- Mulualem Getachew

- Sep 28
- 5 min read

Written on April 7, 2023 and you can find the original post with this link. (https://www.facebook.com/profile/100002335758452/search/?q=ጄኔራል%20አበባው)
እኔ አንተን የትላንት ታሪክህን ጠቅሼ መክሰስ አልፈልግም። ስለኢትዮጵያም ያለህን እምነትህን እና ፍቅርህን መጠየቅ አልሻም። የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ውስጥ ሆነህ ፥ ሀገራችንን ለማገልገል መፍቀድህ በራሱ ለእኔ ትልቅ ቁምነገር ነው። ነገር ግን ባለፉት 5 ዓመታት ሁላችንን ብዙ ነገር አስተምሯል ፥ “ኢትዮጵያ ሱስ ናት” ብለው በቃላቸው ፥ በተግባር ግን አንዱን ብሔር ነጥለው የሚመቱ ፥ 3 መቶ አማሮች በየቀኑ ሲረግፉ ፥ መንገድ ዳር ከተከሉት እና ለጠወለገባቸው አበባ ያሳዩትን ብስጭት ለአማሮች ሞት መግለጽ ያልቻሉ መሪዎችን ነው ያየነው። “አዲስ አበባ ውስጥ የኦሮሞ ጥላቻ አለ” ብሎ ጠረጼዛ እየደበደበ የተናገረ ጠቅላይ ሚኒስትር ፥ 3 መቶ አማሮች በቀን ሲታረዱ ግን ድግስ እየደገሰ ሲደሰት ለህዝብ ያሳያል። ወገኔ ላለው ተጠላ ብሎ በፓርላማ ያዙኝ ልቀቁኝ ሲል ፥ ከመጠላት አልፎ ሕጻን አዛውንት ሳይቀር በገፍ ለታረዱበት የአማራ ሕዝብ ግን የውሸት ሐዘናቸውን እንኳ ሊያሳዩት አልፈቀዱም። ጄኔራል አበባው ፥ ንግግር ሰምተን እና አምነን እማ ፥ ዐብይ አህመድን ልባችን እስኪወልቅ ደግፈነው ፥ ሞቱን ሳይቀር ለመሞት መርጠን ነበር። የዛሬ 5 ዓመት ለዐብይ አህመድ የድጋፍ ሠልፍ ሲወጣበት የነበረው የአማራ ከተሞች እና መንደሮች ነበሩ።ለምን?
(የዛኔ ከጥቂት የኦሮሚያ ከተሞች በቀር ለዐብይ የተደረገ ሠልፍ አላስታውስም።ከ5 ዓመት በኋላ ቃሉን ሳይሆን ተግባሩን ያዩ ሰዎች ለድጋፍ የወጡት በኦሮሚያ ነው።)
አማራ ዐብይ አህመድ “መደመር ይሻለናል ፥ አንድነት ይሻለናል” ስላለ እንጂ ፥ ዐብይ ኦህዴድ መሆኑ ጠፍቶት አልነበረም የደገፈው። አማራንም ጠቅማለው ስላለው አልነበረም። ይልቁስ ጄኔራል ፥ ዐብይ አህመድ ያለን ዛሬ ልክ አንተ ያልከንን ነበር። “አንድነት ይሻላለና ፥ ስንደመር ነው ኃያል የምንሆነው” ነበር ያለን። ዛሬ እሱን የሚያምነው ስለሌለ አንተ እነዚህን ቃላቶች እንድትናገር ላከክ። አንተም የዛሬ 5 ዓመት እሱ የተናገረውን ሳትቀንስ እና ሳትደምር ፥ “በጋራ አድርገን አንድ ጠንካራ ኃይል ልንገነባ ነው” አልከን። ጄኔራል አንተ ሰው አማኝ ምንአልባትም እንዳልከው ፖለቲካ ብዙ የማትወድ ትሆናለህ። እኔም ብችል እንዳንተ ብሆን እና ለዚህ ሕዝብ የተደገሰለት ግፍ ባይገባኝ እመርጥ ነበር። ግን ትምህርቴ እና የሥራ ልምዴ ዓይኖቼን ከፍቶታል። ማኪያቬሌ እንዳለው ፥ ሕይወት ሰዎች የሚናገሩትን ሳይሆን የሚሰሩትን እንድመለከት አስተምራኛለች።
ለዚህ ነው ውድ ጄኔራል አበባው ፥ የምትናገረው ነገር ከሚሰራው ጋር ፈጽሞ አይገናኝም የምልህ። በርግጥ አንተም የምትናገረውን ብዙ ያመንክበት አይመስልም ፥ ምክንያቱም ባንድ በኩል ትልቅ አቅም እንደተገነባ እየፎከርክ ታወራለህ በሌላ በኩል ደግሞ “ዛሬ ባለችው ኢትዮጵያ አይደለም ሰው በነጻነት ሰላም ተሰምቶት ከክልል ክልል ሊሄድ ከቤቱ ወጥቶ ማምሸት እንደማይችል” ትገልጻለህ። ደግሞ መልሰህ ትፎክራለህ። አንድ አባት በአንድ ወቅት ሲናገሩ እንደሰማውት የተሸነፈ ሠራዊት ፉከራ ያበዛል ፥ አንተም አቅማችን ኃይል ነው ብለህ ሳትጨርስ ሰው ከቤቱ ወጥቶ ማምሸት የማይችልበት ኢትዮጵያ እንደተፈጠረች ትነግረናለህ።
የሕዝብ አመጽን ማፈን የሚችል ኃይል ተገንብቷል ፥ ማንም ምንም የማምጣት አቅም የለውም በተደጋጋሚ ትላለህ። ጄኔራል ፥ አንተ የውጭ ፖለቲካ አትከታተል ይሆናል። አይደለም ኢትዮጵያ ውስጥ ፥ አሜሪካ ውስጥ ራሱ የእርስ በእርስ ጦርነት ሊነሳ ይችላል አይችልም የሚሉ ክርክሮች በስፋት በሙሁሩ ዘንድ እየተካሄደ ነው። ይሄ ማለት በኃይል ስልጣን ሊይዝ የሚያስብ አለ ማለት ነው። የማይቻል ነገር ደግሞ አይታሰብም። በአሜሪካ እንኳ ሊሞከር የሚችልን ነገር ነው እርሶ ገና እየተገነባ ያለ ሠራዊትን ይዘው እንዲህ የሚፎክሩት።
እሱ ብቻ ግን አይደለም ፥ አንት እንዳልከው ኃይል ስልጣን የመያዣ መንገድ ብቻ ሳይሆን ፥ በስልጣን ላይ ያለን የማስገደጃም ነው። ለምሳሌ በሕዝብ ከተመረጠ የወራት ዕድሜ ያለው የቢቢ ናታኒሆን (የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር) መንግስት ፥ የጠቅላይ ፍርድ ቤቱን የመወሰን እና ህገ-መንግስታዊ ጉዳዮችን የማየት አቅም የሚያሽመደምድ ረቂቅ ሕግ ለፓራላማው አቅርቦ ሊያጸድቅ ነበር። እስራኤሎች ግን ገና ከመረጡት ወራት ባስቆጠረው ጠቅላይ ሚኒስትራቸው ላይ ሕዝባዊ አመጽ ጠሩ። ምክንያቱም የእስራኤል ብቸኛ ነጻ ተቋም ፍርድ ቤቱ ነበር። ይሄን አጡት ማለት ዲሞክራሲ በእስራኤል አበቃለት ማለት ነው። ቢቢ ናታኒሆን እስራኤልን በመውደድ አቻ የሚገኝለት ሰው አይደለም። ግን ፖለቲከኛ ነው። ፖለቲከኛ ስልጣንን ከምንም ነገር በላይ ይወዳለ። እሱ ብቻ ግን አይደለም። ፖለቲከኛ ብዙ ጊዜ እጁ ቆሻሻ ነው ፥ ስለዚህ ተጠያቂነትን ማስቀረት ይሻል። ለዚህ ነው ከራስ በላይ ንፋስ ብሎ ፥ በእስራኤል የዲሞክራሲ ምሰሶ ላይ የዘመተው። ሕዝብ ግን አደባባዩን አጥለቀለቀው። መንገዶችን ዘጋ። ቢቢ ናታኒሆን በቅርብ ተመርጬ ይሄ እንዴት ተደርጎ ብሎ ያዙኝ ልቀቁኝ አላለም። ምክንያቱም ምርጫ ማለት ኮንትራት ነው። ኮንትራት ማለት ውል ነው። ከአንድ ድርጅት ጋር ለ5 ዓመት ውል ገባህ ማለት ፥ ድርጅቱ ሊጠግንልህ የቀጠርከውን ቤትህን ሲያፈርስ የ5 ዓመት ውሉ እስከሚያልቅ ዝም ብለህ ታየዋለህ ማለት አይደለም። ከውል ውጪ እየፈጸመ ብቻ ሳይሆን ፥ ውሉ ያስፈለገበትን ዋነኛ መሠረት እየናደ ስለሆነ ውሉን የመሰረዝ መብት የትኛውም የአራዊት ሕግ የሌለበት ሀገር ሕግ ይፈቅዳል። የሕግ ባለሙያ ስለሆንኩ የምናገረውን አውቃለው።
በተመሳሳይ የዐብይ አስተዳደር አንድነትን የመፍጠር ቃልኪዳኑ ቀርቶብን እንደ ድሮ ተከፋፍለን እንኳ መኖር እንዳንችል እያደረገን ነው። ክቡር ጄኔራል አንተ ለኢትዮጵያዊ የምታዝን ከሆንክ ፥ በአዲስ አበባ ዙሪያ ከ10 ዓመት በላይ ከኖሩበት ቤት ኢትዮጵያኖች ሲፈናቀሉ ፥ ምን አደረክህ? እውነት ነው ያደረከውን ነገር በአደባባይ ትነግረኛለህ ብዬ ጠብቄ አይደለም ፥ ግን ኢትዮጵያኖች ቤታቸው በላያቸው መፍረሱ ሊቆም ይቅርና ፥ ራሳቸው አፍርሰው ጣሪያና በራቸውን እንኳ መውሰድ አትችሉም ነው የተባሉት። አንተ በውስጥ ስለዚህ ጉዳይ ተናግረሃል ብለን እንመን። አንተ ጄኔራሉ ማስቆም ያቀተህን የዛሬ ግፍ ፥ አማራው ነገ ስለተደገሰለት መከራ ግድ የላችሁም እኔን እመኑኝ ስትል ትንሽ ለህሊናዎ አይከብዶትም።
ጄኔራል ከስልጣን ተባሮ መኖር እንደሚቻል እኮ እርሶ በተግባር ያውቁታል። ግፍ እና ውንብድና ሰርቶ ግን መኖር ቀላል እንዳልሆነ ፥ እርሶም ከቀድሞ የትግል አጋሮቾ ለምን አይማሩም? (በቃለመጠይቁ "ከትግራይ ጦርነት ተማሩ" የሚለውን በብዛት ስለተጠቀሙ ነው። እርሶም ከቀድሞ ጓዶቾ የሚማሩት ብዙ አለ የሚለውን ለማስታወስ ነው።)
ልጠይቆትማ ጄኔራል። ከአማራ ልዩ ኃይል አባላት ጋር አብረን ጎን ለጎን ተዋግተናል። ቆስለናል ፥ ደምተናል አሉን ልበል። እንግዲያውስ ይሄን ይመልሱ። ሕወኃት ቆቦን ስትይዝ ፥ ለምናቹ የጠራችሁት ጄኔራል ፥ በዚህም ምክንያት ከ 10 በላይ ጥይቶችን በእግሩ ውስጥ የተሸከመን ባለውለታ ፥ ለአስቸኳይ ሕክምና ከአገር አትወጣም ብላችሁት እየተሰቃየ ነው። ሲሆን ሲሆን ወጪውን ችላችሁ ማሳከም ሲገባ ፥ ይሄን ምስኪን ጄኔራል ቀስ እያለ እንዲሞት ፈረዳችሁበት። ከጎንህ ሲዋጋ ለቆሰለው ፥ ለሀገሩ ዋጋ ለከፈለው ጄኔራል ተፈራ ያልቆምከውን አንተ ፥ ለሱ መሆን ያልቻልከውን አንተ ፥ በሚሊዮን ሕዝብ ደህንነት ጉዳይ እመኑኝ ነው የምትለን? ክቡር ጄኔራል ፥ እኔ በመጽሐፉ ቅዱስ አምናለው። በመጽሐፉ ቅዱስ ላይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶ ፥ አደራ የሰጠውን ባለሟሉን ጠርቶ ያለው እንዲህ ነው ፥ “አንተ በጥቂት ታምነሃል እና በብዙ ትሾማለህ ፥ ያልታመነውን ደግሞ ያለው “አንተ በጥቂት አልታመንክም እና ያለህም ይወሰድብሃል።” ስለዚህ ክቡር ጄኔራል ፥ አይደለም በብዙ ሚሊዮን ምስኪን የአማራ ወገኔ ጉዳይ ላምንህ ይቅርና ፥ ከዛ ባነሱ ጉዳዮች ሳይቀር እምነቴ መሉ አይደለም።
በመጨረሻ የመንግስት ትዕዛዝን በሰላም የማትቀበሉ ከሆነ ፥ እንጠርጋችሃለን ብለሃል። አሁን የቀደመው ፥ ማስታወስ የማልሻው ማንነትህ ተገለጠ። ግን ክቡር ጄኔራል አንተ እንዳልከው እኛን የማጥፋት ኃይል ቢኖርህ እንኳ ፥ የሕዝባችንን መጥፋት ዓይናችን እያየ ዝም ከምንል ፥ ሁሉን መሆንን እንመርጣለን። ኔልሰን ማንዴላ እንዳለው “ሁሉም ነገር እስከሚሆን ድረስ የማይቻል ነበር።” እግዚአብሔርን የማመሰግነው ፥ “የምንሸነፍ አይደለንም ፥ ጦርነት ባህላዊ ጫዎታችን ነው” ያሉትን ሕወኃቶች ሳይቀር ፥ በእንብርክክ ይቅርታ ጠይቀው መሸነፍ የተፈጥሮ ግዴታ መሆኑን በዕድሜዬ ማየቴ ነው። የአማራ ሕዝብም እንዲህ ባለህ መታበይ ፥ እንዲገጥማችሁ አልሻም። ምክንያቱም ኃይል የእግዚአብሔር መሆኑን ከአንዴም ብዙ ጊዜ አይቻለው እና። የአማራ ሕዝብ ካሸነፈም የሚያሸንፈው የመገፋቱን መጠን ፥ የደረሰበትን ግፍ እና ስቃይ አምላክ ስለቆጠረለት ነው። አዎ ፥ ለምስኪኖች ተስፋቸው ማነው? ፥ እግዚአብሔር አይደለምን?
በዚህ ጥበዓት የአማራ ሕዝብ ለህልውናው ይቆማል ፥ ዳግም በአፈ ሞላጮች ላይሸወደ በአንድነት ይነሳል። ለራሱ ብቻ ሳይሆን ፥ በኢትዮጵያ ምድር ለሚጎሳቆሉ ሁሉ ፥ ለሚጠሉት ሁሉ ፥ የተመቸች የጋራ ቤት ፥ የእኩልነት ቤት ለማቆም ይሰራል። በመጨረሻ የዐብይ ፖለቲካ ግር ለሚላችሁ ይሄን የማኪያቬሊ ምሳሌያዊ ታሪክ ፥ መርህ ይሁናችሁ።
ማኪያቬሊ ሰውን በዓይንህ በምታየው ሳይሆን በእጁ በሚሰራው ፍረድ የሚለውን አስደናቂ ጥበብ ያገኘው በሱ ዘመን ከነበረ አንድ መጽሐፍ ነው ፥ መጽሐፉ ውስጥ የትልቋ እና የትንሻ ወፍ ወግ ይላል። ታሪኩ እንዲህ ነው። አንድ ሰውዬ ወፎችን ሰብስቦ በብረት ወጥመድ (cage) ውስጥ ያስቀምጣቸዋል። የሆነ ቀን እየጠበቀ ፥ ከወጥመዱ እያወጣ እነዚህን ወፎች አንድ በአንድ ያርዳል። ከሁሉ ሕጻን የሆነችው እና ልምድ የሌላት ወፍ ለትልቋ ወፍ ፥ “ዓይኖቹን ተመልከቺ ፥ ጓደኞቻችንን ሲያርድ እኰ አዝኖ እያለቀሰ ነው” ትላለች። ትልቋ ወፍም “ሰውዬውን በዓይኑ ሳይሆን በእጆቹ በሚሰራው ፍረጂ” አለቻት (“Judge by the hands, not by the eyes”)።








