top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jun 13, 2024
  • 5 min read

የዚህ ጹሁፍ ብዙ ክፍሉ ከሲ ኤስ ሉዊስ የተወሰደ ነው።


አንድ ኃጢአት አለ በዚህ ዓለም ላይ ያለ ሰው ሁሉ ነጻ ነኝ ብሎ የማይናገርበት። ይሄን ኃጢአት ሁሉም ሰው በሌላው ላይ ሲያየው ይጠየፈዋል፣ ክርስቲያን ካልሆኑ በቀር ይሄ ኃጢአት አለብኝ ብሎ በድፍረት የሚናገር እምብዛም የለም። እንደዚህ ኃጢአት ሰውን የሚያዋርድ የለም ፥ እንደዚህ ኃጢአትም ሰዎች በራሳቸው ላይ የማያስተውሉት የለም። ይሄ ኃጢአት በራሳችን ላይ በብዛት ሲኖረን ፥ በሌሎች ላይ አብዝተን እንጠለዋለን።


እንደ ክርስቲያን መምህራን፣ ይሄ ትልቁ ኃጢአት ፥ ይሄ አቻ የማይገኝለት መጥፎ የነፍስ ጠረን ፦ ትዕቢት ነው። የኃጢአት ጣሪያ ነው ትዕቢት።


በትዕቢት ፊት ፥ አመንዝራነት፣ ቁጣ፣ ስግብግብነት፣ ስካራ እና ሌሎች ሁሉ እንደ ትንኝ ናቸው። ትዕቢት ነው ሳጥናኤልን ሰይጣን ያደረገው። ትዕቢት የሌሎች ኃጢአቶች ሁሉ ድልድልይ ነው። የእግዚአብሔር ተቃራኒ ትዕቢት ነው። የኃጢአት አቻ ሌላ ስሙ ትዕቢት ነው። ምክንያቱም ኃጢአት ማለት ቦታችንን መልቀቅ፣ የማይገባንን ቦታ መያዝ፣ ያልተፈቀደልንን ነገር የራስ አድርጎ፤ የሚገባን አድርጎ መቁጠር ነው። ሰይጣን ሔዋንን ያላት ያን ነበር። “ይሄን ፍሬ መብላት እንደ እግዚአብሔር ያደርግሻል።” ያን ነው ትዕቢት የሚለው። “እንደ...” የመሆን ፍላጎት ፥ ርካታ የሌለው “እንደ..” የመሆን ናፍቆት እና “እንደ...” እነዛ ያለመሆን መጠየፍ ነው ትዕቢት።


1) ትዕቢተኛ ከሌሎች የተሻለ መሆን ይፈልጋል፤


በትዕቢት ጾር ትቸገራላችሁ? ሉዊስ እንዲህ ይላል ትዕቢት ባላችሁ መጠን አብዝታችሁ በሌላ ሰው ላይ ታዩታላችሁ። ምንድነው የሚሰማችሁ ስትናቁ፣ ሰዎች ከቁብ ሳይቆጥሯችሁ ሲቀር ወይም ከላይ ወደታች ሲያዮችሁ? ትዕቢተኛ ከሆናችሁ ሌላ ሰው እንዲህ ከፍ ሲል፣ ሲያሸንፍ በጣም ነው የምትበሳጩት።

የትዕቢት ደስታው የሆነ ነገር ሲያገኝ አይደለም። ነገር ግን ከሌላው ሰው የበለጠ እሱ ሲኖረው እንጂ። ሰዎች ሀብታም ስለሆኑ፣ ጎበዝ ስለሆኑ ወይም ስለሚያምሩ ትዕቢተኛ ናቸው እንላለን። ለዛ አይደለም ሰዎች ትዕቢተኛ የሚሆኑት። ሰዎች ትዕቢተኛ የሚሆኑት ከሌሎች በላይ ሀብታም ስለሆኑ ነው፣ ከሌሎች በላይ ጎበዝ ስለሆኑ ነው ወይም ከሌሎች በላይ ቆንጆ ስለሆኑ ነው። የሆነ ሰው ከኛ እኩል ጎበዝ፣ ሀብታም ወይም ቆንጆ ከሆነ የሚያስታብይ ምንም ነገር የለም። ንጽጽሩ ነው የሚያስታብየው ፥ ከሌላው የተሻለ ሆኖ መገኘቱ ነው የትዕቢት ርካታ።


2) ትዕቢተኛ ሰው መቼም አይረካም፤


ከሌሎች ጋር መፎካከር ሁልጊዜ የትዕቢት ምልክት አይደለም። ለምሳሌ የሪሶርስ (የሀብት) እጥረት ሲከሰት ሰዎች የድርሻቸውን ለማግኘት ይፎካከራሉ። ትዕቢተኛ ግን የበለጠ ለማግኘት ይጥራል ምንም እንኳ በቂ ቢኖረውም። ብዙ ኃጢአቶች የትዕቢት ልጆች ናቸው። ለምሳሌ ስግብግብነት እና ራስ ወዳድነት። ለምሳሌ ገንዘብን ውሰዱ። ያለጥርጥር ስግብግበነት ሰዎች ብዙ ገንዘብ እንዲፈልጉ ያደርጋቸዋል ምክንያቱም የተሻለ ቤት፣ የተሻለ ምግብ እና መጠጥ ወይም ብዙ የእረፍት ቀን ስለሚፈልጉ። ግን እስከሆነ ነጥብ ድረስ ብቻ ነው። እነዚህን ሁሉ የሚያስገኝ ገንዘብ ካገኙ በኋላ አሁንስ ገንዘብ የምትፈልገው ለምንድነው? ትዕቢት ነው - ከሌሎች የተሻለ ሀብታም የመሆን ትዕቢት፣ ከዛም ስልጣንን መፈለግ።


3) ትዕቢተኛ ሰው ስልጣን ይጠማል፤


ትዕቢት በጣም የሚረካው በስልጣን ነው። ትዕቢተኛ ሰው ከሌሎች የበላይ ለመሆን ያለው ምኞት ወደር የለውም። ስልጣን ደግሞ ይሄን የበላይ የመሆን የትዕቢት ተክል ውሃ ያጠጣዋል። ይሄን የስልጣን ፍላጎት በሁሉም ቦታ እናየዋለን። አድናቂዎች በመሰብሰብ የስልጣን ጥማቷን ከምታረካው ቆንጆ ሴት ፥ ተደማጭነቱን ለማስፋት ስልጣን እስከሚቋምጠው ፖለቲከኛ ድረስ።

ትዕቢተኛ ሰው ከሆንኩኝ ፥ ከኔ የሚበልጥ ሰው በዓለም ላይ አንድ ቢቀር እንኳ እረፍት የለኝም። ያን ሰው እስከምበልጠው ድረስ ጠላቴ ነው (ሰይጣን አንድ የቀረውን ጻድቅ ኢዮብን እንኳ ላለመተው የሄደበትን ርቀት ያስታውሱ። ዓለምን ሁሉ የራሱ ማድረጉ አላረካውም ፥ ትዕቢቱ የኢዮብን አለመንበርከክ መታገስ አልቻለም)።

ትዕቢት ዓለም ከተጀመረ ጀምሮ ትልቁ የመከራ ምንጭ ነው። ለሀገራትም ሆነ ለቤተሰቦች። እንደ ስካራ ያሉ ሌሎች ኃጢአቶች አንዳንዴ ሰዎችን ሲያቀራርቡ ትዕቢት ግን ሁልጊዜ ሰዎችን እንደለያየ ነው። የሰናዖር ግንብ አርቲቴክት ትዕቢት ነበር በዚህም የትዕቢት ልጅ የሆነውን መለያየትን የሰው ልጆች ታቀፉ። ኦ ትዕቢት ፥ ስምን፣ ዝናን፣ ክብርን የመትከል ፥ ለትውልድ የማስቀረት ናፍቆት።


4) ትዕቢት የእግዚአብሔር ጠላት ያደርግኸል፤


ትዕቢት ከሰዎች ጋር ብቻ አይደለም ጠላት የሚያደርገን ከእግዚአብሔርም እንጂ። እግዚአብሔር በሁሉ ነገር ከልኬት በላይ ከእኛ የበላይ ነው። እግዚአብሔርን በዛ መነጽር እስካላየኸው እና አንተ ከሱ ግዙፍ ልኬት-አልባ ማንነት አንጻር ምንም እንደሆንክ ካላወክ በቀር ፥ እግዚአብሔርን አታውቀውም።

ትዕቢተኛ እስከሆንክ ድረስ እግዚአብሔርን አታውቀውም። ትዕቢተኛ ሁልጊዜ ሌሎችን ዝቅ አድርጎ እንዳየ ነው። ሁልጊዜ ዝቅ አድርጎ የሚያይ ደግሞ ከፍ ያለውን ሊያይ አይችልም። ይሄ ከባድ ጥያቄ ያስነሳል። “ታዲያ እንዴት ነው ትዕቢተኛ ሆነው እግዚአብሔርን የሚያመልኩ ሰዎች ያሉት?” እኔ እንደሚመስለኝ እነሱ በአዕምሮአቸው ለቀረጹት ሌላ እግዚአብሔር ነው የሚንበረከኩት። ሀሳብ ወለድ የሆነውን እግዚአብሔርን እያመለኩት በህሊናቸው የሚያስቡት እንዴት ከተራው ሰው የተሻሉ እንደሆኑ ነው ፥ ከዚህ የውሸት የትህትና አምልኮ እጥፍ ትዕቢትን ይሰበስቡበታል።

እንደሚመስለኝ ጌታ ያለው እነዚህን ነው ፥ “በስሜ ይሰብካሉ፣ ድንቅም ነገርን ያደርጋሉ ፥ አጋንትንም ያወጣሉ፤” ይሄ ሁሉ ግን የሚደመደመው ፈጽሞ አላውቃችሁም በሚለው የሱ የመጨረሻ ቃል ነው። ምንአልባትም አንዳንዶቻችን በዚህ የሞት ወጥመድ ውስጥ ነው በዚህ ሰዓት ያለነው።


5) ትዕቢት ለሰይጣን አሳልፎ ይሰጠናል፤


ብዙ ጾሮቻ በስጋችን በኩል ከዳይብሎስ የሚሰነዘሩብን ናቸው። ትዕቢት ግን መንፈሳዊ፣ በጣም ድብቅ እና ገዳይ ነው።

ሰይጣን አንዱ የሚያደርገው ትዕቢትን በመቀስቀስ ሌሎች አነስተኛ ኃጢአቶችን እንድናሸንፍ ያደርገናል። ለምሳሌ መምህሮች ተማሪዎቻቸው ጎበዝ እንዲሆኑ ወይም መልካም ባህሪ እንዲኖራቸው ትዕቢቱን (በነሱ አጠራር ራስን የማክበር ስሜቱን) ይቀሰቅሱበታል። ብዙ ሰዎች ፍርሃትን፣ ዝሙትን፣ ቁጣን ማሸነፍ ችለዋል። እንዴት? እነዚህ ከእኔ ክብር በታች ናቸው ፥ ለእኔ ክብር አይመጥኑም በማለት። ሰይጣን በዚህ እንደሚደስት በምንም አይረካም። ሰይጣን አንተ ንጹሁ በመሆንህ፣ ታጋሽ በመሆንህ ወይም ጀግና በመሆንህ በጣም ደስተኛ ነው ፥ በላይህ ላይ ትዕቢትን እስካነገሰ ድረስ። ካንሰር እሰከሰጠ ድረስ ከቁስልህ መፈወስኽ ሰይጣንን ግድ አይሰጠውም። ትዕቢት መንፈሳዊ ካንሰር ነው፣ ፍቅርን ጨርሶ የሚበላ እና የሰው ልጅ ያለውን አስተውሎት የሚያጠፋ ነው።


6) በራሳችን ትዕቢት እንታወራለን፤


በውዳሴ መደሰት ትዕቢት አይደለም። ከእውነት እስከሆነ ድረስ ሰዎችን በማመስገን ማስደስት ስህተት የለውም፣ ችግሩ የሚጀምረው በውዳሴው መደሰት አቁመኸ በራስኽ መደሰት ስትጀምር ነው። ዋነኛው፣ ሰይጣናዊ ትዕቢት ያለው ሌሎችን ዝቅ አድረገ መመልከት ስትጀምር እና ሰዎች ስለሚሉት ነገር ግድ ሳይሰጥኽ ሲቀር ነው። ስለሰዎች ሀሳብ ምንም አለመጨነቅ አንዳንዴ ተገቢ ብቻ ሳይሆን ግዴታችን ነው ፥ ያ ግን በትክክለኛው ምክንያት ሲሆን ነው። ማለትም እግዚአብሔር ስለእኛ ያለው ሀሳብ ሲበልጥብን።

ትዕቢተኛ ግን የማይጨንቀው ለሌላ ምክንያት ነው። ትዕቢተኛ እንደዚህ ይላል “የማደርጋቸው ነገሮች ሁሉ የማደርጋቸው ለማንነቴ ነው፣ ፍላጎቴን ለማርካት ፥ መጠራቴን ለማስደሰት ነው ወይም ለቤተሰቤ ክብር ስልነው ወይም እኔ እንደዛ ስለሆንኩኝ ነው በቃ። መንጋው ቢወደኝ ይሁን ፥ ካልወደደኝም የራሱ ጉዳይ። እነሱ ለእኔ ምንም ናቸው።”

ትዕቢተኛ ስትሆን የሆኑ መጽሐፍትን በማንበብኽ ትኮፈሳለ ፥ የጻፉት ሰዎች እኮ በመጽሐፉ መደሰት አቁመዋል። (የቶልስቶይን War and Peace እና አና ካሪኒና በማንበቤ እኮፈስ ነበር። ቶልስቶይ ግን በሕይወቱ መጨረሻ እነዚህን መጽሐፎቹን ይጠየፋቸው ነበር)።


7) ትሁቱ ትዕቢተኛ፤


የሆኑ መንፈሳዊ ፍሬዎች ሰይጣንን ምንም አይረብሹትም። የትኞቹ? እንዳለኽ የምታውቃቸው መንፈሳዊ ማንነቶችኽ። በተለይ ለትህትና ይሄ በጣም ትክክል ነው። በጣም ትሁት እንደሆንክ ይሰማኸል ፥ ይሄ ስሜት ከተሰማ በርግጠኝነት ትዕቢተኛ ነህ።


በጣም ትሁት ሳለን፣ በመንፈሳችን መጻጉ ሆነን ሲያገኘን፤ ከዛ በአዕምሮአችን ውስጥ “ዋው! እንዴት ትሁት ነህ እኮ” የሚል ሀሳብ ያሰርጋል። ወዲያው በትህትና ትዕቢት ይመጣል። አዋቂ ሆነን ሳለን “ደድብ ነኝ እኮ እኔ” እንድንል ያደርገናል፣ ለታይታ ወንበር ያስለቅቀናል፣ ወገባችንን ሰብረን ሰው ሰላም እንድንል ያደርገናል፣ አንተ እኮ እንደዚህ ነህ ሲለን “አረ እኔ ፈጽሞ” እያልን የአፍ፣ የከንፈር ጫወታ እንድንጫወት ይጋብዘናል። በዚህ የሰይጣን ጫወታ ሺዎች ትህትና ማለት ቆንጆ ሴት “መልከ ጥፉ ነኝ” ብላ ማመን፣ ጎበዝ ሰው “ደደብ ነኝ” ብሎ ማሰብ፣ ጀግና “ፈሪ ነኝ” ብሎ መቀበል እንዲመስላቸው አድርጓል። እነዚህ ሰዎች መቼም ይሄን በልባቸው እውነት ነው ብለው ስለማይቀበሉ ከእውነተኛው ትህትና ይቆርጣቸዋል። ይልቁስ አዕምሮአቸው ዘወትር በራሳቸው ዙሪያ እንዲሽከረከር ያደርጋል። ሰይጣን በክፋት ከሚያሸንፈን በላይ በበጎ ባህሪያት የሚያሸንፈን ይበልጣል። ለሰዎች ቸርነት ማድረጋችንን ዘወትር ያስታውሰናል፣ ለሰው ስንነግር ደግሞ “መንገር ፈልጌ አይደለም ግን” ብለን ትህትና ጣል እንድናደርግበት ይጋብዘናል። ምክንያቱም ክፋታችንን ካየን ልንታረም እንችላለንእና። ስለዚህ በበጎ ተግባራችን ራሱን ይደብቃል። ትዕቢት እሰከሰጠን ድረስ፣ ቀኝ እጃችን ያደረገውን መልካም ነገር ለግራው በየጊዜው እስካስታወስነው ድረስ ፥ በበጎ ምግባራችን ሰይጣን ተከፍቶ አያውቅም።


 ሉዊስ ስለትዕቢት የጻፈውን ደጋግሜ ካነበብኩኝ በኋላ ራሴን ጠየኩት “ለምንድነው ይሄን ጹሁፍ ደጋግመኸ ያነበብከው?” ብዬ። መልሴ አጭር ነበር። “እንደነዛ ትዕቢተኞች ላለመሆን።” ጹሁፉን ደጋግሜ ካነበብኩ በኋላ ራሱ በትዕቢት ምክንያት እንደማነበው ያወኩት በመጨረሻ ነበር። “እንደነዛ ላለመሆን!” አሁንም ያ የመለየት፣ ልዩ የመሆን የትዕቢት መሠረት ነበር ስለትዕቢት መጥፎነት ራሱ የሚያስነብበኝ።


የትህትና ግቡ ትዕቢተኛ አለመሆን ነበር የመሰለኝ፤ ያውም እንደነዛ ትዕቢተኛ አለመሆን። ሰይጣን በእጅጉ ነበር የተሳካለት ምክንያቱም ስለትዕቢት በመማር በትህትና ወደ እግዚአብሔር መቅረብን ሳይሆን የተማርኩት ፥ ስለትዕቢት በማወቅ ወደ ሚበልጠው፣ ከእኔ እንኳ ወደተሰወረው ትዕቢት ነበር የተመነደኩት።


ትሁት እንዴት መሆን እንችላለን?


የመጀመሪይው ደረጃ ትዕቢተኛ እንደሆንን ማወቅ ነው። ትዕቢተኛ እንደሆንክ ካላወክ ፥ እንግዲያውስ በጣም ትዕቢተኛ ነህ። ትዕቢት እንደመጥፎ የአፍ ጠረን ነው። ከአንተ በቀር ሁሉ ሰው አፍህ እንደሚሸት ያውቃል እንዴት ግን ለአንተ ይንገሩኽ? ከነገሩኹ አሁንም አፍህን ከፍተኸ ልትናገር ነው። በዛም መጥፎ ጠረንኽ ሊረብሻቸው። ለዚህ ነው ትዕቢት አፍኖ የሚገለን።

ትሁት ሰው ደስተኛ ነው፣ ስማርት ነው፣ በሚያወራቸው ሰዎች ልዩ ፍላጎት ያሳያል፣ ሰዎች ከሱ ጋር ሲያወሩ የእሱ ጠቢብነት እና አስተዋይነት ሳይሆን የእነሱ ጠቢብ እና አስተዋይ መሆናቸው ነው የሚታያቸው። ከትሁት ሰው ጋር የሚያወራ ሰው ምንም በደለኛ ቢሆን ያ ሰው እየፈረደበት እንዳልሆነ ቆዳው ስለሚነግረው ምቾት ይሰማዋል። ይሄን ሰው የማንወደው ስለምንቀናበት ነው ምክንያቱም ሕይወትን በቀላሉ ይደሰትባታል። ስለትህትና ፈጽሞ ሲያስብ አታዩትም ፥ አረ እንደውም ስለራሱ ሲያስብ አታገኙትም።



 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jun 13, 2024
  • 3 min read

March 23, 2024


ወንድ ስለሆንኩኝ ስለወንዶች ባህሪ ከሴቶች በተሻለ አውቃለሁ። በተለይ ወንዶች ምን ቢደረግላቸው የተሻለ ባል እና ቤታቸውን የሚወዱ ማድረግ እንደሚቻል ሴቶች መገንዘብ አለባቸው ባይ ነኝ። በማንኛውም ጥምረት ውስጥ ችግር ካለ የአንዱ ችግር ብቻ ነው ብሎ የሚቀበል ሰው ስህተት እየሰራ ነው። ቢያንስ በኛ ዘመን የግዳጅ ጋብቻ የለም። ስለዚህ አሁን የሚማረርባትን ሴት ለጥምረት በመምረጥ ቢያንስ የወንዱ ኃላፊነትም አለ። ስለዚህ ስለሴቶች ስጽፍ ሴቶች ብቻ ናቸው ጥፋተኛ ለማለት ወይም ደረጃ ለማስቀመጥ አይደለም። የማውቀው ላይ ማተኮር የተሻለ ነው በሚል ነው።

በዴል ካርኒጌ የ1936 መጽሐፍ እትም ላይ የነበረ ቀጥሎ ባሉ እትሞቹ ላይ ግን ያልተካተተ (ምክንያቱን አላውቅም) ስድስተኛው ምዕራፍ ላይ ተመስርቶ የተጻፈ ነው።


 ሴቶች ቤትን የሚያፈርሱበት 7 መሳሪያዎች አሉ፤


1) ጭቅጭቅ


ወንዶች መታገስ የማይችሉት ነገር የምትጨቃጨቅ እና የምታኮርፍ ሴት ነው። ወንድ የምትጨቃጨቅ እና የምታኮርፍ ሚስት ያለችበትን ቤት እንደ ሲዖል ነው የሚቆጥረው። ከዛ ነጻ ለመውጣት ሞትን ሳይቀር ይመኛል። ጭቅጭቅ ግን የብዙ ሴቶች በትር ነው።

 በመልኳ ውብ፣ በዘሯ ስመጥር፣ ልጃገርድ እና ሁለመናዋ ድንቅ የነበረችውን ማሪ ዩጄኒክ ኢግናስ ናፖሊዮ ሦስተኛ (የናፖሊዮ ቦናፓርቴ የወንድም ልጅ) ያገባታል። በውጫዊ ውበቷ ከንፎ ነበር ያገባት። ብዙም ግን አልቆየም። ማሪ በቅናት የምትደብን፣ ናፖሊዮንን ሥር ሥሩ የምትከታተል፣ በማልቀስ እና እሱ ላይ በመጮኽ መከራ የምታሳየው ሆነች። እረፍት ነሳችው። በትልቅ በትንሹ መነዝነዝ ሆነ የፍላጎቷ ማሳኪያ መንገዷ።


“የምፈራው ነገር ደረሰብኝ!” እንዳለው ኢዮብ፤ ናፖሊዮን ይሄን መቋቋም ተሳነው። ባገኘው አጋጣሚ ሁሉ ከቤት መራቅ፣ በሳቅ እና በደስታ ወደ ሚቀበሉት ሴቶች መሸሽ፣ ከጓደኞቹ ጋር ብዙ ጊዜ ማሳለፍን ሥራው አደረገ። ምስኪን ሴት ማሪ ፥ ናፖሊዮንን አቃናለሁ ብላ የዘየበችው የመጨቃጨቅ መላ ጭራሽኑ አጠፋው። ጭቅጭቅ እንደ ኮብራ እባብ ነው ፥ የትዳርን ሕይወት ይገላል።


የሊዮ ቶልስቶይ ሚስት ይሄ የገባት ቆይቶ ነበር። ባሏ በመጨረሻ እሷን ከማየትስ ልጥፋ ብሎ፣ አድራሻውን ሳያሳውቅ ሁሉን ትቶላት ጠፋ። The Last Station በጣም ጥሩ ፊልም ነው፣ ይሄን የቶልስቶይን ታሪክ በደንብ መዝግቦታል። ከሚስቱ ሽሽት ከቤቱ አጠፋው፣ በባቡር ጣቢያ ላይ ወድቆ ፥ ሞቱን በመንገድ እንዲሆን አደረገው። ጠቢበኛው ሰሎሞን እንዳለው “ከጠበኛና ከቍጡ ሴት ጋር ከመቀመጥ በምድረ በዳ መቀመጥ ይሻላል።” ምሳ 21፥19። ይሄ የቶልስቶይ ትዳር በሁሉ ዘርፍ ስኬታማ የሚባል ነበር፣ የቶልስቶይ ጹሁፎች ቁጥር ስፍር የላቸውም። ሁለቱ መጽሐፎቹ እስከዛሬ በዓለም ላይ ከታተሙ ምርጥ አስር መጽሐፍት ውስጥ በቁጥር አንድ እና ሦስት የሚቀመጡ ናቸው። ይሄን ሁሉ ያሳካው ከሚስቱ ጋር እና በርሷ ትብብር ነበር። ቶልስቶይ ግን ሥራን አንዱ ከሚስቱ የመራቂያ መንገድ ነበር ያደረገው። ለዚህም ነው ከማንም በላይ የሰራው። ውጫዊው ስኬት የውስጣዊው ሰላም እጦት ምክንያት ነበር። መጨረሻ ላይ ግን ይሄ ስኬት በቂ አልሆን አለው። መታገስ አቃተው። ጠቢበኛው ሰሎሞን እንዳለው ከቁጡ ሚስቱ ይልቅ ፥ ቤት አልባ ሆኖ ጎዳና ላይ መኖርን መረጠ። ሞቱ አፋፍ ላይ ሆኖ እንኳን ሚስቱ መጥታ እንዳታየው ከባብሩ ጣቢያ ተሸክመውት ለሄዱት ሰዎች አሳሰባቸው። ከሞተ በኋላ “ለቶልስቶይ ሞት ምክንያቱ እኔ ነኝ!” ብላ ለመጀመሪያ ልጇ በማልቀስ ነገረቻት፤ አብራት ከማልቀስ በቀር ሴት ልጇ ግን ምንም ልትላት አልቻለችም። ሁሉም የሚያውቀው እውነት ነበርና።


እውነት ነው የቶልስቶይን ታሪክ ላነበቡ ሰዎች የሚስቱን መጨቃጨቅ ተገቢ ነው ብለው ሊወስዱ ይችላሉ። ቁም ነገሩ እሱ አይደለም። ጭቅጭቅ ምን ለውጥ አመጣ ነው? ምን መለወጥ ቻለች ነው ጥያቄው?! ምንም። ጭራሽ እንድታንገሸግሸው ሆነች። ተጠየፋት። በመጨረሻም ሀብቱን ሁሉ ለበጎ ድርጅቶች አከፋፍሎ ፥ ራሱን ብቻ ይዞ ጠፋ።


የአሜሪካ የአንድነት መሪ የሚባለው አብርሃም ሊንከን በስቃይ የኖረ ሰው ነው። ስቃዩ ግን ሚስቱ ነበረች። የሊከን ሚስት አንድም ቀን አመስግናው፣ ሰላም ሰጥታው፣ ትክክል ነህ ብላው አታውቅም። ለርሷ ሊንከን ማለት ዘወትር የሚሳሳት ፍጥረት ነው። በአለባበሱ፣ በአነጋገሩ፣ በአረማመዱ ሁሉ ትወቅሰዋለች። አንዱ ጆሮው ከሌላው በመብለጡ ትፎግረዋለች። እርሱን ከሌሎች ጋር ማወዳደር ሥራዋ ነበር። ሜሪ ቶድ የባሏ ምንም ነገሩ አይጥማትም። “ሁለት ተቃራኒ ሰዎች” ይላቸዋል ዴል ካርኒጌ። ሴናተር አልበርት ጌ ሜሪ ቶድን “ጩኸቷን ጎረቤቱ ሁሉ ያውቀዋል፣ የማያቆመው ንዝነዛዋ ከማንም የተሰወረ አይደለም” ይላል።


ይሄ ቁጣ እና ጭቅጨቃ ሊንከንን ቀየረው? በደንብ። እርሷን ያገባበትን ቀን እንዲረግም አደረገው። ባገኘው አጋጣሚ ሁሉ ሩቅ መንገድ መሄድን፣ በሥራ አሳቦ ከቤት መጥፋትን፣ ከርሱ ጋር ዳኛ ዴቪድ ዳቪስን ተከትለው የሄዲ ጠበቆች በእረፍት ቀን ቤታቸው ለመሄድ እና ከሚስቶቻቸው ጋር ጊዜያቸውን ለማሳለፍ ሲጥሩ፤ ሊንከን ግን አጋጣሚውን ተጠቅሞ ከቤት መራቅ ነበር ምርጫው።

ማሪ ዩጄንክ፣ የቶልስቶይ ሚስት እና ሜሪ ቶድ የሊከን ሚስት በመጨረሻ ቤታቸውን በቁጣ አፈረሱት። ወንድ ቢሆኑ ባሎቻቸውን መደብደብ ማለት ነው ጭቅጭቅ። ብዙ ሴቶች ቤታቸውን ትልቅ መቃብር አድርገውታል በየቀኑ በጭቅጭቅ መቆፈሪያ በሚቆፍሩት ጉድጓድ። ወንድን ለምንጊዜም ለማሸነፍ የመጀመሪያው ሕግ፦ ጭቅጭቅ እና ቁጣን ማሶገድ ነው።


ቀሪዎቹ ስድስት ነጥቦችን በዚህ ሳምንት በቴሌግራም ፔጄ ላይ ማንበብ ትችላላችሁ።



 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jun 12, 2024
  • 3 min read

Updated: Apr 6, 2025


 

ከዩኒቨርስቲ እንደወጣው የመጀመሪያ ሥራዬ በአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን የሕግ ክፍል ኢንተርንሽፕ ነበረ። ምንም ልምድ እና ተጋላጭነት (exposure) ሳይኖረኝ በአንዴ ወደ ዓለም አቀፍ ማህበረሰቡ የተቀላቀልኩበት ወቅት ነበር። በዚህም ዛሬ ሳስባቸው የሚያሸማቅቁኝ ብዙ ተግባሮችን አድርጌያለሁ። በአንድ ወቅት አንድ ባልደረባችን ኩኪሶች አምጥታ ጠረጴዛዋ ላይ አስቀመጠች። በጣም የምንግባባ ስለነበርን፤ ከተግባቦታችን አንጻር አንድ ኩኪስ አንስቼ በላው። ስትመጣ አንድ ኩኪስ ተነስቷል። “ማን ነው ያነሳው? አለች።  “እኔ ነኝ” አልኩኝ። አበደች። ያልተገባ ድርጊት እንደፈጸምኩኝ ተናገረች። እኔም እጅግ ብዙ ነገር ተማርኩ።

 

ዛሬ ላይ ስመለከት፣ በተለይ የሀገራችን ማህበረሰብ ከምዕራባውያን አንጻር ብዙ ለፕሮፌሽናሊዝም ያልተገቡ ባህሪዎች አሉን። ፍቅራችንን ለመግለጽ እና መቀራረባችንን ለማሳየት የምናደርጋቸው ነውር የሆኑ እጅግ ብዙ ተግባሮች አሉ። ሰዎች ሲያወሩ ይቅርታ ሳንጠይቅ፣ ሳናስፈቅድ ዘው ብሎ ስለእኛ ጉዳይ ማውራት በመንግስት መስሪያ ቤቶች የተለመዱተግባሮች ናቸው። ሰውን ያለአገግባብ መንካት፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ ፥ የሰዎችን ድንበር (private space) ሳያከብሩ ጉንጭን፣ ጺምን ማሻሸት የመሰሉ አጸያፊ ባህሪያት የፍቅር እና የመቀራረብ መገለጫ ሆነው ይታያሉ።

 

የሰውን ፈቃድ ሳይጠይቁ ቢሮ ውስጥ ዘው ብሎ መግባት፣ ሰዎች በስልጣን፣ በእርከን ወይም በደሞዝ ከኛ ስለሚያንሱ እንደ አገልጋዮቻችን ማየት፣ በኛ እና በእነሱ መካከል ያለው የግንኙነት ውል ፕሮፌሽናል ሥራችን መሆኑን ዘንግተን ፥ ፍጹም ክብር ያላቸውን ሰዎች የኛ አገልጋይ አድርጎ ማየት ይሄ በኛ የባህል ደም ሥር ውስጥ ያለ ይመስላል።

 

ቤተክርስቲያን ስትሄዱ ደግሞ ይሄ ባህል እንደ ኩራት ሆነው፣ ስልጡን ማህበረሰብ ያሉት የስነምግባር መገለጫዎች ጭራሽ አፈር ድሜ በልተው፣ አሳፋሪ ደረጃ ደርሶ ታዩታላችሁ። በአገራችን በብዙ ነገር ድንቅ ስልጣኔን ያስተዋወቀችው ቤተክርስቲያን ፥ ዛሬ ላይ ግን ራሷን ብቻ ሳይሆን ማህበረሰቡን ራሱ ወደ ኋላ የሚጎትቱ ባህሎች ታቅፋ ታያላችሁ። በዕለተ ሰንበት ወደ ቤተክርስቲያን ሂዱ፣ እርስ በእርስ በክብር ስም ሲጠራሩ እና አንዱ አንዱን የዚህ ታላቅ ደብር፣ የዚህ ታላቅ ሀገረ ስብከት፣ የዚህ ታላቅ ጉባኤ መሪ፣ አባት እየተባባሉ ወይም ታላቁ ያቋቋም፣ ታላቁ ዝባዝንኬ ሲባባሉ ሰዓታችሁን በአግባቡ ከያዛችሁ ብዙ አልተሞጋገሱም  ወይም ሰላምታ አልተሰጣጡም ከተባለ ዝቅተኛው ግምሽ ሰዓት ነው የሚፈጀው። በዛ ላይ ምንም ነገር ሰዓት አይጠብቅም፣ ከጸሎታቱ እና ከቅዳሴው በቀር ምንም ነገር በመርሐ-ግብር እና ወጥ በሆነ መልኩ ሲካሄድ አታዩም።


ለምዕመናን ሰዓት፣ መንፈሳዊ ተመስጦ፣ እና ሰዎች ቤተክርስቲያን ሲመጡ እንዲኖራቸው ስለሚፈልጉት ሥርዓት የተሞላበት ሂደት ምንም እውቀቱም የሌላቸው፣ ማህበረሰቡ ስላለበት ደረጃ እና የአናኗር ዘዬ መገንዘብ የማይፈልጉ ሰዎች ነው የተጠራቀሙበት።


ከዛ ካህናቶቹን እና አገልጋዮቹን ቀርባችሁ ስታዩ ደግሞ የእናንተን በጎ ፍቃድ በትህትና በመጠየቅ እና የራሳችሁ ሕይወት እና እቅድ ሊኖራችሁ እንደሚችል ታሳቢ ያደረገ አቀራረብ ሳይሆን የምታዩት ፥ በመንፈሳዊ ማንነት የሰጣችዋቸውን ክብር እና ፍርሃት በዝብዞ ለመጠቀም የመፈለግ እና በድፍረት ያን የማድረግ ተግባርን ነው። የቅዱስ ጳውሎስ አንድ ምዕራፍ ብቻ የሆነውን ወደ ፊልሞና የተጻፈውን መልዕክት እባካችሁ አንብቡ። ቅዱስ ጳውሎስ እንደምን ባለ ትህትና እና ፍጹም በሆነ ሥነ-ምግብር ፊልሞና የተባለውን ምዕመን አናሲሞስ የተባለው ባሪያው ከድቶት ስለሄደ፤ ፊልሞና ይቅር እንዲለው እና እንዲቀበለው እጅግ በሚገርም ትህትና እና የፊልሞናን የመወሰን መብት ባከበረ መልኩ ሽማግሌው ጳውሎስ ይማጸናል። ወደ ጉዳዩ ከመግባቱ በፊት በዛ 25 ቁጥር ብቻ ባዘለ አንድ ምዕራፍ መልዕክት ውስጥ ጳውሎስ እስከ ቁጥር 10 ድረስ ፊልሞናን በማክበር፣ ስልጣን (autonomy) በራሱ ጉዳይ እንዳለው ግን ጳውሎስ በጌታ ሊያዘው እንደሚችል ፥ ከማዘዝ ይልቅ በፍቅር እሺ እንዲለው ሲማጸን ታዩታላችሁ። ይሄ ነው የክርስቲያኖች ሥነ ምግባር። ከቅዱስ ጳውሎስ የሚበልጥ በመካከላችን አለ ብለን መቼስ አናምንም። ታዲያ ይሄ ትህትና እና የሰውን ድንበር፣ ሰዓት፣ክብር፣ በራሱ ላይ የመወሰን ስልጣንን የማክበር ባህሪ ወዴት ራቀን?


 ሲ ኤስ ሉዊስ ሥርዓት ያለው ነገር ፈጽሞ የሰይጣን ሆኖ አያውቅም ይላል። "ሰይጣን ሥርዓት ያለው ሙዚቃ ሳይቀር ይረብሸዋል" ይላል ሉዊስ። ሥርዓት የስልጡን ማህበረሰብ መገለጫ ነው። እስኪ ሥርዓት የሌለው ግን ታላቅ ስልጣኔ የነበረ አንድ ጠቁሙን? ሥርዓት መደላደሉ ካልሆነ ያ ስልጣኔ ወይ በመፍረስ ላይ ያለ ነው ወይ ገና ወደ ሥልጣኔ መንበር እየተሸጋገረ መሆን አለበት።


እውነት ለመናገር ፕሮፌሽናሊዝምን ብናክልበት ሰዎች ፍቅራችንን እና ቅርበታችንን የበለጠ ያደንቁታል። በጣም የሚቀርበኝ እና በብዙ ነገር ከእኔ የሚበልጥ ወዳጅ አለኝ። ለመደወል ሲያስብ ግን ሁልጊዜ መጀመሪያ መልዕክት (text) ይልካል። አሁን ይመቸኝ እንደሆነ ጠይቆ፤ እሺ ካልኩት ብቻ ነው የሚደውለው። ከእኔ በላይ እጅግ በተጣበበ ሰዓት ውስጥ የሚኖር ቢሆንም ለእኔ ሰዓቶች ግን ከፍተኛ ክብር አለው። ለዚህ ወዳጄ ያለኝ ፍቅር እና ክብር በጣም ጨመረ እንጂ ይሄን በማድረጉ የራቀኝ ወይም መቀራረባችን የተጎዳ መስሎ አንድም ቀን ተሰምቶኝ አያውቅም።

 

በሕይወት፤ በየትኛውም የሕይወት ዘርፍ ቅርበታችን እና አጉል ፍቅራችን እንጂ ፕሮፌሽናሊዝም ለጠብ እና ለመቀያየም አይዳርገንም። ብዙ በአጉል መቀራረብ እና በአጉል ፍቅር የተጣሉ ሰዎችን አይቻለው፤ ፕሮፌሽናል የሆነ አክብሮት እና ሥርዓት በማሳየታቸው የተጣሉ እና የተቀያየሙ ሰዎች ግን እስከዛሬ አልገጠሙኝም።






 

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page