top of page
ree


በዚህ ሳምንት ትልቁ ዜና የቻርሊ ከርክ መገደል ነበር። ቻርሊ ከርክ በብዙ ነጭ አሜሪካዎች ዘንድ ትልቅ ቦታ ያለው፣ ብዙ ወጣቶችን መሳብ እና መማረክ የቻለ ነበር። የሁለት ልጆች አባት እንዲሁም ባለትዳር ነበር። ቻርሊ መገለጫው በአሜሪካ ዩኒቨርስቲዎች እየተጓዘ፣ ወንበር ዘርግቶ ጥያቄ እየተቀበለ ለእነዛ መልስ መስጠት ነበር። በጣም ውስብስብ የሆኑ የማህበረሰብ ጥያቄዎችን፣ የዘር ክፍፍል እና ልዩነት እንዲሁም የእኩልነት እና የጾታ ጉዳዮችን በድፍረት እና በአይዶሎጂ መስመሩ ይመልስ ነበር። ብዙ ነጭ ወላጆች ይወዱታል። ምክንያቱም ባህል፣ ሃይማኖት እና የቀደመው የቤተሰብ አወቃቀር ላይ ስለሚያተኩር እና ያን ለልጆቻቸው ስለሚሰብክ ወደውታል።



በተቃራኒው ቻርሊ ገና በሃያዎቹ ሆኖ ሳለ ሳይቀር ስለጥቁሮች፣ ስለ ስደተኞች እና በተመሳሳይ ጾታ ሰዎች ላይ የሚሰነዝረው ትችት እና የሚሰጠው መልስ ጠንከር ያለ እና ርህራሔ እና ጥልቀት የጎደላቸው ነበሩ። ለዚህም ይመስላል ከነጮች ውጪ ያለው አብዛኛው ማህበረሰብ በመገደሉ ያለው ስሜት እርሱን እንደ ጀግና በመቁጠር አይደለም። በርግጥ ከነጮችም ገዳዩን ጨምሮ የሚቃወመው እንዳለ ሁሉ፣ ከጥቁሮችም ሆነ ከስደተኞች የሚደግፉት አሉ።



አንድ በትልቁ የሚታይ ነገር ግን አለ። ገዳዩም ተገዳዩም ወጣቶች ነበሩ። አንድ የሚባል አባባል አለ። “በሃያዎቹ ዕድሜ አብዮታዊ ካልሆንክ ልብ የለህም፤ በአርባዎቹ ዕድሜ ደግሞ አብዮታዊ ከሆንክ ጭንቅላት የለህም።” ልብ እና ድፍረት ያላቸው ሁለት ወጣቶች ናቸው በዚህ ሳምንት ትኩረት የሆኑት። እኔን የሚገርመኝ ግን አሜሪካ ውስጥ ያሉ አዕምሮ ሊኖራቸው ዕድሜያቸው የሚያስገድዳቸው ሰዎች በእነዚህ ሁለት አብዮተኞች ጎራ ተሰልፈው የቃላት ጦርነት ውስጥ ሲገቡ ነው። ማህበረሰብ እየወደመ ለመሆኑ ትልቁ ማሳያውአርባዎቹ እና ከዛ በላይ የሆኑ ሰዎች አብዮተኞች ሲሆኑ ነው። በሃያዎቹ ያለ ሰው የሚታየው ነገር ውስን ነው። ለውጥ በነውጥ ጭምር ነው የሚታየው። ስለ ሕይወት ያለው ትርጉም በደረሰበት ዕድሜ የሚታየው ብቻ ነው። ያንን ትርጉም የማይጋሩት ሁሉ ደግሞ ጠላቱ እና ክፉዎች አድርጎ ያያል።



ቻርሊ ከርክን የገደለው ሮቢንሰን የሳለ አዕምሮ ያለው እና በትምህርቱ ምጡቅ ነው። ያ ግን አንድ እውቀት እና መረዳት ብቻ ነው። ገና በሕይወት ጉዞ ያልተደላደለ፣ በውጣ ውረድ ያልሰከነ እና ከሌሎች እይታዎች ጋር ያልተፋጨ ነው። ሁላችን ወጣቶች ነበርን። ሁላችን በሃያዎቹ ዕድሜ ነበርን። አሁን ላይ ደግሞ ወደ ኋላ ስንመለከት ምን ያህል ውስን መረዳት እና ደካማ የሆነ እይታ እንደነበረን፣ ጽንፈኝነት እስከ አፍንጫችን እንደነበረ አስተውሉ። ቻርሊ ከርክ ደግሞ ልክ እንደ ጀዋር መሐመድ ያለ ሰው ነው። የነጭ ጀዋር መሐመድ ማለት ነው። አንደበት አለው። የእኔ የሚላቸው ሰዎች በቁጥር ብዙ ናቸው። ለብዙ ማህበረሰብ የተወሳሰበውን ችግር በራሱ መነጽር ብቻ አይቶ የማህበረሰብን አድሎአዊ እይታ በማጽደቅ ይመልሳል። ከፍተኛ ኃይል አለው። አይደክምም። ልክ ጀዋር መሐመድ በአፍላ ዕድሜው ብዙዎች የእርሱ ያልሆኑት እንዲገደል ጭምር ሲመኙለት እንደነበረው፣ ቻርሊንም የሚቃወሙት ሰዎች ያን ነበር የሚመኙለት የነበረው። እርሱም መጀመሪያውኑ የተዋቀረው የአሜሪካ ሥርዓት ያጎሰቆላቸው እና ያዳከማቸው ማህበረሰቦች ላይ በንግግሩ ያቆስላቸዋል። ጥቁሮች ሰነፎች ናቸው፣ እንደውም በሆነ መለኪያ በባርነት ዘመን የተሻለ ሕይወት ውስጥ ነበሩ፣ ባርነት መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጭምር ነው በሚሉ እና ዳታዎችን (ስታስቲኮችን) ልክ እንደ ጀዋር መሐመድ ለራሱ ጥቅም ያለምንም መጠንቀቅ ነበር የሚጠቀማቸው።



እኔ እነዚህ ዕድሜያቸው ከዚህ በላይ እንዲያስቡ ባልፈቀደላቸው ሰዎች እምብዛም አላዝንም። በሁለቱ ጎራ ሆነው ግን ይሄን ሀገር ወደ ተሻለ መምራት የሚችሉ አዕምሮ ሊኖራቸው የሚገቡ ሰዎች የሚያሳዩት ባህሪ ነው የሚደንቀኝ። አንድ ጓደኛዬ የቻርሊ ከርክ ገዳይ ኢሚግራንት ቢሆን ኖሮ፣ አንድ ሳምንት ከቤት አልወጣም አለኝ። ምክንያቱም የተፈጠረው ስሜት የቡድን ነው።



ድንቅ አሳቢው ቶልስቶይ በ”War and Peace” መጽሐፉ ላይ አንድ ጀግና አለው። ጀግናው ወጣቱ ፒየር ነው። ፒየር ፈረንሳይ ሀገር ሄዶ የተማረ እና በዘመናዊ ትምህርት ዳብሮ የሩሲያን የከበርቴውን እና ፊውዳል አስተዳደር መመንገል አለበት ብሎ የሚያምን ነበር። ለንብረትም ሆነ ለሀብት ብዙ ግድ የለውም። እጦትን አይቶ ስለማያውቅ። ፒየር ለናፖሊዮ ቦና ፓርቴ ያለው አብዮታዊ ፍቅር ልዩ ነበር። ሰዎችን አይቶ በባህሪያቸው ወዲያው ይበይናቸው ነበር። ግን ፍጹም ቅን ሰው ነበር። ከችኩልነቱ እና ፈጣን ለውጥ ከመፈለጉ በቀር ውስጡ መልካም ነበር። ቶልስቶይ እንደዚህ ዓይነት የማህበረሰብ ክፍሎች እንዳሉ ያውቃል። ፒየርን ወደ ተደላደለ እውቀት ነበር ማምጣት የፈለገው። ከሚያየው ውጪ ሌላ ዓለም እንዳለ እንዲያስተውል ነበር የፈለገው። ቶልስቶይ በተለይ ይሄን ያሳየው አንድ በፒየር እና መሰሎቹ ዱሪያ ከሚባለው ዶሎኮቭ ጋር ፒየር የሽጉጥ ፍልሚያ ውስጥ በመክተት ነበር።


ዶሎኮቭ የተበላ ቁማርተኛ፣ የሽጉጥ ፍልሚያን የሚያዘወትር፣ ቢጠጣ ቢጠጣ የማይጠረቃ እና ቤተሰብ እንዳላሳደገው የሚኖር ሰው ነበር። ከፒየር ጋር ዶሎኮቭ ይጣላል። የሽጉጥ ፍልሚያ የጥሉ መቋጫ እንዲሆን ይስማማሉ። ሁሉም ዶሎኮቭ ካለው ፍጹም የልምድ ብልጫ በመነሳት ፒየርን እንደሚገለው ገመቱ። ከፍልሚያው በፊት ዶሎኮቭ ለወዳጁ ሮስቶቭ "ይኸውልህ ወደ እንደዚህ ዓይነት ግጥሚያ ስትሄድ እንደምትሞት አስበክ ኑዛዜ ጽፈክ፣ የመጨረሻ ቃል በሚያምር ቃላት ከትበክ መጓዝ የለብህም፡ ግን እንደምትገድል ቅንጣቢ ጥርጣሬ ሳይኖርክ ከገባህበት ሁሉም ነገር ይሰምራል። ልክ እንደ ድብ አዳኝ ፥ ፍርሃቱን ከገለጠ ድቡ ያንን በማሽተት እንደሚያከሽፍበት ሁሉ ፣ ፍርሃት ከተሰማክ ሁሉ ነገር እዛው ያከትማክ።" ሲያቀብጠው እዚህ ጉድ ውስጥ እንደገባ የገባው ፒየር ግን አንዴ ለግጥሚያው እሺ ብያለው እንግዲህ የፈሰሰ ውሃ አይታፈስ በሚል ፍልሚያው ሜዳ ላይ ቆመ። ፒየር ዶሎኮቭን ክፉኛ አቆሰለው። ዶሎኮቭ ፒየርን ሳተው። ሮስቶቭ ጓደኛውን አቃቅፎ ወደ እርዳታ ከነፈ። በመኃል ዶሎኮቭ እያቃሰተ እነዚህን ቃላት ይተፋል "ይሄን ከሰማች ትሞታለች፣ አትተርፍም፣ ለእኔስ ግድ የለኝም እሷ ግን ... እሷ ግን ቆማ መሄዷን እንጃ። ወይኔ ... ይሄን ጉድ ...ማየት የለባትም ... በሕይወት አትኖርም ..." ሮስቶቭ ግራ ገባው! "ስለ ማን ነው የምታወራው?" አለው። "ስለ ... እናቴ! .... ስለ እህቴ!" ከዚህ በኋላ ሮስቶቭ አዕምሮ ውስጥ የተመላለሰው ቃላቶች ናቸው ዘወትር የሚገርመኝ። "ዶሎኮቭ ወንበዴው፣ ዶሎኮቭ ቁማርተኛው፣ ዶሎኮቭ ነዋጩ ...አፍቃሪ ልጅ እና ወንድምም ነበር!"



ቻርሊ ከርክን የገደለው ወጣት የሚያውቀው አንድ የዓለምን ገጽታ ብቻ ነው። እርሱ ልክ ነው ብሎ ያመነውን ዕይታ ብቻ። ከዛ ያን ዕያት የሚቃወመውን ቻርሊንን። ቻርሊ ግን ሁለት ልጆች አሉት። ለእነዛ ልጆች ቻርሊ አባት ነው። ቻርሊ ባልም ነው። ቤተሰብ ያለው እና አሜሪካ ለልጆቹ የተሻለች ሀገር እንድትሆን የሚጨነቅም ነው። ያን ዕይታ ሮቢንሰን ማየት አልቻለም። የሚገድለው ሰው ፥ ሰውነት እንዳለው ማሰብ አልፈቀደም። ወጣት እና ምንአልባትም አንድ ቀን ሊሰክን እና የዕይታ አድማሱን የሚያሰፋ ሰው ሊሆን እንደሚችል ማየትም አልፈቀደም። ምክንያቱም የእኔ ብሎ የሚወደውን ቻርሊ ተችቶበታል እና። ቶልስቶይ ፒየርን ያስተማረው ሊገለው የተኮሰበት ግለሰብ ቁማርተኛ ብቻ ሳይሆን እናት ያለው ልጅ፣ እህት ያለው ወንድም እንደሆነ በማሳየትም ነበር። ዶሎኮቭ ከቁሱሉ በላይ የሌሎች በእርሱ ቁስል መጎዳት ነበር ያመመው። ዶሎኮቭ ግን እስከዛ ደቂቃ ድረስ ያን ስብዕና ለሌሎች ገልጦ አያውቅም ነበር። ሌላ ዓለምም ዶሎኮቭ እንዳለው ለማየት መታገስ እና ዶሎኮቭን በቁሱሉ ሰዓት መስማት ያስፈልግ ነበር። ቻርሊ ከርክም የሚፈርድባቸው ጥቁሮችም ሆነ ስደተኞች ልብን የሚሰብር ታሪክ እና አሜሪካንን ታላቅ የሚያደርግ ብቃት እንዳላቸው ማየት የፈቀደ ሰው አልነበረም። ሁሉንም በአንድ ሳጥን ውስጥ ከቶ አንዳች እርምጃ እንዲወሰድባቸው የሚሰብክ እንጂ። እንደሱ ቤተሰብ፣ ልጆች ያሏቸው እንዲሁም ለሰው እና ለመጡበት ሀገር በጎ ነገር ለማድረግ የሚጥሩ እንዳሉ ሊረዳ ፈቅዶ አያውቅም።



ብዙ ኢትዮጵያውያንም እንደ ፒየር ነን። ጥቁሮች ሰነፎች ናቸው። ጥቁሮች እንደዚህ ናቸው በማለት ለመፍረድ እምብዛም ማሰብ አንፈልግም። ግን ማህበረሰብ ከማንነቱ ተነቅሎ፣ ለዘመናት በባርነት ውስጥ ካለፈ በኋላ የሚፈጥረው ትውልድ ምን ሊመስል እንደሚችል ምንም እውቀቱ የለንም። እኛ ሲከፋን ሳይቀር ሀገሬ ብለን የምንጠራት እና የምንተክዝበት የስሜት ምርኩዝ አለን። ቀና ብለን እንድንሄድ በሚያደርጉ ትርክቶች ነው ያደግነው። ከዛ ደግሞ ከሀገራችን የመጡ እና የአሸነፉ ሰዎች ምሳሌዎች እንደ ጉም ከቦናል። ቅዱስ ጵውሎስ እነዛን ሁሉ በመከራ ውስጥ ያለፉ የቀደሙ የእምነት አባቶችን የጠራው እኮ የሰው ስነልቦና ስለገባው ነው። ሰው ፊትለፊቱ ያለውን መከራ የሚያልፈው በቀደሙ አባቶቹ ታሪክ እና ጀግንነት ነው። ይሄ የሌለው ማህበረሰብ እንዴት ነው የሚያሸንፈው? በምን አቅሙ ነው እንደ ጉም የከበበውን መከራ የሚሻገረው? ለዛውም በሲስተም ታፍኖ እያለ! እኔ ሰበብ ሰበብ ማብዛትን እየደገፍኩ አይደለም። ግን መፍረድም በተመሳሳይ ስህተት ነው ለማለት ነው። በተለይ ፈጽሞ የማንረዳውን እና ውስብስብ የሆነን የማህብረሰብ ውድቀት እና ስኬት ቀላል በሚመስሉ ንድፈ ሃሳቦች ብቻ መልስ ለመስጠት መሞከር አብዮተኛ እንጂ አስተዋይ አያደርግም። ያፈርስ ይሆናል እንጂ ይሄ ዓይነት አስተሳሰብ አይገነባም። የሰው ልጅ እና ማህበረሰብ ፊትለፊት ከምናየው ውጪ ብዙ ውስብስብ ታሪኮች እና እውነቶች አሉት። መግደል ተቃዋሚን በፍጥነት ያሶግድ ይሆናል። የምንፈልገውን ለውጥ ግን በብዙ ነው የሚያዘገየው። አምባገነን ስርዓት አንድን ጉዳይ በፍጥነት ያሳካ ይሆናል፤ የብዙ ዘመናትን ድልድዮች ግን አይገነባም። ተቃዋሚን ማሶገድ እና አንድ ወጥ የሆነ ማህበረሰብ ብቻ ለመፍጠር መጣር ለጊዜው could be effective but not efficient.


 
 
 
ree

የንጉሱን ልብስ ታሪክ ብዙዎቻችን (the emperor cloth) እናውቀዋለን። ታሪኩ ረዘም ቢልም በጥቅሉ ግን የንጉሱ ልብስ ሰፊዎች ለንጉሱ ታይቶ የማይታወቅ ልብስ እንሰፋለን ብለው ተነሱ። ያን ልብስ ማየት የማይችል ሰው በፈጣሪ ርጉም የሆነ እና ኃጢያተኛ ነው አሉ። ንጉሱ ልብሱን ለማየት ቸኮለ። ሕዝቡ ንጉሱ ያን ልብስ ለብሶ ለማየት ቋመጠ። ንጉሱን ልብስ ሰፊዎቹ ለኩት። በወሩ ተመልሰው ልብሱን ይዘን መጣን አሉ። ንጉሱ የለበሰውን ልብስ ሁሉ አሶለቁት። ከያዙት ሳጥን ልብስ እንደሚያወጡ መስለው፤ ከፈቱት። ማንም በዛ ያለ ልብስ አልታየውም። ግን ማን ደፍሮ ይናገራል። ልብሱን ማየት የማይችል ሰው የኃጢያት እና የርግማን ግርዶት ነው ተብሏል። ንጉሱም ልብሱን ማየት አልቻለም። ግን በልቡ ኃጢያተኛ እና በፈጣሪ የተረገምኩኝ መሆን አለብኝ አለ። ንጉሱን ያለበሱት መስለው ተሸከረከሩት። አለበስነው ብለው እልል አሉ። ሁሉም የልብሱን ማማር በአድናቆት ዋው እያለ ገለጸ። የአድናቆት ማዕበል እና ዶፍ ወረደ። ንጉሱ በቤተሰቡ እና በአጃቢዎቹ ተከቦ በአስር ሺዎች ለሚቆጠሩ ሕዝቦቹ ከዚህ አስገራሚ ልብስ ጋር ወደ ሰገነቱ ወጣ። ያን አስገራሚ ልብስ ያየ አንድም የለም። የንጉሱን ሁሉ መላ ከነመላመሉ ግን ሁሉም እያዩ ነው። ግን ሁሉም አስደናቂ ይሆናል ብለው ለተመኘቱ እና ማየት ግን ላልቻሉት ልብስ ከመጀመሪያ ጫፍ እስከ እስከመጨረሻ ጫፍ የአድናቆት ናዳ አወረዱ። በዚህ መኃል በአባቱ ትከሻ ላይ ያን አስደናቂ ልብስ ለማየት እሽኮኮ የወጣ ልጅ ፥ እየሳቀ “ንጉሱ ራቆቱን ነው” አለ። ከዛ ከላይ እስከ ታች ያለው ሕዝብ “ሕጻኑ እኮ ንጉሱ ራቆቱን ነው አለ!” እያሉ ሁሉም ያዩትን፣ የሚያውቁትን እውቀት ለሁሉም ማሰራጨት ጀመሩ። ከላይ እስከ ታች በሕጻኑ አይን ያዩትን የተገለጠ እውነት ማስተጋባት ጀመሩ።



እውቀት ብዙ ዓይነት ነው። አንዱ ግን መጀመሪያ ያወቅነውን ያን እውቀት እንደ ምናውቅ በድፍረት መግለጽ ነው። የታወቀ እውቀት ግን መግለጽ የተፈራ ነገራ ካልታወቀ እውቀት ወይም እውነት ጋር እምብዛም ልዩነት የለውም። ለባለፉት አራት ዓመታት የአሜሪካ ማህበረሰብ ጆይ ባይደን እንዳረጀ፣ የማሰብ እና የማገናዘብ አቅሙ ለሀገር መሪነት ብቁ እንደማያደርገው ያውቅ ነበር። ግን ያን መናገር ለዲሞክራቶች ፓርቲያቸውን መክዳት ነበር የሆነው። ስለዚህ የታወቀውን እውነት ካልታወቀ እውቀት ጋር አቻ አደረጉት። መደበቅ የማይቻልበት ደረጃ ሲደርስ ግን ሁሉም ነገር ከእጃቸው አምልጦ ነበር። በቲቪ ለዓለም በሚታይ መልኩ ከፕሬዝዳንት ትረምፕ ጋር ሲከራከር ትረምፕ “የሚናገረውን ራሱ እንኳ የሚያውቅ አይመስለኝም” ብሎ አሾፈበት። ከዛ ያን የተገለጠ እውነት በሕጻኑ ዓይን አሁን ሁሉም ተቀባበለው። የደረሰውን ውድቀት ግን መቀነስ አልተቻለም።



አሁን ደግሞ ፕሬዝዳንት ትረምፕን ተመልከቱ። ካቢኔው ሲሰባሰብ ሰውዬውን ልክ የአብይ አህመድ ካቢኔ ይመስል አስደናቂ መሪ፣ ባለራዕይ መሪ፣ በአሜሪካ ታሪክ ተፈጥሮ የማያውቅ መሪ፣ ስኬት በስኬት የሆነ መሪ በሚል ነው የሚጀምሩት። በቀደም ለት የቴክ መሪዎችን ሰብስቦ የአፕል ሲኢኦ የሆነው ቲም ኩክ በሦስት ደቂቃ ንግግሩ ትረምፕን ስምንት ጊዜ አስደናቂ መሪ እያለ አመሰገነው። እውነታው ግን የሌበር ዲፓርትመንቱ እንደጠቀሰው ከ2001 ዓ.ም. በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የሥራ አጥ ቁጥር ሪከርድ ደረጃ ዝቅ ብሏል። የአሜሪካ ወዳጅ የነበረችው ሕንድ ከቻይና ጋር ገጥማለች ወይም እየሸሸች ነው። የአሜሪካ ወዳጆች አሜሪካንን እየራቋት ነው። ትረምፕ ሲመጣ ቃል ከገባው የፓናማ፣ የካናዳ እና የግሪን ካርድ ጥቅለላ አንዱም የተሳካ ውጥን የለም። ሀገሪቷ ከመቼውም ጊዜ በላይ ተከፋፍላለች። የኑሮ ውድነት ከባይደን ዘመን በላይ የማይቻል ሆኗል። እውነት ነው ድንበሩ ተዘግቷል። በሕገ ወጥ መልኩ የሚገቡ ኢሚግራንቶች የሉም። ግን ደግሞ የዲፖርቴሽን ሂደቱ ጽንፍ ሄዶ ወንጀል ያለባቸውን ብቻ ሳይሆን ንጹሀንን እና ለኢኮኖሚው ትልቅ አስተዋጽኦ የሚያደርጉትን ሁሉ እያጠቃ ነው። በዚህ ውስጥ ሆነን ነው የንጉሱ ልብስ አስደናቂ ነው የሚሉ የካቢኔ አባላትን የምንሰማው።



በሕይወት እውነትን ግቡ ያላደረገ ሰው የሚያጠፋቸው ጥፋቶች የትየለሌ ነው። ንጉሱ ራቆቱን መሆኑን ሁሉም አይቷል። ያን መናገር ግን ኃጢያተኛ የሚያስብል ከሆነ ወይም ቅጣት ካለው ያን ሪስክ ለመውሰድ ብዙ ሰው አይፈቅድም። መወደድ የመጀመሪያ ግባችን ሲሆን፥ ከሰዎች ጋራ ላለመስማማት እንጥራለን። ሪስክ ከመውሰድ እንሸሻለን። ድንበር ላለመግፋት እንጥራለን። የሌሎች ሰዎች ጥበቃ እስረኛ እንሆናለን።


እውነት ግቡ የሆነ ሰው ከሌሎች ጋር ለመለያየት ብዙ አይፈራም። ሪስክ ከመውሰድ አይሸሽም። ያለ ሪስክ እውነትን መግለጥ አይቻልም እና። ከሁሉም በላይ የሌሎች ሰዎች ፍላጎት እስረኛ አይሆንም።


ይሄ በኛም ግለሰባዊ ሕይወት ውስጥ ያለ ነገር ነው። የምናውቀው፣ ብዙ ዳታዎች ያሉን እውነቶች አሉ። ግን ያን ማወቅ እና መግለጥ አንፈቅድም። ለምን? ከምኞታችን ተቃራኒ ስለሆነ። የምንመኘው እና የምናውቀው ለየቅል ሲሆን፤ ለምኞታችን እንሸነፋለን። ምኞታችን እውቀትን እና እውነትን መግለጥ ከሚፈልገው ክፍላችን በላይ ጠንካራ ነው። ስለዚህ እውነትን በድፍረት የሚነግሩን ሰዎችን በዙሪያችን መክበብ አለብን።



ዛሬ አሜሪካ ውስጥ ስለ ቻይና ያለው አመለካከት ተመሳሳይ ነው። ቻይና በብዙ መንገድ ተመንድጋለች። በብዙ የቴክኖሎጂ ብቃት ከአሜሪካ በልጣለች። ይሄን ማመን ግን የፖለቲካ ሱሳይድ ነው። ስለዚህ ቻይና ሰርቃ ነው፣ አጭበርብራ ነው ወይም ብዙ ደሃ ቻይናዎች አሉ በሚሉ ፕሮፖጋንዳዎች ተጠምደዋል። እውነታውን ማመን ግን ችግሩን ለመቅረፍ የመጀመሪያ መንገድ ነበር። የሰው ልጅ እውነትን መቀበል ዋጋ የሚያስከፍለው ሆኖ ካገኘው፤ ማስደሰትን ይመርጣል።



በዙሪያችን ያሉትን ሰዎች እንገምግማቸው። እውነታን በምንም ዋጋ የሚነግሩን ናቸው ወይስ እኛን ለማስደሰት የሚጥሩ ናቸው። በሚያስደስቱን ሰዎች ራሳችንን ከከበብን የቀን ጉዳይ ነው፤ ከኛ ጋር መሆን አስፈሪ እና የማያስደስት በሆነበት ቀን ጥለውን የሚሄዱ የመጀመሪያ ሰዎች እነርሱ ናቸው። ለዚህ ነው በጆራችን ላይ ሙገሳን ዲቴክት የሚያደርግ ሳይረን ሊኖር የሚገባው። እውነታን ቢመረንም ለሚነግሩን ቀና መንፈስ እና ምቹ ሁኔታን እንፍጠርላቸው። እነርሱ ያድኑናል።




 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 24
  • 3 min read
ree

አንዱ ፍላጎታችን መሉ በኩልሄ መልስ ማግኘት ነው። የትኛውንም ጉዳይ ብንችል በአንድ ሳጥን ውስጥ መክተት እና መረዳት እንፈልጋለን። የምናቃቸውን ሰዎች በምድብ ከፍለን ጥሩ እና መጥፎ ብቻ ወይም ወዳጅ እና ጠላት እንዲሆኑልን እንፈልጋለን። ስለሕይወትም ያለን አረዳድ ሕይወት ትግል ወይም ሕይወት ከባድ እንደሆነ ብቻ ነው። ስለ መንግስትም ሥርዓቶች ያለን ግንዛቤ ጨቋኝ፣ በዝባዣ፣ ፋሺስት ወይም ከኛ የሆነ እና ስህተቱ ይቅርታ የሚባልለት ወይም ነጻ እና ተራማጅ የሆነ ጥቅል ሳጥኖች ናቸው። በመንፈሳዊ ዓለምም የሚድን እና የማይድን፣ ሲዖል ወይም ገነት የሚገባ ብቻ ነው ያለን።


አሁን ላይ በጣም እየተረዳውት የመጣውት ነገር ለሰው ልጅ አዕምሮ ሪያሊትን መረዳት በጣም ከባድ ነገር እንደሆነ ነው። ይሄ ዓለም ከአዕምሮአችን የመረዳት አቅም በላይ በጣም እና እጅግ ውስብስብ ነው። ለምሳሌ ከሰዎች ጋር ስንኖር ግንኙነታችን እከሌ የሚባለው ሰው ሁልጊዜ ጥሩ ስለሆነ አይደለም ወዳጃችን የሚሆነው። ይልቁንስ እኛ የምህረት አቅም ለእርሱ ስላለን ጭምር ነው ወዳጅነት የሚጸናው። ወዳጅ ያልነው ሰው ስለእኛ የሆነ ጊዜ ክፉ ያስባል። እኛም ከዛ ክፋት ነጻ አንሆንም። ከቅናት ወይም ከሌሎች ያልተገናዘቡ ስሜቶች ተነስተን ያን ሰው የሚያሳዝን ባህሪ ወይም ንግግር ልናሳይ፣ ልናወጣ እንችላለን። ለዚህ ነው የምህረት እና የይቅር ባይነት አቅም ያላቸው ሰዎች ብቻ ዘላቂ የሆነ ወዳጅነት የሚገነቡት። እራሱ ውስጥ ያሉትን የክፋት ባህሪዎች እና ሀሳቦች ማስተዋል ያልቻለ ሰው ከሌሎች ጋር ጤናማ ግንኙነት ሊኖረው አይችልም።


ዴቭ ሻፔል ስለ ቢል ኮዝቢ አንድ ያለው ነገር ነበር። ከገደለው ይልቅ ያዳነው ይበልጣል። ከሰዎች ጋር ስንኖር ይሄ ይመስለኛል ውሃ ልኩ። ከሚገለው ይልቅ የሚያድነው ይበልጥ እንደሆነ መጠየቅ። ለብዙ ነገሮች ውሃ ልኩን ማግኘት ነው ወሳኝ። በሕይወት ውስጥም ብዙ ሰዎች የተዛባ ሕይወት የሚኖራቸው ውሃ ልክ ሳይኖራቸው ሲቀር ነው። ወይ አብልጠው ከብዙ ነገር ይልቅ ገንዘብ ይወዳሉ። ወይ ፍጹም አባካኝ ይሆናሉ። ፍጹም የሥራ ፍቅር ይይዛቸው እና ሁሉን ችላ ይላሉ ወይም ሰነፍ ሆነው የሰው ጥገኛ ይሆናሉ። ወይም ፍጹም ሰውን ያምኑና ሲታለሉ ይኖራሉ ወይም ሁሉን ተጠራጣሪ ሆነው ለደስተኛ ሕይወት መሠረት የሆነውን ሰውን ማመን ይሳናቸዋል። በእንግሊዘኛ ይሄ Adjusted ያልሆነ ሕይወት ይባላል።



አጀስት ያልሆነም እውቀት አለ። ሁሉን ነገር በኛ የፕሮፌሽን ዓይን የማየት ብቻ እውቀት። ወይም ጥቂት መጽሐፍ ብቻ በሕይወት ያነበበ ሰው ዓለምን በእነዛ መርሕሆች ብቻ ለመዳኘት እንደሚሞክረው ማለት ነው። በቅርብ የሠላሳ ዓመት ሴት ልጅ ያላት አንድ የሰባ ስድስት ዓመት ነጭ ጋር እያወራን፤ ሴት ልጇ የእርሷን ምክር ለመስማት ምንም ፈቃደኛ አለመሆኗ ገርሟት ታወራኛለች። የስነ ልቦና ባለሙያ ስለነበረች የሴት ልጇ ችግርን ከነ መፍትሔው ታውቀዋለች። ግን መች ለመስማት ፈቅዳ። ሕይወትን ተዋግታ ሕይወትን የኖረች ሴትዮ ፊት ለፊቷ እያለች ሴት ልጇ የርሷ የዓለም ዕይታ የተሻለ ጥራት እንዳለው ታስባለች። አስባ ስኬታማ ብትሆን አንድ ነገር ነው። ግን በሕይወት ከውድቀት ወደ ውድቀት ነው እየሄደች ያለችው።



አንድ ጥሩ የሚያነብ በአስራዎቹ መጨረሻ ያለ የዘመድ ልጅ አለ። ከእኔ ጋር ሲያወራ የእርሱ ፍላጎት የእርሱ የዓለም ምልከታ ትክክል እንደሆነ ለማሳየት ነው ጥረቱ። አንዳንዴ እገረማለሁ። የምገረመው በወጣቶች አዕምሮ ነው። ሁላችንም ያለፍንበት ዓለም ነው። የእኔም የዛ የሃያ ዓመቶቼ አዕምሮ ጭምር ነው የሚደንቀኝ። የሆነ መስመር አንበን ወይም ሰምተን ሁሉን ነገር በዛ የመመዘን ፍጥነታችን እና ከኛ ተለቅ ያሉ ሰዎች የሚያሳዩንን የሕይወት ዝግታ እንደ ሞኝነት የመቁጠራችን ዝንባሌ ማለቴ ነው።



ትልቁ ጥበብ ራስን መግዛት የሆነው ለዚህ ነው። ራስን መግዛት በራሱ እውቀት ሆኖ ሳይሆን ራሱን የገዛ ሰው ብዙ ውሳኔዎችን ማዘግየት ስለሚችል ነው። ያዘገየው ተገዶ ሳይሆን ፈቅዶ ሲሆን ማለቴ ነው። ያን የሚያደርግ ሰው እውነትን ለማግኘት ጥረቱን ስለማያቆም በትግስቱ ውጤቱን ይለውጠዋል።



ሕይወት በነጠላ አትሰራም። እያንዳንዱ ነገር የተያያዘ ነው። አንድ ሰው አንዳች ጥሩ ነገር ሲያደርግ ለኛ በጎ ብቻ አስቦ አይደለም። ለራሱም አስቦ ነው። መጥፎ የሚያደርግም ሰው ለራሱ ብቻ ጥሩ ስላሰበ አይደለም። በዛ ውስጥ የተጎደለ ፍትሕን በራሱ መንገድ ለማሻሻልም በመጣር ነው። በአንድ ጊዜ ብዙ ነገሮች አብረው እንደ ድር ይሰራሉ። ሕይወት ስትሰራ ይሄ ባይሎጂ ነው፣ ይሄ ኬሚስትሪ ነው፣ ይሄ ፊዚክስ ነው፣ ይሄ ቲዎሎጂ እያለች አትንቀሳቀስም። ሕይወት ጭራሽ እነዚህን ክፍፍሎች አታውቅም። ለምሳሌ አንድ መጥፎ ነገር የሚያደርግ ሰው በአንድ ጊዜ የሞራሉ ስንኩልነት፣ የዓየር ጸባዩ መጥፎ መሆን፣ መጥፎ ከማድረጉ በፊት የገጠመው ሕይወት፣ ጥሩ እንቅልፍ አለመተኛቱ በትክክል እንዳያስብ አድርጎት እና ሌሎች ተጨማሪ ጉዳዮች በአንድ ላይ መጥተው ሊሆን ይችላል። ብዙ ጊዜም እውነታው ይሄ ነው። ለዚህ ነው ብዙ ነገሮችን የሚያውቁ ሰዎች በጣም ጥሩ ውሳኔ የመወሰን አቅማቸው ከፍ የሚለው። ምክንያቱም ሪያሊትን በተሻለ የመረዳት አቅም አላቸው እና።


የተገናዘበ ሕይወት ማለት ውጪውን ከመረዳት በላይ ውጪውን የምንረዳበት እና የምናይበትን መንገድ በጥልቀት ማወቅ ነው። በሌሎች ላይ ለመፍረድ እና ለመጨከን የሚሮጥ ሰው ከፈረደባቸው ሰዎች ስብዕና በላይ ስለራሱ ማንነት ይነግረናል። የተገናዘበ ስብዕና ላይ የደረሰ ሰው በውስጡ የሚርመሰመሱ ስሜቶችን ሁሉ ያለ ማፈር እና መሸማቀቅ እውቅና ይሰጣቸዋል። የዚህ ዓለም ዕይታው እና ነገሮችን የመረዳት አቅሙ ከእነዚህ ከውስጡ ከሚመነጩ የስሜት ውጊያዎች ነጻ እንደማይሆን ይረዳል። ዓለሙን የመረዳት አቅሙ ራሱን በተረዳበት መጠን የተወሰነ እንደሆነ ስለሚያውቅ፤ ሪያሊትን የማወቅ ውስንነቱ ገደብ እንዳለበት ያለጥርጥር ይገባዋል። ለዚህ ነው የሕይወት የፍጽማና አቅጣጫ ለሰው ልጅ በባላንስ ብቻ የሚደረስበት የሚሆነው።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page