top of page
Search
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Apr 13
  • 6 min read




አዋቂው ቻርሊ መንገር እንዲህ ይላል "95% የሚሆነው የስኬት ምንጭ ደደብነትን ከሕይወት በማራቅ የሚመጣ ነው።" ብዙ ሰዎች ስኬት የሚገኘው እጅግ አዋቂ በመሆን ይመስላቸዋል። ባለው የዘር ግንድ ሳይሆን ዓለም ላይ ባሳደረው ተጽዕኖ ምክንያት በዌስት ሚኒስትር ለመቀበር የበቃው ቻርልስ ዳርዊንን ብትጠይቁት እውነቱን ይነግራችዋል። ዳርዊን በሕይወቱ ገና ወጣት እያለ ነበር የIQ መጠኑ ዝቅተኛ እንደነበረ የደረሰበት። ግን ታታሪ ሰው ስለነበረ ከሱ በፊት የነበሩ ሰዎችን ስኬት እና ውድቀት ሲያጠና የደረሰበት እውነት ፥ ስኬት እጅግ ብዙ ጊዜ ደደብነትን በማሶገድ የሚገኝ እንጂ ስማርት በመሆን የሚመጣ እንዳልሆነ ነበር። ስለዚህ በሕይወቱ ሁሉ ደደብ ላለመሆን ብቻ ሠራ። ምንአልባት ዓለም ሁለት ትርክት ቢኖራት ፥ አንዱ ትርክት መሠረቱ የዳርዊን ነው። ደደብነትን በከፍተኛ ደረጃ በመቀነስ የዓለም የትርክት አንደኛው ምንጭ ሆነ።



ትዝ ይላችዋል ልጅ ሆነን ወላጆቻችን ደደብ ብለው ለምን እንደሚሰድቡን? ስማርት ስላልሆንን አልነበረም። ፈጽሞ። ደደብነት ስማርት (ጂኒየስ) ያለመሆን አይደለም። ደደብ የሚሉን የነበረው ብዙ ሰው ዓይቶት እኛ ማየት ስለተሳን ነገሮች ነበር። በቀላሉ ግልጽ ሊሆንልን የሚችሉ ነገሮች ከተሰወሩብን ደደብ ይሉናል። እንደ ሮቢንሰን አዳም ትንታኔ ደደብነት ማለት በጣም ግልጽ የሆነን ነገር ችላ ማለት ወይም መካድ ነው።



ሰው ሁሉ ፍቅረኛዋ እየተጫወተባት እና በአፉ ብቻ እየደለላት እንደሆነ እያወቀ ነገር ግን እርሷ ብቻ ይወደኛል ብላ የምታስብ እና “እርሱ እኮ እንዲህ ስለሆነ ነው” እያለች ምክንያት የምትሰጥ ሴትን ደደብ እንላታለን። ምክንያቱም ሁሉም ማየት የቻለውን ነገር እየካደች ነውና። ይህች ሴት በመስታወት ብቻ የሆነ በር ተመልክታ ነገር ግን በሩ ላይ የመክፈቻ እና መዝጊያ መያዣ ያለውን ሳታይ እንደምትጋጭ ሰው ትመስላለች። መስታወቱ ጥርት ማለቱ የበሩን መያዣ እንዳታይ አድርጓታል፤ ምንም እንኳ ያ በግልጽ ቢታይም።



ደደብነት የሚመነጭባቸው ስምንት ዋነኛ ቦታዎችን እንመልከት፤



1) ከየቀን ሁኔታ እና ከምቾት ዞናችን ስንወጣ፤



ለምሳሌ ታዋቂው የጊታር ተጫዋች እና ቦስተን ስቴት የሚኖረው ዮዮ ማ ለኮንሰርት ኒው ዮርክ ከተማ ሲሄድ ታክሲ ውስጥ ጊታሩን ረስቶ ወጣ። ዮዮ ማ ስለሆነ ከከተማው ከንቲባ እስከ ፖሊሲ አለቃው እና የሕዝብ ሬዲዮ ተረባረበ። ይሄን የሰሙ ሰዎችም ሆነ ሌሎች ጊታር ተጫዋቾች “ዮዮ ማ አደንዣዥ ዕጽ (drug) ወስዶ ነበር ወይ ሰክሮ ነበር” እያሉ አሾፉ።


በሚገርማችሁ ሁኔታ ይሄ እንዴት በራሳቸው ላይ ሊፈጠር እንደሚችል ብዙዎች እምብዛም መፈተሽ አልፈለጉም። እውነታው ግን ኒው ዮርክ ከተማ ውስት ለኮንሰርት ከሚሄዱ ጊታሪስቶች 15% የሚሆኑት ጊታራቸው ከኮንሰርት በፊት ወይ በኋላ ይጠፋባቸዋል። ለምን? ምክንያቱም ከየቀን ውሎህ እና ከምታውቀው ከባቢ ስትነጠል አዕምሮአችን የቱ ጋር መልህቁን እንደሚጥል አያውቅም። አዕምሮአችን የሚደገፍባቸው የልምድ እና የአከባቢ መዘውሮች ይቋረጣሉ። ለዚህም ነው አዲስ ከተማ ሄደን የሆቴላችንን ቁጥር የምንረሳው። ለዚህ ነው አንዳንድ ሰዎች ኤርፖርት ደርሰው ፓስፖርታቸው ግን ኪሳቸው ውስጥ የለም። ለምሳሌ ከክፍላቸው መኪናቸውን እየነዱ ለመሄድ አስበው ወጥተው ፥ የመኪናቸውን ቁልፍ ግን ክፍላቸው ረስተዋል። የመጀመሪያው ይሄን ደደብነት የማሶገጃው መንገድ አዕምሮአችን የልምድ እና የአካባቢ እስረኛ መሆኑን ማወቅ ነው። ለምሳሌ መንገድ የሚሄድ ሰው ፖስፖርቱን ነገ የሚያደርገው ጫማ ውስጥ ቢከት ፥ ይሄን ደደብነት በቀላሉ አሶገደ ማለት ነው። ወይም ቁልፋችንን ሁልጊዜ ተመሳሳይ ቦታዎች ብቻ ማኖር። ሁሉንም ነገር ካላንደር ላይ ማኖር እና የጠዋት የመጀመሪያው ሥራችን ካላንደርን ቼክ ማድረግ ቢሆን


ሰዎች ደደብ ነገር ሲያደርጉ ከማሾፍ እና ከመሳለቅ፤ "እኔ በምን ሁኔታ ብሆን ነው ይሄን የምፈጽመው" ብላችሁ ጠይቁ። ያን ቢጠይቁ ኖሮ ዮዮ ማ የሰራውን ደደብነት ሌሎች ጊታሪስቶች ባልደገሙ ነበር።



2) በቡድን ውስጥ መሆን፤



የናሳ የ1986 ትልቁ አደጋ የዚህ የቡድን (የግሩፕ) ውጤት ነው። በጣም ብዙ ኢንጂነሮች የኦሪንግን (O-ring) ችግር ያውቁ ነበር። ግን በቡድን ስብሰባ ወቅት ሌሎቹ ዝም ስላሉ ሁሉም ፈርተው ዝም አሉ። ምክንያቱም ከላይ ያሉት አለቆቻቸው እና ዋይት ሃውስ የፕሮጀክቱን መሳካት እንዲፋጠን ይፈልጉ ነበር። በሰላማዊ ሰልፍ ወቅት ሰዎች በግል ቢሆኑ መቼም የማያደርጉትን ነገሮች ያደርጋሉ። ለምን? ምክንያቱም በግሩፕ ሲኮን ደደብነት ይደበቃል። ደደብነት ጀግንነት ተደርጎ ይቆጠራል።


ካስ ሰንስቲን በአንድ መጽሀፉ ለመሪዎች ምክር ሲሰጥ በስብሰባ ወቅት መጀመሪያ መሪው ፈጽሞ መናገር የለበትም፤ ምክንያቱም እርሱ ከተናገረ በኋላ መቃረን ከባድ ነው። ያ ብቻ ሳይሆን መሪው ተናጋሪ ሰዎች መጀመሪያ እንዲናገሩም መፍቀድ የለበትም። ዝምተኞች፣ ሰዎች ባሉበት መናገር የሚፈሩ ሰዎችን መጀመሪያ ሀሳባቸውን መጠየቅ አለበት። እውነትን ለማወቅ እና ለድርጅቱ ታላቅነት የሚተጋ መሪ ከሆነ። እነዚህ ዝምተኞች ብዙ ጊዜ ተመልካቾች ናቸው። ስለዚህ ሲጠየቁ እውነትን የመፈንጠቅ አቅም አላቸው። ግን ተናጋሪዎች ወይም መሪው አስቀድሞ ከተናገረ ግን “እርሱ እና እርሷ እንዳለችው” እያለ ነው ሁሉም ነገር የሚቀጥለው።


በዓለማችን ብዙ አይሮፕላን የተከሰከሰበት ኤርላይንስ የደቡብ ኮርያው ነበር። ለዚህም ዋነኛው ምክንያት በባህላቸው አለቃን ወይም ከፍ ያለን ሰው መቃረን በጣም አስቸጋሪ ስለሆነ ነበር። ስለዚህ ጥፋት እንደሆነ እያወቀ እንኳን ኮ-ፓይለቱ (co-pilot) የፓይለቱን ስህተት ዝም ብሎ ያልፋል። አሜሪካን ማናጀሮች መጥተው የደቡብ ኮሪያን ኤርላይንስ ባህል እስከሚቀይሩት ድረስ ይሄ ትልቅ ፈተና ሆኖ ነበር።



3) በሙያ እና በእውቀት ከሚበልጠን ሰው አጠገብ መሆን (ወይም ራሳችን በሙያ ፍጹም ከፍ ስንል)፤



አዲስ ተቀጣሪው የኤክስፐርቱን ግልጽ ስህተት እያየ ዝም ይላል። ምክንያቱም እርሱ ከእኔ የተሻለ ያውቃል ብሎ ያስባል። ዶክተሩ ያውቃል ብሎ ስለሚያስብ ፥ ደደብ የሆነ ነገር በሰውነቱ ላይ ሲደረግ እያየ በሽተኛው ዝም ብሎ ያልፋል። በ2008 የነበረው የአሜሪካ የፋይናስ ውድቀትን ብዙ ሰዎች ያስተዋሉት ቢሆንም ኤክስፐርቶች ስለ ኢኮኖሚው ውብ ስዕል መሳላቸውን ስለቀጠሉ እየመጣ የነበረውን ውድቀት ችላ አሉት። በሃይማኖት ውስጥ ያሉ ሰዎች ፥ "እንደዚህ ያሉ የተመራመሩ እና አዋቂ ሰዎች ይሄ ሃይማኖት ልክ ነው ካሉ ፥ ልክ ነው" ብለው ሲቀበሉ አላያችሁም?


 እኛም በእውቀት እጅግ የሚያንሰን ሰው በጣም ተራ የሆነ ስህተታችንን ሲያሳየን ፥ መቀበል ይከብደናል። ለምን?


ምክንያቱም እውቀታችን አደድቦናል።



4) እጅግ ትኩረት የሚፈልግ ነገር ስንሰራ፤



ቼዝ የምትጫወቱ ሰዎች ታውቃላችሁ፤ በራሳችሁ ስትራቴጂ ላይ በጣም ትልቅ ትኩረት ከጣላችሁ ከየት መጣ የተባለ የተቀናቃኝ ጦር ቼክ ሜት ይለናል። በራሳችን ምርጥ ስትራቴጂ ስለተወሰድን የተቀናቃኛችንን ወደ እኛ መጠጋት ፈጽሞ ማየት ይሳነናል። ይሄ ማለት መነጽሩን አድርገን መነጽሩን መፈለግ ማለት ነው። ልክ አናጺዎች እርሳሱን ጆሮአቸው ላይ አድርገው እርሳሱን እንደሚፈልጉ። ወይም ስልኩን እያናገሩበት ስልኩን ራሱ የት አስቀመጥኩት ብለው እንደሚፈልጉ ሰዎች ማለት ነው። በሕይወት እጅግ ብዙ ደደብ ሥራ የምንሰራው ፥ የራሳችንን ብቻ ነገር ስናይ ነው። ይሄ ዓለም ሌሎችም የሚኖሩበት ነው። የሌሎች ተግባር ለኛ ሕልውና ልክ እንደኛው ተግባር የመጥፊያ ምክንያት ሊሆን ይችላል። የአንተ መስመር እና የትራፊክ ሕግ አክብረህ መሄድ በራሱ ከመጥፎ የትራፊክ አደጋ አይጠብቅህም። ለዚህም ነው የሌሎችን አነዳድ እንድናይ መስታወቶች የተገጠሙሉን። እኛ በጣም ጠንቃቃ ብንሆን ሌላው ጠንቃቃ ካልሆነ ሞታችን ቅርብ ሊሆን ይችላል። በዚህ ዓለም የሌሎችንም ተግባሮች ለሕግ እና ለሥርዓት ለማስገዛት መስራት ተገቢ ነው።



ቀላል የማይባሉ ሰርጅኖች ኦፕራሲዮኑ ላይ ብቻ ትኩረት ሲያደርጉ መቀስ ሆድ ውስጥ ጥለው ይወጣሉ። ለዚህ ነው ክፍል ውስጥ የገባውን እቃ እያንዳንዷን ከኦፕራሲዮኑ በፊት ቆጥረው ልክ ያንን ሰርጀሪ ሲጨርሱ መልሰው የሚቆጥሩት። መርሳት የሰው ልጅ ባህሪ ነው። ስለዚህ በራሳቸው የማስታወስ ብቃት አይደገፉም።



5) የመረጃ መብዛት፤



ብዙ መሪዎች መጥፎ ውሳኔ የሚወስኑት ከመረጃ እጥረት ሳይሆን ከመረጃ ብዛት ነው። ስለ ጦርነት እየወሰነ ያለ መሪ ስለኢኮኖሚው፣ ስለትምህርት ጥራት፣ ስለጤናው ዘርፍ በተመሳሳይ ሰዓት ሪፖርት እንዲቀርብለት ከፈቀደ ፥ መጥፎ ውሳኔ የመወሰኑ ነገር ርግጥ ነው። ወላጆች ከሥራ መጥተው ልጆችን የሚገርፉት ወይም ያለሆነ ውሳኔ የሚወስኑት አዕምሮአቸው በመረጃ ቀኑን ሙሉ ደክሞ አሁንም ሌላ መረጃ ሲመጣለት የውሳኔ ባላንሱን ስለሚያጣ ነው። ኢንቬስተርስ በግልጽ የሚታየውን የኢኮኖሚውን ውድቀት የሚስቱት ብዙ መረጃዎችን ስለ ኢኮኖሚው ስለሚሰሙ ነው። ስቶክ ትሬደሮች ቀዩን መስመር ሳያዩት ይቀራሉ ፥ ምክንያቱም እጅግ ብዙ መረጃዎችን በየቀኑ እንደጎርፍ ይቀበላሉ።



ታላቁ ኢንቬስተር ዋረን ባፌት ይሄን ስላወቀ ነበር ከስቶክ ትሬድ ማዕከል ከሆነችው ኒው ዮርክ ጭር ወዳለችው ኦማሃ ከተማ የሄደው። ምክንያቱም የመረጃ ብዛት አይደለም የጥሩ ውሳኔ ምንጭ። ጥቂት ግን ጥራት ያላቸውን መቀበል ነው የጥሩ ውሳኔ አንዱ ምሰሶ።


6) ድካም፤ ሕመም እና የስሜት ውጥረት፤



ከደከመኝ የደንበኞቼን ስልክ አላነሳም። ካነሳውም በጣም ስለደከመኝ ካስቀይመኳቹ የድካሜ ውጤት ነው ብዬ ማስጠንቀቂያ እሰጣለሁ። የደከመው ዶክተር በጣም ግልጽ የሆነውን መረጃ አሳስቶ አንብቦ ለበሽተኛው ያልሆነ መድኋኒት ሊያዝ ይችላል። ዳንኤል ኮነመን እና ካስ ሰንስቲን በጻፉት ኖይዝ በተባለው መጽሐፍ አሜሪካ ውስጥ ያሉ ዳኞች የከተማቸው የእግር ኳስ ወይም የባስኬት ቦል ቲም ተሸንፎ በማግስቱ ለፍርድ ፊት ለፊቱ ከቀረባችሁ ፥ መጥፎ ውሳኔ የመወሰኑ ዕድል በእጥፍ ይጨምራል። የጨወታው የሽንፈት ንዴቱ የፍትሐዊ ሚዛን አቅሉን ያስተዋል። ወላጆቻችን በማያስገርፍ ጥፋት ደብድበውን ያውቃሉ፤ በሌላ ነገር ተናደው ወይም ደክሟቸው ካገኙን።



ሲ ኤስ ሉዊስ የሰይጣን የመጀመሪያው ሥራ እንስሳነትህን ማስረሳት ነው ይላል። እስቲ እንስሳ ሲበላ ምግቡን ቀማው። እንደሚነክስህ እርግጠኛ ነህ። አንተ ጌታው ብትሆን እንኳን። ሰውም እንደ እንስሳ ነው። ሲደክመው ወይም ሲታመም ወይም ሲበሳጭ ከሚገባው እና ከሆነው በላይ ይጮሃል።



7) መሮጥ እና መፍጠን፤



ይሄን አባባል ብዙዎቻችሁ ታውቁታላችሁ። ፈጥኖ ለመድረስ ቀስ ብሎ መንዳት። በፍጥነት የጫማችሁን ማሰሪያ ስታስሩ የበለጠ ትፈቱታላችሁ። 600 ሰው የሞተበት የ1977 የTenerife Airport Disaster በታሪክ ትልቁ የአውሮፕላን አደጋ የደረሰበት እና ሁለት ፓይለቶች አይሮፕላናቸውን ፈጥነው ወደ መውረጃ ማዕከሉ ጣቢያ ለማስጠጋት ሲሞክሩ የደረሰ ነበር። ይሄ የቼክ ሊስት (checklist) አለመከተል ችግር አልነበረም። ቼክ ሊስትን ብቻ የመከተል ችግር እንጂ። አንዱ የአንዱን ፍጥነት ለመመልከት ሳይሆን ፥ ቼክ ሊስታቸውን ለሟሟላት ነበር የፈጠኑት። መፍጠን እና መቸኮል የደደብ ውሳኔዎች እና ውጤቶች ሥር ነው።



8. ፍቅር እና ጥላቻ፤


ፍቅርም ጥላቻም ያሳውራል። ሁላችንም ከዚህ ከሚያሳውር ስሜት ነጻ አይደለንም። በአንድ ነገር ላይ ፍጹም ስናምን ከኛ የሚቃረኑ ሰዎችን ለመስማት እንጨክን። ለመማር በማሰብ። ዓለሙ ሁሉ እንደሞተ ያመነውን ጦር ሜዳ የሄደውን ልጇን ፥ ጦርነቱ ከተጠናቀቀ ከዓመታት በኋላ እንኳን እናት ልጇ እንደሚመጣ ትጠብቃለች። የልጅ ፍቅር እውነትን የመቀበል አቅሟን አሳጥቷታል። ልጅሽ እየተበላሸ ነው ሲሏት የእናት የመጀመሪያ ምላሽ መካድ ነው። ምክንያቱም ፍቅሯ መስማት የሚፈልገው በጎ በጎውን ብቻ ነው። የምትጠሉትም ነገር ተመሳሳይ ነው። ሂትለር ለልጆች ልዩ ፍቅር እንዳለው ፈጽሞ ማመን አንፈልግም።ስለእሱ የሚታየን ያን ሁሉ አይሁድ እና ሌላውን ማህበረሰብ በግፍ መጨረሱን ነው። ግን የሂትለርን የልጆች ፍቅር ውሸት አያደርገውም።


ሴትን ያፈቀረ ወንድ እንከኗን መስማት አይፈልግም። ዘወትር ምክንያት ይሰጣል (justify ማድረግ)። ከሁሉም በላይ የምንወደው ደግሞ ራሳችንን ነው። ራሳችንን ዘወትር መከላከል (defend ማድረግ) ነው የምንፈልገው። ሰዎች አንዴ ቢሰርቁን የእነሱ ነገር በቃን ለማለት ፍጥነታችን። እራሳችንን ግን ሺ ዕድል ለመስጠት፣ መልሰን እና መላልሰን ለማመን ዝግጁ ነን። ለዚህ ነው ሰዎች አሉታዊ አስተያየት ስለ እኛ ሲሰጡን ይሄ የደደብነት ምንጭ የሆነውን የፍቅር መታወር ለጊዜው ያዝ ማድረግ ያለብን።



አሉታዊ (negative) አስተያየት ለመስማት እንፍቀድ። ቢያንስ ሰዎች ተናግረው እስከሚጨርሱ እንታገስ። ከዛ ደግሞ ይሄን አስተያየት ስለሰጣችሁን እናመሰግናለን እንበላቸው (ልክ ቢሆኑም ባይሆኑም)። ያን የመቀበል እና ያለመቀበል ፈንታ የራሳችን የቤት ሥራ ነው።


 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Apr 6
  • 3 min read


ብሩስ ሊ “በሕይወቴ ረዥም ጊዜ ለመማር የወሰደብኝ ግን ደግሞ ለማሸነፌ መሰረታዊ የሆነው ነገር ርጋታን መጎናጸፍነበር” ብሏል። በዚህ ዘመን ከምንም ነገር በላይ እያጣን ያለነው ነገር ርጋታ ይመስለኛል። ሁሉንም ነገር እኛ ባልነው ሰዓት እና ጊዜ ብቻ ማከናወን መፈለግ። ዛሬ ወይም በጣም አጭር በተባለ ጊዜ ውስጥ ሀብታም መሆን። ወይም አዋቂ መሆን።ወይም ታዋቂ። ይሄን ለመከወን ደግሞ ሁሉንም አቋራጭ መንገዶች ለመጠቀም መፈለግ። በዚህ ፍላጎታችን መስመር ውስጥ እንከን ከገጠመን ሰማይ ምድሩ ነው የሚገለባበጥብን።

 

መስከን የሚባል ነገር ርቆናል። ችግር የመቋቋም እና የመቻል አቅማችን ተሟጧል። ኃይሌ ገብረሥላሴ አንዴ እንዲህ ብሎ ነበር። “ታዋቂ መሆን አልነበረም በጣም ከባዱ ነገር ፥ ታዋቂነትን ያጎናጸፈኽን መልካም ስም ይዞ መቆየት እንጂ።” ጅል ውሳኔዎች የፍጥነት ውጤቶች ናቸው። ቶማስ ጀፈርሰን እንዲህ ይላል “ከተናደድክ እስከ አስር ቁጠር። በጣም ከተናደድክ ግን እስከ መቶ ቁጠር።” ይሄ ታላላቅ ተግባራትን የሰሩ ሰዎች ንግግር የሚነግረን የሰው ልጅ አዕምሮ ሁልጊዜ የምንመካበት እንዳልሆነ ነው። በፍጥነት ወቅት ባላንሱን ይስታል።

 

የሆነ ሰው ሲያናደኝ ራሴን የምጠይቀው “በዚህ ምድር ላይ ይሄ ሰው የተናገረውን ንግግር ሰምተው ምንም የማይመስላቸው ሰዎች የሉም? ልክ እኔን የተናገረኝን ቢናገራቸው ፥ ምንም እንዳልተፈጠረ የሚያልፉ የሉም? መልሴ ሁልጊዜ ማለት በሚቻል መጠን “አለ!” ነው። ስለዚህ ይሄ ነገር ግለሰባዊ (subjective) ነው ማለት ነው። የእኔ የዕይታ አድማስ መጥበብ እና የቆዳዬ ስሱነት እንጂ የሰውዬው ንግግር አይደለም ማለት ነው። ያ subjective የሆነ ግብረ መልሴ ዓለምን ከሌላ ሰው አንግል እንዳየው ያግዘኛል። ይሄ ማለት ቀላል ነው ማለት አይደለም። ፈጽሞ። ያልተገራ ውሻ ዘወትር ውስጣችን አለ።ውሻ እየበላ ያለውን ብታነሳበት ይነክስሃል። ምግቡን የሰጠኸው እና ነገም የምትሰጠው አንተ ብትሆን እንኳ።በተመሳሳይ ክብራችን፣ እንጀራችን፣ ኢጎአችን፣ ድንበራችን ፥ ተነካ ስንል ፥ እንናከሳለን። ለውሻው ራስን መግዛት እና ስለነገ ማሰብ ከባድ እንደሆነው ሁሉ ፥ እኛም ያን ማሰብ በጣም ይከብደናል።

 

ይሄ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ያልቆመ ነገር አለ። ሰውን በንዴት እና በቅናት ተነሳስቶ ማጥቃት። ምንም እንኳ ይሄን የሚያደርጉ ሰዎች መጨረሻቸው ጸጸት እንደሆነ እያወቅን እንኳን ዛሬም ያን የሚያደርጉ ሰዎች እልፍ ናቸው።

 

የሒሳብ ሊቁ ብሌዝ ፓስካል “የሰው ልጅ ችግር ሁሉ የሚመነጨው ፥ ሰው ብቻውን በርጋታ አንድ ክፍል ውስጥ ለመቀመጥ ባለመፍቀዱ ነው” ይላል። ሊቁ ጸጋዬ ገብረመድኅን ይሄን ግብዣ ነው ለሁላችንም ያቀረበልን። “አብረን ዝምእንበል” በሚለው ግጥሙ። “አጉል ነው ብለን ሳንፈርድ ድንቅም ነው ብለን ሳናደንቅ አስቲ ለአንድ አፍታ ዝም እንበል” ፥ መገዳደል እና መፍክር ማብዛት ለተጣባው ፖለቲካችን ምክር ሰጠን።

 

ዳንኤል ኮነመን “ብዙ ሰው የሚወደው ስፖርት ፥ ውሳኔ ላይ በፍጥነት መዝለል ነው (jumping to conclusion)” ይላል። ምንአልባት ያን አለማድረግ አንችል ይሆናል። ለሆነ ሰው ስልክ ደውለን ሳያነሳልን ሲቀር ፥ ንቆኝ ነው ማለት ይሆናል መጀመሪያ የሚቀለን። ምን አልባት የሆነ ነገር ፈልገን ስናጣ ፥ እከሌ ሰርቆን ነው ማለት ይሆናል የመጀመሪያው ውሳኔያችን። መጥፎ መጥፎውን ይሆናል መጀመሪያ አዕምሮአችን የሚያሳስበን። እንዲህ አስቤ ከዛ ውጤቱ ሌላ ሲሆን ፥ ራሴን “አየ አይደል!ትቸኩላለህ። ይሄ የመጀመሪያህ አይደለም። ብዙ ጊዜ እንዲህ ብለህ ከጠበከው ውጪ ሆኗል። ስለዚህ ተጠንቀቅ እለዋለሁ።” ከራሳችን ጋር መወቃቀስ እና ራሳችንን ሰው ሳይታዘበን በፊት እንታዘበው። ትላንት ተሳስተሃል። አሁንስ ልትሳሳት ብትችልስ? ስለዚህ ታገሰ። ተረጋጋ እንበለው።

 

ብሩስ ሊ እንዳለው ርጋታን መላበስ ፥ የትኛውንም ውጊያ የማሸነፊያ ጥበብ ነው። በሀገራችን መሪዎች ውስጥ እጅግብዙ ያሳኩ መሪዎቻችን አብዛኛው ጊዜ የሚታወቁት በታጋሽነታቸው ነው። በአጭር ሕይወታቸው የተቀጩ እንደ ቴዎድሮስ፣ ዮሐንስ፣ ኢያሱ እና መንግስቱ ኃይለማርያም ያሉት ደግሞ ቁጡዎች እና ፈጥነው ውሳኔ መስጠት የሚወዱ ነበሩ። እነዚህ ረጅም አልመው በአጭር የተቀጩ  መሪዎች ናቸው። በዘመናቸው ለሕዝባቸው ጦርነትን አብዝተው የሰጡ ነበሩ።

 

ታሪክ የሚነግረን መረጋጋት እና መታገስ የስኬት ጨው መሆኑን ነው። መረጋጋት ማለት ግን ውሳኔ ለመወሰን የሚቸገርን ሰው አይወክልም። የተረጋጋ ሰው መወሰን ተቸግሮ አይደለም። ይልቁንስ ውሳኔው ነው ያረጋጋው። በአዕምሮ ውስጥ ቀጣይ የሚወስዳቸው ርምጃዎች ሁሉ ግልጽ ስለሆኑለት ወይም በርጋታ ውስጥ ያልተገለጡ እና በቅርብ ሊያውቃቸው የሚገቡ መረጃዎችን እየጠበቀ ስለሆነ ነው የተረጋጋው። ንድፈ ሀሳቡን በርጋታ ውስጥ በተግባር እየፈተሸው ነው። ርጋታ ማለት ጉዞ አልባነት አይደለም። ይልቁንስ ርጋታ ማለት የድብቅ እና የስውር ሩጫ ማለት ነው። ርጋታ ማለት ንፋሱን ቁጡ እና ቀበጥባጣው ሰው እንዲሰብረው ግን አንተ ከኋላ ሆነ የደውሉን ፍጻሜ የምትጠባበቅበት ስፍራ ማለት ነው። ርጋታ ማለት ነብር በሆዱ እየቧጠጠ ወደ ሚያድነው ታርጌት ከእይታ ተሰውሮ የሚቀርበብት ሁኔታ ማለት ነው።


ርጋታ ማለት እዩኝ የሌለበት ፈጣን እድገት ማለት ነው።

 
 
 



ዋረን በፌት “ዓለምን የሚያስተዳድረው ስስት ሳይሆን ቅናት ነው” ይላል። መጽሐፍ ቅዱስ ውድቀት በሰው ላይ የተሰነዘረው በሰው ክብር በቀናው ሰይጣን እንደሆነ ይነግረናል። ከዛም የመጀመሪ ወንድማማቾች የተገዳደሉት በቅናት እንደሆነ ተጽፏል። ሕይወት በሜጋ ፎን ለዘላለም የምትናገረው አንድ ሀቅ አላት። “ሁላችንም መቼም እኩል እንደማኖን።” አንዷ እጅግ ውብ ናት ሌላኛ መልክ የሌላት። አንዱ ሞገሱ እና ውበቱ የሚያስደነግጥ ሌላኛው ደግሞ የቀነጨረ የሆነባት ዓለም ናት። አንዱ ሀብትን፣ ዝናን፣ የሕይወትን ስኬት እና ስልጣንን ሁሉ በእጁ ይል ፥ ሌላኛው ደግሞ በእጁ ምንም የለም።



ጥቂት ልዩነቶች ፍትሕ በማጣት የመጡ ቢሆንም ብዙዎቹ ግን ፍጹም ዕድል እና የዕድል ጉዳይ ብቻ ናቸው። አንዳንዶቻችን በጣም ጤናማ ሆነን ስንወለድ ሌሎቻችን ደግሞ የዘር ሕመም አለብን። አንዳንዱ ዜግነቱ በአምስት ሚሊዮን ዶላር የሚሸጥ ሀገር ላይ ይወለዳል። ሌላኛው ደግሞ ሀገር አልባ ሆኖ ይፈጠራል።



ቅናት የእነዚህ ልዩነቶች የተሳሳተ መድኃኒት ነው። የሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ ዘወትር የማታጡት አንድ ነገር ቢኖር ቅናት ነው። የቅናትን ጥንታዊነት ማየት አስደናቂ ነው። የትኛውም ጥናትዊ ሃይማኖት ውስጥ ቅናት የመጀመሪያው ምዕራፍ ላይ ነው ያለው። በጥንታዊ የግብጽ ታሪክ ውስጥ ኦስሪስ እህቱን አግብቶ ስልጣኔን ወደ ግብጽ ያመጣል። ያገባት እህቱ በጣም ቆንጆ እና ብልህ ነበረች። በተቃራኒው ኦስሪስ አስቀያሚ እና የሚጠላው ሴዝ የተባለ ወንድም ነበረው። ሴዝ በኦስሪስ ውበት፣ ስኬት እና ብቃት እጅጉን ይቀና ነበር። የሴዝ ሚስት ኦስሪስን በድብቅ ስለወደደችው ፥ አታላው አብራው እንዲተኛ ታደርገዋለች። በዚህ ወቅት ከኦስሪስ አረገዘች። በቅናት የበገነው ሴዝ ኦስሪስን በመጨረሻ ይገለዋል።



ቅናት ከሰው ልጅ እኩል ጥንታዊ ነው።



እርግጥ ነው ሰዎች በቅናት ተነሳስተው ራሳቸውን ሊያስተምሩ፣ ሊያሳድጉ እና ሊያሻሽሉ ይችላሉ። ግን ቅናት ከቁጥጥር ከወጣ ፥ የሌሎች ስኬት የኛ ሞት ይሆናል። ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ እንደሚለው ጥንብ አንሳን የሚገለው ሽቱ ነው። ቅናተኛ ሰውም የሚመተው በወንድሙ መልካምነት ነው። የሌሎች ከፍ ማለት እኛን ለተሻለ ለውጥ ካነሳሳን መልካም ነው። የሌሎች መሻሻል ግን እኛን እንቅልፍ ነስቶን የእነሱን መውደቅ ካስመኘን ፥ ሽቱ የሚገለን ጥንብ አንሳ ሆነናል ማለት ነው። ቅናተኛ ሰው በወንድሙ ለቅሶ ላይ ለመገኘት ደስተኛ ነው። ሠረጉ ግን ያጠቁረዋል። ክስረቱ ልቡን ቅቤ ያስጠጣዋል። ስኬቱ ግን ያደማዋል። እርሱ ከሚያገኝ ይልቅ ወንድሙ ቢያጣ የበለጠ ደስ ይለዋል።



ቅናት ፍጹም አስቂ ባህሪ ነው። በሚበልጠን አይደለም የምንቀናው። በምናውቀው እና በሚበልጠን ነው የምንቀናው። የአንድ ሚሊዮን ዶላር ያለው ሰው የሚቀናው በኢለን መስክ ሳይሆን ከሱ ተሻግሮ ባለው ባለ አንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ዶላር ግለሰብ ነው። የሰፈር ሁለተኛ ቆንጆዋ የምትቀናው ከሀገሩ ውብ በሆነችው ሳይሆን ከሰፈራቸው አንደኛ በሆነች ነው። ቅናት የፉክክር አድማሱ ጠባብ ነው። ማጥቃት በሚችለው ብቻ ነው ቀናተኛ ሰው የሚታመመው።



ሳይኮሎጂስት ቅናት ሰዎች ሕይወታቸውን ሲያዩ ጉድለት ስለሚሰማቸው ፥ ስሜታቸው የሚያፈልቀው አሉታዊ (negative) ጥበቃ ነው ይላሉ። ለምሳሌ በጓደኛው የሚቀና ግለሰብ የሚቀናው የራሱን ሕይወት ተመልክቶ ለማሻሻል የሚጠይቀውን ልፋት ወይም አስተሳሰቡን ለመቀየር የሚያስፈልገውን የመረዳት ደረጃ ከመድረስ ይልቅ ፥ ብዙ ድካም የሌለበትን የቅናት አጭር መንገድ ይመርጣል። ቃየንን ተመልከቱቱ። እግዚአብሔር ስጦታህን አልቀበልህም ሲለው ፥ ሌላ አምላኩን የሚያስደስት ስጦታ ለማቅረብ ከመልፋት ይልቅ ፥ በአቤል ቀና። አጭሩን መንገድ መረጠ። ምክንያቱም ስህተት ሰርቻለው ብሎ ማመን ለሰው ከባድ ነገር ነው። ወይም በውበት ሌላኛው ወንድሜ ይበልጠኛል ብሎ ማመን። ያ ደግሞ ተፈጥሮአዊ ነው። ያን መቀበል አለብኝ ከማለት ይልቅ ፥ የዛን መልከ መልካም ሰው ማንነት ማጉደፍ ቀላሉ መንገድ ነው። ቅናት ስሜታችን ስንፍናችንን የሚጠብቅበት ቀላሉ መንገድ ነው።



የሕይወትን ሀቅ ከመቀበል ይልቅ ፥ ቅናት ከዛ የእውነት ማዕበል በተቃራኒው እንድንቀዝፍ ያደርገናል። በሌሎች ደስታ ደስ የማይለን ከሆነ ፥ በፍጥነት ራሳችንን እንፈትሽ። የቅርብ ሰዎቻችን ውድቀት የሚያረካን ከሆነ ፥ ጊዜያችንን እየገደልን ነው።



ብዙ ክፋቶች የራሳቸው የሆነ ጥቅም አላቸው። ለምሳሌ የሚሰክር ሰው በመጠኑም ቢሆን በስካር ውስጥ ደስታ ያገኛል። ስርቆት ለጊዜውም ቢሆን ከሰረቅነው ነገር ተጠቃሚ ያደርገናል። ቅናት ነው ሌላውን ለመጉዳት ለመጎዳት የሚፈቅድ። ቅናት ነው ራሱ እየተጎዳ ሌላው እስከተጎዳ ድረስ ደስታ የሚሰማው። ፍጹም ደደብ የሆነ ክፋት ቅናት ብቻ ነው። የሚቀናውን ሰው ምንም አይጠቅመውም። ሌላውን ለማከርፋት እርሱ ቢከረፋ ግን ግድ የለውም።



ቅናትን የማሸነፊያው ዋነኛው መድኃኒት የምንቀናበትን ሰው ሄደን እንደምንቀናበት መንገር ነው። ከቅናት ስትፈወሱ ታዩታላችሁ። ባብዛኛው ያ ሰው በእናንተ እንደሚቀና ሁሉ ሊነግራችሁ ይችላል። ከዛ ግን ስለራሱ ጉድለት እና እንደምናስበው የሚያስቀና ነገር ያለው ብቻ ሳይሆን ጉድለት እንዳለው ይነግራችዋል። ቀጥሎ እንደ ዛ ግልጽ በመሆናችሁ የዛን ሰው ክብር እና ፍቅርም ታተርፋላችሁ። በመጨረሻ ያ ቅናት ከእናንተ ቀስ እያለ ሲተን ታዩታላችሁ።



ችግሩ ብዙዎቻችን በዚህ ባህሪያችን በእጅጉ ስለምናፍር ያን አናደርግም። ትዕቢታችን ደግሞ መዋረድ አድርጎ ስለሚቆጥረው ያን እንድናደርግ አይፈቅድልንም።


ከዛ መልስም ግን መፍትሔ አለ። በሕይወታችን መለወጥ የማንችላቸውን ነገሮች ለመቀበል መስራት። መለወጥ የምንችላቸው ጉዳዮች ላይ ደግሞ በትዕግስት ለመለወጥ መትጋት። ትዕግስት እና ትጋት በመጨረሻ መለወጥ የምንችላቸውን ነገሮች ቀይሮ ያሳየናል።



በሽቱ ለማጌጥ እንጂ ለመሞት አንዳረግ። በሌሎች ስኬት እና ደስታ ለመደሰት እንጣር።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page