top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Nov 3, 2024
  • 3 min read


ree


“ፍላጎት ገደብ የለውም ፥ ሀብት ግን ገደብ አለው” ወይም “demand is unlimited but all resources are scarce” የሚለው የእንግሊዘኛ ዓረፍተ ነገር የኢኮኖሚክስ ክላስ ሁሉ ሀ ሁ ነው። እጥረት ማለት አንድን ፒዛ ለመቶ ሰው ለማከፋፈል እንደመጣር ነው። በኢኮኖሚክስ እጥረት ማለት ብዙ ሰው የሚፈልገው ነገር በተመጠነ ቀጥር ብቻ ሲኖር ማለት ነው። በተመጠነ ቁጥር ያለ ግን ብዙ ሰው የማይፈልገው ነገር ዋጋው በጣም ዝቅተኛ ወይም ርካሽ ነው። በተመሳሳይ ብዙ ሰው የሚፈልገው ነገር ፥ ግን በብዛት ያለ ነገርም ዋጋው ርካሽ ነው። እጥረት የሰዎችን የመወሰን አቅም ይቀርጻል። ማለትም በሆነ ጊዜ በጣም ያጠረን ነገር ዘወትር ባህሪያችንን ሊመራው ይችላል። ለምሳሌ በልጅነቱ በጣም ደሃ የሆነ እና የተቸገረ ሰው ፥ በኋላ ላይ ገንዘብ ቢኖረውም አላስፈላጊ የሆነ ስግብግብነት ወይም የገንዘብ ስስት ሊያሳይ ይችላል። ምክንያቱም ወደ ዛ ችግር እመለሳለው የሚለው ፍራቻ አሁን ላይ ተትረፍርፎት ቢሆን እንኳ አላስፈላጊ የተጋነነ ቁጠባ ውስጥ ራሱን ሊከት ይችላል።



በሚገርም ሁኔታ ግን እጥረት በራሱ መጥፎ ነው ማለት አይደለም። ይልቁንስ መትረፍረፍ የበለጠ ሊጎዳን ይችላል። በዓለም ላይ በረሃብ ከሚሞተው በላይ በውፍረት ከሚመጣ በሽታ የሚሞት ሰው ይበዛል። የዛሬ አስር ዓመት አካባቢ በነበረኝ የስደተኞች ጉዳይ ጥናት ባህር እየተሻገሩ የሚሰደዱ እና የሚሞቱ ሰዎች ድኇች እንዳልሆኑ የደረስንበት ጥናት ነው። ምክንያቱም በሰዓ ያንን ስደት ለማድረግ ከሰባት ሺ እስከ አስራ አምስት ሺ የአሜሪካ ዶላር ያስፈልግ ነበር። ያ ገንዘብ የኢትዮጵያ ድሃ ኖሮት አያውቅም። ስለዚህ ድህነትን ተላቀው የወጡ ሰዎች ነበ ይሄን ስደት የሚመርጡት። ምክንያቱም ሀብታም ለመሆን። ድህነትን ለማምለጥ ሳይሆን።


የብዙ ስህተቶች ምንጭ ከእጥረት በላይ መትረፍረፍ ነው።



የዚህ ጹሁፌ ዓላማ በዚህ የኢኮኖሚክስ ጽንሰ ሀሳብ ላይ አተኩሬ መጻፍ አይደለምይልቁንስ እንዴት እጥረትን እኛ መጠቀም እንደምንችል እና እኛ ራሳችን እጥረት መሆን እንደምንችል ማሳየት ነው።


እጥረት የፈጠራ ምንጭ ነው። የገንዘብ እጥረት ነው ለብዙ መፍትሔዎች መሰረት። ነጋ የሆነ ነገር እንደምናጣ ስናስብ ነው ሰውን በአግባቡ መጠየቅ፣ መልካም መሆን የምንጀምረው። ነገ ገንዘብ ሊያጥረን እንደሚችል ስናስብ ተጨማሪ ሙያ መማር እንጀምራለን። ነገ ብቸኛ ልንሆን እንደምንችል ስናስብ እና ስንሰጋ ወደ ትዳር፣ ልጅ ወደ መውለድ ወዳጆቻችንን ወደ መጠየቅ እንገባለን። እጥረትን በሆነ መጠን ስንቀምሰው ወዲያው ባህሪያችንን መቀየር እንጀምራለን። ጤና የተትረፈረፈ ነገር እንዳልሆነ የምናውቀው የጤና እጥረት ሲገጥመን ነውከዛ ስለጤናችን ማሰብ፣ ጥሩ ምግብ መብላት እና ስፖርት ወደ መስራት እንሄዳለን። “በእጅ ያለ ወርቅ እንደ መዳብ ይቆጠራል" እንላለን። ሁልጊዜ ከእኛ ጋር ያሉ ሰዎች ድንገት ሲለዩን ፥ እነሱ በሕይወት እያሉ ያሳየነው መዘናጋት እንደ እግር እሳት ይለበልበናል። ብዙ ሰው ግን በመትረፍረፍ ውስጥ እንዴት መኖር እንደሚቻል አያውቅም። ስለዚህ እጥረትን እስከሚቀምስ ድረስ ማሰብ አይችልም።



በተያያዘ ደግሞ እጥረት ያላቸው ነገሮች እና ሰዎች የሚፈልጉት ነገር ዋጋው ውድ ነው። ለምሳሌ ወርቅን ተመልከቱ። በየቦታው እንደ ልብ ያለ ቢሆን በዚህ ደረጃ ዋጋው አይወደድም ነበር። እጥረት ነው ዋጋውን ያስወደደው። ለዚህ ነው አንዳንድ ኩባንያዎች ምርታቸውን በጣም ትንሽ ብቻ በማድረግ ዋጋውን ሰማይ ይሰቅሉታል። ለምሳሌ እንደ ሬንጅ ሮቨር ያሉ መኪኖች ከቶዮታ አንጻር ጥንካሬያቸው እና የመገልገያ ዘመናቸው በጣም ያነሰ ቢሆንም ኩባንያው ግን በጣም ትንሽ ቁጥር ያለው ሬንጅ ሮቨር በማምረት ፥ ዋጋውን ሰማይ ይሰቅሉታል፤ በዚህም የክላስ ጉዳይ ያደርጉታል። ይሄ ለሰውም ይሰራል። እጅግ ጥሩ እና መልካም ብትሆኑንም ዘወትር ካላችሁ፣ በቀላሉ የምትገኙ ከሆነ ግን ሰዎች ዋጋችሁን ዝቅ ያደርጉታል። ሁሌ እንደምትገኙ ካሰቡ ላቀረባችሁት መልካምነት የሚሰጡት ዋጋ እጅግ ዝቅተኛ ይሆናል።



ለዚህ ነው እጥረት በራሱ መጥፎ ያልሆነው። ለምሳሌ ታማኝ ናችሁ፣ በዚህ ላይ ጠንካራ ሰራተኛ እና እጅግ ስማርት ናችሁ እንበል። በዚህ ዓለም ላይ እነዚህን ሦስት ባህሪዎች ገንዘብ ያደረገ ሰው በጣም ጥቂት ነው። ታማኝ ሰው ስታገኙ ሥራ አይችልም። ነገር አይገባውም። ነገር የሚገባው ብሩህ አዕምሮ ያለው ሰው ስታዩ ደግሞ ጥቂት ጠጋ ብላችሁ ስትፈትሹት ጠንካራ ሰራተኛ አይደለም። ወይም ታማኝ አይደለም። ስለዚህ እነዚህን ሦስት ማንነቶች ታማኝነትን ከብሩህ አዕምሮ ጋር ፥ ብሩህ አዕምሮን ከትጋት እና ዲሲፕሊን ከሆነ ሰራተኝነት ጋር አዋህደን ከያዝን በዚህ ዓለም ላይ መቼም ሥፍራ አናጣም። የኛ ዋጋ ሁልጊዜ ከፍ ያለ ነው። እንደ እንቁ ውድ ነን። በአንድ ነገር ላይ ምርጥ መሆን ብቻ አይደለም ግን ብዙ ነገሮችን አዋህዶ መያዝን እንጂ። ለዚህ ነው “እጥረት እንሁን” ያልኩት። ምርጥ አይደለም፤ የማንተካ እንሁን። የኛ መጉደል ትልቅ ክፍተት የሚፈጥር ይሁን። ያን በተንኮል ሳይሆን በብቃታችን እንፍጠር። የኛ መጉደል በነካነው ቦታ ላይ ሁሉ በጎ ትውስታን የሚፈጥር ከሆነ የዛኔ እጥረት ነን ማለት ነው።



ጻድቁ ኢዮብ እጥረት ነበር። ፍጹምና ቅን፥ እግዚአብሔርንም የሚፈራ፥ ከክፋትም የራቀ ነበረ። እነዚህን ሦስቱንም የሆነ ሰው አልነበረም። ፈሪያ እግዚአብሔር የሌላቸው ግን ቅን ሰዎች አሉ። እግዚአብሔርን የሚፈሩ ግን ከክፋት መራቅ ያልቻልን አለን። ኢዮብ ግን እጥረት ነበር። ሦስቱንም አካቶ የያዘ።



እጥረትን በጥልቀት እናስብበት። ለኛ ጥቅም እናውለው። በእጥረት ግን እንዳንነዳ እንጠንቀቅ። ምክንያቱም አንዳንድ እጥረቶች የውሸት፣ ሆን ተብለው የተፈጠሩ ወይም አሁን ላይ የሌሉ ናቸው።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Oct 27, 2024
  • 2 min read

ree


አልበርት አንስታይን የህሊና አድማስ (ኢማጅኔሽን) የሌለው ሰው እና የሞተ ሰው እኩል ነው ይል ነበር። የእናንተን አላውቅም የእኔ አዕምሮ ግን በሆነ ነገር ላይ ሲመሰጥ ራሱን የዛ አካል አድርጎ በምልዓት ጠልቆ ይገባል። በዚህ ሳምንት በትንቢተ ኢሳይያስ ምዕ 6 ከቁጥር 1 ጀምሮ ያለው ታሪክ የህሊና አድማሴን ይዞት ሄዷል።



 ረጅሙ እና ከፍ ያለው ዙፋን ላይ የተቀመጠው አምላክ። ፍጹም አስፈሪው ግን ፍጹም ውበት ያለው፤ ያ የተፈራው ዖዝያን ከሞተ በኋላም እርሱ ግን በረዥሙ እና ከፍ ባለው ዙፋን ላይ ተቀምጧል። ይሄን የሚናገረው ስለዙፋን እና ንጉሶች እነሱን በማገልገል እውቀት የነበረው ነቢዩ ኢሳይያስ ነበር። ከዛ ትልቁ እና ውቡን ዝማሬን ሰማ። “ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ” የሚለውን። እንደሚዳሰስ ፍቅር፣ እንደሚነካ የምህረት ፏፏቴ አምላካቸውን በማየት የረኩ ከልብ ደስ ብሏቸው “ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ” እያሉ ከዙፋኑ ሥር ወደቁ። ፍጹም ፍቅር ያለበት ግን ፍርሃት ያልተለየው ያ ምስጋና።



“የመድረኩም መሠረት ከጭዋኺው ድምፅ የተነሣ ተናወጠ።” ይሄ ክብር የሰው ልጅ ክብር ነው። ነቢዩ ይሄን ሲያይ የጠፋ ነበር የመሰለው። ነገር ግን ከሱራፌልም አንዱ እየበረረ ወደ እርሱ መጥቶ ፥ የዚህ ደስታ አካል እንዲሆን ተመኝቶ በፍሙ አነጻው።


ተመሳሳይ ደስታ የምናየው በራዕይ ላይ ነው። ራዕይ ምዕ 4። ሃያ አራት ሽማግሌዎች ዙፋኑን ከበውት ፥ ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ የሚለውን የምስጋና ጅረት ሲሰሙ ወድቀው “አንተ ሁሉን ፈጥረሃልና ስለ ፈቃድህም ሆነዋልና ተፈጥረውማልና ክብር ውዳሴ ኃይልም ልትቀበል ይገባሃል።” ይሉታል።



ይሄ ውበት፣ ይሄ ሞገስ፣ ይሄ ከፍታ የሰው ልጅ የሕሊና አድማስ ነው። ይሄን የውበት ወንዝ እየሳልን ፥ የተጠራነው ከዚህ ፍጹም ሞገስ ጋር አንድ ለመሆን እንደሆነ እንድናውቅ ነው።



ሲ ኤስ ሉዊስ “ሰይጣን ሥርዓት ያለው ዘፈን ሳይቀር ይረብሸዋል” ይላል። እስቲ ሂዱ እና እነዚህ ሰማያዊ መዝሙሮችን ተመልከቱ። ስሜት አልባ እኮ አይደሉም። ድምጽ፣ እሳት፣ ነጎድጓድ አላቸው። ግን ደግሞ ፍጹም ሥርዓትም አላቸው። የመሬት መናወጥ አላቸው ግን ረጋ ብሎ መደፋት እና ሞገስ እና እርከንም (hierarchy) አላቸው። ዙፋኑን የከበቡበት መንገድ፣ ቤቱ በጢስ መሞላቱን ስታዩ ምን ያህል ሕይወት ያለው መዝሙር እና የዛ አካል መሆንን የሚያጓጓ እንደሆነ ታያላችሁ። በተቃራኒው የትህትናው ብዛትን ተመልከቱ። ዓይናቸውን፣ እግራቸውን እየሸፈኑ ግን ደግሞ እየበረሩ የሚያመሰግኑ ነበሩ። ት ህትና ብቻ ነው ወደ ላይ ከፍ የማለት ክንፍ ያለው። ራሱን የሚሸፍን ብቻ ነው የተገለጠውን የሚያየው። ግን ደግሞ ባዶን ነገር መሸፈን አይቻልም። የእውቀት ዓይኖች ፥ የጽናት እግሮች ሲኖሩን ብቻ ነው የሚሸፈን ነገር የሚኖረን። መኖሩ የታወቀ ገንዘብ እንደሚበዘበዝ፣ እንደሚመነዘር ፥ የተደበቀው ግን ወደ በለጠው ክብር ይበራል።



ዙፋኑ ያን ትህትና በሚያሳይ መልኩ ነበር የተዘጋጀው። ረጅም እና ከፍ ያለ ነበር።



ሲ ኤስ ሊዊስ “እንስሳት መሆናችንን ማስረሳት ነው የሰይጣን ተልዕኮ” ይል ነበር። ማለትም ትህትና ዝም ብሎ የሚመጣ ነገር ይመስለናል። በፍጹም። ትህትና በየቀኑ ትንሽነታችንን በሚያስታውስ ነገር ራሳችንን ካልከበብን እየራቀን ይሄዳል። ከድንኮች ጋር ከዋልን ከትዕቢት ውጪ አማራጭ የለንም።



 ሌላ ደግሞ ሽማግሌዎችን እዩአቸው። በዘመን አርጅተዋል። በልምድ ሸብተዋል። ከዚህም የተነሳ ነጭ ለብሰው፣ ከወርቅ የተሰራ አክሊል አጥልቀው እንዲቆሙ ሳይሆን እንዲቀመጡ ነበር የተፈቀደላቸው። ነገር ግን የዙፋኑ መሠረት ኃያል በሆነ ድምጽ ሲመታ እና የምስጋናው ድምጽ ሲሰማ እነዚህ ሃያ አራት አባቶች በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ፥ የሰው ልጅ ቋንቋ የማይገልጸው ውበት ለተላበሰው ወደቁ ፥ ተንበርክከውም ፈቃዱን አደነቁ።



ሥርዓት፣ ሕይወት ያለው ምስጋና፣ ፍጹም ትህትና፣ ንጽህና እንዴት ባለ ገመድ ተሳስረው በሰማያዊው ቤተመቅደስ እንደተገለጡ ተመልከቱ። በዚህ ምድር ላይ እነዚህን ነገሮች ገንዘብ ያደረገ ተቋም የማይበገር ነው። ሥርዓት ያለ ሕይወት (passion) ድብርትን ይጋብዛል። ስሜት (passion) ያለ ትህትና ውድቀትን ይስባል። ንጽህና ደግሞ የዚህ ውበት እና ደስታ ተካፋይ እንድንሆን ያደርጋል። አካል፣ ተካፋይ እንድንሆን ያደርገናል። ይሄን አዕምሮዬ ተመሰጠበት። ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ ፥ የሚለው ዖዝያንም ሞቶ ይቀጥላል። ሃያ አራቱ ሽማግሌዎች በፊቱ ወድቀው ፥ አክሊላቸውን ለርሱ አኖሩ።



በመጨረሻም ዖዝያን ይሞታል። ግድ የላችሁም ፥ እርሱን ግን ነገም በዛ ረዥም እና ከፍ ባለ ዙፋኑ ላይ እናየዋለን።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Oct 20, 2024
  • 5 min read

ree


አንድ እግዚአብሔርን እጅግ የሚወድ ወዳጅ አለኝ። ነገር ግን ስለሲዖል ሲያስብ ግራ ይገባዋል። እግዚአብሔር ምን ያህል ፍቅር እንደሆነ እያወቀ፣ ስለ ሲዖል የሚሰጠውን ትምህርት ደግሞ ለመቀበል ይቸገራል። ልጆች ስላሉት ለዘላለም እግዚአብሔር ልጆቹን በእሳት ያቃጥላል የሚለው ትምህርት አይዋጥለትም። በልጆቹ ፈጽሞ የማይጨክነው እርሱ፤ እግዚአብሔር ፍቅር ሆኖ ሳለ በእጆቹ ውብ ሥራ የሰው ልጆች ላይ ይጨክናል የሚለው ይጸንነዋል። በርግጥ ይሄ እኔንም የሚከብደኝ ትምህርት ነበር። ነገር ግን እግዚአብሔር ፍቅር ብቻ ሳይሆን ፍትሕ እና እውነትም እንደሆነ ስለምንዘነጋ እና ያን ደግሞ ፍቅሩን የተቀበሉት ከእርሱ የሚጠብቁት እንደሆነ ስለምንረሳ ነው። ማለትም እግዚአብሔርን ለማፍቀራቸው አንዱ የእርሱ ፍትሐዊነት እና እውነተኝነትም ነው።



 ይሄን በጥቂቱ ከማብራራቴ በፊት “የእኛስ ቅጣት ከእግዚአብሔር ይለያል ወይ?” የሚለውን ጥያቄ ልጠይቅ በመጀመሪያ፤ ሲዖል በዋናነት የሚከብደን ኃጢአተኛ በመቀጣቱ ሳይሆን ፥ በጥቂቱ የሕይወት ዕድሜው በሠራው ኃጢአት እንዴት ዘላለም ይቀጣል፤ ያውም በገሀነም እሳት የሚለው ነው። ማለትም ‘ኃጢአት የሠራበት ዘመን እና የመቀጣቱ ዘመን ርዝማኔ አይመጣጠንም’ ነው እያልን ያለነው እንጂ “የሰው ልጆችን በእሳት ቼምበር አቃጥሎ ሥጋቸውን ያስፈጨው ሂትለር ያለቅጣት በይቅርታ ይታለፉ፣ የሰረቀ እና ከድኋው በክፋት የነጠቀ፣ ወንድሙ የዕለት እንጀራ አጥቶ እየተቸገር ለብዙ ዓመት የሚያጠራቅመውን ለዛውም በእውነት እና በሀቅ ባልሆነ መንገድ ሲሞትም ደስታ እና ሀሴት ይጠብቀው” እያልን እንዳልሆነ አምናለሁ። ይልቁንስ እያልን ያለነው “የኃጢአት ዘመኑን የሚመጥን ቅጣት ይጠብቀው ነው።” ፍትሐዊ አባባል ነው።



የመጀመሪያው ጌታችን ወደ ቅፍርናሆም እና ቤተሳይዳ እያመለከተ ፥ ፍቅሩ እና የማዳን ሥራው እንደ ጊዮን ውሃ የፈሰሰላቸው እነዚህ ከተሞች ነገር ግን ጌታቸውን ያገለሉ እና ችላ ያሉ በፍርድ ቀን ከጢሮስ፣ ከሰዶም እና ከገሞራ ይልቅ የበለጠ ፍርድ እንደሚጠብቃቸው ነገሮናል። (ማቴ 10፥15፣ ማቴ 11፥22)። ምክንያቱም ሰዶም እና ገሞራ ለሰሩት ኃጢአት ፍርድን ወዲያው በምድር ላይ ተቀብለዋልና፣ በዘላለም ፍርድ ፍትሐዊው ፈራጃችን ያን እንደሚያስብላቸው ነገሮናል። በዚህም የቅጣት ፍርዱ ለሁሉም እኩል እንዳልሆነ አሳወቀን። ያነሰ ፍርድ የሚቀበሉ እንዳሉ ነግሮናል። የዘላለም የገሀነምን እሳት እንዳለ በቅጣት የሚቀበሉም እንዳሉ እንዲሁ። ከእነሱም ዋነኞቹ የመዳን ወንጌሉ ተሰብኮላቸው ፥ የፍቅሩ ተዓምር ተደርጎላቸው ያገለሉት ትልቁን ፍርድ እንደሚቀበሉ ነው የነገረን። ስለዚህ ፍርዱ በሚዛን እንደሚሆን ገልጦልናል። ያ ሚዛን ግን የእሱ ስለሆነ አሁን ላይ ምን እንደሚመስል ከዚህ በጠለቀ ሁኔታ አልተገለጸልንም። ይሄም ለእኛ ስለማይጠቅመን እንደሆነ አምናለሁ። ግን ትልቁን ጥያቄ መልሶልናል። ያም የቅጣቱ ፍርዱ እንደሚለያይ። እዚህ ጋር አንድ ማስመር የምፈልገው ጌታችን ከብሉይ ኪዳን በአሉታዊ መንገድ የጠቀሳት ብቸኛዋ ሴትን ነው። እሷም የሎጥ ሚስት ናት።(ሉቃ 17፥32)። ጌታችን ወደ ሐዋርያት ዞሮ የሎጥን ሚስት አስቧት ብሏቸዋል። ያቺ ከታላቁ የእምነት አባት አብርሃም ዘር የመቆጠርን ዕድል ያገኘችው፣ መላዕክት እጇን ይዘው የእሳትን ባህር የሚያሿግራት የሎጥ ሚስት። በመጨረሻም ፊትለፊቷ ካለው የጽድቅ ተራራ ይልቅ የሰዶም ውበት ትዝታ የሳባት እና ወደኋላ የዞረችው የሎጥ ሚስት። ይህችን ሴት ጌታ በተለየ ሁኔታ እንድናስባት አሳስቦናል። ጌታችን ይሄን ለሐዋርያት ነው የተናገረው። በዛ የፍርድ ቀን ለእናንተ ይብስባችኋል ሲል።



ሁለተኛው ጥያቄ የዘላለም ቅጣት ጉዳይ ነው። በዚህ ምድር ያለ የፍትሕ ፍርድ ቤት እንዴት እንደሚፈርድ ጠይቃችሁ ታውቃላችሁ? ለምሳሌ አንድ ሰው ተናዶ ወደ ቤቱ ሲመጣ ሚስቱ እና ልጆቹ የበለጠ ቢያናዱት እና በዛ የአንድ ደቂቃ ደም ፍላት ምክንያት ሽጉጡን አውጥቶ ሚስቱን እና ልጆቹን ቢገድል ፥ ይሄ ሰውዬ የሚጠብቀው ፍርድ ምን እንደሆነ አስባችኋል? ፍርድ ቤቱ የአንድ ደቂቃ የደም ፍላት ችግር ነው ብሎ እድሜ ልክ ከመፍረድ የሚቆጠብ ይመስላችኋል? የአንድ ደቂቃ ስህተት መሆኑ ለዛ ወንጀል የሚገባውን የእድሜ ልክ ፍርድ ከማሰጠት ያድነዋል? ብዙ ወንጀሎችስ በእውነት ቅጣታቸው ወንጀሉ ከተደረገበት የእድሜ ዘመን በላይ እንደሆነ አስባችሁ አታውቁምን? እነዚህ ቅጣቶች መቼ የፍትሕ ጥያቄ ይነሳባችኋል? ከወንጀል ድርጊቱስ በላይ የምንቀጣው የሰውዬውን የመግደል ፍላጎት እና የአዕምሮ ሁኔታ አይደለምን? ለመግደል ያነሳሳውን ፍላጎት እና ሁኔታ አይደለም ታሳቢ የምናደርገው? ለዛስ አይደለ ሰው የገደለ ሁሉ እኩል ቅጣት የማይከተልበት? ለምሳሌ በጦርነት ያለ ወታደር ምንም ሰው ቢገድል፤ ከአሸናፊው ወገን በመጨረሻ ከሆነ እንደ ገዳይ ሳይሆን እንደ ጀግና እና መልካም ሰው የምናየው የምንቀጣው ተግባሮችን ሳይሆን በዋነኝነት እነዛ ተግባሮች የቆሙበትን ፍላጎት፣ የማህበረሰብ ቀጣይ አኗኗር እና የሌሎች ሰዎችን ባህሪ እና መጠበቅ ታሳቢ በማድረግ አይደለምን? ይሄ የሚያሳየን ቅጣት ወንጀለኛው ለሠራው ክፋት ብቻ ሳይሆን፣ ሌላውንስ ከመውደድ፣ ማለትም በወንጀለኛው ክፋት የተጎዱትን እና የሚጎዱትን በማሰብም ጭምር እንደሆነ እንዴት እንዘነጋለን?



እግዚአብሔር ፍቅር ነው ብለን፣ ሁሉን ያለፍርድ የሚያልፍ፣ በፍቅሩ ታምነው ቃሉን ለጠበቁት ብቻ ሳይሆን፣ ሁሉንም በእርሱ እቅፍ የሚሰበስብ ከሆነ ... አምላካችን ስለዘላለማዊ ቅጣት የተናገረውን የእውነት ቃል አምነው፣ የዚህ ምድርን ጊዜያው ጥቅም እንደጉዳት የወሰዱ ሰዎችን ወዴት እናድርጋቸው? መከራን ስለመንግስቱ ሲሉ የተቀበሉትን ፥ መከራቸውስ ስለከንቱ ነውን?



ሰነፉን ተማሪ እና እንቅልፍ አጥቶ ያጠናውን ተማሪ ስለፍቅር ብሎ እኩል የሚሸልም እና የሚያሳልፍ መምህር ከሁሉ በላይ የጎዳው ፍቅርን አይደለምን? ምክንያቱም ፍቅሩን ከምር የወሰደው ተማሪ ሲጎዳ ፥ እርሱን ያላመነው ግን አላማመኑ እውነት እንደነበረ በውስጡ የተጠራጠረው ልክ አልነበረምን? የትኛውስ ፍቅር ያለፍትሕ ይቆማል? የትኛውስ ፍቅር ያለእምነት (እውነት) ይጸናል?



ብዙ የሚያጠራጥር ነገር በሞላበት ዓለም ውስጥ እየኖሩ፣ ለብዙ ጥያቄዎቻቸው መልስ ሳያገኙ፣ እሱን ግን አምነው ቃሉን የጠበቁት በከንቱ ነበርን? በእነሱ ላይ ያሾፉት እና በደካማው እና ምስኪኑ ላይ ፍርድን ያዛቡት፣ “የእናንተ እግዚአብሔር ቢኖር ይሄ ሁሉ ይፈጸማልን?” እያሉ ከደካማው ነጥቀው የሞላውን ጎተራቸውን የጠቀጠቁትን ፥ “እኔ ፍቅር ነኝ” በሚል ብቻ በመንግስቱ ስለእርሱ ሁሉን እያጡ መከራ ከተቀበሉት ጋር ከደመራቸው ፥ በዚህ ፍርድ አሸናፊው ማነው? ከእግዚአብሔርም ሆነ ከጻድቃን በላይ የዚህ የፍጻሜ ፍርድ አሸናፊዎች የክፋት ሰዎች አይደሉምን?



ቅዱስ ጳውሎስ “እግዚአብሔር አይዘበትበትም፣ ሰው ሁሉ የዘራውን ያጭዳል” ያለው ውሸቱን ነበርን?። (ገላ 6፥8)። ይሄንንስ አምነው መልካም ዘር የዘሩት፣ እግዚአብሔር ላይ ያልዘበቱት፣ ክርስቶስ በፍጻሜ ፍርዱ የዘላለም እሳት አለ ያልኳቹ “ውሸቴን ነው ወይም ትቼዋለሁ፣ እኔ ፍቅር ሆኜ ሳለ ሰውን በገሀነም እሳት እንደኃጢአቱ መጠን ላቃጥል አይገባኝም፤ ስለዚህ ሁላቹሁ የአባቴ ወገን ናችሁና ኑ” ቢል፤ እነዚህ ስለእርሱ ሁሉን ያጡት ስለፍቅሩ ምን ይሰማቸው? ይሄ ፍቅርስ ከእነሱ ይልቅ ለኃጢአተኞች አይደለምንም? ሰነፍ ተማሪዎች መውደቃቸውን አይቶ፤ የጎበዞቹን ልፋት እንደምንም ሳይቆጥር ፈተናው ተሰርዟል ሁላችሁም አልፋችኋል የሚል መምህር፣ ከሁሉም በላይ ፍትሕ የማያውቅ፣ ፍቅሩ ለሰነፎች ያደላ አይደለምን? ፍቅሩስ ለሁሉ ቢሆን መጀመሪያ ያን ለሁሉ አይነግርምን? ይሄ አድሎ ደግሞ በእግዚአብሔር ሲሆን የበለጠ እንደሆነ እንዴት ይጠፋናል፤ ምክንያቱም መምህሩ አስቀድሞ ያን ያላለው ይሄን ያህል ተማሪ እንደሚወድቅ ስለማያውቅ ነው ብለን ልንምረው እንችላለን፤ አላዋቂነቱን አስበን፤ እግዚአብሔር ግን ሁሉን እያወቀ፣ ፍጻሜውን እያወቀ፣ አስቀድሞ ያን ከተናገረ ውሸት ተናግሯል ማለት ነው፤ ለማታለል፣ ሙሉ ለሙሉ ሰዎች ክፍዎች እንዳይሆኑ ሕጻን ልጅን በከረሜላ እንደሚደልሉት፣ የእሱን ፍቅር ያመኑትን ደልሏል ማለት ነው!?



ይሄ ከእኛ ይራቅ። እርሱ በባህሪው ንጹሁ ነው። ውሸት ከእርሱ ጋር ፈጽሞ ሕብረት የለውም። ለቃሉም ተማኝ ነው። አዳምን ያን ፍሬ ከበላክ ትሞታለህ ብሎታል፤ በዚህም አራራለትም። ሞትን ለዘላለም አስጎነጨው እንጂ። የእጁ ሥራ ቢሆን እንኳ፤ እርሱ ለቃሉ ታማኝ ስለነበረ፣ ከገነት አባረረው። ወደ ሞት ዓለም ጣለው። ሊምረው ሲያዝንለት እንኳ ቃሉን ሳይሽረው አደረገው። ምህረቱ ፍርዱን አላሸነፈውም። ፍርዱም ምህረቱን አላጠፋውም። የትኛውም ኃጢአት ያለቅጣት እንደማያልፍ ነገረን እንጂ። በገሀነም የማይቀጣ ኃጢአት ካለ፣ ያ ኃጢአት በመስቀሉ በቀራንዮ ተቸንክሯል ማለት ነው። “የሞት ሞት ትሞታለህ ቃሌን የሻርክ ቀን” ላለው ቃሉ አንድያ ልጁን ኃጢአት አደረገው። (2ኛ ቆሮ 5፥21)። በዚህም በክርስቶስ ኢየሱስ የማይምኑት ሁሉ፣ ከልጁ ሞት ጋር አልተባበሩም እና የኃጢአት ደሞዝን ይቀበላሉ። በእርሱ ጭካኔ ግን አይደለም፣ በወላጆቻቸውም በደል አይደለም፣ በራሳቸው ኃጢአት እንጂ። እርሱማ አዳምን ለዘላለም ሞት ቢጥለው ያ ጭካኔው ሳይሆን ቃሉ እና ፍርዱ ነበር። አትብላ ብሎታል። በላ። ስለዚህ ሞተ። ማንም ባያድነን የሚከሰው የለም። ግዴታ የለበትም እና። ቃሉ እና ሕጉን ነው የፈጸመው። ነገር ግን እንዲሁ ወዶናልና፣ የእጆቹን ውብ ሥራ ለሞት ይተወው ዘንድ ፍቅሩ እና ክብሩ አልፈቀደሉትም። ቃሉን ይሽር ዘንድ ደግሞ እርሱ አይለዋወጥም። ስለዚህ ያን ሞት እርሱ ተሸከመ።



ቀንበሩ ከባድ የሆነን እቃ አጎንብሰን፣ ዝቅ ብለን ትከሻችን ላይ እንደምንጭነው፣ ከዛም ቀና ብለን፣ አሁን በትከሻችን ላይ ያለውን ያ መሬት ተቀምጦ የነበረውን ከራሳችን ጋር እንደምናነሳው፤ በቃሉ ሸክም መሬት የወደቀውን ለማንሳት ዝቅ አለ፣ በትከሻው ላይ በአባቱ ፈቃድ አኖረው፣ ከራሱ ጋር ያን መሬት የወደቀውን ይዞት ተነሳ። እርሱ ወዳለበት ቦታም ወሰደው። ፍርዱን ሳይሽር ፍቅር መሆኑን ገለጠልን። ራሱን ከወደቅነው በታች አድርጎ፣ በፍቅር ትከሻው ይዞን ተነሣ። በዚህም ፍቅሩ ካለ ፍርዱ ሙሉ እንደማይሆን በኛ በሰዎች የዕለት ሕይወት ውስጥ የተገለጠውን እውነት የበለጠ አሳየን።


 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page