top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Nov 24, 2024
  • 3 min read



ree

“ማርታ ግን አገልግሎት ስለ በዛባት ባከነች፤ ቀርባም። ጌታ ሆይ፥ እኔ እንድሠራ እኅቴ ብቻዬን ስትተወኝ አይገድህምን? እንኪያስ እንድታግዘኝ ንገራት አለችው።


 ኢየሱስም መልሶ። ማርታ፥ ማርታ፥ በብዙ ነገር ትጨነቂአለሽ ትታወኪማለሽ፥


 የሚያስፈልገው ግን ጥቂት ወይም አንድ ነገር ነው፤ ማርያምም መልካም ዕድልን መርጣለች ከእርስዋም አይወሰድባትም አላት።” ሉቃ 10፥41፡42።



ይሄን ታሪክ ሳነብ ትዝ የሚለኝ ሴኒካ ለሉሲለስ ወዳጁ የጻፈለት ደብዳቤ ነው። እንዲህ ይለዋል “ሉሲለስ ሆይ ካንተ የሚወሰድብህ ነገር ሁሉ ያንተ አይደለም። ያንተ ባልሆነ ነገር መደገፍን አሶግድ።” ጌታችን ለማርታ “ማርያም የማይወሰድባትን መረጠች” ይላታል። መንገድ ላይ ቆመው የሚለምኑ ሰዎችን ሳይ በእኔ አዕምሮ ስለተወሰደባቸው ሀብት እና ክብር ሳይሆን የሚያስበው፤ ስላልተወሰደባቸው ድፍረት ነው። ኑሮን የመቀጠል ድፍረት። በሕይወት የመኖር እና የመቀጠል ጀግንነት።



በያንዳንዱ ቀን ያለኝ ብርታት ሰዎች ከኔ ሊወስዱብኝ የማይችሉት ነገርን ገንዘብ ባደረኩኝ መጠን ነው። ከአምላኳ እግር ሥር ቁጭ ብሎ ማረፍን ማንም ከማርያም የሚወስድባት አይኖርም። ለዛች ነፍስ የክብር ቦታ፣ VIP ወይም ፊትለፊት ላይሰጣት ይችላል። ታላቅ አስተዳዳሪ፣ ታላቅ ሰባኪ ወይም ታላቅ ምናምን ብለው ላይጠሯት ይችላሉ። ግን ከክርስቶስ እግር ሥር ቁጭ ብሎ ፍጹም መደሰትን ማንም አይነጥቃትም።



ከሁለት ዓመት በፊት ውድ ፍራሽ ለጥሩ እንቅልፍ እንዲሆን ገዛው። ግን በሚገርም ሁኔታ ፍራሹን የገዛው ቀን ምንም እንቅልፍ ሊወስደኝ አልቻለም ነበር። በጠዋት ዳውን ታወን ወዳለው ቢሮዬ ልገባ ስል ከሕንጻው ሥር፤ ሰዎች በፍጥነት በሚራመዱበት ሥፍራ አንዱ አስገራሚ እንቅልፍ ተኝቷል። ውድ ፍራሽ አልነበረውም እንቅልፍ ግን ነበረው። ለአምስት ደቂቃ የሚሆን ጊዜ ቆሜ አየውት። የአስር ሺር ዶላር አልጋ ሊኖርህ ይችላል፤ እንቅልፍ ከሌለህ ግን ትርጉም የለውም። ያን እንቅልፍ ፍራሽ እምብዛም አይሰጥህም። ቅዱስ ጳውሎስ እና ሲላስ በእስር ቤት ሆነው በፍጹም ደስታ ይዘምሩ ነበር። በዓለም ላይ ተፈተው ያሉ ሰዎች ግን ያ ደስታ አልነበራቸውም። ጳውሎስ እና ሲላስን በእግረ ብረት ሆኖ መታሰር ያን ደስታ ሊቀማቸው አልቻለም። የማይቀሙን ነገር አለን?



ሰዎች የማይወስዱብን ነገሮች አሉን?


 ትረምፕም ሆነ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ የማይቀሙን ነገሮች ይኖሩን ይሆን? እኔ ስለሃይማኖት ወይም በዛ ውስጥ ያሉ ሰዎች ስለሚገባቸው ነገሮች ብቻ እየተናገርኩኝ አይደለም። በጣም ብዙ ድንቅ ሰዎችን በሕይወት ተገናኝቻለው። ማንም የማይወስድባቸው ደግነት፣ መረጋጋት፣ ትህትና፣ እውቀት፣ ማስተዋል፣ ጥበብ፣ ስክነት ያላቸው ሰዎች። መክሰርም ሆነ ማግኘት ምንም ያልነቀነቃቸውን ሰዎች አይቻለው። አንዳንዶቹ ምንም ሃይማኖት የሌላቸው ነበሩ። እነዚህ ማንም የማይቀማቸው ውበት የነበራቸው ሰዎች ነበሩ።



ማርታ ጌታን ለማስደስት በጓዷ ትተጋ ነበር። የጌታ መደሰት በማርታ እጅ ላይ የነበረ አልነበረም። በርሷ ቁጥጥር ውስጥ አልነበረም። እርሷ ግን ብዙ ለፋች። ብዙ ተጨነቀች። ማርያም ደግሞ ነፍሷን አደመጠች። ያ ውብ ጌታ እግር ሥር መቀመጠ እርሷን እንደሚያስደስታት ገባት። ስለዚህ አደረገችው። የእርሷ ደስታ ግን በእጇ ነበር። ጌታ ስለመደሰቱ ሳይሆን የእርሷ ነፍስ ስለማረፏ አሰበች። ያን ራስን ማወቅ ከእርሷ ማን ይወስድባታል?



 ሊዮ ቶልስቶይ ስለመደሰት ሲናገር በጣም ቀላል መርህ ነው ያለው። “መደሰት ትፈልጋለህ?” “እንግዲያው ደስተኛ ሁን!” ብቻ ነው የሚለው። ብዙዎቻችን መደሰት ብንፈልግም ደስተኛ የሚያደርገንን ነገሮች ግን አይደለም የምንሰራው። ይልቁንስ ክብር፣ ቦታ፣ ዝና፣ ኢጎ፣ አዋቂ መስሎ መታየት፣ ከቡድን የመነጠል ፍርሃት፣ እንደ ማርታ ሰው ምን ይለኛል የሚል ጭንቀት እና ሌሎች ስሜቶች ነው የሚያስተዳድሩን። የሚቀሙን ነገሮችን ብቻ ነው የምንሰበስበው። ክብር እንደ ጥላችን ነው። አንዳንዴ ከኛ በላይ ትልቅ ነው። አንዳንዴ ከኛ በጣም የሚያንስ ነው። ምክንያቱም የኛ አይደለም።



 የማርታ ሃብቶች ሊወሰዱብን የሚችሉ ናቸው። አያስፈልጉም ሳይሆን ብዙ መትጋት ያለብን ግን የማርያም ሃብቶች እንዲበዙልን ነው። የማርያም ሃብት ያለው ሰው የማርታ ሃብትን በሂደት ገንዘቡ ማድረግ ይችላል። የማርታ ሃብት ያለው ሁሉ ግን የማርያም ሃብት አለው ማለት አይደለም። በማንኛውም እና በየትኛውም ቦታ ብንሆን ቀና ብለን የምንሄድበት ጥበብ አለን? በሁሉም ስፍራ አሸናፊ የሚያደርገን ማንም የማይነጥቀን ሰውነት አለን? ያ በማዕበል እና በወጀብ መኃል ቀና እንዳልን የሚያስኬደን ውሳጣዊ ሃብቶች አሉን? የማርያም ሃብቶች።



መስቀል የበዛባቸውን ሰዎች አላያችሁም? ግን ከፊታቸው ይሄ ሕይወት ውብ ነው የሚል ደስታ የማታጡባቸው! ሲመሽ ደስ የሚላቸው ሲነጋም ፀሐይዋን በድጋሚ አወጣት ብለው የሚደሰቱ ሰዎች። ሉሲለስ ሆይ ካንተ የሚወሰድብህ ሁሉ ያንተ አይደለም። አንዳንድ ሰዎች አልገጠሟችሁም? “ወፈርኩኝ አይደል?” ብለው ጠይቀዋችኹ፤ “አዎ” ስትሏቸው የሚያኮርፏችሁ? በሕግ ትምህርት ቤት እያለሁ፤ አንድ ከእንግሊዝ የመጣች ተማሪ ነበረች። ፊቷ በርበሬ መስሎ አንድ ቀን እኔ የማጠናበት ክፍል ከጓደኞቿ ጋር መጣች። “ፊትሽ ምን ሆኖ ነው?” ስላት (እንግዳ ስለሆነብኝ ነበር)፤ አበደችብኝ። ጓደኞቿም “ያን መጠየቅ አልነበረብህም” አሉኝ። ምን አልባት ልክ ናቸው። ግን ተመልከቱ ምን ያህል insecure እንደሆነች! በሽበት፣ በቁመት፣ በእርጅና እና በሌሎች ጉዳዮች እንዲህ የሚሰማን ሰዎች ሞልተናል። የማርታ ሃብቶች ብቻ ያሉን። ማርያም ግን የማይቀሟትን መረጠች።



ሊወዱን ሊጠሉን፣ ለጊዜው ሊያከብሩን ወይም ሊሰድቡን ይችላሉ። ይሄን ሁሉ እንደ ኢምንት ቆጥረን ፥ ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድኅን እንዳለው በዚህ የሙገሳ እና የስድብ ውርጅብኝ ውስጥ ዝም የምንል ምን ያህሎቻችን ነን? የማይቀሙን የውስጥ ጽናት ያለን? የመንፈስ ቅስማችን የማይወሰድብን ምን ያህሎቻችን ነን? የማይቀሙንን እንያዝ። የማይወስዱብንን ገንዘብ እናድርግ። “ሉሲለስ ሆይ ካንተ የሚወሰድብህ ነገር ሁሉ ያንተ አይደለም።”

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Nov 17, 2024
  • 2 min read

ree

 

ሙያተኛ ስትሆኑ ሰዎች በእናንተ ላይ ሊደገፉ ይፈልጋሉ። የመጨረሻውን ውሳኔ እናንተ እንድትሰጡላቸው ይመኛሉ። ግንበእውቀት እና በልምድ ከፍ ስትሉ እርግጠኝነት የእውቀት እና የልምድ እጥረት ውጤት መሆኑን ታውቃላችሁ። ስለዚህ ያን የበለጠ ታሶግዳላችሁ። ከእናንተ በእውቀት የሚያንሱ ሰዎች ያን እርግጠኝነት ሲያጡ ፥ ከእውቀት እና ልምድ ጋር ያያይዙታል። ስለዚህ ለአጭበርባሪዎች ወይም ላነሰ እውቀት ላላቸው ይሰጣሉ።

 

ወደ ጌታችን የፍጻሜ ዘመን ስብከት ሂዱ። ከሁሉ አዋቂ አባቱ ዘንድ የመጣው ልጅ ፥ ስለፍጻሜው ዘመን ምልክት እንጂ እርግጠኝነት በርሱ ቃላት ውስጥ አልነበረም። ያ በእውቀት ማነስ የመጣ ግን አልነበረም በእውቀት መብዛት እንጂ።ከርሱ እውቀት ጋር የማይነጻጸሩት የሐዋርያትን የፍጻሜ ዘመን ስብከት ደግሞ ተመልከቱ ፥ “ጌታ አሁን ይመጣል” ነበር ያሉን። ምንአልባትም በእነርሱ የእድሜ ዘመን ወይም ከእነርሱ በጥቂት ዘመን ተሻግሮ ክርስቶስ እንደሚመጣ ይሰብኩ ነበር። ያም እርግጠኝነት በተሞላበት መልኩ ነበር። ያ ግን አልሆነም። ከሦስት ሺ ዘመን በኋላም ያን ክስተት እየጠበቅን ነው። በሌላም ዘርፍ እርግጠኝነት አንድን ነገር በጥልቀት የመረዳት እጥረት ነው።

 

ሪስክ የሚወስዱ ሰዎች ናቸው በብዛት የሚያተርፉት። በተመሳሳይ ሪስክ የሚወስዱ ሰዎች ናቸው የሚከስሩት። አሉታዊያን በሕይወት ላይ ብዙ ጊዜ ልክ ናቸው። አዎንታዊያን ግን በሕይወት ደስተኛ ናቸው። ምክንያቱም እነሱ የማይቻል የነበረውን የሚቀይሩ ናቸውና። እርግጠኝነትን መፈለግ የውሳኔ ሽባነትን ያመጣል። ሕይወት ልንሞክራት፣ የማይቻል የሚመስለውን ነገር ፈራ ተባ እያልን ልንገፋው የተሰጠን ስጦታ ናት። ይሄ ሕይወት አንድ ብቸኛ ዕድላችን ናት። አንድ ብቸኛ ዕድል ከዚህ በፊት የነበሩ ሰዎች ባስቀመጡልን ሥሪት ብቻ በመመራት ማለቅ የለበትም። ትንሽ ድንበሮችን መግፋት፣ ትንሽ የተገነቡ ነገሮችን አፍርሶ በተሻለ ለማቆም የምንጥርበትም መሆን አለበት። ለዛ ደግሞ ከእርግጠኝነት ይልቅ የመሆን ዕድልን (probability) ነው ማጤን ያለብን። የመሆን ዕድሉ ከፍ ያለን ነገር እርግጠኛ ስላልሆንን ብቻ ማቆም የበጎ ለውጥ መቅሰፍት ነው።

 

አንገት የሚያጎነብሱ ሰዎችን ሳይሆን አንገትን ቀና የሚያደርጉ ትውልዶችን ስለማፍራት ነው ማሰብ ያለብን። በሆነ መጠን በእውቀት እና በድፍረት እንቢ የሚሉ ሰዎች ብቻ ናቸው ድንበር የሚሻገሩ፣ አይቻልም የሚባሉ ተግባሮችን አስችለው ያሳዩን። እነዚህ ሰዎች እርግጠኝነት ደባሪ የሆነባቸው እና መሞከር የሚያረካቸው ናቸው።

 

ስለሚመጣው ነገር በርግጠኝነት የምናውቅ ቢሆን፤ ሕይወታችን ከሕይወት የተላቀቀ ይሆን ነበር። መደነቅ እና ደስታ የጎደለው፣ መደንገጥ እና መረበሽ የራቀው ፥ መሳቅ እና መቦረቅ የሸሸው ይሆን ነበር። አለማወቅ ነው ተራራ ጫፍ የወሰደን። አለማወቅ ነው ያስወደደን ያስከዳን። እርግጠኝነትን የሚሰጠን ሁሉ ከእውነትም ከሕይወትም የተጣላ ነው። ወይም የኛን ደካማ ጎን ለጥቅሙ የሚያውል ነው። በዚህ ዓለም ላይ ሞት ሳይቀር እርግጠኛ እንዳልሆነ ፥ ሔኖክ እንዳልሞተ መጽሐፍ ቅዱስ ሲነግረን እናያለን። እንደ ብራየን ጆንሰን ያሉ ሰዎች የሞትን እርግጠኝነት እየተጋፉ ነው። ምን አልባት ይሳካላቸው ይሆናል፤ ግን ይሄ ድንበርን መግፋት ነው የሰው እውነተኛ ተፈጥሮ። ማመጽ የሰው ልጅ ተፈጥሮ ነው። የሚጠቅመው ቢሆን እንኳ የሆነን ነገር በአታድርግ ትዕዛዝ መቀበል እንደማይፈልግ የመጀመሪያው ሰው አሳይቷል።

 

ውሳኔ ስንወስን የማይታወቅ ሪስክ ካለው ልምድ እና እውቀት ላይ እንደገፍ፤ የሚታወቅ ሪስክ ከሆነ ደግሞ የመሆን ዕድል (probability) እና አመክንዮ ላይ እንመርኮዝ። እንጂ ከእርግጠኝነት ወዳጅ አንሁን።

 

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Nov 10, 2024
  • 2 min read


ree


ለምንድነው የሶቅራጦስ “ያልተመዘነ ሕይወት እንዳልተኖረ ይቆጠራል ወይም the unexamined life is not worth living” አባባል ከሶስት ሺ ዘመናት በላይ ትርጉም ለሰው ልጅ ውሳጣዊ ልቦና የሰጠው?


ግን ብዙዎቻችን ይሄን አባባል ምን ማለት እንደሆነ አናውቀውም ወይም ልምምዱ የለንም። በሕግ ትምህርት ቤት እያለው ሁለት ሦስት ፕሮፌሰሮቼ ስለዚህ አባባል በተደጋጋሚ ሲነግሩኝ ግራ ይገባኝ ነበር። ሪፍሌክሽን። “ሪፍሌክት አድርግ” ሲሉኝ። እንዴት አድርጌ ነው ሪፍሌክት የማደርገው? ምንድነው እነዚህ ሰዎች እያሉኝ ያሉት? የምን ሪፍሌክሽን?



ሪፍሌክሽን ሳይሆን ዶግማ፣ መመራመር ሳይሆን ማመን፣ መጠየቅ ሳይሆን መታዘዝ፣ ለምን ማለት ሳይሆን እሺ ማለት፣ ፍለጋ ሳይሆን መረጋጋት የማህበረሰቡ እሴት ከሆነበት ሀገር ለፈለቀ ሰው ሪፍሌክሽን እንግዳ ነገር ነው። በዛ ወቅት ከሃይማኖት ልቦናዬ በጣም የራኩበት ዘመን ቢሆንም የአስተሳሰብ መዋቅሬ ግን ሁሌም ሃይማኖተኛ ነበር። ስለዚህ እነዚህ ሰዎች ስለእኔ ሪፍሌክት ቢያደርጉልኝ ራሱ እመርጥ ነበር።



የሰው ልጅ አዕምሮ በተቀረጸበት ማህበረሰብ መነጽር ነው የሚያየው። ከዚህ የዕይታ ግርዶሽ ተሻግሮ ማየት ለሰው እጅግ ፈተኝ ነው። የመኖር እና የመመሳሰል፣ ማህበረሰብ የሚያስቀምጠውን ደረጃ የመያዝ ፍላጎት ፥ ከእንስሳዊ ባህሪው ጋር ማለትም ከሞት ራስን የመከላከል ፍላጎት ጋር ተጣምሮ መጠየቅን ይፈራል። የራሱን አዕምሮ ጭምር ይፈራዋል። የተጠየቅ ቀስቶች ሲወረውርበት በእምነት ማህተም ይመክተዋል። ስለዚህ ሪፍሌክሽን እንዲርቀው ያደርጋል።



ያልተመዘነ ሕይወት እንዳልተኖረ ይቆጠራል ያለው፣ በመጠየቅ አቅሙ የማንንም የእምነት እና ያልተፈተነ ሰንፋፋ የእውቀት ዝናር በቀላሉ የሚያራግፈው ሶቅራጦስ ሳይቀር በዚዎስ ያምን ነበር። ዛሬ ማንም ስላለመኖሩ የማይጠራጠረው ዚዎስ ከሞት በኋላ ለእውነት በመቆሙ እንደሚሸልመው ያምን ነበር። ይሄ በቀላሉ የሚነግረን ሰው ምን ያህል የቆመበትን የፍልስፍና መሠረቶች የመጠየቅ አቅሙ ደካማ እንደሆነ ነው።



ሪፍሌክሽን ከራሳችን እውነተኛ ተፈጥሮ ጋር ለመገናኘት የድልድዩ ጅማሬ ነው። ሩጫን፣ እምነን፣ ግን፣ ዓላማን፣ ተግባን፣ ቃን ከዛም ራን የመጠየቅ እና በጥልቅ የመፈተሽ ከዛም የመታዘብ ልምምድ ነው ሪፍሌክሽን። ብሌዝ ፓስካል እንዳለው “የሰው ልጅ ችግር ሁሉ የሚነሳው ብቻውን በአንድ ክፍል ውስጥ ለመቀመጥ ካለመቻል ነው።” ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድኅን ለዚህ ነው “እንዳይነግርህ አንዳች እውነት አናፋበት ፥ ሸልልበት፤ ሆይ፡ሆይ! በል ጩኽበት፤ ጭንቅላትክን ግዘፍበት ፥ ውቀጥበት ፥ ውገርበት፤ ዝግ ብሎማ ያስብ እንደሁ ፥ ይነግርሃል አንዳች እውነት!” ያለው።



የሰው ልጅ አዕምሮ እንደ እውነት የሚፈራው ነገር የለውም። አዕምሮውን ካሳረፈው ያን እውነት እንደሚደርስበት ስለሚያውቅ፤ በዶግማ፣ በሽምደዳ፣ በመደዴ ትንታኔ፣ በአይዶሎጂ ይሞላዋል። ምክንያቱም ዝግ ካደረገው ያጋፍጠዋል። ያጋፍጠዋል ከባከነው ዕድሉ ጋር፣ ያጋፍጠዋል ከከንቱ እና ከውሸት እምነቱ ጋር። ካልተኖረው የአስመሳይነት መርሁ ጋር። ስለዚህ ያን ከመጋፈጥ ፥ በላይ በላይ ይግተዋል ይሄን መረጃ። ጭንቅላቱን ይገዝፍበታል። አዕምሮውን ከማህበራዊ ሚዲያ እስከ ዜና በሚገኝ ብጣሽ እና ቅራቅንቦ ይሞላዋል። በዚህም ሕይወትን እንደሸሻት ፥ የራሱን ሕይወት ሳይኖር ይሞታል። ለዚህ ነው ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድኅን “እስቲ ለአንድ አፍታ እንኳ ዝም እንበል። አጉል ነው ብለን ሳንፈረድ፣ ድንቅም ነው ብለን ፈጥነን ሳንወድ፣ መንጋነትን አርቀን እስቲ ዝም እንበል። ብቻ ይሄን አለማድረግ ነው ሞት” ይለናል። ዳግመኛ ሞት መሞት ፥ የአዲስ ኪዳን ጨለማ ማለት ይሄ ነው። ራስን ለመፈተሽ ፥ ተረጋግቶ ለማሰብ ፥ ከዛም ለመታዘብ አለመፍቀድ።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page