top of page

ree

 

ከሰባት ዓመት በፊት በጂኒቫ ስዊዘርላንድ በአንድ ዓለም አቀፍ የጠበቆች ቢሮ ውስጥ እሰራ ነበር። አንድ ጀርመናዊ ስማርት ጠበቃ በዚህ ቢሮ ውስጥ አብራን ትሰራ ነበር። በሰዓቱ አብሮን ከሚሰሩት መካከል ሕንዳዊውን ፕራሳድ አንድ ጥያቄ ጠየቀችው። ፕራሳድ ሲበዛ ሊብራል ነው። ግን የሂንዱ እምነት ተከታይ ነው። ጀርመናዊቷ ሕንድ ውስጥ ስላለው የካስት ሥርዓት ጠየቀችው። የሕንድ የካስት ሥርዓት አንድ ሰው በተገኘበት ቤተሰብ መሠረት በማህበረሰብ ውስጥ በዘላቂነት ስለሚኖረው ቦታ የሚወስን ነው። ስለዚህ አንድ ሰው ከሆነ ዘር፣ ጎሳ እና ቤተሰብ በመወለዱ ምክንያት ብቻ ፥ ሌላው ሰው ፈጽሞ ሊገዛለት እና ዝቅ ሊልለት ይገባል። ጀርመናዊቷ በዚህ ግራ በመጋባት ነበር ይሄን እንዲያስረዳት የጠየቀችው።  በተለይ የPHd ዲግሪዋን ስትማር ከሕንድ የመጣ ሌላ የPHd ተማሪ የነበረ ወዳጅ ነበራት። ይሄ ሰው ከእነሱ ጋር በአቻነት ቁጭ ብሎ የሚጫወት እና የሚበላ ነበር። ነገር ግን ከሌላ ካስት የሆነ ሕንዳዊ መጥቶ ሲቀላቀላቸው ፥ ቆሞ ይሄን ሕንዳዊ ማስተናገድ እና ለእርሱ መታዘዝ ጀመረ። ምክንያቱን ተገርመው ሲጠይቁ ያገኙት መልስ “አዲስ የመጣው ሕንዳዊ ከፍ ካለ ካስት እንደሚወለድ ነበር።” ይሄን ልትረዳው አልቻለችም። በተለይ አንድ የPHd ተማሪ የሆነ፣ በትምህርት ችሎታው እና አስተሳሰቡ ምርጥ የሆነ ሰው እንዴት እንደዚህ ዓይነት ስህተት ወይም ጅል እምነት እንደሚይዝ ግራ ተጋብታ ነበር። ፕራሳድም ይሄን በጥልቀት ሊያስረዳት አልቻለም። ምንአልባት እርሱም ያምንበት ይሆናል።

 

እናንተስ ገጥሞአችሁ አያውቅም? እንዲህ ያለ ግራ መጋባት። እዩ ጭፉን የመሰለ አታላይ ሰውዬን ከልብ አምነው እና የክርስቶስ አገልጋይ ብለው የተቀበሉ በብዙ ነገሮች ምርጥ አዋቂ የሆኑ ሰዎች ገጥሞአችሁ አያውቅም? በብዙ የእውቀት ዘርፍ የማትነቅፏቸው ሰዎች በጅል እምነት ታስረው እና ሁላችን ልክ እንዳልሆነ በምናየው አታላይ ላይ እምነታቸውን ጥለው ተመልክታችሁ አታውቁም? ለምን?

 

ጋዜጠኛ ሙሉጌታ ሉሌ የሚለው አለው። በአካዳሚሽያን እና በኢንቴሌክቿል መካከል ልዩነት አለ ይላል። አካዳሚሽያን ስለአንድ ነገር ያለው እውቀት እጅግ ጥልቅ ነው። ስለሌሎች የሕይወት ጉዳዮች ያለው እውቀት ግን ከመኃይምናን የሚያስመድበው ነው። ኢንቴሌክቿል ግን ስለሕይወት  ለመረዳት ነው ዘወትር የሚጥረው። አለማወቅ እና እርግጠኛ አለመሆን አያስፈራውም። ባይሎጂን ብቻ በመረዳት ጥሩ ሕይወት መኖር እንደማይቻል ያውቃል። ስለዚህ ሕይወት ባይሎጂ፣ ፊዚክስ፣ ጂኦግራፊ ወይም ኬምስትሪ እያለች የምትከፋፍል አይደለችም። በምልዓት ሁሉን ነገር ትተገብራለች እንጂ። እኛ የመረዳት ችግር ኖሮብን የከፋፈልነው ነገርን እንደ ሕይወት መረዳት ስህተት ነው። ለዚህ ነው በሆነ ነገር ምጡቅ የሆኑ ሰዎች በሌሎች ነገሮች ሲጃጃሉ የምናየው። ምክንያቱም እነዚህ ግርግዳ ላይ አንድ ሕይወት የተባለችን ትልቅ ስዕል ለመስቀል ከተቦረቦሩት አንዱ ቀዳዳዎች መካከል ናቸው። ወይም ቀዳዳ ውስጥ የሚገቡ ብሎኖች። ስዕሉን አረጋግቶ ለማቆም ከአንድ ቀዳዳ በላይ፣ ከአንድ ብሎን በላይ ያስፈልጋል።

 

ሕይወትን በተሻለ የተረዷት እና የተጠቀሙባት እጅግ ብሪሊያንት ያልናቸው ሰዎች አይደሉም። ይልቁንስ በየቀኑ የአስተሳሰብ ጉድለታቸውን እየሞሉ የሚያድሩ እና የዘወትር ተማሪዎች የሆኑ ሰዎች ናቸው። እነዚህ ሰዎች ለረዥም ጊዜ ሲጃጃሉ አታይዋቸውም። ዘወትር ራሳቸውን ይፈጥራሉ። ራሳቸውን ይሰራሉ። አዲስ ማንነት በመፍጠር ፥ ራሳቸውን የተሻለ ቦታ ላይ ያስቀምጣሉ። ዕድልን ይጠቀማሉ። ዕድልን ይፈጥራሉ፣ ከባከነ ዕድል ይማራሉ።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Sep 22, 2024
  • 3 min read

ክፍል ሦስት


ree


ኮምፕሌክስ ኮሜርሻል ሊቲጌሽን ብቻ የሚሰራ የጠበቆች ቢሮ ሰርቼ ነበር። ሥራው እጅግ ከባድ ነበር። አለቃችን የነበረችው ሴትዮ ከባድ የሕግ ክስ ሲኖርብን ፥ ስለ ኬዙ እንዴት እንደምታስብ ስትነግረን ፥ “እኔ እንደዚህ ከባድ ክስ ሲገጥመኝ ለጁሪው (ፍርድ የሚሰጡት አስራ ሁለቱ የማህበረሰቡ አካላት) ከሚነበበው ትዕዛዝ ነው የምጀምረው” ትል ነበር። ይሄ ማለት ዋናው ቁም ነገር “ምን ተብሎ ነው ጁሪው ሊፈርድብን የሚችለው” የሚለውን የመጨረሻ ትዕዛዝ ማየት ማለት ነው። ከመጨረሻው የጀመረ ሰው ፥ በመኃል በሚወረወርለት ነገር ትኩረቱን አያጣም። በርግጠኝነት የምነግራችሁ ማንኛውንም ነገር ለማሳካት ተነሱ ፥ እጅግ አስተዋይ ካልሆናችሁ በቀር ግባችሁን በቀላሉ የሚያስረሱ አዕምሮአችሁን የሚቆጣጠሩ ጥቃቅን ነገሮች በመኃል እንደ እንጉዳይ ይፈለፈላሉ። በመቀጠል እነዚህ በመኃል የተፈጠሩትን ነገሮች በመፍታት የተነሳችሁበትን ዓላማ ፈጽሞ ትረሳላችሁ። ከዛ ሲጀምር ይሄን ነገር ለምን እንደጀመራችሁት ራሱ ነው ግራ የሚገባችሁ።



አሁን የምነግራችሁ በቅርብ ከአንድ ጠበቃ ወዳጄ ጋር የተወያየንበት ክስ ነው። ከፍተኛ ሽያጭ የነበረው ሰውዬ ተጨማሪ ዕቃ ለማስገባት ካሽ (cash) ያጥረዋል። ደንበኞቹን ላለማጣት ደግሞ ዕቃው የግድ ያስፈልገዋል። ከዛ ወዳጁ ጋር ሄደ ብድር ጥየቃ። ወዳጁን $90 ሺ የአሜሪካ ዶላር እንዲያበድረው ጠየቀው። ይሄ ወዳጁ ጓደኛውን ለመርዳት ተስማማ። ነገር ግን የቤቱ ታይትል ላይ ሊን (የባለቤትነት ድርሻ ወይም (interest)) አኖረ። በአንድ ዓመት ውስጥም እንደሚመልስለት ቃል ገባለት። በአንድ ዓመቱ ግን ጓደኛው መመለስ አልቻለም። የመክፈያ ጊዜውን እንዲያራዝምለት ጥያቄ ቢያቀርብለትም እንቢ አለው። ከዛ ቤቱን ለሽያጭ በማቅረብ ብድሩን ለመመለስ ተካሰሱ። ፍርድ ቤቱ “ቤቱ ለሀራጅ ሽያጭ እንዲቀርብ” ወሰነ። የሁለቱ ሰዎች ወዳጅነት ወደ ጠላትነት ተቀየረ።



ተመልከቱ። የጓደኛው ግብ ወዳጁን መርዳት ነበር። ወዳጅነቱን የበለጠ ማጠንከር ነበር። በብድሩ መጨረሻ ላይ ጓደኛውን እንደሚያጣ ቢያቅ ኖሮ አያበድርም ነበር። እርሱ ያሰበው የጓደኛውን የአሁን ችግር መፍታት እንጂ ነገ ጠላት እየፈጠረ እንደሆነ ፈጽሞ አልገባውም። ምክንያቱም የዚህ መጨረሻ ምን ሊሆን እንደሚችል ፈጽሞ አልገመተም። ሌሎች ሰዎች በተመሳሳይ ምክንያት ከወዳጅነት ወደ ጠላትነት እንደተቀየሩ ቢያቅም ይሄ ግን በእነርሱ ላይ አይደርስም ብሎ አሰበ። የእነሱ ወዳጅነት ከዚህ ነጻ እንደሆነ ገመተ። ከመጨረሻው ለመጀመር አለመፈለግ ማለት ይሄ ነው።



በክርስትና ሃይማኖት ውስጥ ያለን ሰዎች ከመጨረሻው ቀን ብንጀምር ብዙ ነገር የሚቀየር ይመስለኛል። ምንአልባት ብዙዎቻችን ቀላል የማይባለውን ጊዜ ምንም ከዚህ ትዕዛዝ ጋር በማይገናኝ መልኩ እያሳለፍን መሆኑን ይገባን ነበር። የመጨረሻው ትዕዛዝ ይሄ ነው “ማነው ተርቤ ያበላኝ፥ ማነው ተጠምቼ ያጠጣኝ፥ ማነው እንግዳ ሆኜ የተቀበለኝ፥ ማነው ታርዤ ያለበሰኝ ፥ ማነው ታምሜ የጠየቀኝ ፥ ማነው ታስሬ የጎበኘኝ።” “የተራበ ማነው ያበላው” ተባብለው ክርስቲያኖች ሲጣሉ እስካሁን አላየንም። በብዙ በዚህ ቀን መለኪያ ባልሆኑ መስፈርቶች ግን ክርስቲያኖች በየቀኑ በሁሉም ቦታ ይከራከራሉ። ይጣላሉ። የጁሪው ትዕዛዝ በመኃል ተዘንግቷል። ሁሉን ነገር ትቶ ይሄ የመጨረሻው ቀን መጠይቅ (checklist) ላይ ያተኮረ ሰው በመጨረሻው ቀን ከማንም በቀደመ በቀኙ ለመቆም የበቃ ይሆናል።



ከመጨረሻው አለመጀመር። በቅርብ በጣም በሥራ ተወጠርኩኝ። በመኃል በየቀኑ ሥሰራ የነበረውን የአካል እንቅስቃሴ በዚህ ውጥረት ምክንያት ተውኩኝ። የሆነ ሰዓት ባነንኩኝ። ምንድነው የዚህ ሥራ ግብ? ጤናዬን እና ዘላቂ አዕምሮአዊ እና አካላዊ ማንነቴን አሳልፌ የምሰጥ ከሆነ። የሥራ መጨረሻ ለማረፍ ከሆነ፤ ይሄን እረፍት ማግኘት የምችለው ጤናዬ እስካለ ድረስ ብቻ ነው። ስለዛ ግቡን እየዘነጋው ነው። ቅድመ ተከተሉ ጠፍቶኛል።



ከመጨረሻ ቢጀምሩ ኖሮ ዛሬ በሀገራችን ያሉ የእርስ በርስ ጦርነቶች የሚካሄዱ ይመስላችዋል? ግቡ የተማሩ፣ ጤናማ የሆኑ፣ አስተዋይ እና ክብራቸው የተጠበቁ ማህበረሰቦችን ለመፍጠር ከሆነ ፥ የተራዘመ የእርስ በእርስ ጦርነት ይሄን ግብ ሲያሳካ አይታችሁ ታውቃላችሁ? አሁን ግቡ ተረስቷል። ምክንያቱም በመኃል ብዙ ደም ፈሷል። ብዙ ሰው እና ንብረት እንዳይሆን ሆኗል። አሁን ግቡ ግለሰባዊ እና ጀብደኝነት ሆኗል። ዛፉን እንዳታዩ ትፈልጋላችሁ ፥ ደን ውስጥ ደብቁት።


መኪና በጂፒየስ ስትነዱ ምንድነው የምታደርጉት? የመጨረሻውን፣ መዳረሻችንን አድራሻ እናስገባለን። ያ ምን ይሰጠናል? የተዘጉ መንገዶችን ትቶ ትራፊክ ያልበዛባቸውን አማራጮች ያሳየናል። በመኃል መንገድ ጀምረን ሳይቀር፣ መንገዱ ከተጨናነቀ ሌላ አቅጣጫ ይጠቁመናል። መጨረሻውን ስላስገባነው፣ አማራጮችን ማሳየት አይከብደውም። መንገድ ስንስት ሳይቀር በቶሎ ወደ መዳረሻችን አቅጣጫ ይመልሰናል። ለምን ታዲያ ይሄን በሕይወት፣ በኑሮአችን አንጠቀምም? ከመነሳታችን፣ ምንም ነገር ከማረጋችን በፊት መዳረሻችንን ማየት፣ የት መድረስ እንደምንፈልግ በግልጽ ማወቅ። በየመኃሉ ለመዳረሻችን ምን ያህል እየቀረብን እንደሆነ መመልከት፣ ልክ እንደ ጂፒየሱ መዳረሻችንን ፈጽሞ ከእይታችን አለማራቅ። ዘወትር ምንድነው ግን ማሳካት የምፈልገው ብሎ መጠየቅ። ንግግር ጀምሩ ፥ እንዴት በፍጥነት ያ ንግግር ሊያሳካው ካለመው ዓላማ ስትወጡ በመኃል ራሳችሁን ታገኙታላችሁ። ጂፒየሱን የሳተ ንግግር ማለት ይሄ ነው።


በትዳር ውስጥ፣ በጓደኝነት ውስጥ ያላችሁ ሰዎች ታውቃላችሁ። አንደኛው አካል በክርክር እና ነገሮችን በማስረዳት እንዲሁም በቋንቋ አጠቃቀም በጣም ጎበዝ ይሆናል። ከዛ ልክ የሆነ ችግር ተፈጥሮ ማውራት ስትጀምሩ ፥ ያ ሰው አፍ አፋችሁን እየመታ ዝም ያሰኛችዋል። ክርክሩን ሁልጊዜ ይረታል። በዚህም ለጊዜው አሸናፊ ሆኖ ይወጣል። ግን የተሸነፈውን፣ ብዙ ያላወራውን ሰው ልብ ፈጽሞ አላሸነፈውም። ጭራሽ ያ ሰው በውስጡ እየመረረው ነው። ወይ ያን ሰው የሚያስመርር ነገር ይሰራል ወይም ይሄን ወዳጅነት ቀስ እያለ ይርቀዋል። ፍቺውን ይጀምራል። ግን ግቡ ይሄ ነበር? የዛ ክርክር እና ውይይት ግቡ አንዱ አንዱን መገነዛዘብ እና ልባቸውን ማሸነፍ ነበር። ያን ወዳጅነት፣ ያን ትዳር እና ግንኙነት ወደ በለጠ ጥልቀት መውሰድ ነበር። ግን በመኃል የራስን ልክነት ማሳየት ሆነ ግቡ። ግቡ ክርክሩን ማሸነፍ ሆነ። ውጊያውን አሸንፎ ጦርነት ላይ መረታት (wining the battle but losing the war) ይለዋል ስትራቴጂስቱ ሰን ዙ። ከመጨረሻው የማይጀምር ሰው ሁልጊዜ ችግር ያልሆነንን ነገር ሲፈታ ጊዜውን ይጨርሳል።


እስቲ አስቡት ዘወትር መጨረሻችንን ብናስብ። እሱም እንደምንሞት። በጣም በቅርቡ ዓለምን እንደምንረሳ ፥ በጣም በቅርቡ እኛም በዓለም ፈጽሞ እንደምንረሳ ብንገነዘብ እና ያን በየቀኑ ብናስብ የሚኖረንን ውሳኔ አስቡ? ይሄ ፈጽሞ የማይቀር መጨረሻ ነው። ስለሚቀጥለው ነገር ባናውቅ እንኳ ሁሉም ስለሚደርስበት መጨረሻ ሞት ግን እናውቃለን። ያ ዕለታችንን የምንኖርበትን መንገድ ይለውጠዋል። ለሚወረወርብን ሁሉ መልስ የምንሰጥበት ምንም ጊዜ አይኖረንም። በጣም አንኳር የሆኑ ነገሮች ብቻ የኛን ትኩረት ያገኙ ነበር። ያ ደግሞ የብዙ ችግር፣ እጅግ የብዙ ችግር መፍቻ ቁልፍ ነው።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Sep 16, 2024
  • 2 min read


ree

አውግስጢኖስ በ'City of God" መጽሐፉ ስለዚህ ዓለም ደስታ እና ስቃይ እንዲህ ይላል ፥ "የዚህ ዓለም ደስታ ለኃጥዕም ለጻዲቅም ይሰጣሉ፣ ዝናቡን ለሁለቱም እንደሚያወጣ፣ ፀሐይንም ለኃጥዑም ለጻድቁም እንደሚያቆማት። ይሄን ያደረገው የዚህ ዓለም መልካም ነገር ምንም አለመሆኑን ለመረጡት እና ለወደዱት ሲነግራቸው ነው፤ ይሄ ብቻ ግን አይደለም በመግቦቱ ቸርነት ኃጥአን ወደእሱ እንዲሳቡም እንጂ።



መከራም በኃጥዕሙ በጻድቁም ላይ ይመጣል፤ ጻድቁን ግን እንደወርቅ እያነጻው ፥ በመከራ እሳት ሲያልፍ ያበራል። ኃጥዕን ግን በጻድቃን ላይ የደረሰው መከራ ቢደርስባቸውም ያ ወርቅ የሆነውን ጻድቅ ያነጻ እሳት ፥ ገለባ የሆነውን ኃጥዕ ግን ያጨሰዋል። ያ እሳት ለአንዱ ውበት ለሌው ጭስ ይሆናል።



አንዱ መስቀል በቀኝ ለተሰቀለው የገነት መግቢያ ቁልፍ ሲሆን ፥ ያው መስቀል በግራ ለተሰቀለው የሲዖል ሩጫውን አፋጠነው። በክርስቶስ ለሆኑት በዚህ ዓለም ደስታ እና መከራ መካከል አንዳች ልዩነት የለም።



ሁለቱም የምስጋና ምንጮች ናቸው። አጥንታችንን ሰብሮ ሲጠግነን ፥ ያን የምህረት ፏፏቴ ነፍሳችን ታሸተዋለች። በበረክት ሲሞላንም ያን የቸርነት ምንጭ ፥ ነፍሳችን ትጠጣዋለች።



ለኃጥዓንም እንደዚሁ። በዚህ ዓለም ደስታ እና መከራ መካከል ምንም ልዩነት የለውም። ሲያገኙ በትዕቢት የአምላክን መኖር ረስተው፣ በደሃው ላይ ይረማመዳሉ፣ በሆዳምነት እና በትዕቢት ወደ ጥልቁ ይሰምጣሉ።



በመከራ ደግሞ አፋቸውን በአምላካችን ላይ ይከፍታሉ፣ ይረግሙታል፣ አንተ ብትኖር ይሄ ሁሉ ይደረጋል ይላሉ፣ እስቲ ካለህ አሳየን እያሉ አምላካችንን እኩያቸው ያደርጉታል ፥ በዝምታው የፍቅርን በር ቢከፍትላቸውም እነሱ ግን በመታወራቸው የሲዖልን በር በርግደው ከውስጥ በራሳቸው ላይ ይቀረቅሩታል።"



በሌላም ጎኑ በዚህ ዓለም ላይ ብዙ ነገሮች በኛ አጠቃቀም ላይ የተመሰረቱ ናቸው። እኔ ቢላዋ መጀመሪያ ለምን ጉዳይ እንደተፈጠረ አላውቅም። ግን አንዳንድ ሰዎች መልካሙን ምግብ ለማዘጋጀት ቢላዋን ለመክተፊያነት ይጠቀማሉ። አንዳንዶች ግን ይሄንኑ ተመሳሳይ ነገር ምትክ አልባውን የሰውን ልጅ ሕይወት ለማጥፋት ቢላዋን ይጠቀሙታል። በዚህ ዓለም ያለ አብዛኛው ነገሮች እንደ ቢላዋ ናቸው። የኛ እጆች ናቸው ውጤቱን የሚወስኑት። ለአንዱ የገነት መግቢያ የነበረ መስቀል ፥ ለአንዱ የሲዖል ድልድይ ይሆናል። መስቀልነቱ አይደለም የተቀየረው። በመስቀሉ ላይ የሰፈሩት ራሶች እንጂ።



ለአንዱ ክፉ የሆነውን አጋጣሚ፣ አንዱ ግን ያንኑ መሳሪያ የበረከት ውሃ ለማፍለቅ ይጠቀምበታል። በዚህ ዓለም ትልቁ ጦርነት የሚካሄደው በውስጣችን ነው። በስሜት እና በእውቀት መኃል። ስሜት ፈጽሞ በእውቀት፣ በቁጥር፣ በማስረጃ እና በምክንያት መመራት አይወድም። ግን እንደዛም ሆኖ እጅግ ኃይለኛ ነው። ማንም ከስሜቱ ጋር ፊትለፊት ጦርነት ገጥሞ አያሸንፍም። ቅዱስ ጳውሎስ ሳይቀር “ማድረግ የምወደውን ሳይሆን ማድረግ ያልፈለኩትን፣ በብልቶቼ ላይ ግን የሰለጠነውን ያንን አደርጋለሁ” አለ። የምክንያት ክፍላችን ደግሞ በማስረጃ እና ምክንያት፣ በቁጥር እና በማመዛዘን ይመራል።


ይሄ ክፍላችን ስሜትን በጥበብ የረታ ቀን ፥ በኛ ፊት ውድቀት ፀሐይ የለውም። ያን ለማድረግ ግን ይሄን ጦርነት በጥልቀት መገንዘብ ያስፈልጋል። ያለረፍት ሪፍሌክት ማድረግ የሕይወት አንኳር ተግባራችን መሆን አለበት። እውነትን ማወቅ እና ማግኘት የሚያስደስተን መሆን አለበት። የዛኔ ለአንዱ ክፉ የሆነው ነገር ለኛ ጥቅሙ ይታየናል። ራሳችንን ከእውነት ጋር አስታርቀን መጓዝ አይቸግረንም። የዛኔ እኛ የያዝነው ቢላዋ የሌሎች መጥገቢያ እንጂ መቅጠፊያ አይሆንም። የነካው ሁሉ ይባረክለታል የሚለው ይሄን እጅ ነው። እንደ ኢዮብ ያለ እጅን። በመጥገብም ሆነ በመጉደል በፊቱ እና በአንደበቱ አምላኩን በድሎ የማያውቅ ሰው የያዘው ቢላዋ ማንንም አያስፈራም።


ያ ሰው ስሜቱን ለምክንያት ያስገዛ ነው። ያ ሰው በውስጡ ያለውን ጦርነት ያሸነፈ ነው። ያ ሰው ሀገርን ከሚገዛ በላይ ገዢ ነው። ሀገር ገዢው ፈጽሞ ሊገዛ ያልቻለውን የውስጡን የስሜት ፈረስ በቀጭን የማስተዋል ክር ወደ ፈቀደው ይስበዋልና።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page