top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 18, 2024
  • 3 min read



የሁሉም ሰው የሕይወት ተልዕኮ ውስጥ የሰዎችን መከራ ማቅለል አንዱ ነው። ብዙዎቻችን ግን ለችግራችን የምንሰጠው መፍትሔ የበለጠ ችግር ይዞብን ይመጣል። እንግሊዝ ሕንድን ቅኝ በገዛችበት ወቅት ተናዳፊ እባብ ቀኝ ገዚዎችን አስጨነቀ። ለዚህ ቀላሉ መፍትሔ እባቦቹን አድኖ መግደል ነበር። ይሄን ለማበረታት ደግሞ ለሕንዶቹ ተናዳፊ ኮብራ እባቦቹን አጥምደው ባመጡ ሰዓት ማበረታቻ ገንዘብ ቃል ተገባላቸው። ሕንዶቹ ግን ማበረታቸውን ለማግኘት ሲሉ ጭራሽ ኮብራ እባቦቹን ማርባት ተያያዙት። እባቦቹን ለመቀነስ የወጣው ሕግ እባቦቹን በብዙ እጥፍ አበዛቸው።



በየቀኑ የሰዎችን ችግር ስሰማ እና ያን መፍትሔ ለመስጠት መጣር ነው ሥራዬ እና ኑሮዬ። ሰዎች ለብዙ ችግራቸው መፍትሔው ቀላል እና ርካሽ እንደሆነ ሲነገራቸው ደስ ይላቸዋል። መፍትሔው ረዥም መንገድ ሊወስድ እንደሚችል ማንም መስማት አይፈልግም፤ በጥልቀት ከሚያስተውሉ ሰዎች በቀር።



ዛሬ በአማራ ክልል የተነሳው ጦርነት ልክ እንግሊዝ እባቦቹን ለማጥፋት እንደሄደችበት ያለ መፍትሔ የሞከሩ ሰዎች የፈጠሩት መከራ ነው። ፋኖን ትጥቅ ማስፈታት አጭሩ የማስገበሪያ መንገድ መስሎ ታያቸው። ይሄው ሀገሪቷን ረዥም የእርስ በእርስ ጦርነት ውስጥ ነከራት። አንድ ቦታ ቶሎ የመድረሻው መንገድ ረዥሙ መንገድ እንደሆነ ብዙዎቻችን የሚገባን አጭሩን መንገድ ከሞከርን በኋላ ነው። እንዴት ነው ግን ችግሮቻችንን የምንፈታው? እንዴት ነው በሕይወታችን ውስጥ ያሉትን ችግሮች የፈታነው ፥ ፈተን የምናውቅ ከሆነ!



መቼስ አንድ ችግር በሕይወታችን ፈተን እናውቃለን። እንዴት ነው ያን ችግር የፈታነው? እንዴት ነው ዘላቂ መፍትሔ የሰጠነው? ያን የመገምገም እድል አግኝታችዋል? በርግጥ ለብዙ ችግራችን ሌሎች ችግሮችን ስንፈጥር ነው የኖርነው። ለዚህም ይመስላል፤ ሀብት ያለው ሰው ልጆቹ እና ቤተሰቦቹ ያልተሳኩለት የሚሆነው። የድኅነትን ችግር ፈቷል፤ ግን ልጆቹን አጥቷል። ወይም ትዳሩን አጥቷል። ወይም ወዳጆቹን። በዚህም ደስታን አጉድሏል። ሌሎች ደግሞ የቤተሰብ ፍቅር አላቸው ግን ጠኔ ፍቅራቸውን ይፈታተነዋል። አንዳንዶች ልጆቻቸውን ጨዋ ማድረግ ችለዋል ግን ፈጣን አዕምሮ እና በራሳቸው የሚቆሙ ልጆች አይደሉም።



ስዊዘርላንድ እያለው የሰማውት ነው። የስዊዝ መንግስት በስልሳዎቹ ከሁለተኛው ጦርነት በኋላ የገጠመውን የቤት እጥረት ለመቅረፍ ባለአንድ ክፍል ጠባብ አፓርትመንቶችን አብዝቶ ገነባ። ከሠላሳ እና አርባ ዓመት በኋላ ግን ሲዊዘርላንድ ውስጥ ከፍተኛ ብቸኝነት ተስፋፋ። አንዱ ምክንያት በእነዚህ ጠባብ አፓርትመንቶች ውስጥ ከአንድ ግለሰብ በላይ መኖር ከባድ ስለሆነ ነበር። ቤተሰባዊ እና የጋሪዮሽ ሕይወት የሚያበረታታ አልነበረም። የቤት እጥረት መፍትሔ ብቸኝነትን በማሕበረሰብ ውስጥ አዋለደ። ቤተሰብን አፈረሰ።



ለችግሮቻችን እንዴት ነው መፍትሔ የምንሰጠው? ግን መጀመሪያ ለችግሮቻችን መፍትሔ እንዴት መስጠት እንደሌለብን ልግለጽ።



1) መለኮታዊ ሰበብ አለመፈለግ፤



ይሄ ከማመን እና አለማመን ጋር አይገናኝም። ግን ራስን ከማወቅ ጋር እንጂ። የብዙዎቻችን ሕይወት ከዚህ የመመረጥ እና የፈተና መንገድ በብቃት የተነሳ የተወገደ ነው። ግን ብዙዎቻችን ራሳችንን አንድ ፐርሰንቱ ውስጥ እንጂ 99 ፐርሰንቱ ውስጥ ከተን ማየት አንሻም። የኛ ሕይወት ውስብስብ በሆኑ የመንስኤ እና ውጤት ጥምረቶች የሚመተር እና የሚጓዝ ነው። ምርጫችን ነው አሁን ላለንበት ውጤት የዳረገን። ችግር ሲፈጠርም ሮጠን የመለኮት እጅ የኛን የኃላፊነት ድርሻ እንዲተካ አንሩጥ። በርግጥ ማስተዋል እና ርጋታን መለመን አንድ ነገር ነው። ግን ማስተዋል እና ርጋታ እየለመኑ መተኛት ካልቻልን ማስተዋል እና ርጋት ወደ እኛ አይመጣም። ለምሳሌ አንድ ነገር አቅደን መፈጸም ሲሳነን ፥ ሰይጣን ሊያሰናክለን ወጥኖ ያደረገው ነው ከሚል እምነትም ሆነ ቃሎች እንራቅ። ከዛ ይልቅ የኛ ሕይወት ለዚህ ዓይነት ፈተና ገና ብቁ እንዳልሆነ በመገንዘብ የራሳችንን ድርሻ ላይ በማተኮር ያን ለመቅረፍ እንጣር።



2) ጊዜ ይፈታዋል በሚል ራሳችንን አናታል፤



ብዙ ነገሮች ስሜት የላቸውም። ማለትም ፍርድ የላቸውም። ኒውትራል ናቸው። ለምሳሌ ስለሞት ስናወራ ፥ ሞትን ልክ እንደ አንድ ግለሰብ አድርገን ነው የምናወራው። ከሞት ጋር ተፋጥጬ፣ ሞት መጥቶብኝ ወይም ከሞት ጋር ተናንቄ የሚል እና ሞትን ግዝፈተ አካል ሰጥተነው ነው የምንናገረው። ከቋንቋ ውበት እና ንግግር አንጻር ከሆነ መልካም። ይሄ ግን አስተሳሰብ ከሆነ የመረዳት አቅማችንን ያሽመደምደዋል። ሞት ከአንድ ሁኔታ ወደ ሌላ የምንሻገርበት ነው። ሽግግር (state) ነው። ልክ ጊዜም ኒውትራል ነው። ምንም ዓይነት የፍርድ ዝንባሌ የሌለው ኒውትራል ሂደት ነው። ጊዜ የመፍትሔ ዘለላዎች የሉትም። በራሱ የሚፈታልን ወይም የሚያባብሰው አንዳች ነገር የለም። ጀግናም አይደለም ፈሪም አይደለም። ታጋሽም አይደለም አይናደድምም። ስለዚህ ለጊዜ ችግራችንን አሳልፈን አንሰጠውም። መታገስም የጊዜ ሳይሆን የኛ ነው። መናደድም የኛ ውሉድ እንጂ የጊዜ አይደለም። ስለዚህ ለጊዜ ችግራችንን በመስጠት የሚገኝ ምንም ነገር የለም። በዕድል እና በክስተት ለመመራት ከመፍቀድ ውጪ።



ይቀጥላል።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 11, 2024
  • 3 min read



 “በሮም ሳላችሁ እንደሮማውያን ፥ when in Rome do as Romans do” የሚባል አባባል አለ። ለባለፉት ዓመታት የምጥረው ነገር ቢኖር የምኖርበትን ሀገር በጥንቃቄ መረዳት ነው። ብዙ ቅዠት ውስጥ ገብቼ አላውቅም። ምን ማለቴ ነው? እንደ አንዳርጋቸው ጽጌ እንደ ዘመነኞቹ ምዕራባውያንን እየሰደብኩኝ እና ስለክፋታቸው እየተናገርኩኝ ፥ ሕይወቴን ለማትረፍ ግን በመጨረሻ ወደ እነሱ የመጣው አይደለውም። ይልቁንስ ጥቂት ጥሩ ነገር ባይኖራቸውም በብዙ ከኛ እንደሚሻሉ በማመን እና ባለማፈር ምርጫዬ የማደርገው ስልጣኔ እንደሆነ በመናገር ነው። የስልሳዎቹ ትውልዶች ኢምፔሪያሊዝም ይውደም እያሉ ምዕራባውያንን እስኪበቃቸው ካወገዙ በኋላ ግን ሁሉም በመጨረሻ የተጓዙት የሰው ልጆች መብት በአንጻራዊነት ወደ ተከበረባቸው የምዕራብ ሀገራት እንጂ አንዳቸውም ወደ ራሺያ እና ኩባ ወይም ወደ ማኦ ሀገር ቻይና የሄዱ አልነበሩም። ከዚህ በላይ hypocrisy ወዴት ይኖር ይሆን። ሰለሞን ደሬሳ የሚለው አለው “ለሀገሬ የምመኘው ለራሴ የምመኘውን ነው።” ብዙዎቻችን የምንታዌ (dual) ሕይወት መኖር ነው ምርጫችን። ማለትም የምናምነው፣ የምንተገብረው እና የምንናገረው ተዋህዶልን አያውቅም። የምዕራባውያንን ስልጣኔ ሲያወግዝ እና ሲደሰኩር የምታዩት የሃይማኖት መምህር ፥ ተሰዶ በመጨረሻ የምታገኙት የምዕራባውያን ሀገር ነው። የትኛውን ፈጣሪ ሊያስደስት ያን ሁሉ እንደደሰኮረ እርሱ ይወቀው። የእርሱ ምርጫ ግን አልነበረም። የምንታዌ ሕይወት ማለት ይሄ ነው። አንደበት እና ተግባር ያልተዋሀዱበት ሕይወት። ይሄን ረጋ ብለው የሚያስቡ ሰዎች እንዲህ ብለው ይገልጹታል unintegrated life።



ወደ ርዕሴ ልምጣ እና ምንድነው ግን የአሜሪካ ጥበብ? ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ከፎክስ ሚዲያ አንከር ከነበረው ተከር ካርለሰን ጋር ባደረገው ቃለመጠይቅ ስለአሜሪካኖች ፍልስፍና ሲናገር “እነርሱ (እናንተ) የተግባር ሰዎች ናቸው፤ እኛ ደግሞ ፍልስፍና (ሀሳባዊነት) እና መንፈሳዊነት የሚማርከን ነን” አለ። አሜሪካውያን ፕራግማቲስት ይባላሉ። ሁሉ ነገራቸው ምንድነው የሚሰራው፣ ምንድነው የተሻለ ውጤት የሚያመጣው ከሚለው ሀሳብ የሚመነጭ ነው። ለዚህም በሁለት ፓርቲ የፖለቲካ ሥርዓት እና አስገራሚ የስልጣን (power) ባላንስ በሚታይባቸው የአራቱ መዋቅሮቻቸው (ሕግ አውጪው፣ ሕግ አስፈጻሚው፣ ሕግ ተርጓሚው እና ሚዲያው) በመመራት ይሄ የፕራግማቲስት ሳይክል ሀገሪቷን የሚጠሏት ሰዎች ሳይቀር በመጨረሻ ለመጠለል የሚመጡባት እና የምርጦች ምርጥ መናኸሪያ እና የእንቁ አዕምሮዎች መጠራቀሚያ አድርጓታል። ይሄን ፍልስፍና የሚገልጽ አንድ ጸሎት አላቸው። “እግዚአብሔር ሆይ መለወጥ የማልችለውን ነገር እንድቀበል መረጋጋትን ፥ መለወጥ የምችለውን ነገር እንድቀይር ጀግንነትን ስጠኝ፤ ጥበብን ግን ስጠን የሁለቱን ልዩነት ለማወቅ።” “God, grant me the serenity to accept the things I cannot change, the courage to change the things I can, and the wisdom to know the difference.”


በመጨረሻ ግን ሕይወት ማለት ይሄስ አይደል። ይሄ ጥበብ። በእውነትስ የጥበብ ትርጉምስ ከዚህ ውጪስ ነውን? መለወጥ የማንችለው እና መለወጥ የምንችለው የቱ እንደሆነ ማወቅስ አይደል ትልቁ ጥበብ። ጀርሚ ጎልድበርግ እንዳለው “ጀግንነት ማለት እንደምንጎዳ እያወቅን ማድረግ ማለት ነው። ደደብነትም ግን ተመሳሳይ ትርጉም ነው ያለው። ለዛም ነው ሕይወት ከባድ የሆነው።” የደደብነት እና የጀግንነት ትርጉሙ ተመሳሳይ ስለሆነ ነው ሕይወት ከባድ የሆነው። ምክንያቱም ተመሳሳይ ተግባር ደደብነትም ሊሆን ይችላል ፥ ጀግንነትም ሊሆን ይችላል። ምን ጊዜ ደደብነት ፥ ምን ጊዜ ጀግንነት እንደሆነ ለማወቅ ግን ጥበብ ይፈልጋል።


 ተቀጥረን የምንሰራውን ሥራ ትተን የራሳችንን መሞከር ደደብነትም ሊሆን ይችላል ፥ ጀግንነትም ሆኖ አንድ ቀን ያን ውሳኔ ልንኮራበት እንችላለን። ጥበብ ብቻ ነው “መቼ” የሚለው የሚያውቀው። የአሜሪካ ብቃት የሚመስለኝ ይሄ ነው። አንድ ሰው ብቻውን፤ አንድ ግለሰብ ብቻውን የዚህ ጥበብ ሁልጊዜ ባለቤት እንደማይሆን ማወቅ እና አጠቃላይ ሥርዓተ መንግስቱን እና አስተዳደሩን እንደ ቤተሙከራ በሚያይ ፕራግማቲስት አስተሳሰብ ማዋቀራቸው። ለአንድ ፍልስፍና እና ለአንድ ወጥ ለሆነ ዶግማ ያልተገዛ ሀገረ መንግስት ማዋቀራቸው። በነጻ ገበያ ሥርዓት የሰዎች ፍጹም የሆነ መልካምነትንም ሆነ ክፋት እንዲገለጥ የሚያስችል ውቅር መስራታቸው። ከዛም ዘወትር ነገሮችን ለማሻሻል እና የተሻለ ምርጥ አድርጎ ለመስራት የሚጥር አስተሳሰብን መትከላቸው። ለዚህ ደግሞ መጠበቂያው የጥሎ ማለፍ ሥርዓትን ማስቀመጣቸው ነው። እስካልተለወጥክ ድረስ ፥ የተሻለ ነገር ማምጣት እስካልቻልክ ድረስ በአሜሪካ ውስጥ ርህራሄ አታገኝም። ስለዚህም ሕይወት በፍጥነት የሚሄድ ሳይክል ነው። በዚህ ፈጣን ሳይክል ላይ ለመቀጠል ዘወትር ፔዳሉን መምታት ያስፈልጋል።



አሜሪካኖች የሚሉን እንቁላል ጥብስ መብላት ከፈለክ እንቁላሉን መስበር ግድ ነው። ጥሩ ነገሮችን መስራት ትፈልጋለህ ጥሩ ያልሆኑ ነገሮችን ለመስራት መድፈር አለብህ። ያን ደግሞ ማድረግ የምትችለው ሕይወት እንደ ሆነችው መመልከት ስትችል ብቻ ነው። በፍልስፍና እና በማንኛውም ዶግማ መነጽር የምታይ ከሆነ ያልተዋሀደ ሕይወት ይገጥምሃል። የምትናገረው እና የምትሰራው ተቃራኒ ይሆናል።



የአሜሪካኖች ጥበብ ይሄ ነው። “በዚህ ዓለም ለውጥ ማምጣት ትፈልጋለህ? እንግዲያውስ ግልጽ የሆነ ፥ ጭጋግ የሌለበት ዕይታ ሊኖርህ ይገባል። ይሄ ዕይታ በፍልስፍና ያልታወረ፣ በዶግማ ግራ ያልተጋባ እና ነገሮች እንዴት እንደሚሰሩ የሚገነዘብ፣ ሰዎችን የሚመሩ ድብልቅ ፍላጎቶች (mixed motives) የሚረዳ እና አንዳንድ ሰዎችን የሚያስተዳድሩ ዝቅተኛ ስሜቶችን (base interests) የሚገነዘብ ነው።” ይሄን ዓለም እንዳለው እና እንደሆነው ለመረዳት የሚደረግ ጥበብ ነው ይሄ ጥበብ። ነገሮችን በግልጽ፤ ራቆታቸውን ለመረዳት የሚጥር ፥ ጥበብ ነው ይሄ ጥበብ።

 
 
 




በድንገትም ሆነ ታስቦበት የወጣ ቃል ፥ አሸናፊ የማድረግ አቅም አለው። ለምሳሌ ብዙዎቻችን የምናውቀው እና የአሜሪካን የፍርድ ቤት ሥርዓት ወደ ድራማ ትይንት የቀየረው የO J. Simpson ጠበቃ Johnnie Cochran የተናገረው፣ በመጨረሻም O J. Simpson በጁሪው ነጻ እንዲሆን ያደረገው ቃል ይሄ ነበር፦ “If it doesn’t fit, you must acquite” - ፖሊስ በማስረጃነት ስላቀረበው ጓንት ነበር ይሄን የተናገረው። “ልኩ ካልሆነ ልክ አታስገቡት” የሚል አውዳዊ ትርጉም አለው።



የታዋቂው የተከላካይ ጠበቃ የማርክ ገራጎስ ቃልም የብዙ ጠበቆች መስመር ሆኖ ቀርቷል፦ “just because someone says it’s true doesn’t make it true” “የሆነ ሰው እውነት ነው ስላለ ብቻ እውነት አይሆንም።”


የሕግ ሊቀ ሊቃውንት የሰር ዊሊያም ብላክስቶን ቃልስ ፦ “Better that ten guilty persons escape than that one innocent suffer.”። (“አንድ ንጹሁ ሰው ከሚታሰር አስር ወንጀለኛ ነጻ ቢወጣ ይሻላል!”) የሚለው እና የወንጀል ሕግ ሥርዓት መሠረት ሆኖ የቀረው ከዚህ ሊቅ አንደበት የወጣ ነው። ወደ ሀገራችን ስንመጣም ከፈረንሳዩ የሶርባን ዩኒቨርስቲ በሕግ የተመረቀው ልዩ ፍጥረት አክሊሉ ሀብተወልድ እንዲህ የሚለው ቃሉን አንረሳውም።



“አንድ ግብ ብቻ ነው ያለን


ኢትዮጵያ!


አንድ መተባበሪያ አላማ ብቻ ነው ያለን


ኢትዮጵያ!!


አንድ ፕሮግራም ብቻ ነው ያለን


ኢትዮጵያ!!!”



ይሄን የመሰለ ውበት ያለው እና ሁሉን አቃፊ የሆነ መስመርን እንዴት ባለ ጥንቃቄ የሚያፈልቅ፤ ልክ እዚህ ሀገር ባሉ ሊቃውንት ደረጃ ያለ ሰው ነበር አክሊሉ።



ይሄን ያነሳውት ዛሬ ዎልስትሪት ጆርናል የክልሌን ገዢ እጩ ምክትል ፕሬዝዳንት ሆኖ መመረጠ እና ለዛ ያበቃውን ዋነኛ ምክንያት ሲጠቅስ፤ ካሚላ ሀሪስ ባይደንን እንደተካችው፤ ገዢያችን ቲም ዋልዝ ትረምፕን እና ቫንስን “ዊርዶች” ብሎ መግለጹ ነው ይላል። ከዛ በኋላ ሁለቱ ዊርዶች የሚለው ቃል የሊብራል ሚዲያ ቃል ሆነ። ዋልዝንም ለአሸናፊነት አበቃው። ቃላት በዘፈቃድ የሚወጡ አይመስለኝም፤ ጊዜ እና ሁኔታን፤ አውድን እና ሰሚን አስተውሎ እና አጥንቶ የሚለቀቅ ቃል ፥ የቃል ፍጥረትን የሰው ልጅን ይማርኩታል። ቃላት ያድኑናል፤ ቃላት ይገሉናል።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page