top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Oct 13, 2024
  • 3 min read




የየቀን ትግሌ ይሄ ነው። ተዋጊ መሆን። በርግጥ የእንግሊዘኛው ቃል ነው የሚገልጽልኝ። Survivor መሆን። victimhood እኔ ጋር የለም። ሌሎች ላይ ከሆነው የባሰ ነገር በእኔ ምንም ሆኖ አያውቅም። ግን በሕይወቴ እጅ ለመስጠት እና ለማማረር ከበቂ በላይ የሆነ ነገር ውስጥ አልፌያለሁ። ከልጅነት እስከ እውቀት። ግን ሁልጊዜ survivor ነኝ።



በእኔ ውስጥ እንዲሰለጥን የማልፈልገው አስተሳሰብ አለ። እጅ መስጠት። ተበዳይ መሆን። ተፈጥሮ በድላኛለች፣ አምላክ ትቶኛል ብሎ ማሰብ። በእኔ ይሄ አስተሳሰብ ቤቱን ሰርቶ አያውቅም። የሆነውን ለመቀበል ነው የምቸኩለው። በሆነው ውስጥ የተሻለውን እና ማግኘት የምችለውን ነገር ለማግኘት ነው የምሰራው። ልቤ አንበሳ እንዲሆን ነው የማደርገው። አላውቀውም ፥ አልችለውም ብዬ አልቀመጥም። ዛሬ ባላውቀው፣ ዛሬ ባይኖረኝ፣ ዛሬ ባልችለው ነገ ግን እንደሚለውጥ እና ያንንም እንደምለውጥ አምናለሁ። እንደዛ ዓይነት ታሪኮች እንጂ የመበደል እና ሌሎችን ሰይጣን አድርጎ የመሳል ታሪክ እና ትርክት እኔ ጋር ብዙ ቦታ እንዲኖረው አልፈቅድም። በእኔ ላይ የተፈጠሩ ብዙ ነገሮችን የምቆጣጠረው ላይሆን ይችላል። ነገር ግን ከሁኔታዎች በታች ራሴን ለማድረግ ፈቅጄ አላውቅም። ዊል ስሚዝ እንዳለው “በትሬድ ሚል ላይ መሞት ከሆነም ለመሞት ዝግጁ ነኝ ፥ ግን አላቋርጥም።” እርዳታ ቢስ እና ተስፋ የሌለኝ ሆኜ ለመታየት አልፈቅድም። ለራሴ ሌላ ትርክት ነግረዋለሁ እንጂ። ሰዎች ወደ እኔ መጥተው “ልጅ ሆኜ አባቴ እንዲህ ስላረገኝ ነው፣ እናት አባቴ እንዲህ ስላረጉኝ ነው፣ ልጅ ስለሆንኩኝ ነው፣ ወይም አስተዳደጌ ይሄ ስለሆነ ነው” ሲሉኝ ፥ እነዚህ ሰዎች ከዚህ በፊት በእነሱ ላይ ለተከሰተ ነገር ምን ያህል ራሳቸውን ባሪያ አድርገው እንደሰጡ ነው የማየው። አሁን ያ የሚሉት ስቃይ እና ማነቆ ባይኖር እንኳ ፥ አዲስ ማንነት ፈጥሮ ፥ አዲስ ማንነት ሰርቶ ከዛ ለመውጣት ፈቃደኞች አይደሉም። ነገር ግን የትላንት ባሪዮች ሲሆኑ ሳይ አዝናለሁ። ዛሬን እና ነገን ለትላንት ማስገበር።



የሰው ልጅ ልዩ ባህሪው ፈጣሪ መሆኑ ነው። የመፍጠር ችሎታችን ነው ከሌሎች ሁሉ የለየን። የማንፈጥር ካልሆንን ፥ የጎደለ ስብዕና ነው ያለን። መፍጠር የሚጀምረው ደግሞ ራስን ለዛሬ እና ለነገ በድጋሚ በሚስማማ መልኩ በመፍጠር ነው። ልክ ነው ብዙ መከራ ደርሶብን ይሆናል፤ ግን ዓይናቸውን፣ ጆሮአቸውን፣ እንደውም ተጨማሪ አካላቸውን አጥተው እኛ ፈጽሞ በሕይወት ዘመናችን ሁሉ ሰርተን የማናውቀውን ነገር የሚሰሩ እና ያሳኩ ፥ ዓለምን ጉድ ያሰኙ ሰዎች አልገጠሟችሁም?



በሕይወታቸው ላይ በደረሰ አንድ ሁለት ሦስት ክስተቶች ምክንያት ሙሉ ሕይወታቸውን አሳልፈው የሚሰጡ ሰዎችን ተመልከቱ። እነዚህ ሰዎች እነዚህን አጋጣሚዎች ወደ ዕድል ለመለወጥ አለመቻላቸው አስገራሚ ነው። በእኔ ላይ በራሴ ጥፋትም ሆነ ያለ እኔ በደል የደረሱብኝን ክፉ አጋጣሚዎች ሁሉ አፈቅራቸዋለሁ። እነዚህ ራሴን በጥልቀት እንዳውቅ እና ነጥሬ በአዲስ ማንነት እንድነሳ ያደረጉኝ ናቸው። ራሴን በድጋሚ የፈጠርኩባቸው ክስተቶች ናቸው። ያለእነሱ እኔ አይደለሁም።



ከ100% በታች ኃላፊነት በሕይወት የሚወስዱ ሰዎች፣ ለደስታቸውም ሆነ ለሐዘናቸው እነሱ ብቻ ተጠያቂ እንዳልሆኑ የሚገልጹ፣ መቆጣጠር ስለማይችሉት፣ መለወጥ ስለማይችሉት ነገር በማሰብ ጊዜያቸውን የሚያጠፉ፣ ወደ ፊት መሄድ ሳይሆን ከጊዜ ማዕበል ጋር መጋፋት የሚወዱ ቪክተሞች አሉ። አሉ ደግሞ እሱ ነው፣ እሷ ናት፣ እከሌ ነው፣ ሚስቴ ናት፤ እርሱ በሕይወቴ እስኪመጣ ድረስ ሰላማዊ ነበርኩኝ፤ እከሌ እስኪቀላቀለን ድረስ ሀሴት ነበር ሕይወታችን የሚሉ ፥ የሚደፈድፉበት ነገር የሚመስጣቸው፤ ክርስቶስን ሰቃዮች ፥ በበጉ ደም መፍሰስ እነርሱ የሰሩት ኃጢአት እንዲደመሰስ የሚሹ ፥ ከሳሾች አሉ። አሉ ደግሞ በሕይወታቸው የተፈጠረውን ነገር ከሥሩ ከመፍታት ይልቅ ፥ ትንሽ በማልቀስ፣ ትንሽ በመተንፈስ፣ ትንሽ በማማረር ወይም ችግራቸውን የሚረሱበት ከNetflix እስከ ሲጋራ በመሳብ ለጊዜው እፎይ ማለት ብቻ የሚመርጡ ቪክተሞች። በጣም የሚገርመው እነዚህ ቪክተሞች ሁሌ ልክ ናቸው። ሌላው እና ሌሎች እንጂ እነርሱ ሁልጊዜ ልክ ናቸው። ስለዚህ ለውድቀታቸው ከሳሾች ናቸው። ቪክተሞች መሆናችሁን ለማወቅ ቀላሉ መንገድ የተቀየማችሁት ሰው እንዳለ እና እንደሌለ መጠየቅ ነው። ካለ የቪክተም አስተሳሰብ ተጠቂዎች ናችሁ። ይቅር ማለት የማይችል ልብ ያለው ሰው ፥ መፍጠር አይችልም። ሁሉን ነገር ሲሪየስሊ መውሰድ የሚቀናው ሰው ፥ አዕምሮ የመፍጠር ችሎታውን የተነፈገ ነው። ምክንያቱም በራሱ ላይ በተፈጠረው ነገር መሳቅ የማይችል ሰው የመማር አቅሙን አጥቷል።



ማማረር እና ማሳበብ ልጆች ከወላጆቻቸው የሚማሩት ነው። እንደ እኛ ሀገር ባለ ፖለቲካ ደግሞ ማማረር የአጭር ጊዜ እንጀራ ነው። ቪክተም መሆን ለጥቂቶች የስልጣን ኮርቻ ነው። ትውልድ ግን ይሞታል። የትውልድ አዕምሮ በሙሉ ከጥቅም ውጪ ይሆናል። ትላንት ኦሮሞ ነበር። ዛሬ ደግሞ አማራ ሆኗል ይሄን የቪክተም ስነልቦና የሚጋተው። እስቲ አንድ የተሳካለት፣ ሕይወቱ ያማረለት፣ በፈጠራ ችሎታው እና በአገልግሎቱ አንቱ የተባለ ግን የቪክተም አስተሳሰብ የሚያራምድ አንድ ሰው ጥቀሱልኝ? አንድ ማምጣት አትችሉም። አንድ!!!



ለምን? መልሱ ግልጽ ነው። ቪክተም ስነልቦና መጀመሪያ የሚያደርገው የመፍጠር ችሎታችን መንፈግ ነው። 100% ስለሕይወቱ ኃላፊነት የማይወስድ ሰው መፍጠር አይችልም። ጥርጣሬ የሌለው ሰው፣ ሕይወትን ከሌሎች መነጽር አንጻር ለማየት የማይችል ሰው፣ ሌሎችን ይቅር ለማለት የማይፈቅድ ሰው ፥ አንቱ ሊባል አይችልም።



አዎ፦ በየቀኑ ተዋጊ ነኝ። ከሕይወት ጋሪ ጋር ወደ ፊት በመሮጥ የምተባበር፤ የኋላዬን እየረሳው ወደፊት የሚጠብቀኝን ለማየት እና ለመያዝ የምዘረጋ ነኝ። Survivor ነኝ። የደረሰብኝ ሁሉ ከትምህርት የዘለለ ትርጉም የለውም። በሕይወቴ መጨረሻ “የተሰጠኝን አበዛውት፣ በብዙ እጥፍ አድርጌም ለሰጪው ሰጠውት” ለማለት የምዘረጋ እንጂ የምጎተት አይደለውም።

 
 
 


 

ከሰባት ዓመት በፊት በጂኒቫ ስዊዘርላንድ በአንድ ዓለም አቀፍ የጠበቆች ቢሮ ውስጥ እሰራ ነበር። አንድ ጀርመናዊ ስማርት ጠበቃ በዚህ ቢሮ ውስጥ አብራን ትሰራ ነበር። በሰዓቱ አብሮን ከሚሰሩት መካከል ሕንዳዊውን ፕራሳድ አንድ ጥያቄ ጠየቀችው። ፕራሳድ ሲበዛ ሊብራል ነው። ግን የሂንዱ እምነት ተከታይ ነው። ጀርመናዊቷ ሕንድ ውስጥ ስላለው የካስት ሥርዓት ጠየቀችው። የሕንድ የካስት ሥርዓት አንድ ሰው በተገኘበት ቤተሰብ መሠረት በማህበረሰብ ውስጥ በዘላቂነት ስለሚኖረው ቦታ የሚወስን ነው። ስለዚህ አንድ ሰው ከሆነ ዘር፣ ጎሳ እና ቤተሰብ በመወለዱ ምክንያት ብቻ ፥ ሌላው ሰው ፈጽሞ ሊገዛለት እና ዝቅ ሊልለት ይገባል። ጀርመናዊቷ በዚህ ግራ በመጋባት ነበር ይሄን እንዲያስረዳት የጠየቀችው።  በተለይ የPHd ዲግሪዋን ስትማር ከሕንድ የመጣ ሌላ የPHd ተማሪ የነበረ ወዳጅ ነበራት። ይሄ ሰው ከእነሱ ጋር በአቻነት ቁጭ ብሎ የሚጫወት እና የሚበላ ነበር። ነገር ግን ከሌላ ካስት የሆነ ሕንዳዊ መጥቶ ሲቀላቀላቸው ፥ ቆሞ ይሄን ሕንዳዊ ማስተናገድ እና ለእርሱ መታዘዝ ጀመረ። ምክንያቱን ተገርመው ሲጠይቁ ያገኙት መልስ “አዲስ የመጣው ሕንዳዊ ከፍ ካለ ካስት እንደሚወለድ ነበር።” ይሄን ልትረዳው አልቻለችም። በተለይ አንድ የPHd ተማሪ የሆነ፣ በትምህርት ችሎታው እና አስተሳሰቡ ምርጥ የሆነ ሰው እንዴት እንደዚህ ዓይነት ስህተት ወይም ጅል እምነት እንደሚይዝ ግራ ተጋብታ ነበር። ፕራሳድም ይሄን በጥልቀት ሊያስረዳት አልቻለም። ምንአልባት እርሱም ያምንበት ይሆናል።

 

እናንተስ ገጥሞአችሁ አያውቅም? እንዲህ ያለ ግራ መጋባት። እዩ ጭፉን የመሰለ አታላይ ሰውዬን ከልብ አምነው እና የክርስቶስ አገልጋይ ብለው የተቀበሉ በብዙ ነገሮች ምርጥ አዋቂ የሆኑ ሰዎች ገጥሞአችሁ አያውቅም? በብዙ የእውቀት ዘርፍ የማትነቅፏቸው ሰዎች በጅል እምነት ታስረው እና ሁላችን ልክ እንዳልሆነ በምናየው አታላይ ላይ እምነታቸውን ጥለው ተመልክታችሁ አታውቁም? ለምን?

 

ጋዜጠኛ ሙሉጌታ ሉሌ የሚለው አለው። በአካዳሚሽያን እና በኢንቴሌክቿል መካከል ልዩነት አለ ይላል። አካዳሚሽያን ስለአንድ ነገር ያለው እውቀት እጅግ ጥልቅ ነው። ስለሌሎች የሕይወት ጉዳዮች ያለው እውቀት ግን ከመኃይምናን የሚያስመድበው ነው። ኢንቴሌክቿል ግን ስለሕይወት  ለመረዳት ነው ዘወትር የሚጥረው። አለማወቅ እና እርግጠኛ አለመሆን አያስፈራውም። ባይሎጂን ብቻ በመረዳት ጥሩ ሕይወት መኖር እንደማይቻል ያውቃል። ስለዚህ ሕይወት ባይሎጂ፣ ፊዚክስ፣ ጂኦግራፊ ወይም ኬምስትሪ እያለች የምትከፋፍል አይደለችም። በምልዓት ሁሉን ነገር ትተገብራለች እንጂ። እኛ የመረዳት ችግር ኖሮብን የከፋፈልነው ነገርን እንደ ሕይወት መረዳት ስህተት ነው። ለዚህ ነው በሆነ ነገር ምጡቅ የሆኑ ሰዎች በሌሎች ነገሮች ሲጃጃሉ የምናየው። ምክንያቱም እነዚህ ግርግዳ ላይ አንድ ሕይወት የተባለችን ትልቅ ስዕል ለመስቀል ከተቦረቦሩት አንዱ ቀዳዳዎች መካከል ናቸው። ወይም ቀዳዳ ውስጥ የሚገቡ ብሎኖች። ስዕሉን አረጋግቶ ለማቆም ከአንድ ቀዳዳ በላይ፣ ከአንድ ብሎን በላይ ያስፈልጋል።

 

ሕይወትን በተሻለ የተረዷት እና የተጠቀሙባት እጅግ ብሪሊያንት ያልናቸው ሰዎች አይደሉም። ይልቁንስ በየቀኑ የአስተሳሰብ ጉድለታቸውን እየሞሉ የሚያድሩ እና የዘወትር ተማሪዎች የሆኑ ሰዎች ናቸው። እነዚህ ሰዎች ለረዥም ጊዜ ሲጃጃሉ አታይዋቸውም። ዘወትር ራሳቸውን ይፈጥራሉ። ራሳቸውን ይሰራሉ። አዲስ ማንነት በመፍጠር ፥ ራሳቸውን የተሻለ ቦታ ላይ ያስቀምጣሉ። ዕድልን ይጠቀማሉ። ዕድልን ይፈጥራሉ፣ ከባከነ ዕድል ይማራሉ።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Sep 22, 2024
  • 3 min read

ክፍል ሦስት




ኮምፕሌክስ ኮሜርሻል ሊቲጌሽን ብቻ የሚሰራ የጠበቆች ቢሮ ሰርቼ ነበር። ሥራው እጅግ ከባድ ነበር። አለቃችን የነበረችው ሴትዮ ከባድ የሕግ ክስ ሲኖርብን ፥ ስለ ኬዙ እንዴት እንደምታስብ ስትነግረን ፥ “እኔ እንደዚህ ከባድ ክስ ሲገጥመኝ ለጁሪው (ፍርድ የሚሰጡት አስራ ሁለቱ የማህበረሰቡ አካላት) ከሚነበበው ትዕዛዝ ነው የምጀምረው” ትል ነበር። ይሄ ማለት ዋናው ቁም ነገር “ምን ተብሎ ነው ጁሪው ሊፈርድብን የሚችለው” የሚለውን የመጨረሻ ትዕዛዝ ማየት ማለት ነው። ከመጨረሻው የጀመረ ሰው ፥ በመኃል በሚወረወርለት ነገር ትኩረቱን አያጣም። በርግጠኝነት የምነግራችሁ ማንኛውንም ነገር ለማሳካት ተነሱ ፥ እጅግ አስተዋይ ካልሆናችሁ በቀር ግባችሁን በቀላሉ የሚያስረሱ አዕምሮአችሁን የሚቆጣጠሩ ጥቃቅን ነገሮች በመኃል እንደ እንጉዳይ ይፈለፈላሉ። በመቀጠል እነዚህ በመኃል የተፈጠሩትን ነገሮች በመፍታት የተነሳችሁበትን ዓላማ ፈጽሞ ትረሳላችሁ። ከዛ ሲጀምር ይሄን ነገር ለምን እንደጀመራችሁት ራሱ ነው ግራ የሚገባችሁ።



አሁን የምነግራችሁ በቅርብ ከአንድ ጠበቃ ወዳጄ ጋር የተወያየንበት ክስ ነው። ከፍተኛ ሽያጭ የነበረው ሰውዬ ተጨማሪ ዕቃ ለማስገባት ካሽ (cash) ያጥረዋል። ደንበኞቹን ላለማጣት ደግሞ ዕቃው የግድ ያስፈልገዋል። ከዛ ወዳጁ ጋር ሄደ ብድር ጥየቃ። ወዳጁን $90 ሺ የአሜሪካ ዶላር እንዲያበድረው ጠየቀው። ይሄ ወዳጁ ጓደኛውን ለመርዳት ተስማማ። ነገር ግን የቤቱ ታይትል ላይ ሊን (የባለቤትነት ድርሻ ወይም (interest)) አኖረ። በአንድ ዓመት ውስጥም እንደሚመልስለት ቃል ገባለት። በአንድ ዓመቱ ግን ጓደኛው መመለስ አልቻለም። የመክፈያ ጊዜውን እንዲያራዝምለት ጥያቄ ቢያቀርብለትም እንቢ አለው። ከዛ ቤቱን ለሽያጭ በማቅረብ ብድሩን ለመመለስ ተካሰሱ። ፍርድ ቤቱ “ቤቱ ለሀራጅ ሽያጭ እንዲቀርብ” ወሰነ። የሁለቱ ሰዎች ወዳጅነት ወደ ጠላትነት ተቀየረ።



ተመልከቱ። የጓደኛው ግብ ወዳጁን መርዳት ነበር። ወዳጅነቱን የበለጠ ማጠንከር ነበር። በብድሩ መጨረሻ ላይ ጓደኛውን እንደሚያጣ ቢያቅ ኖሮ አያበድርም ነበር። እርሱ ያሰበው የጓደኛውን የአሁን ችግር መፍታት እንጂ ነገ ጠላት እየፈጠረ እንደሆነ ፈጽሞ አልገባውም። ምክንያቱም የዚህ መጨረሻ ምን ሊሆን እንደሚችል ፈጽሞ አልገመተም። ሌሎች ሰዎች በተመሳሳይ ምክንያት ከወዳጅነት ወደ ጠላትነት እንደተቀየሩ ቢያቅም ይሄ ግን በእነርሱ ላይ አይደርስም ብሎ አሰበ። የእነሱ ወዳጅነት ከዚህ ነጻ እንደሆነ ገመተ። ከመጨረሻው ለመጀመር አለመፈለግ ማለት ይሄ ነው።



በክርስትና ሃይማኖት ውስጥ ያለን ሰዎች ከመጨረሻው ቀን ብንጀምር ብዙ ነገር የሚቀየር ይመስለኛል። ምንአልባት ብዙዎቻችን ቀላል የማይባለውን ጊዜ ምንም ከዚህ ትዕዛዝ ጋር በማይገናኝ መልኩ እያሳለፍን መሆኑን ይገባን ነበር። የመጨረሻው ትዕዛዝ ይሄ ነው “ማነው ተርቤ ያበላኝ፥ ማነው ተጠምቼ ያጠጣኝ፥ ማነው እንግዳ ሆኜ የተቀበለኝ፥ ማነው ታርዤ ያለበሰኝ ፥ ማነው ታምሜ የጠየቀኝ ፥ ማነው ታስሬ የጎበኘኝ።” “የተራበ ማነው ያበላው” ተባብለው ክርስቲያኖች ሲጣሉ እስካሁን አላየንም። በብዙ በዚህ ቀን መለኪያ ባልሆኑ መስፈርቶች ግን ክርስቲያኖች በየቀኑ በሁሉም ቦታ ይከራከራሉ። ይጣላሉ። የጁሪው ትዕዛዝ በመኃል ተዘንግቷል። ሁሉን ነገር ትቶ ይሄ የመጨረሻው ቀን መጠይቅ (checklist) ላይ ያተኮረ ሰው በመጨረሻው ቀን ከማንም በቀደመ በቀኙ ለመቆም የበቃ ይሆናል።



ከመጨረሻው አለመጀመር። በቅርብ በጣም በሥራ ተወጠርኩኝ። በመኃል በየቀኑ ሥሰራ የነበረውን የአካል እንቅስቃሴ በዚህ ውጥረት ምክንያት ተውኩኝ። የሆነ ሰዓት ባነንኩኝ። ምንድነው የዚህ ሥራ ግብ? ጤናዬን እና ዘላቂ አዕምሮአዊ እና አካላዊ ማንነቴን አሳልፌ የምሰጥ ከሆነ። የሥራ መጨረሻ ለማረፍ ከሆነ፤ ይሄን እረፍት ማግኘት የምችለው ጤናዬ እስካለ ድረስ ብቻ ነው። ስለዛ ግቡን እየዘነጋው ነው። ቅድመ ተከተሉ ጠፍቶኛል።



ከመጨረሻ ቢጀምሩ ኖሮ ዛሬ በሀገራችን ያሉ የእርስ በርስ ጦርነቶች የሚካሄዱ ይመስላችዋል? ግቡ የተማሩ፣ ጤናማ የሆኑ፣ አስተዋይ እና ክብራቸው የተጠበቁ ማህበረሰቦችን ለመፍጠር ከሆነ ፥ የተራዘመ የእርስ በእርስ ጦርነት ይሄን ግብ ሲያሳካ አይታችሁ ታውቃላችሁ? አሁን ግቡ ተረስቷል። ምክንያቱም በመኃል ብዙ ደም ፈሷል። ብዙ ሰው እና ንብረት እንዳይሆን ሆኗል። አሁን ግቡ ግለሰባዊ እና ጀብደኝነት ሆኗል። ዛፉን እንዳታዩ ትፈልጋላችሁ ፥ ደን ውስጥ ደብቁት።


መኪና በጂፒየስ ስትነዱ ምንድነው የምታደርጉት? የመጨረሻውን፣ መዳረሻችንን አድራሻ እናስገባለን። ያ ምን ይሰጠናል? የተዘጉ መንገዶችን ትቶ ትራፊክ ያልበዛባቸውን አማራጮች ያሳየናል። በመኃል መንገድ ጀምረን ሳይቀር፣ መንገዱ ከተጨናነቀ ሌላ አቅጣጫ ይጠቁመናል። መጨረሻውን ስላስገባነው፣ አማራጮችን ማሳየት አይከብደውም። መንገድ ስንስት ሳይቀር በቶሎ ወደ መዳረሻችን አቅጣጫ ይመልሰናል። ለምን ታዲያ ይሄን በሕይወት፣ በኑሮአችን አንጠቀምም? ከመነሳታችን፣ ምንም ነገር ከማረጋችን በፊት መዳረሻችንን ማየት፣ የት መድረስ እንደምንፈልግ በግልጽ ማወቅ። በየመኃሉ ለመዳረሻችን ምን ያህል እየቀረብን እንደሆነ መመልከት፣ ልክ እንደ ጂፒየሱ መዳረሻችንን ፈጽሞ ከእይታችን አለማራቅ። ዘወትር ምንድነው ግን ማሳካት የምፈልገው ብሎ መጠየቅ። ንግግር ጀምሩ ፥ እንዴት በፍጥነት ያ ንግግር ሊያሳካው ካለመው ዓላማ ስትወጡ በመኃል ራሳችሁን ታገኙታላችሁ። ጂፒየሱን የሳተ ንግግር ማለት ይሄ ነው።


በትዳር ውስጥ፣ በጓደኝነት ውስጥ ያላችሁ ሰዎች ታውቃላችሁ። አንደኛው አካል በክርክር እና ነገሮችን በማስረዳት እንዲሁም በቋንቋ አጠቃቀም በጣም ጎበዝ ይሆናል። ከዛ ልክ የሆነ ችግር ተፈጥሮ ማውራት ስትጀምሩ ፥ ያ ሰው አፍ አፋችሁን እየመታ ዝም ያሰኛችዋል። ክርክሩን ሁልጊዜ ይረታል። በዚህም ለጊዜው አሸናፊ ሆኖ ይወጣል። ግን የተሸነፈውን፣ ብዙ ያላወራውን ሰው ልብ ፈጽሞ አላሸነፈውም። ጭራሽ ያ ሰው በውስጡ እየመረረው ነው። ወይ ያን ሰው የሚያስመርር ነገር ይሰራል ወይም ይሄን ወዳጅነት ቀስ እያለ ይርቀዋል። ፍቺውን ይጀምራል። ግን ግቡ ይሄ ነበር? የዛ ክርክር እና ውይይት ግቡ አንዱ አንዱን መገነዛዘብ እና ልባቸውን ማሸነፍ ነበር። ያን ወዳጅነት፣ ያን ትዳር እና ግንኙነት ወደ በለጠ ጥልቀት መውሰድ ነበር። ግን በመኃል የራስን ልክነት ማሳየት ሆነ ግቡ። ግቡ ክርክሩን ማሸነፍ ሆነ። ውጊያውን አሸንፎ ጦርነት ላይ መረታት (wining the battle but losing the war) ይለዋል ስትራቴጂስቱ ሰን ዙ። ከመጨረሻው የማይጀምር ሰው ሁልጊዜ ችግር ያልሆነንን ነገር ሲፈታ ጊዜውን ይጨርሳል።


እስቲ አስቡት ዘወትር መጨረሻችንን ብናስብ። እሱም እንደምንሞት። በጣም በቅርቡ ዓለምን እንደምንረሳ ፥ በጣም በቅርቡ እኛም በዓለም ፈጽሞ እንደምንረሳ ብንገነዘብ እና ያን በየቀኑ ብናስብ የሚኖረንን ውሳኔ አስቡ? ይሄ ፈጽሞ የማይቀር መጨረሻ ነው። ስለሚቀጥለው ነገር ባናውቅ እንኳ ሁሉም ስለሚደርስበት መጨረሻ ሞት ግን እናውቃለን። ያ ዕለታችንን የምንኖርበትን መንገድ ይለውጠዋል። ለሚወረወርብን ሁሉ መልስ የምንሰጥበት ምንም ጊዜ አይኖረንም። በጣም አንኳር የሆኑ ነገሮች ብቻ የኛን ትኩረት ያገኙ ነበር። ያ ደግሞ የብዙ ችግር፣ እጅግ የብዙ ችግር መፍቻ ቁልፍ ነው።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page