top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Oct 26
  • 3 min read

ree


የአዕምሮ ጅምላስቲክ ሕጻናት ጋር የተለመደ ነው። ምንም ነገር ያስባሉ። ምንም ነገር ለመሆን ፈቃደኛ ናቸው። ምንም ነገር ከመጣላቸው ይጠይቃሉ። እንደ ወፍ ለመብረር፣ እንደ ጉንዳን ለመዳህ፣ እንደ ጉዑዝ ነገር ለመድረቅ ፈቃደኛ ናቸው። ማሰሪያ የሌለው የሀሳብ ዋና ውስጥ ራሳቸውን ያስገባሉ።



አዋቂዎች ጋር ይሄ የተለመደ አይደለም። እንሸማቀቃለን። ትላንት የተናገርነውን ላለመቃረን ዛሬ ስህተት መድገም ይቀለናል። ብዙ ልጓሞች አሉብን። እንዲህ ሆኜ እንዴት እንደዚህ ሆናለሁ ብለን ራሳችንን ከፈጠራ እንገድባለን።



በዚህ ሳምንት ከአንድ ወዳጄ ጋር ስናወራ፤ እንዲህ ተባባልን። ብዙ አፍሪካኖች ወደ አሜሪካ መምጣት ይፈልጋሉ። ምንአልባትም በአንዳንድ ሀገሮች ሁሉም ሰዎች ከዛ ተነስተው ኢዚህ መግባት ይሻሉ። ለምሳሌ ይሄ ሀሳብ መጣልን። አሜሪካኖች እና አውሮፓኖች ለሁሉም አፍሪካኖች “እሺ ወደ ሀገራችን መምጣት ትፈልጋላችሁ። ሁላችሁም ኑ። እንደውም እናንተ የኛን ሀገር ውሰዱ። አሁን እንዳለው። ምንም ነገር ሳንቀንስ እንስጣችሁ። እናንተም የናንተን አፍሪካ ስጡን። ማለትም አሁን ባለንበት ሁኔታ ሙሉ ለሙሉ ቦታ እንቀያየር።”



ይሄ አይሆንም። ግን ቢሆን ምን የሚመስል ይመስላችዋል? በእኔ ግምት አሜሪካውያን እና አውሮፓውያን አፍሪካን ልክ ለቀው እንደሄዱበት ሀገራት በጥቂት ዓመታት ውስጥ ያደርጉታል። በተቃራኒው አፍሪካውያን አሜሪካንን እና አውሮፓን ያወድሙታል። የመጡበት አፍሪካን ያስመስሉታል።



የብዙ ሰው ግምት ይሄ የሚሆን ይመስለኛል። ለምን እንደዚህ አሰብኩኝ? ምክንያቱም አፍሪካ በዓየር ጸባይ እና በመልካ ምድር ምቹነት ከብዙ የአውሮፓ ሀገራት እና የአሜሪካ ስቴቶች የተሻለች ነች። ግን በዛ ምድር የምንኖር ሰዎች አመለካከታችን፣ ባህላችን እና የትምህርት ደረጃችን በጣም ዝቅ ያለ ነው። ሰጥቶ መቀበል የሚባለው ባህል፣ ስትራቴጂክ ሆኖ ማሰብ፣ የፖለቲካ ባህላችን እና መሰል ለሰው ልጆች በሰላም እና በብልጽግና የመኖር ዋስትና የሆኑ ከአዕምሮ የሚነሱ ሀብቶች ላይ በጣም ዝቀተኛ ነን።



ይሄ ለምን እንደሆነ በርግጠኝነት እኔ መናገር አልችልም። ብዙ ጥናት የሚሻው ይመስለኛል። የማውቀው አንድ ነገር ጥቁሮች ዝቅተኛ IQ ስላለን እንዳልሆነ ነው። ምክንያቱም በአውሮፓ እና አሜሪካ መጥተን እንደ ነጮች በእነሱ ዘርፍ ጥሩ የሆኑ ብዙ ስላሉ። በተለይ ጥሩ ትምህርት ገና በልጅነታቸው ያገኙ ሰዎች በብቃት ደረጃ ምንም አይተናነሱም።



ይሄ ዓይነት የሀሳብ ጨዋታ የሚጠቁመን ብዙ ነገሮች አሉ። አንደኛው የጎደሉንን ነገሮች ቆም ብለን እንድናስብ እና ችግሮቻችንን በተለየ መነጽር እንድናይ ያደርገናል።



ለምሳሌ በአሜሪካ ውስጥ ሁለት በጣም ሀብታም ስቴቶች አሉ። ኒው ዮርክ እና ካሊፎርኒያ። በአሜሪካ ውስጥ ሁለት በጣም ቅይጥ (diverse) የሆኑ እና ከነጩ ይልቅ ሌላው ማህበረሰብ በቁጥር የሚበልጥበት ስቴቶች አሉ። ኒው ዮርክ እና ካሊፎርኒያ። በደቡቡ የአሜሪካ ስቴቶች ውስጥ በጣም ሀብታሙ ከተማ አትላንታ ነው። በጣም ቅይጡ (diverse) ከተማም አትላንታ ነው። የአትላንታ ሀብት ብቻ በደቡቡ ካሉት ስቴቶች ሁሉ ይበልጣል። ደቡቡ እንደ ሚሲሲፒ፣ አላባማ፣ ሚዙሪ፣ አርካንሳ፣ ሉዊዚያና የመሰሉ ስቴቶች ከ90% በላይ ነጭ ሲሆን፤ እጅግ ደሃ ስቴቶች ናቸው።



ከዚህ ምን እንማራለን?



ለምሳሌ ወደ ሀገራችን እንሂድ። ሐዋሳ የዛሬ አስር ዓመት ኢትዮጵያ ውስጥ በፍጥነት እያደጉ ከነበሩ ከተሞች አንዷ ነበረች። ብዙ ሀብታሞች መፈጠር እና ሆቴሎች፣ ንግዶች መስፋፋት ጀመሩ። የመሬት ዋጋ ሰማይ መንካት ጀመረ። ሐዋሳ የዛሬ አስር ዓመት የነበራት ቅይጥነት አስገራሚ ነበር። የመንግስት መስሪያ ቤቶች ያሉ የስልጣን ቦታዋች በብዙ ብሔሮች የተያዙ ነበሩ። አንድ ዓይነት ነገር የለም። ማንም ቤቱ የሚመስለው ከተማ ሐዋሳ ነበር።



ከዛ ምን ሆነ? የክልል ጥያቄን ያነሱት ሰዎች ብዙ ስህተት ሰሩ። የክልል ጥያቄን መጠየቃቸው አይመስለኝም ስህተቱ። ይልቁንስ የከተማዋን የእድገት ምስጢር ፈጽሞ አለመረዳታቸው ነበር። ዛሬ የመሬት ዋጋ ወድቋል። ማውቃቸው ትልልቅ ባለሀብቶች ሁሉም ለቀው አዲስ አበባ ገብተዋል። ለመመለስም ፈጽሞ አያስቡም። ያሉትም መውጣት ይሻሉ። ለምን? መልሱ ግልጽ ይመስለኛል።



ኦሃዮ፣ ስፕሪንግ ፊልድ የዛሬ ስምንት እና ሰባት ዓመት የጎስት ከተማ እየመሰለ ነበር። የከተማው ባቡር ቆመ። ባዶ የሆኑ ቤቶችን መመልከት የተለመደ ሆነ። ፋብሪካዎች ተዘጉ። ከዛ ዲሞክራት ሲመጡ ከተማዋን ለማነሳሳት ከሄቲ የመጡ ስደተኞችን በገፍ ወደ ስፕሪግ ፊልድ ወሰዷቸው። ከተማዋ መነሳሳት ጀመረች። የከተማው ባቡር መንቀሳቀስ ጀመረ። የቤቶች ዋጋ ከፍ ማለት ጀመረ። ለምን? መልሱ ግልጹ ነበር። ከተማዋ በአዲስ መጤዎች ጉልበት እና የፈጠራ አቅም መነሳሳት መጀመሯ ነበር።



አንድ ብልህ መሪ ምንድነው የሚያደርገው? ከዚህ በፊት በሌሎች ቦታዋች የሰሩ ሙከራዎችን በርሱም ግዛት መሞከር ነው። ኢትዮጵያ ውስጥ የትም ቦታ ብትሔዱ ከነባሩ ሕዝብ በላይ ለዛ አከባቢ መጤ የሆነው ማህበረሰብ ንግድ ውስጥ አለ። የቀዳማዊ ኃይለሥላሴን የካቢኔ ስብሰባዎች የጻፈው አምባሳደር ዘውዴ ረታ የኢትዮጵያን የንግድ አውታሮች ተቆጣጥረው ይዘውት ስለነበሩ አረቦች ጽፏል። መጤዎች ነበሩ ኢትዮጵያ ውስጥ በንግድ የተሳካላቸው። የአረቦች መብዛት ያስፈራው የንጉሱ ካቢኔ ሀሳብ ዘየደ። ይሄን ሀሳብ ለንግድ ሚኒስትሩ መኮንን ሀብተወልድ የነገረው አንድ የተማረ ጉራጌ ነበር። ጉራጌዎች የንግድ ክህሎት አላቸው። አረቦችን ሊተኩ የሚችሉት እነርሱ ናቸው። ስለዚህ አረቦችን ገፍትረን ከምናሶጣ ጉራጌዎችን አምጥተን ብድር እንስጣቸው። ከዛ ጎን ለጎን ሱቅ ይክፈቱ። በዓመቱ አረቦቹ ሲከስሩ በራሳቸው ለቀው ይወጣሉ አለው። የሀብተወልድ ልጅ ይሄን ሀሳብ ተቀበለ። መንግስት ጉራጌዎችን በገፍ አምጥቶ መርካቶ ላይ በማስፈር ብድር በመስጠት ንግድ እንዲሰሩ አደረገ። በዓመቱ አረቦች ከስረው በራሳቸው ጊዜ ለቀው ወጡ። መርካቶ ከአፍሪካ ትልቁ የገበያ ማዕከል ሆነ።



ስለሀገሩ ትልቅነት የሚያስብ ሰው በሀሳብ ይጫወታል። የሰዎችን ዝቅተኛ የዘረኝነት እና የጎሳነት ስሜት በመጫር ሳይሆን ከእውነት ጋር ማህበረሰብ እንዲጋፈጥ ያደርጋል። መጽሐፉ ቅዱስ የስደት ታሪክ የተከተበበት መጽሐፍ ነው። ሰዎች ከእናት አባታቸው ተለይተው ታላቅ የሆኑበትን ታሪክ የምናነብበት መጽሐፍ ነው። በሀገራችንም ከቀዬ ውጣ ከምንል ይልቅ ወደ ቀያችን እና መንደራችን አዳዲስ ማህበረሰቦች እንዲመጡ፣ በመንግስትም ሆነ በግሉ ዘርፉ ላይ ገብተው እንዲወከሉ ብናደርግ ተዓምር መስራት እንችል ነበር።



ከኢትዮጵያ ብቻ አይደለም፣ ከጎረቤት ሀገራት ጭምር እየመጡ በነጻነት እንደ ዜጋው ንግድ ውስጥ እንዲገቡ፣ የራሳቸውን ባህል እና ማንነት እንዲያጎለብቱ ብንፈቅድላቸው ተዓምራዊ ለውጥ ማየት እንችል ነበር። ከቦታ ቦታ ሰዎች እንደልብ ተዟዝረው መስራት እና ሀብት ማፍራት ቢፈቀድላቸው ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ከተሞች ተዓምር መስራት ይችላሉ።



ዛሬ በስደተኞች ታላቅ የሆነችው ሀገረ አሜሪካ የታላቅነቷ መሠረት የሆነው ስደት ላይ በሯን እየቆለፈች ነው። የዛሬ ዓመት የነበረው የኢኮኖሚ መነቃቃት ዛሬ የለም። በሁሉም ከተሞች ድብታ እየሰፈነ ነው። ኢኮኖሚው በጣም ተቀዛቅዟል። እስከዛሬ የነበረው የአሜሪካ ብልሃት ነገሮች እንዲህ ሲከፉ መንገዳቸውን (course) ቶሎ ማቃናት ይችላሉ። አሁንም ሳይረፍድ ዘረኝነት ያነሳሳው እብደት እና ዕውረነት ይሰክናል የሚል እምነት አለኝ።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Oct 19
  • 3 min read
ree

አሸናፊው ስብዕና ነው ደግነት። በዚህ ምድር ላይ ሰውን ወደ ሕይወታችሁ ለማስጠጋት አንድ መለኪያ፣ አንድ ሜቲሪክ፣ አንድ ሚዛን ብቻ ቢኖራችሁ። ያ ደግነት መሆን አለበት። ጥሩ ነገሩ ብዙ መለኪያዎች አሉን። ግን ደግነት የጎደለው ሰው ሁሉ ነገር ቢኖረው እንኳ በፍጹም ወደ ሕይወታችን መግባት የለበትም። ደግነት የሰው ልጅ የመልካምነቱ ውሃ ልክ ነው። ምንም እውቀት ቢኖረው ሰው ደግ ካልሆነ በዚህ ዓለም ላይ እዳ እንጂ ትሩፋት አይደለም። ምንም ገንዘብ እና ጠቃሚ ምግባሮች ቢኖሩት ደግነት የሌለው ሰው ይሄን ዓለም የመረዳት አቅም የለውም።

 

ደግነት ሕጻን ሲያይ ይራራል። ደግነት ሰው ሲያይ ያ ሰው ምስኪን እናት እንዳለችው፣ እህት ና ወንድም እንዳሉት፣ ልጆች ሊኖሩት እንደሚችሉ ያስባል። ደግነት የሰው ልጅን የዓለም መጋረጃ ከፍቶ በዛ ሰው ውስጥ ያለውን ውጣ ውረድ ለመመልከት ይችላል። ደግነት የሰውን የውጣ ውረድ ታሪክ ሲሰማ እንባውን ያፈሳል። ሕይወት በሞት አላዝር ፊት እንባውን እንዳፈሰሰ።

 

ሁላችሁን እስቲ ወደ ጋዛ ልውሰዳችሁ። የዋህ እና ደግ የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእነዛ ሕጻናት መካከል በእግሩ ቢራመድ ምን የሚል ይመስላችዋል? እናንተ ሙስሊሞች፣ እናንተ የነገ ሀማሶች፣ እናንተ የእፉኝት ልጆች የሚል ወይስ እነዛ ያለ አባት፣ እናት፣ ወንድም እና ቤት ከቀሩ ልጆች ጋር የሚያነባ ይመስላችዋል? ደግነት የሚያደርገው ያቺን ሳምራዊት ሴት ያሳያትን ደግነት ነው ለእነዚህ የጋዛ ሕጻናት የሚያሳየው። አብሮ ቁጭ ብሎ ያነባል። አብሮ መከራቸውን ይጋራል።

 

ደግነት ፍርሃቱ እንዲያሸንፈው አይፈቅድም። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሥጋ ፍርሃት ራሱን አሳልፎ የሰጠ ቢሆን ምን ሊሆን እንደሚችል አስቡት። በቀራጩ ቤት ምሳ አይበላም። በዛች በዘማዊት ሽቱ ለመዳሰስ እና ለመታጠብ አይፈቅድም ነበር። ምክንያቱም ሰው ምን ይለኛል፣ ባህሉ እና የተዘረጋው መዋቅር ምን ይፈርድብኛል ብሎ ከፈሪሳውያን ጋር ይቆም ነበር።

 

ደግነት ግን ድንጋይ በእጃቸው ጨብጠው አንዲት ምስኪን ሴትን ለመውገር በተሰበሰቡ ሰዎች ፊት አጎነበሰ። ያቺን ሴት ሊያድን መሬቱን ፋቀ። ደግነት ድንጋይ (መሳሪያ) ከያዙ ሰዎች ጋር አይተባበረም። ደግነት የክፋትን ሠራዊት ይበትናል እንጂ። ዘማዊቷን ለማዳን ደግነት ምንም አይሸማቀቅም። የሌሎች ክፋት ለእነርሱ በችግራቸው ጊዜ ለመድረስ የእርሱን ርህራሔ አያጎድለውም። ልቤ ሆይ ደግነትን በየቀኑ ተማር።

 

ደግነት ፊት ለፊቱ ላለው የሰው ልጅ የውጣ ውረድ ሕይወት ቦታ ይሰጣል። ከፍርሃት ጋር አይቆምም። ቡዙዎቻችን በሚገባ ፍቅር እና የሰው ልጅ ደግነት መካከል ያደግን አይደለንም። ዛሬም በሕግ ማስከበር ሰበብ ከሀገራችን ኢትዮጵያ እስከ አለንበት የስደት ቦታ ድረስ የምናየው የክፋትን ጥግ ነው።


በቤተመንግስት ውስጥ ሆኖ ስለ አትክልቱ እና በእግሩ ስለሚራመድበት የውበት ኮሊደር የሚጨነቅ መሪ እንጂ በእርሱ ወታደሮች እና ድሮኖች ስለሚናጋው የቤተሰብ ሕይወት እምብዛም የማይገደው የጭካኔ መሪን ነው የምናየው። ግን ይሄው መሪ ጩጬ ምስኪን ወንድ ልጅ አለው። ወንድ ልጁን ይወዳል። ሌሎችም እንደርሱ የሚወዱት ልጆቻቸው እየተገደሉባቸው እንደሆነ ግን ማሰብ አይፈቅድም። ልቡን ለደግነት አልከፈተውም። ነጻ አውጪ ነን ያሉትም ነጻ እናወጣዋለን ያሉትን ሕዝብ በግፍ ቀንበር ይገርፉታል።

 

ተሰደን በመጣንበትም ሀገር ማስክ ያጠለቁ ሰዎች የጭካኔ እና የዘረኝነት ክፋታቸውን በኢሚግሬሽን ሰበብ በምስኪን ሰዎች ላይ ያዘንቡበታል።



ዛሬ ያለን የነገ አፈሮች ነን። ነገ በታሪክ መጻፍ ውስጥ እንኳ የማንገባ ኢምንቶች ነን። ይሄ እድሜያችን በሚገርም ፍጥነት ይበራል። ከዛም ያልቃል። በሞት ወደ ምንምነት እንቀየራለን። እንግዲህ ለዚህ ሕይወት ነው ሰው ጎድተን፣ በሌሎች ላይ ጥቅም ይዘን፣ ተቆሳስለን የምናልፈው። ከልጅነት ጀምሮ በጭቆና ያደግንበትን በሌሎች ላይ ድጋሚ ያን ክፋት እና ጭቆና አንጸባርቀን እናልፋለን። የተጎዳ እና ያልታከመ ልብ ፥ ሌሎችንም ጎድቶ እና አቁስሎ ያልፋል።

 

ደግነት የሌለው ሰው ሌላው ሁልጊዜ ያስፈራዋል። ደግነት የጎደለው ሕይወት ሌላው ጥቅም እንደሚይዝበት፣ የእርሱ. የሆነውን ነገር ሊነጥቀው እንደሚፈልግ ነው ሁልጊዜ የሚያስበው። ደግነት አልቦ ሰው በቁስ ማጠራቀም ሕይወቱን ያፍናታል። ከሰው ጋር ነጻ ሆኖ መደሰት አይችልም። በትንንሽ ነገሮች መሳቅ አይችልም። ነጻ ያልሆነ፣ ያልተላቀቀ፣ የሚከብድ ስብዕና ነው ያለው። ሁልጊዜ ያስመስላል። ከፍ ያለ ቦታ ላይ ሲሆን ደግሞ ይጨቁናል። እድሉን ሲያገኝ ያሰቃያል።

 

በየቀኑ በጉዞአችን፣ በየቀኑ በሥራችን፣ በየቀኑ በመንገዳችን የተጎዱ ሰዎች ይገጥሙናል። ደግነትን ሆን ብለን ካልተለማመድን ፍርሃት ነው ባህሪያችንን የሚቆጣጠረው። ያን ጊዜ እነዚህን ሰዎች መልሰን እንጎዳለን። ለዚህ ነው የበራችን መቀነት ላይ፣ የየቀን መንገዳንች ላይ “ልቤ ሆይ ደግ ሁን!!!” ማለት ያለብን። ቢያንስ ባንደበታችን ሰው ላለመጉዳት መጠንቀቅ ይኖርብናል። ክፉ ከመናገር እና ሰውን ከማቁሰል ራሳችንን መገደብ ይኖርብናል። “ልቤ ሆይ ደግ ሁን” ልንለው ይገባል። ለሰዎች ብለን ብቻ እንዳይመስላችሁ። ደግነት የራሳችንን የልጅነት እና የአዋቂነት የመንፈስ ትሮማ (ስቃይ) እና የውስጥ ቁስል መፈወሻ ብቸኛው መድኃኒት ስለሆነም ጭምር እንጂ። የደግነት እንባ የውስጥ ቁስል ፈዋሽ ፋፋቴ ነው። ከመፍረድ ያዘገያል ደግነት። የማናውቀውን የሰው ልጅ ሕይወት መጋረጃ ከፍቶ ያሳየናል።


ለጊዜያዊው ለዚህ ሕይወት ውበቱ እና ክብሩ ደግነት ነው። ደግ የሆነ ሰው ትንሿን ዘመኑን ያከብራታል።


በሞቱ አልጋ ላይ የመጨረሻ ዓይኖቹን ሲጨፍን ለዚህ ነበር ብሎ አይዘጋውም። ይሄ ሕይወት አጭር እንደነበረ ገና ድሮ እንደገባው ግን ደግሞ የሌሎችን ቁስል ፈውሶበት ያሳለፈው መሆኑን በማየት እየሳቀ ዓይኖቹን ይጨፍናል።

 

ልቤ ሆይ ደግ ሁን።

 
 
 
ree


አላን ዋትስ ስለ ካርል ዩንግ በጻፈው መጣጥፍ ላይ ከራሱ ጋር የታረቀ ሰው በዚህ ዓለም ላይ ካርል ዩንግ ነበረ ይላል። ዩንግ ራሱ ላይ ያሉትን ሕጸጾች እና ድካሞች በይሁንታ ያለማፈር የተቀበለ ሰው ነበር። በተለይ በ1950ዎቹ ሲዊዘርላንድ ላይ ለቀሳውስት ያደረገው ንግግሩ ዩንግ የሰውን ተፈጥሮ በጥልቀት መረዳቱን የሚያሳይ ነበር።



ሰዎች ለራሳቸው ጥቅም እንደሆነ እስካወቁ ድረስ ምንም ክፋትን በሰዎች ላይ የማድረግ አቅም አላቸው። የሰው ልጆች በጎ ላደረገላቸው እና መልካሙን ነገር ለሰጣቸው ሳይቀር የእነሱ ሕይወት የሚሰምር ከመሰላቸው ወይም በጣም የሚፈልጉት ነገር እንዲሆንላቸው የወደዱ እንደሆነ ክፋትን ለማድረግ ፈቃደኛ ናቸው። ለዚህ ነው ለክርስቲያኖች የክርስቶስ ሕይወት አስገራሚ የሆነው። ምክንያቱም በበርባን ምትክ ንጹሁ ክርስቶስ ለመሞት ፈቅዷልና። በቅርብ አንድ ወዳጄ ስለ ልጁ ነገረኝ። ልጁ ገና አራት እና አምስት ዓመቷ ነው። በቤቱ ውስጥ እርሷ ነበረች እንደ እንቁ የምትታየው። ነገር ግን አዲስ ልጅ ሲወለድ የቤተሰቡ ትኩረት ሁሉ ወደ ሕጻኑ ሆነ። ከዛ ይህች ሕጻን ልጅ አዲስ የተወለደውን ልጅ ጠላችው። መምታት ጭምር ፈለገች። እኔን በጣም የገረመኝ የአንዲት ነፍስ ያላወቀች ልጅ ሪያክሽን ራሱ ከፍቅር ይልቅ ቅናት መሆኑ ነው። በዚህ ዓለም ላይ ገና ክፍትን ያልተማረች ሕጻን ልጅ ተፈጥሮዋ የነገራት አዲስ የመጣው ልጅ ትኩረቱን ስለወሰደ ጠላትሽ ነው የሚል ነው። ይሄ የሚነግረን የሰው ልጅ ጠባዩ እንስሳዊነት ሲሆን፤ ተፈጥሮውም እስካልተገራ ድረስ ከበጎነት ይልቅ ለክፋት የተመቸ መሆኑን ነው።



ለዚህ ነው ሰው የራሱን ጥቅም ከሚያጣ፤ ሰዎችን አሳልፎ መስጠት እና መጉዳት ምርጫው የሚሆነው። ይሄን ለክፋት የተመቸን ማንነታችንን እውቅና ካልሰጠነው እና በፍጹም ሰብአዊ አስተሳሰቦች እና ክርስትናዊ ፍቅር ካልገራነው በቀር ሰው አውሬ ነው። ክርስቶስን የተለየ የሚያደርገውም ይሄ ነው። ተፈጥሮ ለመልካም ነገሮች ያደላ ነው። ፍጹም ስለራሱ ሕመም ብቻ ማሰብ በሚገባው የመስቀል ሰዓት ያሰበው ከራሱ ይልቅ ስለ ሰቀሉት ምህረትን ነበር። ከዛም ለሚወዳት እናቱ ልጅ እና ተንከባካቢን መስጠት ነበር። ከዛም በዛ መራራ ሰዓት አንተም እንደኛው ወንጀለኛ ነህ እያለ በሚከሰው አላዋቂ ከመናደድ እና ከመራገም ይልቅ በሌላኛው ጎኑ ሆኖ አንተ ልዩ ነህ ያለውን ያን ሰው የገነት ቁልፍን መስጠት ነበር ሥራው ያደረገው። ለክፋት ፈጽሞ አልመለሰም። ከክፋት ጋር ድርድር ውስጥ አልገባም። ፍርድን ሊሰጥ ከማይችል ከጲላጦስ ፊት አለፈለፈም። ሦስቴ የከሰሰውን ሰው ከሰስከኝ ብሎ አላወራውም። ይሄ ሁሉ ክፋት ምንም አላስደነቀውም።



የበሰሉ ሰዎች የሚደርሱበት ደረጃ ያ ይመስለኛል። በሰው ክፋት አለመደነቅ። ከሰው ልጆች ሞራል እና ከፍታን አለመጠበቅ። የሰው ልጅ ተፈጥሮ በሆኑ ጉዳዮች ጉድ አለማለት። ያ ብቻ ሳይሆን እነርሱም ለዛ ክፋት ብቁ መሆናቸውን ማወቅ። ለጴጥሮስ መመለስ ትልቁ አስተዋጽኦ ክርስቶስ በርሱ መክዳት አለመደነቁ ነው። የሰው ልጅ የሚድን ከመሰለው ሁሉን ትቶ የተከተለውን መልሶ ይክደዋል።



ተመልከቱ አሜሪካ ውስጥ እየተካሄደ ያለውን ጉድ። በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ክርስትናን የሚያራምድ ነው። አሜሪካ ውስጥ በባለፉት ሃምሳ ዓመታት ውስጥ እንደዚህ ጊዜ ስደተኞች ባይተዋርነት ተሰምቷቸው አያውቅም። ጥቁር እና ስደተኛ ፍጹም ወደ ሆነ ባይተዋርነት እየተገፉ ያለበት ዘመን ላይ ነን። አንገታቸው ላይ መስቀል ያደረጉ እና የቻርሊ ከርክን መገደ አስመልክቶ ወደ ቤተክርስቲያን እየጎረፈ ያለ የትረምፕ ደጋፊዎች ናቸው ስልጣን ላይ ያሉት። ከክርስትና በላይ ለስደተኞች መጨነቅ ያለበት ሃይማኖት መኖር ያለበት አይመስለኝም። ምክንያቱም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰደደ ነበር። ለስደተኞች ፍጹም ርህራሄ እንድናሳይ የተጋበዝንበት ሃይማኖት ነበር። ክርስትና መሠረቱ፣ ምሰሶው፣ ጣሪያው ሁሉ ምስኪኖችን እና መሄጃ የሌላቸውን በመቀበል ላይ የተመሰረተ ነው። ቤተክርስቲያን ለዚህ ነው የስደተኞች ቤት የምትባለው። ተሰደው የመጡ ሰዎች የሚጠለዩት የክርስቶስ ቤት ውስጥ ነው።



አሁን ግን ክርስትና የሰው ክፋትን ሊገራው ይቅርና የመጨቆኛ መሳሪያ ሆኖ መጥቷል። ኃጢያተኞች ቤት እየሄደ በአመንዝራዋ እንባ እግሮቹ የታጠበ፣ በቀራጩ ቤት እራት የበላ፣ ከወንበዴው ጋር ንግግር ያደረገ፣ ባል እየቀያየረ ከኖረች ሴት ጋር ለማውራት በጠራራ ፀሐይ ወንዝ ዳር ቁጭ ብሎ የጠበቀን አምላክ የምናመልክ እና የምንከተል ሰዎች ፈጽሞ ልንሆን አንችልም፤ አሁን የምናደርገውን እያደረግን። ይሄ የክርስትና ተቃራኒ ነው። ይሄ ፖለቲካ እንጂ ክርስትና፣ ሃይማኖት ሊሆን አይችልም። ለባህሪያችን የሚስማማ ነገር እያደረግን ክርስቲያን ተብለን ልንጠራ አንችልም።



ለዚህ ነው ዩንግ በዚህ ስብከቱ ለእነዛ ቀሳውስት የክርስትና መሠረቱ በራሳችን ውስጥ ያለውን በርባንን፣ ያን ወንበዴ፣ ያን ዘረኛ የሆነውን እና ቡድነኝነት የሚስማማውን ተፈጥሮአችንን መቀበል ነው ያለው። በርሱ ማፈር ሳይሆን መቀበል፣ በውስጣችን እንደሚኖር ማወቅ ነው ያለብን። ምክንያቱም ሰዎች እንደዛ ነን። ያንን በውስጣችን ያለው የክፋት ጥግ ስናውቅ ሌላው ላይ የመፍረድ አቅም አይኖረንም። ሌሎችንም ከፍ ወዳለ ስብዕና እና እርከን ማውጣት እንችላለን። ያኔ ብቻ ራሳችንን ወደ ማወቅ እና ክርስቶሳዊ ፍቅርን ወደ መላበስ ማደግ እንችላለን።


አረመኔያዊ ነገሮች ሊደርሱብን የፈቀድን ካልሆንን የክርስቶስን ፍቅር መሸከም የምንችል አይመስለኝም። ምክንያቱም መልካም ካልሆንን የሰዎች ክፋትን መቋቋም እንችላለን። የሰዎች ክፋትን ስናውቅ ነው ደግሞ እውነተኛ መልካም መሆን የምንችለው። ምክንያቱም በጎ እንደሚሰጠን እያመንን መልካም ካደረግን’ማ ከተፈጥሮአችን ተቃራኒ የሆነን እምነት አልተከተልም። ክፋት እና መከዳት እንደሚጠብቀን አምነን መልካምነትን የመረጥን ከሆንን ብቻ ነው በመርህ እየተጓዝን ያለነው። በሰው ልጆች እንደምንጎዳ አውቀን ነው ፍቅርን የመረጥነው። ባጎረስን እንደምንነከስ በፍጹም ጠብቀን ነው እጃችንን በክፋት አፍ ውስጥ የከተትነው። ለምን? ይሄ ምርጫ ነው። ምርጫችን በጨለማው ዓለም ውስጥ ጨለማ ላለመሆን ነው። በጨለማው ዓለም ውስጥ ላለመታየት የፈለገ ሰው እርሱም ጨለማ ነው መሆን ያለበት። ከጨለማው ጋር የተባበረ በጨለማው አይጎዳም። የጨለማውን ጨለማነት በመልካም ባህሪ እና በፍቅር ለመለወጥ የፈለጉ ሰዎች ብቻ በዚህ ዓለም ክርስቲያን ተብለው ይጠራሉ። ከዓለም እና ከተፈጥሮአችን ግብዣ ውጪ ክፋትን በክፋት ላለመመለስ ወስነዋልና። እንደሚጠቁ እና እንደሚከሰሱ እያወቁ ራሳቸውን ለሚበልጠው የስብዕና ማማ አሳልፈው ሰጥተዋል። ከርሱ የመከዳት የውስጥ ሕመም እና የሀሰት ክስ ስቅላት ቁስል ጋር አሁን ተባብረው ፥ ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ለመተባበር የመርህ ውሳኔ አድርገዋል። በስም ሳይሆን በተግባር ክርስቶስን ለመምሰል መጣር የእነዚህ ራስን እና ሰውን የመረዳት ጉዞ እና ከዛ ተፈጥሮአችን በተቃራኒ የመጓዝ ውሳኔ ነው።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page