top of page
Search
ree

፩) የኢዮብ ወዳጆች ለመከራ እና ለክፋት መልስ አለን ብለው መቅረባቸው፤

እውነት ለመናገር ብዙዎቻችን ብዙ ነገር አናውቅም። ግን አላውቅም ማለት በጣም ከባድ ነው። መክበዱ ብቻ አይደለም መልስ ሳይኖረን ተረጋግተን መኖር እና መቀጠል ይሳነናል። በተለይ ዓይናችን ሥር ትልቅ ክስተት ስናይ የዛን መንስኤ መተንተን ያስጎመጀናል። በተማሩ ሰዎች መካከል ደግሞ አላውቅም ማለት ነውር ይሆናል። አለማወቅ ተማርን ማለታቸውን ያሳንስባቸዋል። ማህበረሰባዊ ጫናውም ከፍተኛ ነው። አንድ አክስቴ ብዙ ጊዜ ስትጠይቀኝ አላውቅም፣ አላውቅም ስላት “እንዴ የተማርክ አይደለህም እንዴ?” አለችኝ። የዚህ ዓይነት ጫና ስለማናውቀው ነገር ሳይቀር ትንታኔ እንድንሰጥ ይጋብዘናል። ዝም ማለት በትልልቅ ክስተቶች ፊት እጅግ ከባድ ነው። የኢዮብ አዋቂ ወዳጆቹ የተሳናቸው ያ ነበር። በእግዚአብሔር ጉባኤ ተወስኖ በጻዲቁ ኢዮብ ላይ የተከናወነው ነገር ለማናቸውም የሰው ልጆች የተገለጠ አልነበረም። ግን የኢዮብ ወዳጆች ዝም ከማለት ይልቅ ለኢዮብ መከራ ምክንያት ፈለጉለት። ኃጢአተኛ ስለሆንክ ነውና ንስሃ ግባ አሉት። ቢያንስ በሀሳብህ በድለሃል አሉት። ውጤትን ዓይተው መንስኤውን ተነተኑ።



 የደራሲ ዓለማየው ገላጋይን አንድ የተቆረጠ ቪዲዮ ተመለከትኩኝ። ያለንበት ድህነት እና መከራ እረፍት የነሳው ይመስላል። ይሄ አዋቂ ደራሲ ከዛ እንዲህ አለ “እግዚአብሔር ጣልቃ አይገባም በሕይወታችን።” የየቀን ሠሪውን እግዚአብሔርን “ሁሉን ነገር ሠርቶ ጨርሶ ቀድመው ለነቁ ሰዎች አስረክቦናል” አለን። “ለዚህም ነው ከዚህ በፊት የጠፉ ሰዎች ሲያይ ጣልቃ ያልገባው፣ በእኛም ሕይወት ጣልቃ አይገባም፣ ራስህ ሠርተ ለፍተህ ልበስ፣ ብላ፣ ተጋደል። እርሱ ጣልቃ አይገባም፣ ለዚህም ነው የሰለጠኑት፣ ቀድመው የነቁት ሁልጊዜ የሚገዙን” አለ። ይሄ መከራ ላይ፣ ድህነት ላይ፣ ችግር ላይ ቆሞ ስለመንስኤው የማውራት ዝንባሌ እና አባዜ ነው። ጥራት ባለው አስተሳሰብ ዙሪያ ብዙ የተማሩ ሰዎች የሚሰሩት ትልቁ የማሰብ ስህተት ነው፣ መንስኤን ከውጤት ለማግኘት መጣር። ይሄ ጥራት ላለው አስተሳሰብ ጋንግሪን ነው። ከእግዚአብሔር ጋር ስናያይዘው ደግሞ ቁጣው እንደእሳት የሚነድበት የአስተሳሰብ ዝንባሌ ነው። ስለኢዮብ ባይሆን ኖሮ ቁጣዬ እንደ እሣት በልቷቹ ነበር ነው ያለው።



በየቀኑ ይሄን የአስተሳሰብ ስህተት እንሰራለን። የታመመ ሰው እናያለን ፥ እግዚአብሔር ቀጣው እንላለን። ሀብታም እናያለን ፥ እግዚአብሔር ባረከው እንላለን። ድሀ እናያለን ፥ ሰነፍ ነው፣ እግዚአብሔር አልባረከውም እንላለን። ውጤት ላይ ቆሞ መንስኤን የማግኘት አባዜ። እስቲ በሕይወታችሁ አንድን ነገር ስንት ሁኔታዎች ሊያመጡት እንደሚችሉ ጠይቁ እና ያን ለእናንተ የተገለጠውን ብቻ ፈትሹ። በእናንተ ሕይወት እንደዛ ከሆነ፣ እጅግ ውስብስብ በሆነው በዚህ ዓለም አነዋወር ውስጥ የአንድ ነገር መንስኤ ከኛ የማሰብ አቅም ቢያንስ ያለጥልቅ ጥናት የረቀቀ ሊሆን ይችላል ብላችሁ አትገምቱም?


ደራሲ ዓለማየው መንስኤውን ለማወቅ በመቸኮሉ፣ ውጤቱንም በአግባቡ የተረዳው አይመስልም። ለምሳሌ በእውነት ይሄ ዓለም ኃያል የሆነው የሰው ልጅ (በዘመናዊ ቴክኖሎጂ) ደካማ የሆነውን ፍጹም የሚገዛበት ነው ወይስ ብዙ ዓይነት ኃይሎች በሰዎች የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ ላይ እና የነገ ሕይወታችን ላይ ያልተጠበቁ እና ተገማች ያልሆኑ አሻራቸውን እና ተጽዕኖዎችን የሚያሳርፉበት ዓለም ነው? በዚህ ዓለም ሰዎች የፈጠሯቸው ግዙፍ ቴክኖሎጂዎች ፥ በጣም ደካማ በሆኑ ፍጥረታት ወይም ክስተቶች አቅጣጫቸውን ሲቀይሩ እና ሲዘወሩ አላየንምን? ለምሳሌ የኮቪድ ቫይረስ እንዴት የሰው ልጆችን ሁሉ ባህሪ እና አነዋወር በቅጽበት እንደለወጠ ተመልከቱ። ይሄ ክስተት የሚነግረን ይሄ ዓለም በኃያላን ፍላጎት እንደፈለጉት የሚዘወር ዓለም እንዳልሆነ አይደለምን? የታላቋን አሜሪካ የውጪ ጉዳይ እና የሀገር ውስጥ የደኅንነት ፖሊሲ ፍጹም የቀየረው ከደካማዋ ሀገር አፍጋኒስታን የመጣ ጥቃት አልነበረምን? በርግጥስ ይሄ ዓለም ኃያላን እንዳሰቡት የሚኖሩበት ዓለም ነውን?



መሥራትን፣ ለፍቶ ማደርን፣ መፍጠርን ለማበረታታት የግድ ጽንፍ መሄድ አያስፈልገንም። እነዚህ ነገሮች ጥሩ ናቸው። ግን ሌላም እውነት አለ። እነዚህ ብቻ በቂ አይደሉም። እነዚህ ብቻ መልስ አይደሉም። “ሥራ ነጻ ያወጣኻል፣ Arbeit macht frei” የሚለውን መፈክር እናውቀዋለን። ይሄ በፍሬድሪክ ኒቼ ተጠንስሶ ናዚዎች የወረሱት እና በናዚ ካምፖች ሁሉ የተሰቀለ መፈክር ነበር። ሥራ ብቻውን የጥላቻ እና የትዕቢት ባርነት ውስጥ ጀርመኖችን ጨምሮ፣ ውድቀታቸውን አስከተለ እንጂ ነጻ አላወጣቸውም።



ጠቢበኛው ሰሎሞን ስለመንስኤ ሲናገር ከኛ ውጪ ባሉ ኩነቶች ማለትም በጊዜ እና በዕድል የሚወሰኑ እንደሆነ ተናግሯል። እዚህ ላይ የደረሰው ከብዙ ማሰብ በኋላ እንደሆነ ሲያሳይ “እኔም ተመለስሁ” ብሎ ይጀምራል። “እኔም ተመለስሁ፥ ከፀሐይ በታችም ሩጫ ለፈጣኖች፥ ሰልፍም ለኃያላን፥ እንጀራም ለጠቢባን፥ ባለጠግነትም ለአስተዋዮች፥ ሞገስም ለአዋቂዎች እንዳልሆነ አየሁ፤ ጊዜና እድል ግን ሁሉን ይገናኛቸዋል።” መክ 9፥11።


፪) ሁለተኛው ነቀፋ ቲዎሎጂ እና አይዶሎጂ ነው። የኢዮብ ወዳጆች ጠንካራ ቲዎሎጂ ነበራቸው። ያም ክፋት ስለሚሸነፍበት መንገድ ነው። የእነሱ መንገድ ብቻ ኢዮብን ከቁስሉ እንደሚፈውሰው ደሰኮሩ። እየተፈራረቁ የቁስሉ መድኅን እነሱን መስማት መሆኑን ነገሩት። ይሄ በሃይማኖት ሰዎች መካከል በጣም ጠንካራ ዝንባሌ ነው። ለሁሉም ነገር መፍትሔ አለን። ለሁሉም ነገር ስንዱ ነን። የሚገርመው ግን ክፋትን እግዚአብሔር እንዴት እንደሚያሸንፍ ከኛ የተሰወረ ጥበብ መሆኑ ነው። ክፋትን በመስቀሉ እንደሚረታ ለማንም የተሰወረ ነበር በብሉይ ኪዳን። መስቀል ነበር \ የእግዚአብሔር ጥበብ ፥ ክፋትን የረታበት። የሰው ልጆችን ቁስል የፈወሰበት። ያ ግን በድንግዝግዝ ተመለከቱት እንጂ ለአንዳቸውም አበው አልተገለጠላቸውም ነበር። ቲዎሎጂ በፍጥነት አይዶሎጂ ይሆናል፤ ለሁሉም ነገር መልስ አለኝ ብሎ ሲያስብ። ክፋት እና መጥፎ ነገሮች ለምንላቸው ሁሉ መልስ አለኝ ብሎ ሲገምት። ዝምታ እና ለእግዚአብሔር ዕድል እና ጊዜ መስጠት ብዙዎቻችን በየቀኑ መማር ያለቡን ጸጋዎች ናቸው። “ምነው ዝም ብላችሁ ብትኖሩ፦ ይህ ጥበብ በሆነላችሁ ነበር።” ኢዮ 13፥5።


 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 4 min read
ree

በውጭ ጉዳይ በቢዝነስ ዲፕሎማሲ ዘርፍ ስሠራ፣ አንድ የጀርመን ኩባንያ ከሀገር ነቅሎ ሲወጣ ለመ/ቤታችን የጻፈው ደብዳቤ ሁልጊዜ ትዝ ይለኛል። “የኢትዮጵያ መንግስት እንደ ሁሉም ኋላ ቀር ሀገራት በሕግ ብዛት ችግሮችን መፍታት የሚቻል የሚመስለው ነው፤ ችግሮች ሲገጥሙ በውይይት እና መፍትሔ ለመፈለግ በሚሆን አዕምሮ ከመሥራት ይልቅ በሕግ ላይ ሕግን ማውጣት ባህሪው ስላደረገ እና በዚህ ሁኔታም ኩባንያችን በዚህ ሀገር ውስጥ ለመሥራት ስለሚቸገር ለቀን ወጥተናል” የሚል ጠንካራ ደብዳቤ ጽፈው ነበር የኩባንያው ኋላፊዎች ከሀገር የወጡት። አንድ የጀርመኖች አባባል አለ “The more laws, the less justice” የሚል።


 ይሄን ያነሳውበት ምክንያት ብዙ ጊዜ የተወሳሰቡ ነገሮች፣ መዋቅሮች፣ ብዛት ያላቸው ሥርዓቶች፣ ትንታኔዎች ይመስለናል ትክክለኛው መልስ ወይም ለችግሮቻችን መፍትሔ። ለዚህም በሁሉም የሕይወታችን ክፍል ውስጥ ማቅለልን ሳይሆን ማክበደን እና ማስጨነቅን፣ ማወሳሰብን የጥራት፣የአዋቂነት መለኪያ አድርገን እንወስደዋለን።


የ14ኛው ክፍለዘመን ቲዎሎጂያን እና የሎጂክ ሰው ዊሊያም ኦክሃም የፈጠረው እና ኦካም ራዛር ተብሎ የተሰየመ የችግሮች መፍቻ ሂደት አለ። ሁልጊዜ ቀላሉ መፍትሔ በጣም ውስብስብ ሆኖ ከቀረበው በላይ ምርጡ መፍትሔ ነው ይላል። (The simplest solution is almost always the best. ... simplicity is better than complexity)።


ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእስራኤል መኃል የተጠየቀውም ይሄን ነበር። በፈሪሳውያን እና ሰዱቃውያን የሕግ እና የሥርዓት ቀንበሮች እና ውስብስብ የአምልኮ ማስመሰሎች መኃል ጌታችን በአንድ የሕግ አዋቂ “ከሕግ ማናቸይቱ ትእዛዝ ታላቅ ናት?” ተብሎ ተጠየቀ። (ማቴ 22፥36)። ከ613 ሕግጋት መካከል የትኛውን እንደሚያስበልጥ ሲጠይቀው ጌታችን እንዴት ባለ መልኩ የሕግጋትን ሁሉ መስፈሪያ ለዚህ ሰው እንደነገረው ተመልከቱ።


613 ሕግጋት መኃል ሁለቱን ምሰሶዎች፣ በጫካው የተሸፈኑ ሁለቱ የሕይወት ዛፎችን አሳየው። “ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስም በፍጹም አሳብህም ውደድ።” እና “ባልጀራህን እንደራስህ ውደድ” የሚለውን።


እነዚህን ሁለቱን ሕግጋት ሳይፈጽም ቀሪዎቹን ሕግጋት ሁሉ ቢፈጽም፤ ለሰው ምንም አይጠቅመውም። እነዚህን ሁለቱን ሕግጋት ብቻ የሚፈጽም ደግሞ ሁሉንም ሕግጋት ይፈጽማል። ለዚህ ነው ቅዱስ አውግስጢኖስ “እግዚአብሔርን ውደዱት ከዛ ሁሉን ማድረግ ትችላላችሁ ያለው።” (Love God and you are allowed to do everything)። ምክንያቱም ፍቅር የተፈቃሪውን ደስታ ከራሱ በላይ የሚሻ እና ተፈቃራዊን ለማስደሰት የሚሰራ ስለሆነ ነው።


ሌላ ጊዜ ደግሞ እንዲሁ ሌላ የሕግ አዋቂ የጌታን እውቀት ሊፈትን መጣ። የሕግ አዋቂዎች ማወቃቸውን የሚያሳዩት የረቀቀ ነገር በመናገር፣ ግልጽ የሆነውን ነገር ሳይቀር በማወሳሰብ፣ ሰው ሁሉ በሚገባው ቋንቋ ሳይሆን ፥ ሁሉ የሚያውቀውን ቋንቋ የውጭ ሀገር ቋንቋ እስኪመስል ድረስ በማራቀቅ ነበርና፣ ታላቅ የሆነን ሰማያዊ እውቀት በቀለለ ቋንቋ፣ ሁሉም በሚረዳው መልኩ የሚያቀርበውን መምህር አልወደደውም። ለሕግ አዋቂዎች ብቻ ተወስኖ የነበረውን፣ ተራው ሕዝብም እንዳይገባው በሚመስል መልኩ የቀረበውን እውቀት፣ ይዘቱ ሳይጓደል ለተራው እስራኤላዊ የሚያስተምረው የዚህ መምህር ዘይቤ ለተኮፈሰው ማንነታቸው አደጋ ነበርና ፥ ይሄ የሕግ አዋቂ ጌታችንን “ባልጀራዬ ማነው?” ብሎ ጠየቀው።


በሉቃስ ወንጌል 10፥30 ላይ “ባልጀራ ማነው?” የሚለውን በደጉ ሳምራዊ ታሪክ ገለጠለት። ባልጀራ ማነው የሚለውን ለማስረዳት አዲስ ሕግ አላወጣም። ረቂቅ ትንታኔ አልሰጠም። በወንበዴዎች ተደብድቦ የወደቀውን አይሁዳዊ እና ሌሎች ሳይረዱት ያለፉትን፤ የእርዳታ እጁን የዘረጋለትን እውነተኛ ባልጀራ ደጉ ሳምራዊን በትረካ አሳየው እንጂ። (በሰዓቱ አይሁድ እና ሳምራዊያን እንደ ጠላቶች ነበሩ)። ጠላቶቻችን ሳይቀሩ የኛ ፍቅር እንደሚገባቸው በማስረዳት ፥ ባልጀራ ማነው የሚለውን በሚደንቅ ቅለት ነገረው።


እውነት ለመናገር አንድ ነገር እንደገባን ማወቅ የሚቻለው ለ6 እና ለ7 ዓመት ሕጻን ልጅ ወይም ለአሮጊት አያታችን ማስረዳት ስንችል ነው። እስከዛ ድረስ እኛም ገና አልገባንም።

አንድን ነገር አቅልሎ የሚያሳይ ሰው የዛ ነገር “essence” ወይም ዋናው አንኳር የገባው ሰው ነው። በተቃራኒው የሚያወሳስቡ ሰዎች አልገባቸውም ወይም ብዙ ጊዜ አጭበርባሪዎች ናቸው።

ከ90 ዓመት በፊት የአሜሪካ ኃያል ባለሀብት የነበረው ጆን ሮክፌለር (ከሀብቱ ብዛት የአሜሪካ መንግስት አስገድዶት ገንዘቡን ተበድሮታል) በጣም የሚታወቅበት ነገር ያልገባውን ነገር በልምድ ወይም ሰዎች ሲያደርጉት ስላየ ፈጽሞ አለማድረጉ ነው። በነዳጅ ማጣሪያው ስፍራ ቆሞ ሲመለከት ሠራተኛው ስምንት ጊዜ ማጣሪያውን ይጫነዋል፣ ይሄ ሂደት ሠራተኞች እይተቀያየሩ የሚከውኑት ነበር። ሮክፌለር አንዱን ኃላፊ “ለምንድነው ስምንት ጊዜ የምታደርጉት፣ ለምን አንድ ጊዜ ብቻ አታደርጉም?” ብሎ ጠየቀው። እሱም “ከዚህ በፊት ስምንት ጊዜ ነበር የምናደርገው” አለው። “ምክንያቱን ግን አላውቅም” ብሎ መለሰለት። “በሚቀጥለው ቀን ምክንያቱን አጥንተ አቅርብልኝ” ብሎት ሄደ። ሰውዬው በጥናቱ የደረሰበት ስምንት ጊዜ የሪፋይነሪ ፓምፑን መጫን እንደማያስፈልግ እና ይሄ በሆነ አጋጣሚ የተከሰተ፣ አሁን ግን ፈጽሞ የማያስፈልግ መሆኑን አጥንቶ አቀረበ። “ለምን” ብሎ በመጠየቁ ብቻ ሮክፌለር ሠራተኞቹ የሚያጠፉትን ሰዓት አዳነ፣ የሪሶርስም ብክነት ቀነሰ።

በየቀን ሕይወታችን የምናደርጋቸው ቀላል የማይባሉ ሥራዎች ያለምክንያት ሊሆኑ ይችላሉ። ሥርዓት ስለሆነ ብቻ፣ ከዚህ በፊት ሌሎች ስላደረጉት ወይም ያን አለመከተል ከሌሎች ሊነጥለን እና ጥፋት ብናጠፋ አደጋ ውስጥ ሊጥለን ይችላል ብለን ስለምናስብ የምናደርጋቸው ነገሮች ብዙ ናቸው።



ይሄ የማይነካው የሕይወት ክፍል የለም። ብዙ ግራ የሚገቡን እና ዓላማውን የሳቱ ወይም ከዓላማው በላይ ሥርዓቱን ዓላማ ያደረጉ ነገሮች በሃይማኖት ስፍራ እናያለን፣ በሥራ ቦታዎቻችን እነዚህ ውስብስብ ሥራዓቶች እና ቢሮክራሲዎች የደካሞች መደበቂያ ሆነው እናገኛለን።

ከወራት በፊት የወዳጄ ቤት ስሄድ፣ በቤቱ ውስጥ አንድ ጉዙፍ ውሻ አለ። ውሻው በአንገቱ ላይ ገመድ አለው። ዓላማው በቀን አንዴ ውጪ ይዞት ሲወጣ፣ እዛ የአንገት ገመድ ላይ ረዥም ሌላ ገመድ አስሮ ለመውጣት ነው። በዚህ ሀገር ውሻን ያለማሰሪያ (leash) መንገድ ላይ ይዞ መወጣት በሕግ ስለሚከለከል ነው። ውሻው ቤት ውስጥ ስለነበረ ይሄን የአንገት ገመት አወለኩለት። ውሻው ግን መታሰሪያውን መልሰ ካላጠለክልኝ ብሎ አበደ። በጣም ገረመኝ። ምንአልባት እንግዳ ስለሆንኩኝ እና እኔ ስላወለኩለት ይሆናል ብዬ፤ እነሱ እንዲያወልቁለት እና እንዴት እንደሚሆን ለማየት ጠየኳቸው። ውሻው ግን ማንም ያን የአንገት ገመድ ከአንገቱ እንዲወስድበት አልፈቀደም። ምክንያቱም ከልጅነቱ ጀምሮ ይሄ ገመድ ዘወትር አንገቱ ላይ ስለነበረ፤ ከዛ ማሰሪያው ገመድ ጋር ከፍተኛ ቁርኝት ፈጥሯል። ነጻ እንዲሆን እና እንዲቀለው የተመኘነውን ሁሉ ሊፈቅድልን አልቻለም።

ይሄ የውሻ ታሪክ ብቻ ከመሰለን በጣም ተሳስተናል። እውነት ለመናገር ያ ውሻ ራሴን እንድፈትሽ ነበር የጋበዘኝ። “በእኔ ሕይወት ውስጥ ምክንያቱን የማላውቃቸው ከልምድ አንጻር፣ ከማህበረሰብ ላለመለየት ስል ብቻ ወይም ሳይገባኝ ሌሎች ስላደረጉት ብቻ የማደርገው ነገር ምንድነው?” ብዬ መጠየቅ ነው የጀመርኩት።



ታላቁ ሳይኮሎጂስት ካርል ዩንግ በዚህ ዓለም ላይ በጣም ከባዱ ነገር አንድን ነገር ማቅለል ነው፤ ራስንም አቅሎ ለማቅረብ ታላቅ ጥበብ ይፈልጋል ይላል። (But simple things are always the most difficult. In actual life, it requires the greatest art to be simple.)።

የትኛውንም ነገር ጠንቅቃችሁ ለማወቅ ትፈልጋላችሁ፣ ያን ነገር አቅልሉት። ውስብስብ ነገሮችን በቀላል ነገር ተኳቸው፣ ሥርዓት የበዛበት ነገር ስታዩ ቆም ብላችሁ ጠይቁ፤ “ምንድነው የዚህ ሥርዓት ዓላማ? ማነው ይሄን የደነገገው? ምን ለማሳካት ታልሞ ይሄ ሥርዓት ወጣ? ዓላማውን ለማሳካት ዛሬ ላይ ከዚህ የተሻለ መንገድ የለም?” ለእነዚህ ጥያቄዎች ውስብስብ መልስ የሚሰጣችሁ ሰው ወይ ራሱ አልገባውም ወይም እያጭበረበረ ነው።



ነገር ግን ያለዕውቀት ለማቅለል የሚሞክር ሰው ሕጻን ነው። ሕጻን ብቻ ነው አንድን ነገር የሚያስከትለውን የተለያዩ መዘዞች በአግባቡ ሳያጤን ለማፍረስ የሚሯሯጠው። ያ ቀላል የሕጻን አዕምሮ ነው።



ማካበድ ደግሞ የጀማሪ አዋቂ ወይም ትንሽ እውቀት ያለው ሰው ባህሪ ነው። ይሄ ሰው በውስብስብ ሕጎች፣ ቢሮክራሲዎች፣ ሥርዓቶች፣ በረቀቁ ትንታኔዎች፣ በከባድ ቋንቋዎች (ቃላቶች) ብቻ ነው ከፍ ማለት የሚችለው፣ መኖር እና አዋቂ ተብሎ መከበር የሚችለው። እነዚህ ዓይነት ሰዎች “ሰንበት ለሰው እንጂ ሰው ለሰንበት የተፈጠረ” አስመስለው ሥርዓት እንደዘረጉት ፈሪሳውያን ናቸው። በማወሳሰብ ብዛት አዋቂ ተብለው ለመኖር የሚቋምጡ።


በእውቀት ላይ ተመስርቶ ቀንበርን ማቅለል ግን የጥበበኛ እና የፍጹም አዋቂ ሰው ባህሪ ነው። እንደዚህ ዓይነት ሰዎች የማንኛውንም ነገር essence ወይም ኮር ዓላማ ወይም ዋነኛ ግብ ለማወቅ የሚጥሩ ሰዎች ናቸው። ያን ጠንቅቀው ካወቁ በኋላ፣ ዓላማውን በተሻለ መንገድ፣ ከድሮው በቀለለ ሂደት ለማሳካት የሚጥሩ ናቸው።

በተለያዩ ርዕሶች ዙሪያ ጹሁፎቼን በቴሌግራም ገጼ ማግኘት ትችላላችሁ።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 3 min read
ree

በዚህ ሰሞን ሁለት ታላላቅ አሜሪካውያን ሞተዋል። አንደኛው የአሜሪካ ቢዝነስ ላይ ኃያል ተጽዕኖ ያሳደረ ሲሆን፣ ሌላኛው ደግሞ የ12 የአሜሪካ ፕሬዝዳንቶች የውጭ ጉዳይ እና የብሔራዊ ደኅንነት ፖሊሲ አማካሪ የነበረ ነው። ቻርሊ መንገር በ99 ዓመቱ ሲሞት፣ ሄነሪ ኪሲንጀር በ100 ዓመቱ ሞቷል።


በኖሩበት ዘመን ልክ ተጽዕኖ የፈጠሩ፣ በተሰማሩበት መስክ አስገራሚ ለውጥ ማምጣት የቻሉ ናቸው። ሕይወታቸው እስከሚያልፍ ድረስ ሰዎች የሚሰሟቸው ነበሩ። ሌላኛው አሜሪካዊ ሙሁር ናሲም ታሌብ ስለቻርሊ እና ኪሲንጀር ሲናገር “አንደኛው ወደ ገነት ሌላኛው ወደ ሲዖል እንደሄዱ የታወቀ ቢሆንም፣ ሁለቱም ግን በዚህ ዓለም ቆይታቸው በሚያዋዥቅ ሙሁራዊ እንቅስቃሴ (athletic activities) ጊዜያቸውን አላጠፉም” ይላል። ከሁለቱም የምንማረው ነገር ቢኖር፤ እኛ ኢትዮጵያውያን በከፍተኛ ደረጀ የጎደለን ነገርን ነው። አንድን ነገር አድምቶ የመረዳት እና ከሥር መሰረቱ የማወቅ፣ ከዛ ሰው ወደደን ጠላን ለሚል ጊዜያዊ ሁካታ ሳይሆን ፥ በጽንአት በዛ አቋም መቆምን ነው። ማለትም ለጊዜያዊ ትክክለኝነት ስንል፣ ከጥልቀት ምርምር እና መረዳት በኋላ የያዝነውን አስተሳሰብ አለመለወጥ። ለዘላቂ ጥቅም ጠላት የሆነ አንድ ነገር አለ፣ ሕዝባዊነት ነው። ለጊዜው ሞኝ እና ስህተተኛ ሆኖ ለመቆጠር ያልደፈረ ሰው፣ ለረጅም ጊዜ የሚዘልቅ ግብን ማሳካት አይቻለውም። ቻርሊም ሆነ ኪሲንጀር በተሰማሩበት ሕይወት እንደዛ ነበሩ።



 ለዛሬ እ.ኤ.አ በሜይ 2023 ዓ.ም. ዋረን በፌት እና ቻርሊ መንገር ከበርክሸር ኢንቬስተሮች ጋር ባደረጉት የሁለት ቀን ስብሰባ ወቅት ከተናገሩት እና በጊዜው ለጥቂት ወዳጆቼ ያጋራውትን አጋራችኋለው። ከድንቁ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ አሳቢ ኪሲንጀር ደግሞ አንድ ከአገራችን ወቅታዊ ሁኔታ ጋር የሚመሳሰል የተናገረውን ነጥብ በቁጥር ዘጠኝ ላይ አክያለሁ። መልካም ንባብ።

ዋረን በፌት 92 ዓመቱ ሲሆን ፥ ቻርሊ መንገር ደግሞ 99 ዓመቱ ነው። ሁለቱም ከ20ዎቹ ዓመታቸው ጀምሮ ኢንቬስተሮች ሲሆኑ ፥ ከ50 ዓመት በላይ ቢሊየነር የሆኑ ጥቂት አሜሪካኖች ውስጥ በመጀመሪያው ረድፍ ስማቸው የሚቀመጥ ነው። ቻርሊ እና ዋረን በርክሽርን (ኮካ ኮላ እና አፕል ስልክን ጨምሮ ትልልቅ ኢንቨስትመንቶች ውስጥ የአንበሳው ድርሻ የያዘ ድርጅት ነው) በሚመሩበት ወቅት፣ ድርጅቱ 2,000,000% መነሻ ኢንቨስትመንቱ ላይ መመለስ ችለዋል። ትላንት ካነሱት ወሳኝ ነጥቦች ፥ በሕይወት እነዚህን ካደረጋቹ ስኬታማ ትሆናላችሁ ብለዋል፤


1) ወጪያቹ ከገቢያችሁ ማነስ አለበት። ቀሪውን ገንዘብ በጥንቃቄ ኢንቬስት አድርጉት፣


2) ከልጅነቴ ጀምሮ የተማርኩት ነገር በሕይወት የሚመጡልኝ ጠቃሚ ዕድሎች ጥቂት እንደሆኑ ነው፣ ጥበቡ እነዚህን ጥቂት ዕድሎች እንዳያመልጡን መዘጋጀት ላይ ነው። ይሄን የኢንቨስትመንት ካውንስል ላይ ሲናገሩ አትሰሟቸውም፣ እነሱ የሚመስላቸው ሚሊዮን ነገሮችን በማጥናት ሚሊዮን ነገሮችን ማግኘት የሚቻል ነው።


3) በየዕለቱ ከመተኛታችሁ በፊት የዛ ቀን ስትነሱ ከነበራችሁ እውቀት ትንሽ አዋቂ ሆናችሁ ለመተኛት ቁረጡ፣ ኃላፊነታችሁን በታማኝነት እና በጥሩ ሁኔታ ተወጡ።


በዚህም ሲስተማቲካሊ ወደፊት ትጓዛላችሁ፤ የግድ በፍጥነት ላይሆን ይችላል። ነገር ግን ይሄን በማድረጋችሁ ጠንካራ ሥነስርዓት (discipline) ስለምትገነቡ ወደፊት በፍጥነት መስፈንጠር ትችላላችሁ። በየቀኑ አንድ እርምጃ ወደፊት ተጓዙ፣ ቀን በቀን ለማደግ ሞክሩ፤ በመጨረሻ ረዥም ዕድሜ ከኖራችሁ በሕይወት የሚገባችሁን ነገር አታጡም። (ቻርሊ ከፈጣን ዕድገት ይልቅ ሰውን ወደ ግቡ የሚያደርሰው ዝግ ያለ ግን የማይቆም ዕድገት ነው የሚል ፍልስፍና አለው። ሲ ኤስ ሉዊስ ስለሰይጣን ስትራቴጂ ሲናገር “የሰውን ልጅ በርግጠኝነት ሲዖል ማስገባት የሚቻለው በፈጣኑ የክህደት ሃዲድ ሳይሆን፣ ዝግ ብሎ በሚሄደው የክህደት መስመር ነው” ይላል። በርግጥስ ከጥንቸል ይልቅ የአሸነፈችው ያለማቋረጥ ግን ደረጃ በደረጃ የተጓዘችው ኤሊ አይደለች። ዊንስተን ቸርችል ስለአሜሪካ ሲናገር “ቶሎ ለውጥን አይቀበሉም ነገር ግን ሁልጊዜ ትክክለኛው ነገር ላይ ይደርሳሉ” ይላል)።


4) ሰዎችን በፍጹም አትውቀሱ ፥ ሰውን ሳትወቅሱ ጥፋታቸውን ማሳየት ትችላላችሁ፣(የከፍተኛ ትምህርት ዘይቤ በሚለው መጽሐፋቸው ሊቁ እጓለ ገብረዮሐንስ፤ “አንድን አሮጌ ቤት አሮጌ ሳትሉ ማርጀቱን መግለጽ ትችላላችሁ” ይላሉ። “ይሄም አጠገቡ አዲስ ቤት በመገንባት ነው። የዛኔ ያንተን አዲስነት፣ የዛን ቤት አሮጌነትም ይናገራል” ይላሉ። “ነቢይ እና ሕጻን ነው በቀጥታ ሰውን የሚወቅሱት። እኔ ደግሞ ሁለቱንም አይደለውም” ይላሉ ሊቁ። ቻርሊ እና ዋረን የሚሉንም ተመሳሳይ ነው)።


5) በሕይወታችሁ መርዛማ ሰዎችን በፍጥነት አሶግዱአቸው (ተንኮልን እወቁ ግን ተንኮል አትስሩ ፥ የጥፋተኝነት ስሜት እንዲሰማችሁ አድርገው ሊበዘብዟችሁ ያሉ ሰዎችን በተቻለ መጠን ከሕይወታችሁ በቶሎ ቆርጦ መጣል ወሳኝ ነው።)


6) በሞታችሁ ጊዜ እንዲነበብላችሁ የምትፈልጉትን ከአሁኑ ጻፉ (obitury) እና በዛ መሰረት ኑሩ። ያኔ በየቀኑ በጥበብ ታድጋላችሁ።


7) ዕዳ ውስጥ ፈጽሞ አትግቡ ፥ አንዴ ከገባችሁ መውጫ የለውም ምን አልባት ቤት መግዛት ላይ በዕዳ ልታደርጉት ትችላላቹሁ ከዛ ውጪ ግን ፈጽሞ።


8. የምታደርጉትን ሁሉ ይሄን ነገር በየቀኑ እያደረኩኝ ብቀጥል የዛሬ አስር ዓመት የት ያደርሰኛል ብላችሁ ጠይቁ። ያኔ ነው ዛሬ ላይ ደደብ የሆነ ነገር ከመስራት የምትቆጠቡት። በሁሉም ነገር የረዥም ጊዜ እይታ ይኑራችሁ።


9) ኪሲንጀር ከጎቴ (Goithe) አዘውትሮ የሚጠቅሰው አባባል አለው፣ “በፍትሕ እና በሥርዓት (order) መካከል ምርጫ ቢሰጠኝ፣ ሥርዓትን ነው የምመርጠው። ምክንያቱም አንዴ ሥርዓት አልበኝነት ከነገሰ ለፍትሕ ቦታ የለውም። (ኪሲንጀር በዚህ ሳምንት ቢሞትም ይሄ አባባሉ ግን በዓብይ ኢትዮጵያ ዛሬ እየኖርነው ነው። ሰው “ምን ነው ሁሉ ነገር ቀርቶብኝ በሰላም ወጥቼ በሰላም በገባው” እያለ ነው፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ መሞቱ ብቻ አይደለም ዛሬ ያማረረው። ገዳዩ መብዛቱ እንጂ። አንድ ገዳይ ቢቻ ቢኖር ያን መንግስት ብሎ ይታዘዝለት እና የሚፈልገውን ያህል ይገብርለት ነበር። ሥርዓት አልበኝነት ባለበት ፍትሕ ሆነ ዲሞክራሲ ቅንጦት ናቸው። ሥርዓት ባለበት ግን ቢያንስ ቢያንስ የተገደበ ፍትሕ በርግጠኝነት አለ)።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page