top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jun 25, 2024
  • 4 min read

June 24, 2023




ብዙ ሰዎች በወጣትነታቸው ሕይወትን ሌሎች ሰዎች ከኖሩት ውጪ የሚኖሩ ይመስላቸው እና ብዙ ለማሳካት ይጥራሉ። አንዳንዶች ያሳካሉ ፥ ልክ እንደ ብዙ ነገር አንዳንዶች ደግሞ የፈለጉትን ሳያገኙ ይቀራሉ። ያሳኩት ግን ፥ አጥብቀው የፈለጉት ነገር እጃቸው ላይ ሲገባ “ለዚህ ነበር እንዴ?” ይላሉ። የሕይወት ትርጉምን በሕይወታቸው መጨረሻ ድጋሚ ይጠይቃሉ። ስቲቪ ጆብ የሕይወት ታሪኩን ለሚጽፍለት ዋልተር አይዛክሰን ያለው ይሄን ነበር፤ “ምንድነው ሕይወት፣ በቃ ለዚህ ነበር የደከምኹት? ልክ ስትወለድ ብቻኽን እንደመጣኸው ስትሞትም ብቻኽን ልፋትኽን ሁሉ አራግፈክ ትሄዳለኽ።” የተሳካላቸው የምንላቸው ሰዎች ከሞላ ጎደል በሞታቸው አልጋ ላይ ይሄን ጠይቀዋል።

 ሊዮ ቶልስቶይ የኢቫን ሞት በሚለው መጽሐፉ ፥ የስመጥሩን ዳኛ ኢቫን ሞትን የሰሙ ጓደኞቹ በዛው ሰከንድ ያሰቡት የእርሱን ቦታ ማናቸው እንደሚወስዱ እንደነበር ጽፎልናል። ልጆቻችን ሳይቀር በዚያው ሰከንድ የሚያስቡት ስለራሳቸው ቀጣይ ሕይወት ነው። ይሄ ዑድት በእነርሱ ሞት ሰዓትም ይቀጥላል።


የመጽሐፍ ቅዱሱ ኢዮብ “ምንድነው የተፈጠረው?” ብሎ ግራ የተጋባ ሰው ነበረ። ለዚህም እግዚአብሔር ይምጣና ለጥያቄዎቼ መልስ ይስጥ አለ። ጓደኞቹ በተግባር ኃጢአት እንዳልሠራ ቢያምኑም በልቡ እና በቃሉ ግን በድለኽ ይሆናል ብለው ከሰሱት። ኢዮብ ግን ለዚያም መልስ ነበረው፤ “በቃሌም ኃጢአት ሠርቼ ከሆነ በልቤም በድዬ ከሆነ ኃጢአቴን በይፋ ይግለጠው። እኔም ንስሓ ልግባ” አለ። በመጨረሻም መከራን ከኃጢአት ጋር ያገናኙት የኢዮብ ወዳጆች ሲቀጡ ለኢዮብ ጥያቄ ግን እግዚአብሔር መልስ ሳይሰጥ ቀረ። ለምን? በሰጥቶ መቀበል መርሕ የተገነባው የሰው ልጅ ሕይወት “የጽድቅ ሥራ ዋጋ ሁልጊዜ በረከት ነው የኃጢአትም ዋጋ መቅሰፍት” ብሎ ያስባል። ይሄ አስተሳሰብ ከቅዱስ ዳዊት ጀምሮ እስከ ሌሎች ብዙኃን ቅዱሳን ግራ ያጋባ ነገር ነበር። ኃጢአተኛ ሲያብብ እና ሲለመልም አይተው “ጽድቅ መሥራታችን ታዲያ ምንድነው ዋጋው?” ብለው ነበር። ዛሬም ብዙዎቻችን “’ባክህ ሰው ሁሉ እንዲያ ነው የሚያደርገው” በማለት የክፋትን በር እናንኳኳለን።


እግዚአብሔር ግን ፍጥረቱን በፍትሕ ብቻ የሚመራ እንዳልሆነ ፥ የኃይሉን ስፋት እና የፍጥረቱን ብዛት ለኢዮብ በመግለጥ ፥ ኢዮብ በትህትና የዚህን ዓለም ሕይወት እንዲቀበል ሆነ። ጠቢቡ ሰሎሞን ይሄን በሚገርም አገላለጽ ጽፎታል። “እኔም ተመለስሁ፥ ከፀሐይ በታችም ሩጫ ለፈጣኖች፥ ሰልፍም ለኃያላን፥ እንጀራም ለጠቢባን፥ ባለጠግነትም ለአስተዋዮች፥ ሞገስም ለአዋቂዎች እንዳልሆነ አየሁ፤ ጊዜና እድል ግን ሁሉን ይገናኛቸዋል።” መክ 9:11


አላን ዋትስ “የሕይወት ግብ መኖር ብቻ ነው” ይላል። ስኬትን የሕይወት ግብ አድርጎ የሚያስብ ሰው በሕይወት ጎስቋላ ፍጻሜ ከሚኖረው አንዱ ነው። ሕይወት ሕይወት ብቻ ነው ግቧ። በሕይወት ጥበቃቸው አንስተኛ የሆኑ ሰዎች ደስታቸው በጣም ትልቅ ነው። ሁሉ ነገር በእነሱ ሊደርስ እንደሚችል ያምናሉና።በናዚ ኦሽዊትዝ ካምፕ ውስጥ ዘግናኝ ሕይወትን ያሳለፈው ቪክቶር ፍራንክል በካምፑ ውስጥ ከሁሉም በፍጥነት የሞቱት “optimist”ቶች ነበሩ ይላል። ሴኒካ ለጓደኛው በጻፈው ደብዳቤ ላይ “ለምንድ ነው ሞት የሚያስፈራ?” ፥ “በሕይወት ያለ ብቻ እኮ ነው የሚሞተው” ይለዋል። ይሄ ማለት ሞት የሕይወት ምስክር ነው። ይሄ ማለት መከራ የመልካም ነገር ትንሣኤ ነው።እያለን ነው። ግን ሁልጊዜ በሕይወት የሆነ ነገር ማግኘት አለብን ብለን ስለምናስብ ፥ ሕይወትን ሳናውቃት እናልፋለን። የኢዮብ መጽሐፍ ጸሓፊ የሚጋብዘንም ለእያንዳንዱ የእግዚአብሔር ሥራዎች ምክንያት መፈለግን እንድንተው እና የሆነውን ነገር መቀበል እንድንለምድ ነው። መተው መቀበል ጥቂት ሰዎች የታደሉት የስብዕና ደረጃ ነው።


ይሄ የገባት የታላቁ ሊቅ እና ምጡቅ አእምሮ ባለቤት የቅዱስ አውግስጢኖስ እናት ሞኒካ ነበረች። አውግስጢኖስ በዘመኑ ከነበሩ አዋቂዎች የሚወዳደረው ያልነበረ እና በዚህም ከአልጄሪያ ካርቴጅ ተነሥቶ የሮም ንጉሥ የቫለንቲኒያን የንግግር አስተማሪ የነበረ ነበር። በሃያዎቹ መጨረሻ ክርስቲያን እስከሚሆን ድረስ መጽሐፍ ቅዱስን የሕፃናት ተረት ተረት ነበር የሚለው። ለእርሱ የአመክንዮ አእምሮ አንሶበት ነበርና። አውግስጢኖስ ከእናቱ ጋር ምሳ ሲበሉ ብዙ ጊዜ ስለብዙ የዓለም ሁኔታዎች የማውራት ልምድ ነበራቸው። ክርስቲያን ከሆነ በኋላ የሚያስታውሰው አንድ ታሪክ ነበረው። እርሱም ምሳ በልቶ እንደጨረሰ የበላውን ነገር ረሳው። ከዚያ እናቱን ምን እንደበላ ጠየቃት። እርሷም ስቃ ዝም አለች። ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ስለመጽሐፍ ቅዱስ ሲያወሩ “ይሄ ለአዕምሮዬ አይመጥንም” አላት። እሷም “አሁን የበላኸውን ምሳኽን የረሳው አዕምሮ ነው እሱ?” በማለት በደቂቃዎች ውስጥ የተፈጸመን ነገር የሚረሳ አዕምሮው ክርስቶስን ለማወቅ መደገፊያው መሆኑ ምን ያህል ስህተት እንደሆነ አሳየችው። ሕይወት ከአዕምሮአችን በላይ ነው። ለሕይወት በአዕምሮአችን ብቻ ትርጉም የምንፈልግለት ከሆነ ፥ ምስኪን ብኩን ሆነን ነው የምንቀረው።


በርትራንድ ራስል ስለኢዮብ የሚነግረን የሚመስል ምሳሌ አለው:- የዶሮዋ ሕይወት። ዶሮዋ በየቀኑ ጌቶቿ ይመግቧታል። ይሄ በየቀኑ እና ለብዙ ጊዜ ከመካሄዱ የተነሳ ዶሮዋ በየቀኑ በጌቶቿ መመገብ የማይቀር የሕይወት ሐቅ አድርጋ ቆጥረዋለች። አንድ ቀን ግን ያ ሁሉ መግቦት በጌቶቿ ቢላዋ ይተካል። ይሄ መታረድ ፥ ይሄ ቢላዋ ልትገምተው የምትችለው አይደለም። ምክንያቱም ሲከሰት አንዴ ነው። ከተከሰተ ደግሞ ትምህርት የሚወሰድበት ዕድልም የለም። ብዙዎቻችን ለሕይወት መጥፎ ነገር እንዘጋጃለን። መጥፎ የምንለው ነገር ሳይቀር ግን ትላንት በሌሎች ላይ የተከሰተ ነው። ከዛ ውጪ መጥፎ ነገር አዕምሮአችን እራሱ ሊያስብ አይችልም። ዶሮዎ ትላንት ያደረገችውን ነገር እስካደረገች ድረስ ፥ ዛሬም ሕይወት በተመሳሳይ መቀጠል አለባት ብላ ታስባለች። ያ ግን ሁልጊዜ እውነት አይደለም። ኢዮብ በመጽሐፉ እንደሚነግረን በየቀኑ ለእራሱ ብቻ ሳይሆን ለልጆቹ ጭምር ለእግዚአብሔር መሥዋዕት የሚያቀርብ ሰው ነበር። በዚህም የጽድቅ ዋጋ የሆነውን ነገር አላጣም ፥ ያ ቢላዋ እስከሚመጣ ድረስ። ለዚህ ነው ትርጉም ያጣለት። ለዚህ ነው ትርጉም የፈለገው።

አጼ ቴዎድሮስ ራስ ጉግሳን ከማረኩ በኋላ የደበከውን ወርቅ አምጣ ብለው በፈረስ ጭራ አስጎተቱት። በኋላ የቀበረውን ወርቅ ሲያወጣ ፥ “ይሄን ሁሉ ለምን ነበር ቆፍረኽ የቀበርኸው?” ሲልቱ “ለክፉ ቀን ብዬ” አለ። አጼ ቴዎድሮስ ፈገግ ብሎ “በበጎ ቀን የተቀመጠ ለክፉ ቀን መውጫ ከሆነማ ፥ ምን ክፉ ቀን አለ!” አሉት።


ሰር ሚካዬል ሀዋርድ በ1973 ዓ.ም በሰጠው ሌክቸር “በውጊያ ውስጥ የጦር መሪዎች እና ወታደሮች መማር ያለባቸው ፈጽሞ የማይገመተው፣ ማንም የማይጠብቀው ነገር ሲመጣ እንዴት ያንን መቀበል እና በዛ ውስጥ ማለፍ እንደሚገባ ነው” ይላል። የጦር ስትራቴጂስቱ ካርል ቫን ክላስዊትዝ “ጦርነት ማለት የሁለት ሰዎች ጥል (two persons duel) ወደ ሀገራት ከፍ ብሎ ማለት ነው” ይላል። ፕሮፌሰር ሎረንስ ፍሬድማን ደግሞ ያልታሰበ ነገር (suprise) በጦርነት ብቻ ሳይሆን ፥ “ሀገራትም 100% ሰላም ነን፣ ችግር የለም ብለው በተቀመጡበት ራሳቸውን በጦርነት፣ በጥልቅ ችግር እና በአሳፋሪ ሁኔታ የጠላትን ሴራ ቀድመው መንቃት ተስኗቸው ያገኙታል” ይላል። ልክ እንደጦርነት ሕይወት ፈጽሞ ያላሰብነው ፥ መቼም ያልጠበቅነው ነገር የምታስተናግድ ናት። ይሄን ቀና እንዳሉ ፥ ከነሞገሳቸው እንደ ኢዮብ የሚያስተናግዱት ግን ጥቂቶች ናቸው። ለምን? ብዙዎቻችን “በሰጥቶ መቀበል” እና “በአመክንዮ” መታወራችን ምክንያት ሊሆን ይችላል።


ሴኒካ ለሉሲለስ ሲጽፍለት “ካንተ የሚወሰድብህ ነገር ሁሉ ያንተ አይደለም። ያንተ ባልሆነ ነገር መደገፍን አሶግድ” ይለዋል። የእኛ የሆነ ነገር ፥ ሊወሰድብን የማይችል ምን አለ?

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jun 23, 2024
  • 2 min read

መንገድ ላይ የሚለምኑ ሰዎችን ሳይ፣ ብዙ የማስባቸው ሀሳቦች ቢኖሩኝም፤ አንደኛው ግን አድናቆት ነው። እነዚህ ሰዎች በስንፍናም ይሁን ያለእነሱ ጥፋት በመጣ ድህነት ችግር ላይ ወደቁ። ግን ከመስረቅ፣ ነፍሰ ገዳይ ሆኖ ግፍን በመፈጸም ችግራቸውን ከማባረር ይልቅ አንድ ነገር መረጡ። ራሳቸውን ዝቅ አድርገው ፥ የመለመንን ድፍረት ተላበሱ። መለመን ቀላል የሚመስለው ይኖራል። ግን መለመን ይቅርና ለመማር የገባንበት ትምህርት ቤት ውስጥ ራሱ ደደብ ተብሎ ላለመቆጠር ስንት ሰው ነው ጥያቄ የማይጠይቀው ወይም መልስ የማይመልሰው። እንግዲህ መሳሳት መብታችን በሆነበት የትምህርት ዞን ውስጥ የሰው ፍርድን ፈርተን ራሳችንን ከእውቀት ከገደብን፤ ክብርን አዋርዶ መለመን ምን ያህል ከባድ ሊሆን እንደሚችል አስቡ። በርግጥ ለጥቂቶች ይሄ ሱስ እና ቢዝነስ ሆኗቸው ይሆናል። አንዳንዶችም የአዕምሮ ጤናቸው ስለተቃወሰ ይሄን ያደርጉ ይሆናል። ግን ብዙዎች ችግር ነው ያወጣቸው።

 

የዛሬ የሰንበት ዕይታ በሰዎች የስኬት ጉዞ ውስጥ ቁልፍ ስለሆነው ስነልቦናዊ እንቅፋት ነው የሚዳስሰው። ታላቁ አሳቢ ሾፐንሀወር “የሰው ልጅ ትልቁ ፍርሃት ደደብ ተደርጎ መቆጠር ነው” ይላል። በእውነትም ትልቁ የስኬታማ ሕይወት እንቅፋት ደደብ ተደርጎ ለመቆጠር አለመፍቀድ ነው።

 

ሕጻናት ለመውደቅ ፍቃደኛ ባይሆኑ ኖሮ መቼም መራመድ አይችሉም ነበር። ግን ያን የመረዳት ስነልቦናዊ አቅማቸውስላላደገ፤ መውደቅን ሳይፈሩ መራመድን ተለማመዱ። እንደ እኔ ሥራችሁ ከብዙ ሰዎች ጋር የሚያገናኛችሁ ሰዎች ከሆናችሁ፤ ሰዎች የሆነ ትምህርት ወይም ሥራ ለምን እንደማይጀምሩ ስትጠይቋቸው የሚመልሱት መልስ “በዚህ ዕድሜዬ” የሚል ነው።

 

ለምን ዕድሜ ተጽዕኖ ፈጠረባቸው?

 

ትልቁ ምክንያት በዚህ ዕድሜያቸው ተጠያቂ እንጂ ጠያቂ፣ አስተማሪ እንጂ ተማሪ፣ ከፍ ብሎ እንጂ ዝቅ ብሎ ለመታየት አለመፍቀዳቸው ነው።

 

ስናድግ ሕጻናትን መራመድ ያስተማራቸውን ትልቁን የስኬት ስነልቦና አውልቀን እንጥለዋለን። እሱም በሰዎች ፊት ለመውደቅ መፍቀድን ነው። ሞኝ መስሎ ላለመታየት መፈለግ የእውቀት መዝጊያ ቁልፍ ነው።

እውነተኛ ጅል ለመሆን ትፈልጋላችሁ? አዋቂ መስሎ ለመታየት ጥረት አድርጉ። ያልገባችሁን ነገር እንደገባችሁ እለፉ።ከንግግራችሁ አላውቅምን አሶግዱ። ሁሉ  እንደገባችሁ ነገር ጭንቅላታችሁን ነቅንቁ። ጥያቄ መጠየቅን ሳይሆን ለማስረዳት እና ለማስተማር ቸኩሉ።

 

የሰው ልጅ ውድቀት ሲጀምር፤ ከውድቀት የመውጫውን መንገድ ፈጣሪ ለአዳም ጠቁሞታል። አዳም ሆይ ፥ “ወዴት ነህ? የሚለው ያላዋቂዎች ጥያቄ በአዋቂው በእግዚአብሔር ተጠቆመው። ሁሉን አዋቂው ከመፍረዱ በፊት አላዋቂ ሆኖ ለመቆጠር ፈቀደ። ምንም ምንም በፊቱ ያልተሰወረበት እርሱ ፥ ሁሉ ነገር የተሰወረበትን ጠየቀ። “ወዴት ነህ?” እያለ። በዚህ ምድር በእኛ አቅም የጥበብን ጥግ ማግኘት ከፈለግን እናውቀዋለን የምንለውን ነገር ሳይቀር እንደ አላዋቂ በመጠየቅ እንጀምር። ብዙ አውቀናል የምንላቸው ነገሮችን ፈጽሞ እንደማናውቃቸው የዛኔ ይገባናል።

 

በሕይወት እጅግ ብዙ ነገር የሚገኘው ሞኝ ሆኖ ለመወሰድ ባለ ድፍረት ውስጥ ነው። ሼን ፓሪሽ እንደሚለው “የላቀ ውጤት ለማግኘት ሞኝ ሆኖ የመቆጠር ብቃት ላይ መድረስ አለብን። ምክንያቱ ይሄ ነው። ሁሉም ሰው የሚሰራውን ሥራ ከሰራችሁ ሁሉም ሰው የሚያገኘውን ውጤት ነው የምታገኙት። ከጅምላው ለመለየት የተለየ ዕይታ ያስፈልጋችዋል።” በሀያ ዓመታችን ዓለም ሁሉ ስለኛ የሚጨነቅ ይመስለናል። በአርባ ዓመታችን ስለዓለም ወይም ስለ ሰው አንጨነቅም ማለት እንጀምራለን። በስልሳ ዓመታችን ግን ማንም ስለኛ ተጨንቆ እንደማያውቅ ይገባናል።

 

መጽሐፍ ቅዱስ ስለጻድቃን ሲናገር በመውደቀቻው በማፈር አይደለም፤ በመነሳታቸው ተደስቶ እንጂ። የሰው ልጅ ትልቁ ክብረ በዓሉ ያለመውደቅ በዓል አይደለም ፥ ከውድቀት የመነሳቱ ትንሣኤው እንጂ። ሁለቱ ነገሮች በአንድ ጊዜ ሊኖሩን አይችሉም፤ ወይ ደደብ ሆኖ የመቆጠር ድፍረቱን እንመርጣለን አልያም የውሸት አዋቂ ሆነን እንኖራለን።

 

ኖህ ለሀያ ዓመታት ሞኝ ሆኖ ለመቆጠር ባይፈቅድ ኖሮ መርከብን ባልገነባ ነበር። ሰማዩ በጠራ ሰዓት፣ ፀሐይዋ መውጣት ባላቋረጠች ወቅት፣ ጉምጉምታ እና ነጎድጓድ በሌለበት እና ከሁሉም በላይ ደግሞ ሰዎች ሁሉ ምርጥ የተባለውን የዓየር ንብረት እየተዝናኑ ባለበት ፥ ከጎርፍ የሚጠብቅ መርከብን ለመገንባት ሞኝ ሆኖ ለመቆጠር መድፈርን ይፈልጋል። ዝናቡ እስከሚዘንብ ድረስ ኖህ ነበር ሞኙ።

 

ታስታውሳላችሁ ስንቶች ትላንት ሞኝ ይሏችሁ እንደነበር? ያኔ ሞኝ ይሏችሁ የነበሩ ዛሬ ግን የት ናቸው? ዛሬም ያን መራመድን ያስተማረንን “በሰው ሁሉ ፊት መውደቅን የመፍቀድ ስነልቦና” መልሰን እናለምልመው።



 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jun 20, 2024
  • 2 min read


ብድግ በል ፥ ተነስ። ማድረግ ያለብህን ነገር ሁሉ በሕይወት አድርግ። ስንፍና እና እንቅልፍ ማብዛት በሽታ ናቸው።ማማረር እና ሰበብ ማብዛት እንደ ካንሰር ሰርስረው የሚገሉት አንተኑ ነው። በራስህ ጉዳይ ኃላፊነት ውሰድ። ሕይወት ለአንተ ከሌሎች ሰዎች በላይ ከብዶ ሊሆን ይችላል። ከአንተ አስር እጅ ሕይወት የከበደባቸውን ሰዎች አስብ።


በዚህ ምድር ላይ ያለህ ውድ ነገር፣ ማንም የማይሰጥህ፣ በዕንቁ ወይም በማንኛውም የከበረ ነገር የማትለውጠው ጊዜህ ነው።ጊዜህን የሚያባክንብህ ሰው አንደኛ ጠላትህ ነው። በቶሎ ራቀው። ጊዜህን ተጠቀምበት። በወሬ እና በክፉ ነገሮች ክቡር የሆነውን ጊዜህን እንዳታሳልፍ ተጠንቀቅ። በቻልከው መጠን ሁሉ በየቀኑ ሩጥ። ሰውነትህን አድምጠው። ሲደክምህ በማረፍህ ደስ ይበልህ። ከድካምህ ስታርፍ ግን ተነስተ ተራመድ። ፈጽሞ እንዳትቆም ዳኽ ፥ እየተንፋቀክም ቢሆን ወደፊት ሂድ። አሁን ከአየኸው በላይ፣ አሁን ከያዝከው በላይ ለማየት፣ ለመጨበጥ ሩጥ። አምላክህ የሰጠኽን ጸጋዎች በእጥፍ አባዝተህ፣ አበርክተኽ ታስረክበው ዘንድ ፈጽሞ መዘናጋትን ለራስህ እንዳትሰጥ።


ምርጥ ለመሆን አትስራ ፥ በተሰማራሕበት መስክ የማትተካ ብቸኛ እና አንደኛ ለመሆን ብቻ ልፋ። ለዚህ መተው ያለብህ ነገር ካለ ተው።መቧጠጥ ያለብህ ካለህ ቧጥጥ። ሥራ ያዝናና። ሥራክ የሰዎችን እና ያንተን ሕይወት እንዴት የተሻለ እያደረገ መሆኑን በመመልከት ተደሰት። "በምንድነው የምትዝናናው?" ሲሉ በሥራዬ በላቸው። በዚህ አትፈር። ያንተ ሕይወት ለሌሎች ደባሪ ሊሆን ይችላል። ላንተ ሳቢ እና ማራኪ መሆን እንጂ የሚጠበቅበት ለሌሎች ማማለል የለበትም።


"ጥሩ እና ይሁን እስቲ" በሚባሉ የሕይወት ኩሬዎች አትዋኝ። ራስህን ዘወትር በአዲስ የለውጥ ውሃ ውስጥ ንከረው። መለወጥ አይቻልም የሚባሉ የሕይወት ዘርፎች ያሉት እስከሚለወጡ ድረስ ብቻ ነው። "ወፍ ብቻ ነው የሚበረው" ብለው የሚያምኑ ሰዎች የነበሩበት ዘመን ነበር፤ አይሮፕላን እስከሚፈጠር ድረስ። "በሩቅ ሀገር ካለ ሰው ጋር በመልክ እየተያዩ ማውራት በመለኮት ኃይል እንጂ ማንም ተራ ሰው ማድረግ አይቻለውም" ብለው የሚያምኑ ሰዎች ነበሩ፤ ኢንተርኔት እና ስማርት ስልክ እስከሚመጣ ድረስ። ስለዚህ ሰዎች አይቻልም ሲሉህ ብዙ ጊዜ እነደዚያ ያሉ ሰዎች እንደነበሩ እና ጥቂቶች እንደሚቻል እንዳሳዩ አስታውሳቸው። ለውጥን አምጥተህ እስከምታሳይ ድረስ ሰዎች ባንተ ባለማመናቸው አትደነቅ። አንተ ግን ለውጥ እንደሚቻል እመን።


በውጤቱ ሳይሆን በሂደቱ መደሰትን ተለማመድ። ለስንፍና እና ለክፋት እንቢ በማለትህ እና መልካምን ነገር ለማምጣት በመሥራትህ ተደሰት። ትግስት ግን ውጤቱን እንደሚቀይር እመን። የትግስት ማጣት ውጤቱን ይለውጠዋል።


ያንተ ሕይወት ያንተ ሕይወት ነው። የሌሎች የሌሎች ነው። ያንተ ስኬት የነሱ ቢሆን ሁሉም ይመኙታል። ያን የማድረግ ዲሲፕሊን ስላጠራቸው ነው አንተን ሊያሸማቅቁ የሚፈልጉት። በሌሎች ማስመሪያ ያንተን ሕይወት አትለካ። ያንተ ሕይወት ያንተ ሕይወት ነው። አንተን እንጂ መምሰል ያለበት ሌሎችን መምሰል የለበትም። ይሄን ስጦታ ሕይወትን ሳታባክን ተጠቀምበት።



 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page