top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jun 20, 2024
  • 4 min read


May 12, 2023



በየቀኑ እናሳየለን። በየደቂቃው አንዳች ነገር እንለቃለን። ጎበዝ መሆናችንን፣ ስኬታማ መሆናችንን፣ ቆንጆ መሆናችንን የሚያሳዩ ምልክቶችን፣ ብልጭታዎችን በየደቂቃው እንለቃለን። ብዙ ጊዜ ጎበዝ መሆናችንን ወይም ቆንጆ መሆናችንን በይፋ እንዲህ ነን ብለን አንገልጽም። አንድም ጉራ ስለሚመስልብን፣ አንድም ሰዎች እንደዚህ ስንል ሊጠየፉን ስለሚችሉ እና ጉራን ብዙ ሰዎች ስለሚጠሉ በቃላት ከመግለጽ እንቆጠባለን። ታዲያ ምንድነው የምናደርገው? ምልክት እንሰጣለን።



ትሁት ነን ብለን መናገር አንፈልግም። ያ’ማ ትዕቢት ሆነ። ስለዚህ ትዕቢትን በትህትና ምልክት እንደብቃለን። አንገትን ቀንጥሶ ሰላም ማለት፣ ጎብጦ መሄድ፣ ቆንጆ ሆነን ሳለ “ቆንጆ ናችሁ ስንባል ፥ አረ ምናምን” ማለት፣ ጎበዝ ሆነን ሳለ “እኔ ካንተ በላይ አላውቅም” የሚሉ የቃላት ጫወታዎችን መጫወት የትህትና ምልክት መስጠት ነው።



ሀብታም ነን፣ ገንዘብ አለን ብለን ማውራት አንፈልግም። ግን ምልክት እንሰጣለን። በምንነዳው መኪና፣ በምንኖርበት ቤት ምልክት እንሰጣለን። ጫማችን፣ መጠጣችን፣ ሰዓታችንን የምናሳልፈበት ሁኔታ ምልክት ነው። ለዓለም የምንሰጠው ምልክት ነው። ድብቅ ቋንቋዎች ናቸው።



ምልክቶች ለሰዎች ስለማንነታችን የምንሰጠው ውድ ቋንቋዎች ናቸው። ለምሳሌ ምንም ገንዘብ ሳይኖረን ገንዘብ እንዳለን ምልክት የምንሰጥ ከሆነ፤ ያ ምልክት በጣም ውድ ምልክት ነው። እንደዚህ ዓይነት ማሳያዎች ብዙ ጊዜ እና አቅም ይወስዳሉ። ምክንያቱም የምናሳየው ምልክት ታማኝ እንዲሆን ብዙ ዋጋ መክፈል ይኖርብናል።



ለምሳሌ ኢትዮጵያ ውስጥ ብዙ ሰው ትልቅ ወጪ አውጥቶ የሚገነባው ከሰባት ሰዓት በላይ የሚያሳልፈበትን መኝታ ቤቱን አይደለም፤ አጥሩ ላይ እንጂ። ወይም ለሰዎች ዕይታ የሚውሉ ቁሶች ላይ ኢንቨስት ማድረግን ይመርጣል። በመሠረታዊነት ሕይወቱን የሚለውጡ ጉዳዮች ላይ ገንዘቡን እና አቅሙን ከማዋል ይልቅ።



ሰዎች የሚሰጡንን ምልክት በጥንቃቄ መገንዘብ ይኖርብናል። ምክንያቱም የዛ ሰው አጠቃላይ ስነልቦናዊ መዋቅር ከእነዛ ምልክቶች ጋር የተያያዘ ነው። ምልክቶችን ችላ ማለት ሰዎችን አለመገንዘብ ያስከትላል። ናሲም ታሌብ አንድ ታሪክ አለው። ከታላላቅ ዩኒቨርስቲዎች የሚመረቁ ተማሪዎችን ብቻ የሚቀጥር ሆስፒታል ውስጥ ታማችሁ ብትሄዱ እና ሁሉም ዶክተሮች ጽዱ የለበሱ፣ የተመረቁበትን ሠርተፊኬት በቢሯቸው ግርግዳ ላይ የለጠፉ ቢሆኑ፤ ከእነዚህ ግን አንዱ ዶክተር ጸጉሩ የተንጨባረረ፣ ግርግዳው ላይ ምንም ሠርተፊኬት ያለጠፈ፣ አለባበሱም እንደነገርየው ቢሆን፤ እናንተ ወደዚህ ሆስፒታል ብትሄዱ እና ከማንኛው ዶክተር ጋር መታከም እንደምትፈልጉ ምርጫ ቢሰጣችሁ፤ ከዛ በፊት ስለማንኛውም ዶክተሮች ምንም እውቀት ባይኖራችሁ የትኛውን ዶክተር ነው የምትመርጡት?



ናሲም ታሌብ እንዲህ ይላል፦ የኔ ምርጫ ይሄ አለባበሱ እንደነገሩ የሆነ፣ ከታላቅ ዩኒቨርስቲ መመረቁን የሚያሳይ ምልክት ያለጠፈው፣ ጸጉሩን በአግባቡ ያላበጠረው ዶክተር ነው። ምክንያቱም ይላል ታሌብ እንደዚህ ባለ ታላቅ ሆስፒታል ውስጥ እንደዚህ ያለ ዶክተር በሥራው ለመቀጠል አቻ የሌለው ሙያ ሊኖረው ይገባል። ሁሉም በዚህ ተቋም ለመቀጠል ምልክት ማሳየት እና የተቋሙን የእይታ ፕሮቶኮል መጠበቅ ግዴታቸው ነበር። ይሄ ዶክተር ግን ያን ውጪያዊ ፕሮቶኮሎች ችላ ብሎ እንዲቀጥል የተፈቀደለት አንዳች ማንም የሚተካው ሙያዊ ብቃት ስላለው ነው። ልብ በሉ ይሄን ምርጫ እንድትመርጡ የተገደዳችሁት ስለማናቸውም አስቀድሞ ምንም እውቀት ከሌላችሁ ነው።



በዚህ ዓለም ላይ ስንኖር ጥሩ ውሳኔን የመወሰን ችሎታን የሚተካ ምንም ችሎታ የለም። ጥሩ ሕይወት ማለት የተከታታይ ጥሩ ውሳኔዎች ውጤት ነው። ብዙ ውሳኔዎች ደግሞ በእንደዚህ ዓይነት ጥበባዊ ብቃት ካልሆነ በፊታችን እሣት እና ውሃ ቀርቦልን ወደ ፈለከው እጅህን ክተት የሚል ዓይነት አይደለም። ውሃው እሣት በሚመስልበት፣ እሣቱ ውሃ በሚመስልበት ዓለም ውስጥ ሆነን ነው ጥሩ ውሳኔ እንድንወስን የተጋበዝነው። ስለዚህ ምልክቶችን መረዳት በጣም ወሳኝ ነው።



ለምሳሌ በቤታችን ብዙ ወርቅ ቢኖረን ምን ውስጥ ነው የምናስቀምጠው? ምን ዓይነት ምልክት (signal) ነው ቤት ውስጥ በድንገት ለሚገቡ ሰዎች መስጠት የምንፈልገው። ወርቁን ወርቅ በመሰለ ዕቃ ውስጥ ነው የምንደብቀው ወይስ ሌባ ቢገባ ችላ ሊለው በሚችል ተራ ዕቃ ውስጥ ነው የምንደብቀው? ማንም ወርቁን ከሌባ ለመደበቅ የሚሻ ሰው ሌቦች ቤት ውስጥ ድንገት ቢገቡ ወርቁ ሊኖር ይችላል ብለው በማይጠረጥሩት ዕቃ ውስጥ ነው ወርቆቹን የሚደብቀው።



እንደ መንሱር ጀማል ያለ ሰው ዘወትር ስለሀብቱ ምልክት መስጠት አለበት። ምክንያቱም ሀብት የለውም እና። እንደ ኃይለ ገብረሥላሴ ያለ ሰው ሀብቱን የገነባው በባንክ ብድር እንደሆነ፣ ከፍተኛ የባንክ ብድሮች እንዳሉበት ምልክት መስጠት አለበት። ምክንያቱም ከፍተኛ ሀብት አለውና።



እምብዛም ደስታ እና ፍቅር የሌላቸው ፍቅረኛሞች ፥ ፍቅር እና ደስታ እንዳላቸው በየጊዜው በማህበራዊ ድረገጽ በሚለጥፉት ፎቶዎች ያን መግለጽ አለባቸው። ምክንያቱም ጉድለት በቤታቸው እንዳለ ይሰማቸዋልና። ሰውን እናንጨርጭረው ብለው ፎቶ የሚለጥፉ ሰዎች ሞልተዋል።



ምልክቶችን መረዳት በጣም ወሳኝ ነው። ምክንያቱም ትልልቅ ውሳኔዎችን በሕይወት የምንወስነው ሰዎች በሚያሳዩን ምልክቶች ነው። በቅርብ በቤተክርስቲያን ቅዳሴ ወቅት ከአጠገቤ በነጭ ሽበት ጸጉር እና ጺም የተዋቡ ትልቅ ሰው ቆመዋል። አዕምሮዬ እኚን ሰው እንደ ቅዱስ መሳል ፈለገ። ወዲያው ግን “ለምንድነው እኚን ሰው እንደዛ ያየኸው?” ብዬ ራሴን ጠየኩኝ። መልሱ ሽበታቸው ነው የሚል ብቻ ነው። በቅዱሳን ስዕል አድኅኖ ላይ ዘወትር የምናየው እንደዛ ዓይነት ገጽታ ስለሆነ፥ አዕምሮዬ እኚን ሰው በአንዴ በውስጤ ከተመዘገበው ስዕል አድኅኖ ጋር በማያያዝ ቅድስና ሰጣቸው። ግን እኚ ሰው መልካም እና ክፉ የመሆናቸው ዕድል ተመሳሳይ ነው። ገጽታቸው ብቻውን ለምንም ነገር በቂ ምልክት አይደለም። እንደዚህ ዓይነት ሪፍሌክሽን የማያደርግ ሰው፣ እኚ ሰው ተጠግተውት ገንዘብ አበድረኝ ከዛም በሳምንቱ እከፍልሃለው ቢሉት እና ሌላ ተመሳሳይ ሽበት የሌለው ሰው ቢጠይቀው፤ በሽበት ለተሞላው ሰው የበለጠ እምነት ይኖረዋል። ምክንያቱም ምልክቶችን ያለምንም ሪፍሌክሽን ተቀብሎ አስተናግዷል።ሊዮ ቶልስቶይ እንዲህ ይላል “ውበትን መልካም ከመሆን ጋር የምናመሳስለው ነገር እጅግ አስደናቂ ግራ መጋባታችን ነው።”



አንዳንዴ ደግሞ ምልክት መስጠት ሳንፈልግ ምልክት እንሰጣለን። ማለትም በጣም ሀብታም ሆነን ሳለ ድሀ የሚውልበት ሥፍራ መታየት እንፈልጋለን። መስጠት የምንፈልገው ምልክት “ትሁት ነው” የሚልን ነው። “ራሱን አይቆልልም” የሚለውን ነው። ወይም እሱ አያካብድም የሚለውን ምልክት መስጠት ስለምንፈልግ አለባበሳችንን እንደነገሩ፣ አነጋገራችንን እንደዘመኑ፣ ወይም የገባው ነው የሚለው ስያሜ እንዲሰጠን ለዛ ተስማሚ የሆኑ ምልክቶችን እንሰጣለን። ለምሳሌ ሥርዓት ላይ አለመጠንቀቅ ወይም በጣም ሀብታም ሆነን ሳለ በቲሸርት መታየት ወይም ቀሎ መገኘት ምክንያቱም የገባው ነው የሚለውን ስያሜ እንፈልገዋለን። ይሄ ማለት ምልክት መስጠትን ባለመፈለግ ምልክት መስጠት ማለት ነው (the act of signaling something by not signaling that thing)። ለምሳሌ በጣም ሀብታም የሆኑ ወላጆች እና ሀብታቸው የታወቀላቸው ‘ልጆቻቸው ዘንጠው ስለመታየታቸው’ እምብዛም አይጨንቃቸውም፤ ምክንያቱም ሀብታም ሆኖ የመታየት ጭንቀት የለባቸውምና። በጣም ጎበዝ ተማሪ ለምሳሌ ጎበዝ መሆኑን ለማሳየት ጥያቄ ለመመለስ እጁን ለማንሳት አይሯሯጥም፣ አንድም ዶክተሮች የእጅ ጹሁፋቸው አስቀያሚ የሚሆነው ፥ የተገነባ ክብር ስላላቸው በእጅ ጹሁፋቸው ማስመስከር የሚፈልጉት ነገር የላቸውም። የተደላደለ ጥሩ ዝና ያለው ሰው ለትንንሹ ነቀፋ ሁሉ መልስ ሲሰጥ አይውልም። በጣም ጎበዝ የሆነው ዶክተር በግርግዳው ላይ የተመረቀበትን ሠርተፊኬት የመለጠፍ ፍላጎት የለውም።



ጆን ስቴንቤክ እንዲህ ይላል “በዚህ ምድር ላይ በጣም ውበት ያላቸው ነገሮች ምንም ጥቅም የሌላቸው ነገሮች መሆኑን አትርሱ፤ ለምሳሌ ፒኮክ እና ሊሊ አበባን ተመልከቱ።”



በብዙ የሥራ ቦታዎች ሰዎች ታማኝ መሆናቸውን እና ጠንካራ ሠራተኛ መሆናቸውን ምልክት መስጠት አለባቸው። ስለዚህ እውነተኛ ታማኝ ከመሆናቸው በላይ፣ ሥራቸውን በጥራት ከመሥራታቸው በላይ ቁምነገሩ ምልክት መስጠታቸው ይሆናል። በአንድ ወቅት እሠራ በነበረበት የሕግ ቢሮ ውስጥ ያለው የጠበቆች ረዳት ጠረጴዛው በወረቀት እና በፋይል የተሞላ ነበር። ጠጋ ብዬ በዚህ ሁኔታ ፋይሎች ሊጠፉ ስለሚችሉ ጠረጴዛውን ንጹሁ እንዲያደርገው፣ እርዳታም ከፈለገ ላግዘው እንደምችል ነገርኩት። እሱ ግን “ጠረጴዛዬ ንጹሁ ከሆነ አለቆች ሥራ እየሠራው አይመስላቸውም፣ ብዙ ሥራ እየሠራው መሆኔን እና የተጨናነኩኝ እንደሆንኩ ለማሳየት ጠረጴዛዬ እንዲህ በፋይል እና በወረቀት መሞላት አለበት” አለኝ። የሕግ ቢሮው ከእውነተኛ ሥራ ይልቅ ማስመሰልን የሚያስቀድም መሆኑ አሳዘነኝ። ይሄ ልጅ ከፋይል መጥፋት እና ሥራው በአግባቡ ከመሠራቱ ይልቅ የቢዚነትን ምልክትን የሚያበረታታ ባህል በዚህ ትልቅ የሕግ ቢሮ ውስጥ እንዳለ ስለገባው ፥ ይሄን የቢሮ ፖለቲካ በአግባቡ እየተጫወተው ነበር።



ምልክት የሰዎች ቃላት አልባ ቋንቋ ነው። ባህል፣ ድንበር እና ማንነትን ተሻግሮ ያለ ነው። ብዙዎቻችን እነዚህን ምልክቶች አንብበን የተሳሳተ ውሳኔ ላይ እንደርሳለን። ለምሳሌ በጣም የምንወዳት አርቲስት ያስተዋወቀችውን ቅባት ልንገዛ እንችላለን፣ ምንም እንኳ ያቺ አርቲስት አንድ ቀንም ያን ቅባት ተጠቅማ ባታውቅም። ጥሩ የለበሰን ሰው ታማኝ አድርገን እንወስዳለን። ቀልድ አዋቂን ሰው ብናገባ በትዳራችን ሁሉ ሲያስደስተን የሚያኖረን ይመስለናል። መልኳ ያማረችን ሴት ከጥሩ ባህሪ ጋር አንድ እናደርጋታለን። የሚያቆላምጠን ሰው የሚወደን ይመስለናል። ስለምልክቶች እና የድብቅ ምልክቶች (ማለትም ሀብታም ሆኖ ድኅ፣ ቆንጆ ሆኖ አስቀያሚ ለመምሰል) ማወቅ ለጥሩ የሕይወት ውሳኔ ጥቅም አለው። እኛም ስለምንሰጠው ምልክቶች እናስተውል። ምን ያህል እውነተኛ እና ተገቢም እንደሆነ እንመዝን።



 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jun 18, 2024
  • 3 min read

April 20, 2023


ጥሩ ሕይወት የጥሩ ውሳኔዎች ድምር ውጤት ነው። ግን ማነው ጥሩ ውሳኔ መወሰን የማይፈልግ? ማነው የመጥፎ ውሳኔዎች ባለሙያ መሆን የሚሻ? ይልቁስ በሙያችን ተቀጥረን የምንሰራ ወይም ሙያችንን የምንሸጥ ሰዎች ፥ ቀጣሪዎቻችን ስለውሳኔያችን አይደል እንዴ የሚከፍሉን? እንደ ጠበቃ ደንበኞቼ የሚከፍሉኝ ስለ ጥሩ ውሳኔዎቼ እንደሆነ አውቃለሁ። ስለዚህ የዘወትር ሥራዬ ጥሩ ውሳኔዎችን እንዴት ነው መወሰን የምችለው የሚለውን ጠንቅቄ ማወቅ ነው። መጥፎ ውሳኔዎቼ የእኔን ሕይወት ብቻ ሳይሆን የሌሎችንም ሰዎች ሕይወት ይጎዳል።


ነገር ግን አይደለም ብዙ የማናውቃቸው ነገሮች ባሉበት ጉዳዮች ቀርቶ ብዙ እውቀት ባለን ጉዳይ ራሱ ጥሩ ውሳኔ መስጠት በጣም ከባድ ነገር ነው። በርግጥ አንዳንዴ አንዳንድ ውሳኔዎችን በቀላሉ በፍጥነት ስንሰጥ በሌሎች ጉዳዮች ደግሞ መዘግየት እና ሪስክን ለመቀነስ መጣር ይገባል።

 የአማዞን ባለቤት ጄፍ ቤዞ ውሳኔዎችን እንደ በር ወይም እንደ መንገድ ነው የሚያያቸው። የሆነ ነገር ሲገጥመው መጀመሪያ የሚጠይቀው ይሄ ነገር አንድ አቅጣጫ በር ነው ወይስ ሁለት አቅጣጫ (one way route or two-way route)? ምን ማለት ነው? ምንድነውስ ልዩነቱ?


በተለይ በሃይዌይ ላይ የምትነዱ ከሆነ ይሄ በቀላሉ ይገባችዋል፤ በአንድ አቅጣጫ መንገድ ውስጥ ከገባችሁ ወደ ኋላ መመለስ የለም። አንዴ ከገባችሁ ገባችሁ ነው ፤ ሌላ መውጫ አግኝታችሁ በሌላ መንገድ እስከምትሄዱ ድረስ። ሁለት አቅጣጫ ከሆነ ግን፤ ከሳታችሁ እዛው መንገዱን አቋርጣችሁ መታጠፍ ትችላላችሁ። ጄፍ ለሼር ሆልደሮቹ በጻፈው ደብዳቤ እንዲህ ይላል፤ “አንዳንድ ውሳኔዎችን ማጠፍ እና መለወጥ አይቻልም። እነዚህን ውሳኔዎች በጥንቃቄ፣ በጣም ቀስ ተብሎ፣ ከፍተኛ ጊዜ ወስዶ እና ብዙ ምክክር አድርጎ መወሰን ያስፈልጋል። እነዚህን ውሳኔዎች አንድ አቅጣጫ ውሳኔ እንላቸዋለን። ነገር ግን ብዙ ውሳኔዎች እንደዛ አይደሉም። በቀላሉ ማጠፍ፣ መለወጥ እና መቀየር እንችላለን። እነዚህን ባለሁለት አቅጣጫ ውሳኔዎች እንላቸዋለን። እነዚህ መመለስ የምትችሉባቸው በሮች ናቸው። በሩን እንዳለፋችሁ፣ ልክ ካሎናችሁ፣ በሩን መልሶ ከፍቶ ወደ መጡበት መሄድ ነው። ትልቁ ጥፋት ለደረጃ አንድ የሚገባውን ዓይነት ውይይት፣ ክርክር እና ጊዜ ለሁለተኛው፣ ማለት መመለስ ለምንችልበት ውሳኔዎች ስንሰጥ ነው። ስለዚህ ጥበቡ የትኛው ነው ባለአንድ አቅጣጫ? የትኛው ነው ባለሁለት አቅጣጫስ? የሚለውን ማወቅ እና ለአንዱ የሚያስፈልገውን ጊዜ እና ትኩረት ለሌላው አለመስጠት ነው።


ለምሳሌ አዲስ የጥርስ ቡርሽ ለመሞከር የሚፈልግ ሰው፣ ስለዛ ጉዳይ ከአንድ እና ሁለት ደቂቃ በላይ ማሰብ አይገባውም። ካልተመቸው መቀየር ይችላል። ባለሁለት አቅጣጫ መንገድ (ውሳኔ) ነው። ይሄ ግን ቤት ለመግዛት ወይም የትዳር አጋሩን ለመምረጥ ለሚፈልግ ሰው የሚጠቅም አይደለም። ምክንያቱም ያ ባለ አንድ አቅጣጫ መንገድ ነው። አንዴ ከገቡበት በኋላ ፥ መዘዙ እስከ እለተ ሞታችን ሊከተለን ይችላል። ስለዚህ ከፍተኛ ጊዜ መውሰድ፣ መወያየት፣ ማጥናት፣ ምክር መጠየቅ እና ሌሎች ተጨማሪ ማስረጃዎችን መሰብሰብ ሊያስፈልገን ይችላል። ውሳኔዎችን በዚህ ዓይን ማየት ከጀመራችሁ ፥ ሁሉ ነገር ይቀየራል።


አንድ አቅጣጫ ባለው ውሳኔዎች ጉዳይ ላይ የሚያስቸኩሏችሁ ሰዎች አጭበርባሪዎች ወይም አላዋቂ ናቸው። ከእነዚህ ተጠበቁ። ሁለት አቅጣጫ ባላቸው ጉዳዮች ላይ የሚያዘገዩአችሁ ሰዎች ደግሞ ፈሪዎች ናቸው፣ እነዚህ ኋላፊነት የሚሸሹ እና ምንም ነገር እንዳትፈጽሞ ማነቆ የሚሆናችሁ ስለሆነ ፥ ይሄን አውቃችሁ ፍጥነትን ገንዘብ አድርጉ።


ሁለት አቅጣጫ ባላቸው ውሳኔዎች ዙሪያ ውሳኔዎችን በፍጥነት ወስኑ። መሪነት ማለት ያ ነው። አንድ አቅጣጫ ባላቸው ጉዳዮች ላይ ግን ዘግዩ። አማክሩ። ተማከሩ። ማስረጃ ሰብስቡ። ሪስኮችን ዳሱ። ራሳችሁን ብቻ አትመኑ።


አንድ አቅጣጫ ባላቸው ጉዳዮች ላይ ትልቁ አደጋ ስህተት መስራት ነው። ስለዚህ ጊዜ በመውሰድ የምታባክኑት እንደኪሳራ አትቁጠሩት።


የዛሬ ስምንት ዓመት የሕወኃትን ሥርዓት በመሳሪያ የሚታገለውን ግንቦት ሰባት የተባለ ድርጅትን ኤርትራ ድረስ ሄደው ለመቀላቀል የወሰኑ የሦስት ሰዎችን ታሪክ በቅርበት አውቃለሁ። እነዚህ በትልልቅ ቦታዎች ላይ የነበሩ ጓደኛሞች በሰዓቱ የመጨረሻ ከፍተኛ ኋላፊነት ላይ የነበሩትን የድርጅቱ አመራሮች በስልክ ተገናኝተው፣ የሚሄዱበትን አቅጣጫ ሁሉ አውርተው፣ ወደ ኤርትራ ጉዞ የሚጀምሩበትን ቀን ቆርጠው ነበር። ከመኃከላቸው አንዱ ከጉዞው ጥቂት ቀናት በፊት የመንፈሳዊ አባቱን አማከረ። እኛም አባት በጣም ብዙ ጥያቄዎችን ጠየቁት። በተለይ ድርጅቱን እንዴት እንዳመኑት፣ እርስ በእርስ እንዴት እንደተማመኑ፣ ስለድርጅቱ ስለሚያውቁት መረጃዎች ሁሉ በጥልቀት ጠየቁት። ልጁ በኢሳት ከሚሰማው ውጪ ስለድርጅቱ ምንም ጠንካራ የሦስተኛ ወገን መረጃ እንዴለለው ተገለጸለት። ስለጓደኞቹም ጽኑ አቋም ከእነሱ ከሰማው ውጪ በምንም እርግጠኛ እንዳልሆነ ገባው። ከዛም እኛ አባት የልጁን ውሳኔ ፊት ለፊት ከመቃወም ይልቅ፣ ለስድስት ወራት እንዲያራዝመው ብቻ ጠየቁት። ተስማማ።


በሦስት ወር ውስጥ ብዙ ነገር ተፈጽሞ ጠበቀው። ከመካከላቸው አንዱ ወደ ትዳር ዓለም ገባ። ከዛ በተባለው ጊዜ ውስጥ ስለግንቦት ሰባትም ብዙ መረጃዎች አገኘ። ትግሉም መስመሩን መለወጥ ጀመረ።


ያኔውኑ እንደወሰኑ ተነስተው ቢሄዱ ኖር፣ ዛሬ ላይ የጸጸት ሕይወትን ሊኖሩ እንደሚችሉ አስቡት። ጊዜያዊ ስሜታቸው እንጂ ሁሉም ለትግል ከምርም ዝግጁ እንዳልነበሩ የጥቂት ጊዜ መራዘም ነገሮችን ግልጥ አደረገ። ከዛም በላይ ያ መስመር ፍጹም የተሳሳተ እና የተባለውን ውጤት ያላመጣ፣ በዛ ትግል ውስጥ ያለፉም ሰዎች ታሪካቸው ራሱ የማይዘከር ወይም ዛሬም በሌላ ማለቂያ የሌለው ትግሉ ውስጥ እንዳሉ ተመልከቱ። “ለአንቺ ነው ኢትዮጵያ” ብለው ስንቱን ወጣቶች ለትግል እና ለሞት የዳረጉ የግንቦት ሰባት አመራሮችም ሆነ የኢሳት ባልደረቦች ዛሬ ላይ ያሉበትን ሁኔታ ስትመለከቱ የአንድ አቅጣጫ ውሳኔን ባህሪ ተረድተው ፥ በጥበብ ያዘገዩት እኛ መንፈሳዊ አባት ለወዳጄ ታላቅ ባለውለታ እንደሆኑት ታያላችሁ።


በሕይወት የአንድ አቅጣጫ ውሳኔን ስትወስኑ ምራቅ የዋጡ፣ ብዙ ታሪኮችን ያዩ፣ እውቀት እና ልምድ ያላቸው፣ ከስሜት የራቁ ሰዎችን ማናገር እና ማወያየት ከዘላለም ጸጸት ያድናል።

በተቃራኒው ደግሞ ልብስ ለመግዛት፣ ዕቃ ለመቀየር ወይም ሠራተኛም ለማባረር በፍጥነት ልትወስኑ ትችላላችሁ። ነገር ግን የሕይወት አቅጣጫችሁን ለሚቀይር ነገር፣ የባለ አንድ አቅጣጫ ውሳኔ ግን ልብ ግዙ።



 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jun 16, 2024
  • 7 min read

በሊዮ ቶሎስቶይ

ትርጉም በሙሉዓለም ጌታቸው


የመጨረሻ ክፍል


6

 

ባሽኪርሶች እየተከራከሩ እያሉ በቀበሮ ጸጉር የተሰራ ኮፍያ ያጠለቀ ከተፍ አለ። ሁሉም በአንዴ ዝም አሉ ፥ ወዲያውም ቆሙ። አስተራጓሚውም ይሄው የጎሳችን መሪ አለው።


ፋሆም ወዲያው ምርጥ የሆነውን ልብስና ካባ አምጥቶ ስጦታ ሰጠ ፥ አምስት ፓውንድ የሚመዝን የሻይ ቅጠልም አስረከበ። የጎሳውም መሪ ስጦታውን ተቀብሎ በክብር ቦታው ተቀመጠ። ባሽኪርሶች የሆነ ነገር ይነግሩት ጀመር ፥ መሪያቸውም ዝም ብሎ ከሰማ በኋላ በጭንቅላቱ ዝም እንዲሉ ምልክት ሰጠ። ከዛም በራሺይኛ ለፋሆም ራሱ ይነግረው ጀመር እንግዲያውስ የፈለከውን ያህል መሬት ምረጥ እኛ ብዙ መሬት ነው ያለን አለው።

 

“እንዴት ነው የፈለኩትን ያህል መሬት የምወስደው?” አለ ፋሆም በልቡ። በውል ካላሰርኩት በቀር ከባድ ነው ፥ ነገ ተነስተው ሰጥተንኻል ያሉትን መሬት ቢነጥቁኝስ።

 

“ስለመልካም ቃላታቹ ከልብ አመሰግናለሁ።” አለ ፋሆም።  “እናንተ ብዙ መሬት ነው ያላችሁ እኔ ደግሞ የምፈልገው ጥቂት ነው። ነገር ግን የትኛው መሬት የኔ እንደሆነ ማወቅ እፈልጋለሁ። ተለክቶ ሊሰጠኝ አይችልምን? ሕይወት እና ሞት በእግዚአብሔር እጅ ነው። እናንተ መልካም ሰዎች መሬቱን ብትሰጡኝም ልጇቻችሁ ግን ሊወስዱብኝ ይችላሉ።”

 

“በጣም ልክ ነህ አለ መሪው። ላንተ ለክተን እንሰጥኸለን።”

 

“አንድ ነጋዴ በዚህ እንደነበረ እና በውል አስራችሁ መሬት እንደሰጣችሁት ሰምቻለሁ። እኔም ልክ እንደሱ እንዲሆንልኝ እመኛለሁ” አለ ፋሆም።

 

የጎሳው መሪውም እንደተረዳው አሳየ።

 

“ልክ ነው” አለ ፥ “ያ በቀላሉ ሊደረግ ይችላል። በከተማ ጻሐፊ አለ ፥ ወደሱ ሄደን ውሉ በአግባቡ እንዲዘጋጅ እናደርጋለን።”

 

“ዋጋው ስንት ነው?” አለ ፋሆም።

 

“ዋጋችን  ሁሌ ተመሳሳይ ነው። በቀን አንድ ሺ ሩብልስ።”

 

ፋሆም አልገባውም።

 

“አንድ ቀን? ምን ዓይነት መለኪያ ነው እሱ ደግሞ? ምን ያህል ሄክታር መሬት ነው እሱ?”

 

“እኛ መለካቱን አናውቅበትም። የምንሸጠው በቀን ነው። በእግርህ በቀን ውስጥ መራመድ እስከቻልክበት ድረስ ያንተ ነው እናም ዋጋው አንድ ሺ ነው በቀን።”

 

ፋሆም ተደነቀ።

 

“ግን በቀን ውስጥ እጅግ ብዙ መሬት ማዳራስ ይቻላል።” አለ።

 

የጎሳው መሪ ሳቀ።

 

“ያንተ ነው እንደዛ ከሆነ። ነገር ግን አንድ ቅድመ ሁኔታ አለ ፥ በዛው ቀን ፥ ፀሐይ ከመጥለቋ በፊት ወደተነሳህበት ቦታ ካልመጣክ ገንዘብህ ባክኖ ነው የሚቀረው” አለው።

 

“እንዴት ነው የተነሳውበትን ቦታ ማስታወስ የምችለው።”

 

“ለምን እኛ መነሳት የፈለክበት ቦታ አብረንህ አንሄድም? ከዛማ ከዛ ቦታ ትነሳለህ ፥ መቆፈሪያ ከራስህ ጋር ትወስድ እና ምልክት እያኖርክ ትቀጠላለህ። አስፈላጊህ ሲመስልህ ምልክት አኑር፣ በመታጠፊያ ላይ ቆፍር እና ሣር ከምርበት ፥ እኛም ማረሻ ይዘን ከአንዱ ጉድጓድ ወደ ሌላኛው እንሄዳለን።”

 

ፋሆም በደስታ ፈነደቀ። በሌሊት ለመጀመር ተስማሙ። ከዛም ትንሽ አወጉ፣ ወተት ጠጡ፣ የበጉን ሥጋ በሉ፣ በጋራም ሻይ ጠጡ ከዛም ማታው ሲመጣ ለፋሆም ከላባ የተሰራ አልጋን ለቀቁለት ፥ ባሽኪሮችም ወደየ ድንኳናቸው ተበተኑ ፥ ፀሐይ ሳትወጣ ለመገናኘት ተቀጣጥረው።

 

 VII

 

ፋሆም በላባ አልጋው ቢጋደምም እንቅልፍ ግን ሊወስደው አልቻለም ፥ ስለመሬቱ ማሰቡን ቀጠለ።

 

“ምን ያህል ብዙ መሬት ላይ ምልክት ማኖር እችላለሁ?” ብሎ አሰበ። “አምስት ኪሎሜትር እንደሄድኩኝ ውሃ ሊጠማኝ ይችላል። ቀኑ በዚህ ወቅት ረዥም ነው ግን ደግሞ በ35 ኪሎሜትር ውስጥ ምን ያህል መሬት ሊኖር ይችላል። የማይረባውን መሬት ለገባሮቹ ሸጬ አሪፍ የተባለውን ለራሴ አስቅርና አርሳለሁ። ሁለት በሬ ገዝቼ እና ሁለት የጉልበት ሠራተኞችን ቀጥሬ ወደ መቶ ሃምሳ የሚጠጋ ሄክታሩን አርሳለሁ ቀሪውን ደግሞ ከብቶች አረባበታለሁ።”

 

እልቅልፍ እስከሌሊት ድረስ በዓይኑ ሳይዞር ቆይቶ ሊነጋጋ ሲል ብቻ ትንሽ ጋደም አለ። ወዲያውም ዓይኖቹ ሳይከድኑ ሕልም ማለም ጀመረ። ቅድም በነበሩበት ድንኳን ውስጥ ሆነው ሰዎች ከውጭ ሲያስካኩ ይሰማል። ማን እንደሆነ ለማየት ብድግ ብሎ ሲወጣ የባሽኪሮቹ መሪ በድንኳኑ ፊት ለፊት ተቀምጦ አንድ ጎኑን በአንድ እጁ ተደግፎ ይስቃል። ወደ መሪው ቀረብ ብሎ ፋሆም ጠየቀ ፥ በምንድነው የምትስቀው። ሲጠጋው ግን የበሽኪሮች መሪ አልነበረም ይልቁስ ያ በቤቱ ያለፈው እና ስለበሽኪሮች መሬት የነገረው ነጋዴ ነበር። እዚህ ምን ያህል ቆየክ ብሎ ሊጠይቀው ሲል ወዲያው ሰውዬው ነጋዴው ሳይሆን ፥ ከቮልጋ ወደ አሮጌው ቤቱ የመጣው ያ ጢሰኛ ነበር። ወዲያው ግን ጢሰኛው ሳይሆን ሰይጣን ከነጥፍሮቹ እና ቀንዶቹ ሲያሽካካ እንደሆነ አየ ፥ ፊትለፊቱም አንድ ሱሪ ብቻ የለበሰ ከላዩ የተራቆተ ሰው በመሬት ላይ ተነጥፎ አየ።

 

መሬት ላይ የተጋደመው ሰውዬው ማን እንደሆነ በአትኩሮት ሲያይ ፥ ሰውዬው መሞቱን አስተዋለ ፥ ያ ሰውም እሱ ነበር። በዚህ ሰዓት ነው ብድግ ብሎ ባኖ ከእንቅልፉ የተነሳው። በድንጋጤ በላብ ሰምጦ ነበር የተነሳው።

 

"ሰው ስንት ነገር ያልማል? አለ።

 

በቀዳዳው አሾልኮ ሲያይ ፥ መንጋት ጀምሮ ነበር።

 

“ልቀሰቅሳቸው ይገባል ፥ አሁን ልንጀምር ይገባል” አለ።

 

ተነሳቶ ፥ በጋሪው ላይ የተኛውን አገልጋዩን ቀሰቀሰው። ከዛም ወደ ባሽኪሮች አመራ ፥ ሊቀሰቅሳቸው።

 

"ወደ አውላላው ቦታ የመሄጃ እና መሬቱን የመለኪያ ሰዓቱ ነው" አላቸው።

 

ባሽኪሮች ተነሱ ፥ አለቃቸውም ተገኘ። እርጓቸውን እና ሻያቸውን ጠጡ ፥ ለፋሆም ቢያቀርቡለትም እሱ ግን የሚያስረፍደው ስለመሰለው መሄድን መረጠ።

 

“የምንሄድ ከሆነ እንሂድ ፥ ቀኑ ሳይረፍድ” አለ።

 

VIII

 

ባሽኪሮች ብድግ ብለው ተነሱ፤ ሁሉም ተዘጋጁ ፥ አንዳንዶቹ በፈረስ ፥ ገሚሶቹ በጋሪ ላይ ተሳፈሩ። ፋሆም ከረዳቱ ጋር በትንሿ ጋሪው ላይ ተሳፈረ ፥ መቆፈሪያም ይዞ ነበር። በሜዳው ሲደርሱ የጠዋቷ ፀሐይ ደም መስላ ቦግ ብላ ነበር። ባሽኪርስ ሺኪያን የተባለው ጉብታ ላይ ወጥተው ከጋሪያቸው እና ከፈረሶቻቸው ወርደው ፥ ሁሉም በአንድ ቦታ ላይ ተሰባሰቡ። መሪያቸውም ወደ ፋሆም ተጠግቶ ተመልከት ይሄ ሁሉ የኛ ነው አለው እጆቹን ዘርግቶ እያሳየው ፥ የፈለከውን መጠን ለራስህ ማድረግ ትችላለህ አለው።

 

የፋሆም ዓይኖች እንደ ባትሪ አበሩ። መሬቱ እንደ እጆቹ መዳፍ የተዘረጉ ፥ እንደ ሀባብ ፍሬ የጠቆረ አፈር ያለባቸው ነበሩ። የተለያዩ ዓይነት ሣሮችም መሬቶቹ ላይ በቅለው ነበር።

 

መሪውም በላባ የተሰራውን ካባውን አውልቆ መሬት ላይ በማነጠፍ ፥ ይሄ የመነሻ ምልክትህ ይሁን። ከዚህ እንደጀመርከው ፀሐይ ሳትጠልቅ ከዚህ መድረስ አለብህ። የረገጥከው መሬት ሁሉ ያንተ ይሆናል እዚህ በሰዓቱ ከደረስክ አለው።

 

ፋሆምም ገንዘቡን አውጥቶ በካባው ላይ አኖረ። ከዛም የውስጥ ሸሚዙ ሲቀር ኮቱን አውልቆ በወገቡ ላይ አጥብቆ አሰረው። ቁራሽ ዳቦም በኮቱ ኪስ ውስጥ ወሸቀ ፥ የኮዳም ውሃን ከቀበቶው ጋር አያይዞ አሰረ። የተሸበሸበውን የቦቲ ጫማውን ወደ ላይ ሳበው። መቆፈሪያውን ከረዳቱ ተቀብሎ ለመሄድ ዝግጁ ሆነ። ለደቂቃ በየት በኩል መጀመር እንዳለበት አሰበ ፥ በሁሉም በኩል ለመሄድ ያጓጓ ነበር።

 

የትኛውም ያው ነው ብሎ ወሰነ። ወደ ፀሐይ መውጫ በኩል እሄዳለው።

 

ፊቱን ወደ ፀሐይ መውጫ መለሰ ፥ ጥቂት ተሳበ እና ፀሐይዋ በራሱ ላይ እስከምትሆን ጠበቀ።

 

ሰዓት ማባከን የለብኝም ሲል አሰበ። ደግሞ ፀሐዩ ሳይከር መጀመር ይሻላል ብሎ ተነሳ።

 

የፀሐይዋ ጨረር ገና ወደ ፋሆም አልደረሰም ነበር ፥ መቆፈሪያውን በትከሻው ላይ አኑሮ ወደ ሜዳው አቀና።

 

ፋሆም ሳያዘግምም ፥ ሳይፈጥንም መጓዙን ቀጠለ። ወደ ዘጠኝ መቶ ሜትር እንደሄደ ጉድጓድ ቆፍሮ ሰርዶ ደራረበበት ፥ በግልጽ እንዲታይ። ከዛም ቀጠለ፤ አሁን ሰውነቱ ስለተሟሟቀ እርምጃውን ጨመረ። ከዛም አሁንም ጉድጓድ ቆፈረ።

 

ፋሆም ወደ ጀርባው ተመለከተ። ጉብታው በግልጽ ይታይ ነበር ፥ ሰዎች በላይ ቆመው ፥ ከአንጸባራቂ የጋሪ ጎማዎች ጋር። በግምት ወደ አራት ኪሎሜትር እንደመጣ ደመደመ። መሞቅ ስለጀመረ ፥ ኮቱን ፈቶ በጭንቅላቱ ላይ አኖረ። ከዛም ጉዞውን ቀጠለ። ከበፊቱ የበለጠ መሞቅ ስለጀመረ ፥ ቀና ብሎ ፀሐይዋን ተመለከተ። አሁን የቁርስ ሰዓት ነው።

 

“የመጀመሪያው ዙር ተጠናቋል ነገር ግን በቀን ውስጥ አራት ዙሮች አሉ። ለመመለስ በጣም ገና ነው ፥ ነገር ግን ቦቲዬ አወልቃለው” አለ ለራሱ።

 

“ሌላ አራት ኪሎሜትር ሄድ እና ወደ ግራ እታጠፋለሁ። ይሄ ቦታ በጣም አስገራሚ ነው ፥ ፈጽሞ ማጣት የለብኝም። በሄድኩኝ መጠን መሬቱ የሚያስገርም ነው እየሆነ” አለ።

 

ጥቂት ወደፊት እንደተራመደ ዞር ብሎ ሲያይ ጉብታው በችግር ነው የሚታየው ፥ በሱ ላይ የቆሙት ሰዎች ጉንዳን ነው የሚመስሉት ፥ ከፀሐዩ ጋር የሆነ የሚያንጸባርቅ ነገር ይታያል።

 

“አሃ!” አለ ፋሆም ፥ “በዚህ አቅጣጫ ብዙ ሄጃለሁ ማለት ነው ፥ አሁን የመታጠፊያ ጊዜ ነው። ደግሞም ብዙ አልቦኛል ፥ ውሃም ለጉድ ጠምቶኛል።”

 

ቆሞ መሬቱን በመቆፈር ሰርዶ ከመረበት። ከዛም የውሃውን ኮዳ ከቀበቶው በማላቀቅ ከጠጣ በኋላ ፥ እንዲሁ ወደ ግራ ታጠፈ። መራመዱን ቀጠለ ፥ ጉዞውን ቀጠለ። ሣሮቹ በጣም ያደጉ፣ ሙቀቱ ሐሩር ነበር።

 

ፋሆም ጉልበቱ መድከም ጀመረ። ፀሐይዋን ሲመለከት እኩለ ቀን ነው ብሎ ገመተ።

“እንግዲያውስ ፥ የግድ ማረፍ” አለብኝ አለ።

 

ተቀምጦ ትንሽ ዳቦ በላ ውሃም ጠጣ። ነገር ግን መጋደም አልፈለገም ፥ እንቅልፍ ይወስደኛል ብሎ ስለሰጋ። ትንሽ እንደተቀመጠ ፥ ጉዞውን ቀጠለ። መጀመሪያ በቀላሉ ተራመደ የበላው ዳቦ ጉልበት ስለሆነው ፥ ግን ሙቀቱ እጅግ ስለጨመረ ፥ እንቅልፉ መጣ። መሄዱን ግን አላቋረጠም ፥ ለራሱም “ለሰዓታት መሰቃየት ከዛ በሕይወት ሁሉ መደሰት።” አለ።

 

በጣም ርቆ ከሄደ በኋላ ወደ ግራ ሊታጠፍ ነበር ፥ ርጥብ ለጥ ያለ መሬት ያየ ስለመሰለው "ይሄን'ማ መተው የለብኝም ፥ በተለይ ለተልባ የተመቸ መሬት ነው" አለ። ስለዚህ ወደ ስፍራው ሄዶ ጉድጓድ በመቆፈር ምልክት ካኖረ በኋላ ታጠፈ። ወደ ጉብታው ሲመለከት ፥ ዓየሩ ብዥ ብሏል። የሚንቀጠቀጥ ይመስላል በዚህም ምክንያት ምንም የሚታይ ነገር አልነበረም።

 

“አሃ! ይሄ ማለት በዚህ በኩል ብዙ መጥቻለው ፥ በዚህ አቅጣጫ ግን ብዙ መሄድ የለብኝም” አለ። ስለዚህ በሦስተኛው መታጠፊያ በፍጥነት ተራመደ። ወደ ፀሐይ ሲመለከት ከአድማሱ ግማሽ ሆኗል ፥ በዚህ መስመር ገና ሦስት ኪሎሜትር ራሱ አልሄደም። የሱ ግብ እስከ አስራ አምስት ኪሎሜትር ለማካለል ነው።

 

“አይሆንም" አለ፤ "ይሄ መሬቴን በአንድ አቅጣጫ የተጣመመ ያደርገዋል ግን ወደ ኋላ ቀጥታ በፍጥነት መመለስ አለብኝ። ብዙ ርቀት መጥቻለው ፥ እንዲሁ እንዳለ እንኳን በጣም ብዙ መሬት ነው ያለኝ።"

 

ስለዚህ ፋሆም ቶሎ ቶሎ መቆፈር ጀመረ ፥ ወደ ጉብታው በቀጥታ መመለስ ጀመር።

 

11

 

 

ፋሆም ወደ ጉብታው ቢመለስም ጉልበቱ ግን በጣም ታዳክሞ ነበር። በሙቀቱ ሰውነቱ ዝሎ ነበር ፥ እግሮቹ ተበሳስቶ እና ተቆራርጧል ፥ ሰንበር በሰንበር ሆኗል ፥ እግሮቹ አልታዘዝ ማለት ጀመሩ።

 

ለማረፍ ጓጓ ነገር ግን ፀሐይ ከመጥለቋ በፊት መድረስ ከፈለገ ማረፍ የማይታሰብ ነው። ፀሐይ ማንንም አይጠብቅም ፥ ቀስ በቀስ ወደ መጥለቂያዋ እያጋደለች ነበር።

 

“ኦ ጌታ ሆይ ፥ ብዙ ለማግኘት ስል ጊዜዬን ባላጠፋ ኖሮ” አለ ፥ “አርፍጄ ይሆን?” ሲል ሰጋ።

 

ወደ ጉብታው ከዛ ደግሞ ወደ ፀሐይ መጥለቂያ ተመለከተ።ፀሐይዋ ወደ መግቢያዋ ቦታ ደርሳለች።

 

ፋሆም ተራመደ ፥ አሁንም ተራመደ ነገር ግን መራመድ ከባድ ነበር። ለመፍጠን ፥ ለመራመድ ቢጥርም።

 

ተጫነው ራሱን ፥ ነገር ግን አሁንም ከጉብታው በጣም ሩቅ ነበር። መሮጥ ጀመረ፣ ኮቱን ወረወረ፣ ቦቲውን ጣለ፣ ኮዳውን ተወው ፥ እንደ መደገፊያም ያገለገለውን መቆፈሪያውን ብቻ በትከሻው አስቀርቶ።

 

ምን ማድረግ ይሻለኛል ሲል በድጋሚ አሰበ፣ ብዙ ሰበሰብኩኝ እና ሁሉን አበላሸውት። ፀሐይ ሳትጠልቅ መድረስ አልችልም።

 

ፍርሃቱ ደግሞ ትንፋሹን አቆራረጠው ፥ ፋሆም አሁንም መሮጡን ቀጠለ ፥ ሸሚዙ በላብ ሰመጠ፣ ሱሪው በላብ ከሰውነቱ ጋር፣ አፉ ከከንፈሩ ጋር በድርቀት ተጣበቀ። ጡቶቹ እንደ ቀጥቃጭ ወናፍ ሆኑ ፥ ልቡ እንደ ከበሮ ይመታ ጀመር ፥ እግሮቹ የሰውነቱ አካል እንዳልሆኑ ነገር ይክዱት ጀመር። ፋሆም የሚሞት ስለመሰለው በድንጋጤ ተዋጠ። ነገር ግን የሚሞት ቢመስለውም ከመሮጥ ግን አልቆመም።


ይሄን ሁሉ መጥቼ እዚህ ደርሼ ከቆምኩማ ፥ ጅል ነው የሚሉኝ። ሮጠ ፥ ራሱን እየገፋ ቀጠለ። የባክሺሮቹን ጩኸት እና ድምጽ ሲሰማ ፥ ልቡን የበለጠ አሞቀው። ያለውን የመጨረሻ ጉልበት ሰብስቦ ሮጠ።

 

ፀሐይዋ ወደ መጥለቂያዋ ደረሰች ፥ የከበባት ደመና ጨመረ ፥ ልክ እንደ ደም ቀይ መሰለች። “አሁን ፥ አዎ! አሁን ፥ የመግቢያዋ ሰዓት ደረሰ ፥ እሱም ግን ወደ ግቡ ቀርቦ ነበር። ፋሆም በጉብታው ላይ ያሉ ባሽኪሮች እንዲፈጥን እጃቸውን ሲወዘውዙ ይታየዋል። መሬት ላይ የተዘረጋው ያ የላባ ካባ ፥ በሱ ላይ የተቀመጠው ገንዘብ ይታየዋል፤ መሪው ወገቡን ይዞ መሬት ተቀምጦ ይታየዋል። ፋሆም ህልሙን አስታወሰ።

 

"በጣም ብዙ መሬት አለ" ሲል አሰበ "ግን እግዚአብሔር እንድኖርበት ይፈቅድልኛል?" ሲል አሰበ። ሕይወቴን አጣው ፥ ሕይወቴን አጣው ፥ በፍጹም እዛ ጋር አልደርስም።

 

ፋሆም ፀሐይን ቀና ብሎ አያት ፥ ግማሽ ጎኗ ብቻ ቀርቷል። በቀረው ጥንካሬ ሁሉ ፥ ግማሽ አካሉን ወደፊት ዘርግቶ ሞከረ  ፥ ወገቡ ታጠፈ ፥ አብረውት ሊጓዙ ያልቻሉትን እግሮቹን ትቶ ይሄድ ይመስል ተውተረተረ። ወደ ጉብታው ሲደርስ ፥ ጨለመ። ወደ ፀሐይ ሲመለከት ፥ የለችም።

 

አለቀሰ ፥ ልፋቴ ሁሉ በከንቱ ነበር አለ ፥ ሊቆም ሲል ከላይ ያሉት ባሽኪሮች አሁንም እየጨውለት ነበር። የሆነ ነገር ትዝ አለው ፥ “ከዚህ ታች ፀሐይ የጠለቀች ብትመስልም ለእነሱ ከላይ ግን አሁንም ገና ትታያቸዋለች።” በረዥሙ ተንፍሶ ወደ ላይ ሮጠ። ከላይ ገና ብርሃን ነበር። ጫፍ ላይ ሲደርስ ካባውን አየው። ከፊት ለፊቱ ፥ መሪያቸው ተቀምጦ ወገቡን ይዞ ይስቃል። ፋሆም በድጋሚ ህልሙን አስታወሰ ፥ የሲቃ ድምጽ አወጣ ፥ ወደፊት በመውደቅ ካባውን በእጆቹ ነካቸው።

 

“አሃ! ፥ ይበቃል ወዳጆቻችን” አለ በኃያል ድምጽ መሪው ፥ “እጅግ ብዙ መሬት አግኝቷል።”

 

የፋሆም ረዳት እየሮጠ መጥቶ ሊያነሳው ሞከረ፣ ነገር ግን ደም ከአፉ መውጣት ጀመር። ፋሆም ሞተ።

 

ባክሺሮች በምላሳቸው ድምጽ በማውጣት ሐዘናቸውን ገለጡ።

 

የፋሆም ረዳት መቆፈሪያውን አንስቶ ለፋሆም የሚበቃ ጉድጓድ ቆፈረ ፥ በዛም ውስጥ ቀበረው። ከራሱ እስከ እግሩ መቶ ሰማንያ ሴንቲሜትር ብቻ ነበር ያስፈለገው።



 

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page