነት ለማምለጥ በር ያገኛል። ለጭካኔያችን ጠንካራ አመክንዮ ይኖረናል። ምን እያልኩኝ ነው? እያልኩኝ ያለውት “ሕይወት እንዴት እንደሚሰራ እንወቅ ፥ ሕይወት እንዲህ እንዲሰራ የፈቀደው ለምክንያት ነውና” ነው። ማለትም ሺዎች በሚራቡበት ሀገር ውስጥ “ለዚህ አጠገቤ ላለው ሰው የዕለት እንጀራውን ብችልለት ምን አመጣለሁ” የሚል ሰው ጭካኔን እና አረመኔነትን በምክንያት የሚተክል ነው። ልክ ነው። በሀገሪቷ የተንሰራፋውን ድህነት እና ችጋር ጎረቤቱ ያለውን ድኋ በመርዳት የሚቀርፈው አይደለም። ይሄ ድህነትን ስታስቲክስ ፥ ረሀብን ዴታ (ቁጥር) ስናደርገው ነው። የሰው ልጅ ቁጥር ሲሆን ፥ በዚህ ምድር የከፋው አረመኔ ነገር የሚከሰተው የዛኔ ነው። ከባህር ማዕበል የሚተፋቸውን በመቶዎች ከሚቆጠሩ አሣዎች መካከል በእግሩ ሥር የወደቁትን በማንሣት መልሶ ወደ ባህር ለመመለስ እና ለማትረፍ የሚጥር ሰው ፥ በአንድ የኔቢጤ እንዲይ ይባላል “አብደኸል፣ ምን ሊረባኽ ነው የምትደክመው? ተመልከት ማዕበሉ ከቁጥር የሚልቁትን ነው እየተፋ ያለው አንተ ደግሞ በጣት የሚቆጠሩትን ነው ለመመለስ የምትጥረው። ምን ለውጥ አመጣ ብለህ ይለዋል? ያ ሰው ግን ወደ እጁ ወዳለው አሣ እያመለከተው “የማደርገው ነገር ለዚህ አሣ ትርጉም አለው” አለው።


የእስራኤል መንግስት ኃላፊነት ለእስራኤሎች ነው። የሀማስም ፍቅር ከፍልስጤማውያን ጋር ነው። ጠንካራ የኔ የምትለው መንግስት ሲኖርህ የእያንዳንዱ ዜጋ ሕይወት ዋጋ ይኖረዋል። መንግስትህ አንተ ሞተ ዝም እንደማይል ስታውቅ ፥ ያን መንግስት የኔ ፥ ሀገሪቷን ደግሞ እንደእናት ትቀበላታለህ።

ከዚህ ውጪ ግን ለዝምድናህ ባሳየኸው ቅናት እና በወገንህ ላይ በደረሰ ጥቃት የምታነሳውን በትር ፥ ሊያሸማቅቅህ የሚሞክር ሁሉ አይዶሎጂ ነው። ይሄ አይዶሎጂ እንዴት በሀገራችን እንደተተገበረ ላሳይ።


ኢትዮጵያው ውስጥ ባለፉት አምስት ዓመታት የሞቱት አማሮች በአይዶሎጂ ጭካኔ ታውረን ቁጥር ነበር ያደረግናቸው። ቁጥሮች ነበሩ በኢትዮጵያ ስም ለተደራጁ የፖለቲካ ኃይሎች እነዛ ምስኪን አማሮች። ለመንግስትም ቁጥሮች ነበሩ ምክንያቱም ዙፋኑ የሚጸናለት የአማራ መንግስት እንዳልሆነ ለብሔር ብሔረሰቦች ሲነግራቸው ነው። ኢትዮጵያ ማለት ሀማስ መንግስት የሆነባት ሀገር ማለት ናት። ሀማስ ክፉ ነው ደግ ነው የሚል ግልብ ድምዳሜ ላይ መድረስ አልፈልግም። የፖለቲካ እምነቱ ግን እስራኤል የምትባል ሀገር በዛ አካባቢ መኖር የለባትም የሚል ነው። ይሄ ብቻ ግን አይደለም እስራኤሎች በዘመናት ሂደት ውስጥ ታሪካዊ ሀገራችን ባሉት ቦታ ሀገራቸውን አጽንተው ለማቆየት ብዙ ግፉ ፈጽመዋል። ይሄ ደግሞ ለሀማስ የፖለቲካ አቋም ፥ ሕዝብ የማሰባሰቢያ እና ግፍ የመፈጸሚያ ጥሩ ቤንዚል ሆነለት። ሀማስ ከተፈጠረበት መነጽር ውጪ እስራኤልን ማየት ይከብደዋል። ከአይዶሎጂው በሚነሳ የማጥፋት ተግባሩ የእስራኤልን መንግስት ግፍ ዘወትር ይጋብዛል። ይሄ ማንም ለወገኑ ከሚሰማው የተቆርቋሪነት ስሜት የሚመነጭ እልህ ነው። ማለትም አንድ ኃይል በተመሳሳይ ጊዜ ግፈኛ እና ተጠቂ ይሆናል። ተጠቂ እና ግፈኛም እንደዚሁ። ይሄን ወደ ፍጹም ፍትሐዊ ወደ ሆነ ሚዛን አምጥቶ ሁሉም በሰላም የሚኖርበት ሀገር መፍጠር አይቻልም። ግን ወደ አንጻራዊ ፍትሕ ማስጠጋት ይቻላል። ያ የሚሆነው ግን ፍልስጤማውያንም የሚጮህላቸውን እና መጠቃታቸው የሚያበሳጨው ኃይል ራሳቸው ሲፈጥሩ ብቻ እንጂ ፥ ከእስራኤልም ሆነ የፖለቲካ ኃይልን እያየ ከሚፈርድ ዓለም አይደለም።

በተመሳሳይ ማንነቴን አማራ በሚባል ብሔር ተነጥቄያለው፣ ግፍ እና መከራም ይሄ ብሔር አድርሶብኛል ብሎ በሚያምን ድፍን የኢትዮጵያ ብሔር ባለበት ውስጥ ፥ በገፍ የሚገደለው አማራ ከሌላው ፍትህ እና መቆርቆርን አገኛለው ብሎ ካሰበ ፖለቲካን አለመረዳት ብቻ አይደልም ፥ የሰው ልጅ እንዴት እንደሚያዝን እና እንደሚቆረቆር፣ ከሀዘን የሚፈልቀው ለተገፉት የመቆም ስነልቦና እንዴት እንደሚሰራ አለመገንዘብም ነው።


ለእናትህ ሞት ላለማዘን በሌሎች ላይ የምታየው ሰቆቃ መጽናኛ ከሆነኽ ፥ ለሌሎችም የሚሆን ሀዘኔታን እንዳጣ ተረዳው። ለራስህ እና ለወገንህ ያለህ ፍቅር ብቻ ነው ለሌሎች ርሕራሔ እንዳለህ የሚነግረኝ። ያንተ የምትላቸውን ላለማስደፈር የምታደርገው ጥረት ነው ፥ ሌሎች ለራሳቸው ወገን ያላቸውን ስነልቦናዊ ትስስር እንድትገነዘብ የሚያደርግህ። ለዚህም ነው መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትዕዛዙ ራሱ “ባልንጀራህን ውደድ” የሚለው ፥ ሰውን ውደድ ከማለት ይልቅ። ጎረቤትህን ስትወድ ብቻ ነው ፥ የሰውን ልጅ መውደድ የምትጀምረው። ዓለሙን ሁሉ እንድንረዳ አልተጠራንም። ዓለምን በችግር መዓበል እያናወጠ ፥ ባልጀራህ ላይ ዓይንህን እንድታደርግ የታዘዝከው የፍቅርኽ ትከሻ መሸከም የሚችለውን ቀንበር ስለሚያውቀው ነው። ይሄ የፍቅር ክንድን አሰራር የተረዳው ሙሴ ነው ግብጻዊውን በክርኑ ጉልበት ገድሎ የዕብራዊውን ስቃይ ያስታገሰው።


 “ሀገሪቷ እንዳትፈርስ” በማለት ዛሬ እስራኤልን በፍልስጤም ላይ እንድትዘምት ካደረጉ ብዙ እጥፍ በላይ የሚሆኑ አማሮች ሲገደሉ አፋቸውን የሚለጉሙ ፥ “ፖለቲካ ማለት” በማለት በሐዘን ቤት መጥተው ዲስኩር የሚያሰሙ ሰዎች ፥ ኢትዮጵያን ከመውደድ የሚናገሩ አይደሉም። የአንተ ሞት እና ስቃይን የመረዳት አቅም ስለሌላቸው እና ያንተ ሞት ከቁጥር እንዳይሻገር ለዝምድና የመቆም እና የመቆርቆር፣ ከዛ የሚመነጭ ፖለቲካን ማራመድ ባለመቻልህ ነው። የእኔ እናት ለሌላው እንደማንም ሴት አንዲት ሴት ናት። ለእኔ ነው እናትነቷ። ያን ባለማፈር በመግለጽ፣ እናቴ ይገባታል ብዬ ለማምነው መብት እና ክብር መቆም ያለብኝ እኔ ነኝ። ይሄን የተለየ ስሜት እኔ መግለጽ ካልቻልኩኝ ግን ዘፋኟ እንዳለችው “እናቱን የማይወድ ሰው ሰው ነው አልለውም አውሬ ነኝ ባይ ነኝ።” ሌላውን ራሱ የመውደድ አቅም እንደሌለኝ ይናገራል።


 እነዚህ ሰዎች የአማራን ሞት እንደራሳቸው ባይሰማቸው ለእኔ የፍልስጤማውያን እና የእስራኤላውያን ሞት ከቁጥር በላይ ሰላም እንዳነሳኝ እነሱንም እረዳቸዋለሁ። ነገር ግን ለኢትዮጵያ ብለን ነው ብለው ሀዘኔን አሳንሰው የእነሱን ጭካኔ እና የሰዎችን የሀዘን ስብራት በተራ የፖለቲካ ዲስኩር ሊያጣጥሉት ሲሞክሩ ግን ይሄን ድራማ ከዚህ በፊት አይተነዋል ማለት ያስፈልጋል። ይሄን ድራማ አሌክሳንደር ሶልዦኒስተን በሦስት ተከታታይ ቅጽ መጽሐፉ ጽፎልናል። ያ ድራም ሁሉም ጋር አንድ ጭብጥ (theme) አለው። አይዶሎጂ ነው። ሶልዦኒስተን እንዳለው አይዶሎጂ መጀመሪያ ከሰብአዊነት ያወጣኽ እና ዓለም አቀፋዊ ያደርግሃል። ከዛ እግዚአብሔርን ያስረሳኸል።


አይዶሎጂ ፦ የፖለቲካ እና የማህበረሰብ አስተዳደር የጭካኔ ፍልስፍናችንን በእኛ እና በሰዎች ፊት ደግነት ያስመሰለ፣ ነውረኝነታችንን ለሀገር የተከፈለ፣ ለለውጥ ሲባል ለማህበረሰብ የተሰጠ ቸርነት ያስመሰለ ነው አይዶሎጂ። አይዶሎጂ ክርፋት ብልግናችን ውግዘት ሳይሆን ጭብጨባ እና አድናቆት ያላበሰው ነው። አይዶሎጂ ሕዝብ ሲቀነስ መደመር ነው ያለን፣ ረሀብ ሲገርፈን መበልጸግ ነው ያለን፣ የምስኪኖች ቤት ሲፈርስ ከተማ ማስዋብ ነው ያለን ነው። ወንድምን አለመውደድን፣ ለቤተሰብ እና ለወገንህ አለመቆምን፣ ፍቅር የሞተበት ልብህን ዓለማቀፋዊ ወዛደርነት፣ ለጭቁን ብሔሮች የቆመ፣ አርቆ አሳቢ በማለት ሊፒስቲክ ይቀባዋለ።


ይሄን ሂፖክራሲ “የዓለም ጭቁን ሰራተኞች፣ የዓለም ጭቁን ሕዝብ፣ የዓለም ጭቁን ብሔር” በማለት ለአውሬነት ስብዕናችን ፍልስፍና ሰጥተን ሁሉን ድኋ፣ ሁሉን አሽከር፣ ሁሉን ጭሰኛ በመጨረሻ ያደረገውን ፍልስፍናዊ ድራማ አይተነዋል። በአይዶሎጂ ተሸብበኽ ለሚሞተው ወገንሕ መታገል ካልቻልክ ፥ አንተን ነክቶ ሌላው በሰላም መኖር እንደማይችል ካላሰየኸ የሰው ልጅ ስነልቦና አልገባንም ማለት ነው።


ይሄ ማለት ግን የኔ ፍትህ በሌሎች ውረደት እና ስቃይ ይከበር እያልኩኝ አይደለም። “ለእኔ እና ለወገኔ መብት እና ክብር የማልታገል ከሆነ ለማንም የመቆም አቅም የለኝም” እያልኩኝ እንጂ። ለባልጀራው ቁራሽ እንጀራ ላለመስጠት የሰው ልጆችን ረሀብ እንደምክንያት የሚያነሳ ሁሉ ፥ ለማንም የሚሆን ፍቅር በውስጡ እንዳይበቅል የፈቀደ ነው። አስመሳይ እና ውሸታም ነው። ያንተ ለሆኑት ኃላፊነት አለብህ። ሰውነትን እንጂ አምላክነትን ከኛ አይጠብቅም ፥ አይፈልግምም። በቁጥር፣ በማነጻጸር፣ በመደመር በመቀነስ እንድናስብ አልተጠራንም። እንደዛም አናስብም። እንደዛ እንድናስብ የሚነግረን ሁሉ ሀዘናችንን የመካፈል አቅም የሌለው ብቻ ነው። ይልቁንስ እኔ እና ቤቴ ብለን ስለራሳችን ኃላፊነት እንድንወስድ እና የወገናችን መሞት እረፍት እንዲነሳን ነው የተጠራነው። በሞት ፊት ሕይወት እንባውን ካፈሰሰ ፥ የወገኑ ሞት ቁጥር የሆነበት ሁሉ በውስጡ ሕይወት የሌለው ነው።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Oct 13, 2024
  • 3 min read

ree



የየቀን ትግሌ ይሄ ነው። ተዋጊ መሆን። በርግጥ የእንግሊዘኛው ቃል ነው የሚገልጽልኝ። Survivor መሆን። victimhood እኔ ጋር የለም። ሌሎች ላይ ከሆነው የባሰ ነገር በእኔ ምንም ሆኖ አያውቅም። ግን በሕይወቴ እጅ ለመስጠት እና ለማማረር ከበቂ በላይ የሆነ ነገር ውስጥ አልፌያለሁ። ከልጅነት እስከ እውቀት። ግን ሁልጊዜ survivor ነኝ።



በእኔ ውስጥ እንዲሰለጥን የማልፈልገው አስተሳሰብ አለ። እጅ መስጠት። ተበዳይ መሆን። ተፈጥሮ በድላኛለች፣ አምላክ ትቶኛል ብሎ ማሰብ። በእኔ ይሄ አስተሳሰብ ቤቱን ሰርቶ አያውቅም። የሆነውን ለመቀበል ነው የምቸኩለው። በሆነው ውስጥ የተሻለውን እና ማግኘት የምችለውን ነገር ለማግኘት ነው የምሰራው። ልቤ አንበሳ እንዲሆን ነው የማደርገው። አላውቀውም ፥ አልችለውም ብዬ አልቀመጥም። ዛሬ ባላውቀው፣ ዛሬ ባይኖረኝ፣ ዛሬ ባልችለው ነገ ግን እንደሚለውጥ እና ያንንም እንደምለውጥ አምናለሁ። እንደዛ ዓይነት ታሪኮች እንጂ የመበደል እና ሌሎችን ሰይጣን አድርጎ የመሳል ታሪክ እና ትርክት እኔ ጋር ብዙ ቦታ እንዲኖረው አልፈቅድም። በእኔ ላይ የተፈጠሩ ብዙ ነገሮችን የምቆጣጠረው ላይሆን ይችላል። ነገር ግን ከሁኔታዎች በታች ራሴን ለማድረግ ፈቅጄ አላውቅም። ዊል ስሚዝ እንዳለው “በትሬድ ሚል ላይ መሞት ከሆነም ለመሞት ዝግጁ ነኝ ፥ ግን አላቋርጥም።” እርዳታ ቢስ እና ተስፋ የሌለኝ ሆኜ ለመታየት አልፈቅድም። ለራሴ ሌላ ትርክት ነግረዋለሁ እንጂ። ሰዎች ወደ እኔ መጥተው “ልጅ ሆኜ አባቴ እንዲህ ስላረገኝ ነው፣ እናት አባቴ እንዲህ ስላረጉኝ ነው፣ ልጅ ስለሆንኩኝ ነው፣ ወይም አስተዳደጌ ይሄ ስለሆነ ነው” ሲሉኝ ፥ እነዚህ ሰዎች ከዚህ በፊት በእነሱ ላይ ለተከሰተ ነገር ምን ያህል ራሳቸውን ባሪያ አድርገው እንደሰጡ ነው የማየው። አሁን ያ የሚሉት ስቃይ እና ማነቆ ባይኖር እንኳ ፥ አዲስ ማንነት ፈጥሮ ፥ አዲስ ማንነት ሰርቶ ከዛ ለመውጣት ፈቃደኞች አይደሉም። ነገር ግን የትላንት ባሪዮች ሲሆኑ ሳይ አዝናለሁ። ዛሬን እና ነገን ለትላንት ማስገበር።



የሰው ልጅ ልዩ ባህሪው ፈጣሪ መሆኑ ነው። የመፍጠር ችሎታችን ነው ከሌሎች ሁሉ የለየን። የማንፈጥር ካልሆንን ፥ የጎደለ ስብዕና ነው ያለን። መፍጠር የሚጀምረው ደግሞ ራስን ለዛሬ እና ለነገ በድጋሚ በሚስማማ መልኩ በመፍጠር ነው። ልክ ነው ብዙ መከራ ደርሶብን ይሆናል፤ ግን ዓይናቸውን፣ ጆሮአቸውን፣ እንደውም ተጨማሪ አካላቸውን አጥተው እኛ ፈጽሞ በሕይወት ዘመናችን ሁሉ ሰርተን የማናውቀውን ነገር የሚሰሩ እና ያሳኩ ፥ ዓለምን ጉድ ያሰኙ ሰዎች አልገጠሟችሁም?



በሕይወታቸው ላይ በደረሰ አንድ ሁለት ሦስት ክስተቶች ምክንያት ሙሉ ሕይወታቸውን አሳልፈው የሚሰጡ ሰዎችን ተመልከቱ። እነዚህ ሰዎች እነዚህን አጋጣሚዎች ወደ ዕድል ለመለወጥ አለመቻላቸው አስገራሚ ነው። በእኔ ላይ በራሴ ጥፋትም ሆነ ያለ እኔ በደል የደረሱብኝን ክፉ አጋጣሚዎች ሁሉ አፈቅራቸዋለሁ። እነዚህ ራሴን በጥልቀት እንዳውቅ እና ነጥሬ በአዲስ ማንነት እንድነሳ ያደረጉኝ ናቸው። ራሴን በድጋሚ የፈጠርኩባቸው ክስተቶች ናቸው። ያለእነሱ እኔ አይደለሁም።



ከ100% በታች ኃላፊነት በሕይወት የሚወስዱ ሰዎች፣ ለደስታቸውም ሆነ ለሐዘናቸው እነሱ ብቻ ተጠያቂ እንዳልሆኑ የሚገልጹ፣ መቆጣጠር ስለማይችሉት፣ መለወጥ ስለማይችሉት ነገር በማሰብ ጊዜያቸውን የሚያጠፉ፣ ወደ ፊት መሄድ ሳይሆን ከጊዜ ማዕበል ጋር መጋፋት የሚወዱ ቪክተሞች አሉ። አሉ ደግሞ እሱ ነው፣ እሷ ናት፣ እከሌ ነው፣ ሚስቴ ናት፤ እርሱ በሕይወቴ እስኪመጣ ድረስ ሰላማዊ ነበርኩኝ፤ እከሌ እስኪቀላቀለን ድረስ ሀሴት ነበር ሕይወታችን የሚሉ ፥ የሚደፈድፉበት ነገር የሚመስጣቸው፤ ክርስቶስን ሰቃዮች ፥ በበጉ ደም መፍሰስ እነርሱ የሰሩት ኃጢአት እንዲደመሰስ የሚሹ ፥ ከሳሾች አሉ። አሉ ደግሞ በሕይወታቸው የተፈጠረውን ነገር ከሥሩ ከመፍታት ይልቅ ፥ ትንሽ በማልቀስ፣ ትንሽ በመተንፈስ፣ ትንሽ በማማረር ወይም ችግራቸውን የሚረሱበት ከNetflix እስከ ሲጋራ በመሳብ ለጊዜው እፎይ ማለት ብቻ የሚመርጡ ቪክተሞች። በጣም የሚገርመው እነዚህ ቪክተሞች ሁሌ ልክ ናቸው። ሌላው እና ሌሎች እንጂ እነርሱ ሁልጊዜ ልክ ናቸው። ስለዚህ ለውድቀታቸው ከሳሾች ናቸው። ቪክተሞች መሆናችሁን ለማወቅ ቀላሉ መንገድ የተቀየማችሁት ሰው እንዳለ እና እንደሌለ መጠየቅ ነው። ካለ የቪክተም አስተሳሰብ ተጠቂዎች ናችሁ። ይቅር ማለት የማይችል ልብ ያለው ሰው ፥ መፍጠር አይችልም። ሁሉን ነገር ሲሪየስሊ መውሰድ የሚቀናው ሰው ፥ አዕምሮ የመፍጠር ችሎታውን የተነፈገ ነው። ምክንያቱም በራሱ ላይ በተፈጠረው ነገር መሳቅ የማይችል ሰው የመማር አቅሙን አጥቷል።



ማማረር እና ማሳበብ ልጆች ከወላጆቻቸው የሚማሩት ነው። እንደ እኛ ሀገር ባለ ፖለቲካ ደግሞ ማማረር የአጭር ጊዜ እንጀራ ነው። ቪክተም መሆን ለጥቂቶች የስልጣን ኮርቻ ነው። ትውልድ ግን ይሞታል። የትውልድ አዕምሮ በሙሉ ከጥቅም ውጪ ይሆናል። ትላንት ኦሮሞ ነበር። ዛሬ ደግሞ አማራ ሆኗል ይሄን የቪክተም ስነልቦና የሚጋተው። እስቲ አንድ የተሳካለት፣ ሕይወቱ ያማረለት፣ በፈጠራ ችሎታው እና በአገልግሎቱ አንቱ የተባለ ግን የቪክተም አስተሳሰብ የሚያራምድ አንድ ሰው ጥቀሱልኝ? አንድ ማምጣት አትችሉም። አንድ!!!



ለምን? መልሱ ግልጽ ነው። ቪክተም ስነልቦና መጀመሪያ የሚያደርገው የመፍጠር ችሎታችን መንፈግ ነው። 100% ስለሕይወቱ ኃላፊነት የማይወስድ ሰው መፍጠር አይችልም። ጥርጣሬ የሌለው ሰው፣ ሕይወትን ከሌሎች መነጽር አንጻር ለማየት የማይችል ሰው፣ ሌሎችን ይቅር ለማለት የማይፈቅድ ሰው ፥ አንቱ ሊባል አይችልም።



አዎ፦ በየቀኑ ተዋጊ ነኝ። ከሕይወት ጋሪ ጋር ወደ ፊት በመሮጥ የምተባበር፤ የኋላዬን እየረሳው ወደፊት የሚጠብቀኝን ለማየት እና ለመያዝ የምዘረጋ ነኝ። Survivor ነኝ። የደረሰብኝ ሁሉ ከትምህርት የዘለለ ትርጉም የለውም። በሕይወቴ መጨረሻ “የተሰጠኝን አበዛውት፣ በብዙ እጥፍ አድርጌም ለሰጪው ሰጠውት” ለማለት የምዘረጋ እንጂ የምጎተት አይደለውም።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page