top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Nov 17, 2024
  • 2 min read


 

ሙያተኛ ስትሆኑ ሰዎች በእናንተ ላይ ሊደገፉ ይፈልጋሉ። የመጨረሻውን ውሳኔ እናንተ እንድትሰጡላቸው ይመኛሉ። ግንበእውቀት እና በልምድ ከፍ ስትሉ እርግጠኝነት የእውቀት እና የልምድ እጥረት ውጤት መሆኑን ታውቃላችሁ። ስለዚህ ያን የበለጠ ታሶግዳላችሁ። ከእናንተ በእውቀት የሚያንሱ ሰዎች ያን እርግጠኝነት ሲያጡ ፥ ከእውቀት እና ልምድ ጋር ያያይዙታል። ስለዚህ ለአጭበርባሪዎች ወይም ላነሰ እውቀት ላላቸው ይሰጣሉ።

 

ወደ ጌታችን የፍጻሜ ዘመን ስብከት ሂዱ። ከሁሉ አዋቂ አባቱ ዘንድ የመጣው ልጅ ፥ ስለፍጻሜው ዘመን ምልክት እንጂ እርግጠኝነት በርሱ ቃላት ውስጥ አልነበረም። ያ በእውቀት ማነስ የመጣ ግን አልነበረም በእውቀት መብዛት እንጂ።ከርሱ እውቀት ጋር የማይነጻጸሩት የሐዋርያትን የፍጻሜ ዘመን ስብከት ደግሞ ተመልከቱ ፥ “ጌታ አሁን ይመጣል” ነበር ያሉን። ምንአልባትም በእነርሱ የእድሜ ዘመን ወይም ከእነርሱ በጥቂት ዘመን ተሻግሮ ክርስቶስ እንደሚመጣ ይሰብኩ ነበር። ያም እርግጠኝነት በተሞላበት መልኩ ነበር። ያ ግን አልሆነም። ከሦስት ሺ ዘመን በኋላም ያን ክስተት እየጠበቅን ነው። በሌላም ዘርፍ እርግጠኝነት አንድን ነገር በጥልቀት የመረዳት እጥረት ነው።

 

ሪስክ የሚወስዱ ሰዎች ናቸው በብዛት የሚያተርፉት። በተመሳሳይ ሪስክ የሚወስዱ ሰዎች ናቸው የሚከስሩት። አሉታዊያን በሕይወት ላይ ብዙ ጊዜ ልክ ናቸው። አዎንታዊያን ግን በሕይወት ደስተኛ ናቸው። ምክንያቱም እነሱ የማይቻል የነበረውን የሚቀይሩ ናቸውና። እርግጠኝነትን መፈለግ የውሳኔ ሽባነትን ያመጣል። ሕይወት ልንሞክራት፣ የማይቻል የሚመስለውን ነገር ፈራ ተባ እያልን ልንገፋው የተሰጠን ስጦታ ናት። ይሄ ሕይወት አንድ ብቸኛ ዕድላችን ናት። አንድ ብቸኛ ዕድል ከዚህ በፊት የነበሩ ሰዎች ባስቀመጡልን ሥሪት ብቻ በመመራት ማለቅ የለበትም። ትንሽ ድንበሮችን መግፋት፣ ትንሽ የተገነቡ ነገሮችን አፍርሶ በተሻለ ለማቆም የምንጥርበትም መሆን አለበት። ለዛ ደግሞ ከእርግጠኝነት ይልቅ የመሆን ዕድልን (probability) ነው ማጤን ያለብን። የመሆን ዕድሉ ከፍ ያለን ነገር እርግጠኛ ስላልሆንን ብቻ ማቆም የበጎ ለውጥ መቅሰፍት ነው።

 

አንገት የሚያጎነብሱ ሰዎችን ሳይሆን አንገትን ቀና የሚያደርጉ ትውልዶችን ስለማፍራት ነው ማሰብ ያለብን። በሆነ መጠን በእውቀት እና በድፍረት እንቢ የሚሉ ሰዎች ብቻ ናቸው ድንበር የሚሻገሩ፣ አይቻልም የሚባሉ ተግባሮችን አስችለው ያሳዩን። እነዚህ ሰዎች እርግጠኝነት ደባሪ የሆነባቸው እና መሞከር የሚያረካቸው ናቸው።

 

ስለሚመጣው ነገር በርግጠኝነት የምናውቅ ቢሆን፤ ሕይወታችን ከሕይወት የተላቀቀ ይሆን ነበር። መደነቅ እና ደስታ የጎደለው፣ መደንገጥ እና መረበሽ የራቀው ፥ መሳቅ እና መቦረቅ የሸሸው ይሆን ነበር። አለማወቅ ነው ተራራ ጫፍ የወሰደን። አለማወቅ ነው ያስወደደን ያስከዳን። እርግጠኝነትን የሚሰጠን ሁሉ ከእውነትም ከሕይወትም የተጣላ ነው። ወይም የኛን ደካማ ጎን ለጥቅሙ የሚያውል ነው። በዚህ ዓለም ላይ ሞት ሳይቀር እርግጠኛ እንዳልሆነ ፥ ሔኖክ እንዳልሞተ መጽሐፍ ቅዱስ ሲነግረን እናያለን። እንደ ብራየን ጆንሰን ያሉ ሰዎች የሞትን እርግጠኝነት እየተጋፉ ነው። ምን አልባት ይሳካላቸው ይሆናል፤ ግን ይሄ ድንበርን መግፋት ነው የሰው እውነተኛ ተፈጥሮ። ማመጽ የሰው ልጅ ተፈጥሮ ነው። የሚጠቅመው ቢሆን እንኳ የሆነን ነገር በአታድርግ ትዕዛዝ መቀበል እንደማይፈልግ የመጀመሪያው ሰው አሳይቷል።

 

ውሳኔ ስንወስን የማይታወቅ ሪስክ ካለው ልምድ እና እውቀት ላይ እንደገፍ፤ የሚታወቅ ሪስክ ከሆነ ደግሞ የመሆን ዕድል (probability) እና አመክንዮ ላይ እንመርኮዝ። እንጂ ከእርግጠኝነት ወዳጅ አንሁን።

 

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Nov 10, 2024
  • 2 min read




ለምንድነው የሶቅራጦስ “ያልተመዘነ ሕይወት እንዳልተኖረ ይቆጠራል ወይም the unexamined life is not worth living” አባባል ከሶስት ሺ ዘመናት በላይ ትርጉም ለሰው ልጅ ውሳጣዊ ልቦና የሰጠው?


ግን ብዙዎቻችን ይሄን አባባል ምን ማለት እንደሆነ አናውቀውም ወይም ልምምዱ የለንም። በሕግ ትምህርት ቤት እያለው ሁለት ሦስት ፕሮፌሰሮቼ ስለዚህ አባባል በተደጋጋሚ ሲነግሩኝ ግራ ይገባኝ ነበር። ሪፍሌክሽን። “ሪፍሌክት አድርግ” ሲሉኝ። እንዴት አድርጌ ነው ሪፍሌክት የማደርገው? ምንድነው እነዚህ ሰዎች እያሉኝ ያሉት? የምን ሪፍሌክሽን?



ሪፍሌክሽን ሳይሆን ዶግማ፣ መመራመር ሳይሆን ማመን፣ መጠየቅ ሳይሆን መታዘዝ፣ ለምን ማለት ሳይሆን እሺ ማለት፣ ፍለጋ ሳይሆን መረጋጋት የማህበረሰቡ እሴት ከሆነበት ሀገር ለፈለቀ ሰው ሪፍሌክሽን እንግዳ ነገር ነው። በዛ ወቅት ከሃይማኖት ልቦናዬ በጣም የራኩበት ዘመን ቢሆንም የአስተሳሰብ መዋቅሬ ግን ሁሌም ሃይማኖተኛ ነበር። ስለዚህ እነዚህ ሰዎች ስለእኔ ሪፍሌክት ቢያደርጉልኝ ራሱ እመርጥ ነበር።



የሰው ልጅ አዕምሮ በተቀረጸበት ማህበረሰብ መነጽር ነው የሚያየው። ከዚህ የዕይታ ግርዶሽ ተሻግሮ ማየት ለሰው እጅግ ፈተኝ ነው። የመኖር እና የመመሳሰል፣ ማህበረሰብ የሚያስቀምጠውን ደረጃ የመያዝ ፍላጎት ፥ ከእንስሳዊ ባህሪው ጋር ማለትም ከሞት ራስን የመከላከል ፍላጎት ጋር ተጣምሮ መጠየቅን ይፈራል። የራሱን አዕምሮ ጭምር ይፈራዋል። የተጠየቅ ቀስቶች ሲወረውርበት በእምነት ማህተም ይመክተዋል። ስለዚህ ሪፍሌክሽን እንዲርቀው ያደርጋል።



ያልተመዘነ ሕይወት እንዳልተኖረ ይቆጠራል ያለው፣ በመጠየቅ አቅሙ የማንንም የእምነት እና ያልተፈተነ ሰንፋፋ የእውቀት ዝናር በቀላሉ የሚያራግፈው ሶቅራጦስ ሳይቀር በዚዎስ ያምን ነበር። ዛሬ ማንም ስላለመኖሩ የማይጠራጠረው ዚዎስ ከሞት በኋላ ለእውነት በመቆሙ እንደሚሸልመው ያምን ነበር። ይሄ በቀላሉ የሚነግረን ሰው ምን ያህል የቆመበትን የፍልስፍና መሠረቶች የመጠየቅ አቅሙ ደካማ እንደሆነ ነው።



ሪፍሌክሽን ከራሳችን እውነተኛ ተፈጥሮ ጋር ለመገናኘት የድልድዩ ጅማሬ ነው። ሩጫን፣ እምነን፣ ግን፣ ዓላማን፣ ተግባን፣ ቃን ከዛም ራን የመጠየቅ እና በጥልቅ የመፈተሽ ከዛም የመታዘብ ልምምድ ነው ሪፍሌክሽን። ብሌዝ ፓስካል እንዳለው “የሰው ልጅ ችግር ሁሉ የሚነሳው ብቻውን በአንድ ክፍል ውስጥ ለመቀመጥ ካለመቻል ነው።” ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድኅን ለዚህ ነው “እንዳይነግርህ አንዳች እውነት አናፋበት ፥ ሸልልበት፤ ሆይ፡ሆይ! በል ጩኽበት፤ ጭንቅላትክን ግዘፍበት ፥ ውቀጥበት ፥ ውገርበት፤ ዝግ ብሎማ ያስብ እንደሁ ፥ ይነግርሃል አንዳች እውነት!” ያለው።



የሰው ልጅ አዕምሮ እንደ እውነት የሚፈራው ነገር የለውም። አዕምሮውን ካሳረፈው ያን እውነት እንደሚደርስበት ስለሚያውቅ፤ በዶግማ፣ በሽምደዳ፣ በመደዴ ትንታኔ፣ በአይዶሎጂ ይሞላዋል። ምክንያቱም ዝግ ካደረገው ያጋፍጠዋል። ያጋፍጠዋል ከባከነው ዕድሉ ጋር፣ ያጋፍጠዋል ከከንቱ እና ከውሸት እምነቱ ጋር። ካልተኖረው የአስመሳይነት መርሁ ጋር። ስለዚህ ያን ከመጋፈጥ ፥ በላይ በላይ ይግተዋል ይሄን መረጃ። ጭንቅላቱን ይገዝፍበታል። አዕምሮውን ከማህበራዊ ሚዲያ እስከ ዜና በሚገኝ ብጣሽ እና ቅራቅንቦ ይሞላዋል። በዚህም ሕይወትን እንደሸሻት ፥ የራሱን ሕይወት ሳይኖር ይሞታል። ለዚህ ነው ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድኅን “እስቲ ለአንድ አፍታ እንኳ ዝም እንበል። አጉል ነው ብለን ሳንፈረድ፣ ድንቅም ነው ብለን ፈጥነን ሳንወድ፣ መንጋነትን አርቀን እስቲ ዝም እንበል። ብቻ ይሄን አለማድረግ ነው ሞት” ይለናል። ዳግመኛ ሞት መሞት ፥ የአዲስ ኪዳን ጨለማ ማለት ይሄ ነው። ራስን ለመፈተሽ ፥ ተረጋግቶ ለማሰብ ፥ ከዛም ለመታዘብ አለመፍቀድ።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Nov 3, 2024
  • 3 min read




“ፍላጎት ገደብ የለውም ፥ ሀብት ግን ገደብ አለው” ወይም “demand is unlimited but all resources are scarce” የሚለው የእንግሊዘኛ ዓረፍተ ነገር የኢኮኖሚክስ ክላስ ሁሉ ሀ ሁ ነው። እጥረት ማለት አንድን ፒዛ ለመቶ ሰው ለማከፋፈል እንደመጣር ነው። በኢኮኖሚክስ እጥረት ማለት ብዙ ሰው የሚፈልገው ነገር በተመጠነ ቀጥር ብቻ ሲኖር ማለት ነው። በተመጠነ ቁጥር ያለ ግን ብዙ ሰው የማይፈልገው ነገር ዋጋው በጣም ዝቅተኛ ወይም ርካሽ ነው። በተመሳሳይ ብዙ ሰው የሚፈልገው ነገር ፥ ግን በብዛት ያለ ነገርም ዋጋው ርካሽ ነው። እጥረት የሰዎችን የመወሰን አቅም ይቀርጻል። ማለትም በሆነ ጊዜ በጣም ያጠረን ነገር ዘወትር ባህሪያችንን ሊመራው ይችላል። ለምሳሌ በልጅነቱ በጣም ደሃ የሆነ እና የተቸገረ ሰው ፥ በኋላ ላይ ገንዘብ ቢኖረውም አላስፈላጊ የሆነ ስግብግብነት ወይም የገንዘብ ስስት ሊያሳይ ይችላል። ምክንያቱም ወደ ዛ ችግር እመለሳለው የሚለው ፍራቻ አሁን ላይ ተትረፍርፎት ቢሆን እንኳ አላስፈላጊ የተጋነነ ቁጠባ ውስጥ ራሱን ሊከት ይችላል።



በሚገርም ሁኔታ ግን እጥረት በራሱ መጥፎ ነው ማለት አይደለም። ይልቁንስ መትረፍረፍ የበለጠ ሊጎዳን ይችላል። በዓለም ላይ በረሃብ ከሚሞተው በላይ በውፍረት ከሚመጣ በሽታ የሚሞት ሰው ይበዛል። የዛሬ አስር ዓመት አካባቢ በነበረኝ የስደተኞች ጉዳይ ጥናት ባህር እየተሻገሩ የሚሰደዱ እና የሚሞቱ ሰዎች ድኇች እንዳልሆኑ የደረስንበት ጥናት ነው። ምክንያቱም በሰዓ ያንን ስደት ለማድረግ ከሰባት ሺ እስከ አስራ አምስት ሺ የአሜሪካ ዶላር ያስፈልግ ነበር። ያ ገንዘብ የኢትዮጵያ ድሃ ኖሮት አያውቅም። ስለዚህ ድህነትን ተላቀው የወጡ ሰዎች ነበ ይሄን ስደት የሚመርጡት። ምክንያቱም ሀብታም ለመሆን። ድህነትን ለማምለጥ ሳይሆን።


የብዙ ስህተቶች ምንጭ ከእጥረት በላይ መትረፍረፍ ነው።



የዚህ ጹሁፌ ዓላማ በዚህ የኢኮኖሚክስ ጽንሰ ሀሳብ ላይ አተኩሬ መጻፍ አይደለምይልቁንስ እንዴት እጥረትን እኛ መጠቀም እንደምንችል እና እኛ ራሳችን እጥረት መሆን እንደምንችል ማሳየት ነው።


እጥረት የፈጠራ ምንጭ ነው። የገንዘብ እጥረት ነው ለብዙ መፍትሔዎች መሰረት። ነጋ የሆነ ነገር እንደምናጣ ስናስብ ነው ሰውን በአግባቡ መጠየቅ፣ መልካም መሆን የምንጀምረው። ነገ ገንዘብ ሊያጥረን እንደሚችል ስናስብ ተጨማሪ ሙያ መማር እንጀምራለን። ነገ ብቸኛ ልንሆን እንደምንችል ስናስብ እና ስንሰጋ ወደ ትዳር፣ ልጅ ወደ መውለድ ወዳጆቻችንን ወደ መጠየቅ እንገባለን። እጥረትን በሆነ መጠን ስንቀምሰው ወዲያው ባህሪያችንን መቀየር እንጀምራለን። ጤና የተትረፈረፈ ነገር እንዳልሆነ የምናውቀው የጤና እጥረት ሲገጥመን ነውከዛ ስለጤናችን ማሰብ፣ ጥሩ ምግብ መብላት እና ስፖርት ወደ መስራት እንሄዳለን። “በእጅ ያለ ወርቅ እንደ መዳብ ይቆጠራል" እንላለን። ሁልጊዜ ከእኛ ጋር ያሉ ሰዎች ድንገት ሲለዩን ፥ እነሱ በሕይወት እያሉ ያሳየነው መዘናጋት እንደ እግር እሳት ይለበልበናል። ብዙ ሰው ግን በመትረፍረፍ ውስጥ እንዴት መኖር እንደሚቻል አያውቅም። ስለዚህ እጥረትን እስከሚቀምስ ድረስ ማሰብ አይችልም።



በተያያዘ ደግሞ እጥረት ያላቸው ነገሮች እና ሰዎች የሚፈልጉት ነገር ዋጋው ውድ ነው። ለምሳሌ ወርቅን ተመልከቱ። በየቦታው እንደ ልብ ያለ ቢሆን በዚህ ደረጃ ዋጋው አይወደድም ነበር። እጥረት ነው ዋጋውን ያስወደደው። ለዚህ ነው አንዳንድ ኩባንያዎች ምርታቸውን በጣም ትንሽ ብቻ በማድረግ ዋጋውን ሰማይ ይሰቅሉታል። ለምሳሌ እንደ ሬንጅ ሮቨር ያሉ መኪኖች ከቶዮታ አንጻር ጥንካሬያቸው እና የመገልገያ ዘመናቸው በጣም ያነሰ ቢሆንም ኩባንያው ግን በጣም ትንሽ ቁጥር ያለው ሬንጅ ሮቨር በማምረት ፥ ዋጋውን ሰማይ ይሰቅሉታል፤ በዚህም የክላስ ጉዳይ ያደርጉታል። ይሄ ለሰውም ይሰራል። እጅግ ጥሩ እና መልካም ብትሆኑንም ዘወትር ካላችሁ፣ በቀላሉ የምትገኙ ከሆነ ግን ሰዎች ዋጋችሁን ዝቅ ያደርጉታል። ሁሌ እንደምትገኙ ካሰቡ ላቀረባችሁት መልካምነት የሚሰጡት ዋጋ እጅግ ዝቅተኛ ይሆናል።



ለዚህ ነው እጥረት በራሱ መጥፎ ያልሆነው። ለምሳሌ ታማኝ ናችሁ፣ በዚህ ላይ ጠንካራ ሰራተኛ እና እጅግ ስማርት ናችሁ እንበል። በዚህ ዓለም ላይ እነዚህን ሦስት ባህሪዎች ገንዘብ ያደረገ ሰው በጣም ጥቂት ነው። ታማኝ ሰው ስታገኙ ሥራ አይችልም። ነገር አይገባውም። ነገር የሚገባው ብሩህ አዕምሮ ያለው ሰው ስታዩ ደግሞ ጥቂት ጠጋ ብላችሁ ስትፈትሹት ጠንካራ ሰራተኛ አይደለም። ወይም ታማኝ አይደለም። ስለዚህ እነዚህን ሦስት ማንነቶች ታማኝነትን ከብሩህ አዕምሮ ጋር ፥ ብሩህ አዕምሮን ከትጋት እና ዲሲፕሊን ከሆነ ሰራተኝነት ጋር አዋህደን ከያዝን በዚህ ዓለም ላይ መቼም ሥፍራ አናጣም። የኛ ዋጋ ሁልጊዜ ከፍ ያለ ነው። እንደ እንቁ ውድ ነን። በአንድ ነገር ላይ ምርጥ መሆን ብቻ አይደለም ግን ብዙ ነገሮችን አዋህዶ መያዝን እንጂ። ለዚህ ነው “እጥረት እንሁን” ያልኩት። ምርጥ አይደለም፤ የማንተካ እንሁን። የኛ መጉደል ትልቅ ክፍተት የሚፈጥር ይሁን። ያን በተንኮል ሳይሆን በብቃታችን እንፍጠር። የኛ መጉደል በነካነው ቦታ ላይ ሁሉ በጎ ትውስታን የሚፈጥር ከሆነ የዛኔ እጥረት ነን ማለት ነው።



ጻድቁ ኢዮብ እጥረት ነበር። ፍጹምና ቅን፥ እግዚአብሔርንም የሚፈራ፥ ከክፋትም የራቀ ነበረ። እነዚህን ሦስቱንም የሆነ ሰው አልነበረም። ፈሪያ እግዚአብሔር የሌላቸው ግን ቅን ሰዎች አሉ። እግዚአብሔርን የሚፈሩ ግን ከክፋት መራቅ ያልቻልን አለን። ኢዮብ ግን እጥረት ነበር። ሦስቱንም አካቶ የያዘ።



እጥረትን በጥልቀት እናስብበት። ለኛ ጥቅም እናውለው። በእጥረት ግን እንዳንነዳ እንጠንቀቅ። ምክንያቱም አንዳንድ እጥረቶች የውሸት፣ ሆን ተብለው የተፈጠሩ ወይም አሁን ላይ የሌሉ ናቸው።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page