top of page
Search
Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew


September 2023


የሁለት ሺ ዓመት ታሪክን በሚደንቅ ውበት የሳለ፣ በታላቁ የስዕል ጠቢብ በቪንሰንት ቫን ጎ “ይሄን ስዕል መሳል የቻለ ሰው ብዙ ሞትን ራሱ የሞተ ነው” ተብሎ የተመሰከረለት ፥ በዚህ ምድር ሁሉን ነገር አግኝቶ ያጣ ፥ የ17ኛው ክፍለ ዘመን የደች የምን ጊዜም ምርጥ ሰዓሊ ራምበረንት እና የጠፋው ልጅ ታሪክ።



ራምበረንት በ17ኛው ክፍለ ዘመን የነበረ ታዋቂ ሰዓሊ ነበር። በጊዜው ሀብታም ሰው ሁሉ ለሱ ማንኛውንም ክፍያ ከፍሎ በሱ መሳልን ፥ የሱን የቡርሽ አሻራ በቤቱ ማኖር የሚፈልጉ ሁሉም ከበርቴዎች እና ባላባቶች ነበሩ። በዚህ ዝናው በሚመጣ ሀብት እና ክብር ራምበረንት የጉብዝናውን ወራት ፍጹም በተጋነነ የዝሙት እና የስካር ሕይወት ማሳለፍ ጀመረ። ደንበኞቹን መስደብ እና ማመናጨቅ፣ የጠመዳቸውን ሰዎች ከፍተኛ ገንዘብ ከፍሎ የሚያሳስር፣ የአዕምሮ ሕክምና ጣቢያ ውስጥ የሚያስጨምር ሆነ። ያን ረምበረንት ነበር ዓለም እስከመጨረሻው የሚያውቀው ፥ ለራሱ ክፋት ሁለተኛ ዕድል የሚሰጠው የሰው ልጅ ሌላ ሰው ሲሳሳት እና ሲበድል ቢያየው ግን የወደፊቱን ብቻ ሳይሆን የቀደመውንም ጽድቅ ነው የሚነሳው። ድሮም ሲያስመስል ነበር ይላል። ወደፊትም በጎ ይሰራል ብሎ አይቀበልም።



ራምበረንት ያን ፍርድ ነው ከዓለም ያገኘው። በሉቃስ ወንጌል (15፥12) የምናገኘው ታናሹ ልጅ ልክ እንደ ራምበረንት ከአባቱ ሀብት ተካፍሎ (ጸጋ ወስዶ) ወደ ሩቅ ሀገር ሄደ ይላል መጽሐፍ ቅዱስ። በዚህ የሉቃስ ወንጌል ላይ ጥናት የሰራው የሀርቫርዱ ሄነሪ ኖዌን በየትኛውም የዓለማችን ክፍል ባሉ ማህበረሰቦች ባህል አባት ሳይሞት ፥ ልጅ የአባቱን ንብረት አይጠይቅም ይላል። በሌላ አነጋገር ታናሹ ልጅ ያለው “አባቴ ሆይ አትሞትም እንዴ? የማትሞት ከሆነ ቆሜ አልጠብቅህም” ነው። ሞቱን ተመኝቶ ንብረቱን ተካፍሎት ርቆ ሄደ።



ራምበረንት ይሄን ልቅ ሕይወት ሲመራ የመጀመሪያ ወንድ ልጁን በ1635 በሞት ተነጠቀ። ከመቼውም ጊዜ በላይ ለቀሪ ልጆቹ መራራት እና ከሚስቱ ሳሲካ ጋር በሀዘኑ ምክንያት ቅርበትን ፈጠረ። ራምበረንት ግን የመጀመሪያ ሴት ልጁን በ1638 በሞት ተነጠቀ። ብዙም አልቆየም በ1640 ኮሪኒላ የተባለች ሴት ልጁ በሞት ተለየችው። በዚህ ጊዜ የራምበረንት ዝና እና ክብር ወርዶ ፥ ሕይወቱ መመሰቃቀል ጀመረ። የገንዘብ ዕዳ ውስጥ እየተነከረ መጣ። በዚህ ወቅት ነበር ሚስቱ ሳሲካ የዘጠኝ ወር ልጅ አሳቅፋው በ1642 በሞት የተለየችው። ከልጁ ሞግዚት ጋር ግንኙነት ቢመሰርትም ፥ በክስ እና በመጨረሻም እሷ በአዕምሮ ሕክምና ጣቢያ ውስጥ በሚያሳስር ፍርድ ተጠናቀቀ። ስቶፈል ከተባለች ሴት ጋር ተጋባ ፥ ሁለት ልጆች ወለደችለት። ነገር ግን አሁንም የወለደችለት ወንድ ልጁ በ1652 ሞተበት። በዚህ ወቅት ቤቱ እና ስዕሎቹ ሁሉ በሀራጅ ተሸጡበት። በዚህ ሰዓት የሳላቸው ስዕሎች በጣም ልዩ እንደሆኑ እና “ሰውን እና ተፈጥሮን በሚደንቅ መነጽር ማየት የጀመረበት፣ ከዚህ በፊት በስዕሉ የሚታዩ ውጪያዊ ጫጫታዎች የራቁት ነበሩ” ይላል ስለሱ የጻፈው ጃኮብ ሮዘንበርግ። ሁለተኛ ሚስቱ በ1663 ሞተችበት። ከዓምስት አመት ቆይታ በኋላ ራምበረንት ከመጀመሪያ ሚስቱ የወለደው ብቸኛ ወንድ ልጁ እና በጣም የሚወደው ቲተስ ሞተ። ራምበረንት በዚህ ወቅት ነበር ፥ ቡሩሹን አንስቶ ማንም ስሎት በማያውቀው ጥልቀት የጠፋውን ልጅ ታሪክ የሳለው።



የእርያዎችን አሰር መብላት ሲከለከል የአባቱ ቤት ሕይወት እንደታወሰው የጠፋው ልጅ ብቻ አይደለም ራምበረንት አሁን እግዚአብሔርን ያወቀው። ይልቁስ በጠፋው ልጅ ታሪክ የተሰወረውን የአባት ፍቅር ነበር ራምበረንት በስዕሉ አውጥቶ ያሳየው። የጠፋው ልጅ ልሂድ ሲል ፥ እንደ ወላጅ “አትሂድ አላለውም” ያ አባት። ታናሹ ልጅ ለመሄድ የሚያስፈልገውን ሁሉ ሰጠው እንጂ። ከዚህ ቤት ውጪ ደስታ እንደሌለ ቢያውቅም ፥ ደስታን ከአባቱ እቅፍ ውጪ ለፈለገች ነፍስ በዓለም የሚያስፈልጋትን ሁሉ ሰጥቶ ሸኛት። ያ ሀብት እንደሚያልቅ፣ መቁሰል እና መጎዳት እንዳለ ቢገነዘብም ፥ ያ አባት ግን አደጋን ለመጋፈጥ ለፈቀደች ነፍስ ነጻነትን ሰጣት። ራምበረንት “ታናሹ ልጅ ከአባቱ ቤት ሲሄድ ብቻ ሳይሆን ወደ አባቱ ቤት ሲመጣም አባቱን እንዳላወቀው ስለገባው” ነበር ፥ የጠፋውን ልጅ ጭንቅላት የሕጻን ልጅ ሰውነቱን የአዋቂ አድርጎ የሳለው። አባቱ ቤት ሲመለስ ንግግር እየተለማመደ፣ ምን መናገር እንዳለበት እያሰበ ነበር የመጣው። የሱ ንግግር የአባቱን ልብ የሚያራራ መስሎት። ከእግዚአብሔር ፍቅር በላይ የኛ ቃላት ፍቅር የተሸከሙ ይመስለናል። አባቱ ግን ገና ሩቅ ሳለ አዘነለት። ልጁ ንስሐውን ሳይጨርስ አባቱ ልጁን አለበሰው፣ እጁን በቀለበት እግሩን በጫማ አሳመረው።



ራምበረንት ወደ እግዚአብሔር መንግስት እንደ ልጅ ካሎናችሁ አትገቡም የሚለውንም አሳየን።የጠፋውን ልጅ ጭንቅላት ከማህፀን የወጣ ጭንቅላት አስመስሎ ስሎ። አባቱን ሁለት ዓይነት እጆች ያሉት፥ የሴት እና የወንድ አድርጎ ሳለው። እንደምንጎዳ እያወቀ ለነጻ ፍቃዳችን እሺታውን የሚሰጥ አባት (ልቤ ጨከነ እንዳለ ዳዊት)፥ ስንመለስ ደግሞ በፍቅር ሮጦ የሚቀበለን እናት ነው እግዚአብሔር። ራምበረንት ግን ታላቁንም ሳለው። በውስጥ ሳለ የጠፋውን ፥ ከጠፋው ይልቅ በውስጡ መራራነትን ያዘለውን። ከወንድሙ መዳን ይልቅ የሰባው ፍሪዳ መታረድ ያስጨነቀው ፥ መመለሱ ሳይታወቅ ታሪኩ የተጠናቀቀው ታላቁ ልጅ። ባለፈው ዓመት በሀገራችን ያየነው ይሄን የታላቁን ልጅ ማንነት ነበር።



ታላቁ ልጅ በልቡ በታናሹ ልብ ውሳኔ የሚደሰት ሰው ነበር። የሚጠብቀው አባቱ ሞቶ ታናሹን ማስቀናት፣ ከሱ የበላይ ሆኖ መኖር ነበር። ሁልጊዜ ከአባቱ ጋር መሆኑ አላስደሰተውም ፥ የሚጠባበቀው አንድ ቀን የአባቱን ሁሉን መውሰድ እንጂ። ስለዚህ ከአባቱ ምንም እንዳይጎድል በስስት ይጠብቅ ነበር። የክህነት ቀሚስ ገድቧቸው እንጂ እንደታናናሿቹ መጋደል ያማራቸው፣ ታናናሾቹ ሲታረቁ ሞተን እንገኛለን ብለው የአባታችንን ቤት ቆልፈው የሄዱ ታላላቆችንም ያየነው ባለፈው ዓመት ነበር።



ለምን እንደሆነ አላውቅም ፥ ስለራምበረንት እስከማውቅ ድረስ የጠፋው ልጅ ያባከነው ‘ገንዘብ እና ጸጋ’ ብቻ ነበር የሚመስለኝ። ለካ ሁሉም ነገር ስጦታ ነው። ማለትም ራምበረንት ልጆቹን እና ሚስቱን አጣ ፥ እነዚህ ሁሉ የእግዚአብሔር ስጦታ ነበሩ። ኢዮብ ልጆቹን እንዳጣ፣ ኑኃሚን ከባሏ እና ከሁለት ልጆቿ ጋር ከእስራኤል ወጥታ ፥ ባሏን እና ሁለት ልጇቿን አጥታ ባዶ እጇን እንደተመለሰች ፥ የሚወሰደብን ነገር ምን እንደሆነ አናውቀውም። ሁሉም ግን የሱ ስጦታ ነው። ከሱ በተለየን መጠን የሚጠፉ ፥ የሚባክኑ፣ የሚያልቁ ናቸው።



ራምበረንት የመጨረሻ ልጁን ባጣ በሁለት ዓመት ውስጥ እሱም ሞተ። በሉቃስ ወንጌል 2፥28 እንደምናገኘው ስምዖን “እርሱ ደግሞ ተቀብሎ አቀፈው እግዚአብሔርንም እየባረከ እንዲህ አለ። ጌታ ሆይ፥ አሁን እንደ ቃልህ ባሪያህን በሰላም ታሰናብተዋለህ”፤ ራምበረንት በክርስቶስ እቅፍ ውስጥ በመጨረሻ አረፈ። ከሩቅ ያየው አምላኩ ከሱ ብዙ አልጠበቀምና ወደራሱ ሰበሰበው። የራምበረንት የመጨረሻ ስዕልም የነበረው ይሄ የአዛውንቱ ስምዖን ነበር። "አሰናብተኝ ፥ ነፍሴ የተጠማችሁን በመጨረሻ አየውት" የሚለው የአዛውንቱ የስምዖን ስዕል ነበር የራምበረት ፍጻሜ።



አዲሱ ዓመት ወደ ልቦናችን የምንመጣበት ዓመት ይሁነን። የእግዚአብሔር ፍቅር ይግባን። እሱም ወንድምን ከፍሪዳዎች በላይ መውደድ እና አባታችን እኛን በፍጹም ፍቅሩ እንደሚወደን ማወቅ ነው። “ይሄ የምወደው ልጄ ነው” የሚለው ድምጽ ከእርሱ ጋር ሕብረት ቢኖረን ለኛም ነው። የፈረድንባቸው እና ከመጠን በላይ የምንጠላቸው ሰዎች ሁሉ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸው። የሰባውን ፍሪዳ የሚያርድላቸው፣ አንባር የሚያጠልቅላቸው ፥ ጫማ የሚያደርግላቸው አንገታቸውን አቅፎ የሚስማቸው ናቸው። ይሄን ስናውቅ በወንድሞቻችን ላይ ጥላቻ ሊኖረን እንደምን ይችላል? ይሄ ፍቅር ካለበትስ ቤት ወዴት እንሄዳለን?

89 views0 comments
Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew




“ማርታ ግን አገልግሎት ስለ በዛባት ባከነች፤ ቀርባም። ጌታ ሆይ፥ እኔ እንድሠራ እኅቴ ብቻዬን ስትተወኝ አይገድህምን? እንኪያስ እንድታግዘኝ ንገራት አለችው።


 ኢየሱስም መልሶ። ማርታ፥ ማርታ፥ በብዙ ነገር ትጨነቂአለሽ ትታወኪማለሽ፥


 የሚያስፈልገው ግን ጥቂት ወይም አንድ ነገር ነው፤ ማርያምም መልካም ዕድልን መርጣለች ከእርስዋም አይወሰድባትም አላት።” ሉቃ 10፥41፡42።



ይሄን ታሪክ ሳነብ ትዝ የሚለኝ ሴኒካ ለሉሲለስ ወዳጁ የጻፈለት ደብዳቤ ነው። እንዲህ ይለዋል “ሉሲለስ ሆይ ካንተ የሚወሰድብህ ነገር ሁሉ ያንተ አይደለም። ያንተ ባልሆነ ነገር መደገፍን አሶግድ።” ጌታችን ለማርታ “ማርያም የማይወሰድባትን መረጠች” ይላታል። መንገድ ላይ ቆመው የሚለምኑ ሰዎችን ሳይ በእኔ አዕምሮ ስለተወሰደባቸው ሀብት እና ክብር ሳይሆን የሚያስበው፤ ስላልተወሰደባቸው ድፍረት ነው። ኑሮን የመቀጠል ድፍረት። በሕይወት የመኖር እና የመቀጠል ጀግንነት።



በያንዳንዱ ቀን ያለኝ ብርታት ሰዎች ከኔ ሊወስዱብኝ የማይችሉት ነገርን ገንዘብ ባደረኩኝ መጠን ነው። ከአምላኳ እግር ሥር ቁጭ ብሎ ማረፍን ማንም ከማርያም የሚወስድባት አይኖርም። ለዛች ነፍስ የክብር ቦታ፣ VIP ወይም ፊትለፊት ላይሰጣት ይችላል። ታላቅ አስተዳዳሪ፣ ታላቅ ሰባኪ ወይም ታላቅ ምናምን ብለው ላይጠሯት ይችላሉ። ግን ከክርስቶስ እግር ሥር ቁጭ ብሎ ፍጹም መደሰትን ማንም አይነጥቃትም።



ከሁለት ዓመት በፊት ውድ ፍራሽ ለጥሩ እንቅልፍ እንዲሆን ገዛው። ግን በሚገርም ሁኔታ ፍራሹን የገዛው ቀን ምንም እንቅልፍ ሊወስደኝ አልቻለም ነበር። በጠዋት ዳውን ታወን ወዳለው ቢሮዬ ልገባ ስል ከሕንጻው ሥር፤ ሰዎች በፍጥነት በሚራመዱበት ሥፍራ አንዱ አስገራሚ እንቅልፍ ተኝቷል። ውድ ፍራሽ አልነበረውም እንቅልፍ ግን ነበረው። ለአምስት ደቂቃ የሚሆን ጊዜ ቆሜ አየውት። የአስር ሺር ዶላር አልጋ ሊኖርህ ይችላል፤ እንቅልፍ ከሌለህ ግን ትርጉም የለውም። ያን እንቅልፍ ፍራሽ እምብዛም አይሰጥህም። ቅዱስ ጳውሎስ እና ሲላስ በእስር ቤት ሆነው በፍጹም ደስታ ይዘምሩ ነበር። በዓለም ላይ ተፈተው ያሉ ሰዎች ግን ያ ደስታ አልነበራቸውም። ጳውሎስ እና ሲላስን በእግረ ብረት ሆኖ መታሰር ያን ደስታ ሊቀማቸው አልቻለም። የማይቀሙን ነገር አለን?



ሰዎች የማይወስዱብን ነገሮች አሉን?


 ትረምፕም ሆነ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ የማይቀሙን ነገሮች ይኖሩን ይሆን? እኔ ስለሃይማኖት ወይም በዛ ውስጥ ያሉ ሰዎች ስለሚገባቸው ነገሮች ብቻ እየተናገርኩኝ አይደለም። በጣም ብዙ ድንቅ ሰዎችን በሕይወት ተገናኝቻለው። ማንም የማይወስድባቸው ደግነት፣ መረጋጋት፣ ትህትና፣ እውቀት፣ ማስተዋል፣ ጥበብ፣ ስክነት ያላቸው ሰዎች። መክሰርም ሆነ ማግኘት ምንም ያልነቀነቃቸውን ሰዎች አይቻለው። አንዳንዶቹ ምንም ሃይማኖት የሌላቸው ነበሩ። እነዚህ ማንም የማይቀማቸው ውበት የነበራቸው ሰዎች ነበሩ።



ማርታ ጌታን ለማስደስት በጓዷ ትተጋ ነበር። የጌታ መደሰት በማርታ እጅ ላይ የነበረ አልነበረም። በርሷ ቁጥጥር ውስጥ አልነበረም። እርሷ ግን ብዙ ለፋች። ብዙ ተጨነቀች። ማርያም ደግሞ ነፍሷን አደመጠች። ያ ውብ ጌታ እግር ሥር መቀመጠ እርሷን እንደሚያስደስታት ገባት። ስለዚህ አደረገችው። የእርሷ ደስታ ግን በእጇ ነበር። ጌታ ስለመደሰቱ ሳይሆን የእርሷ ነፍስ ስለማረፏ አሰበች። ያን ራስን ማወቅ ከእርሷ ማን ይወስድባታል?



 ሊዮ ቶልስቶይ ስለመደሰት ሲናገር በጣም ቀላል መርህ ነው ያለው። “መደሰት ትፈልጋለህ?” “እንግዲያው ደስተኛ ሁን!” ብቻ ነው የሚለው። ብዙዎቻችን መደሰት ብንፈልግም ደስተኛ የሚያደርገንን ነገሮች ግን አይደለም የምንሰራው። ይልቁንስ ክብር፣ ቦታ፣ ዝና፣ ኢጎ፣ አዋቂ መስሎ መታየት፣ ከቡድን የመነጠል ፍርሃት፣ እንደ ማርታ ሰው ምን ይለኛል የሚል ጭንቀት እና ሌሎች ስሜቶች ነው የሚያስተዳድሩን። የሚቀሙን ነገሮችን ብቻ ነው የምንሰበስበው። ክብር እንደ ጥላችን ነው። አንዳንዴ ከኛ በላይ ትልቅ ነው። አንዳንዴ ከኛ በጣም የሚያንስ ነው። ምክንያቱም የኛ አይደለም።



 የማርታ ሃብቶች ሊወሰዱብን የሚችሉ ናቸው። አያስፈልጉም ሳይሆን ብዙ መትጋት ያለብን ግን የማርያም ሃብቶች እንዲበዙልን ነው። የማርያም ሃብት ያለው ሰው የማርታ ሃብትን በሂደት ገንዘቡ ማድረግ ይችላል። የማርታ ሃብት ያለው ሁሉ ግን የማርያም ሃብት አለው ማለት አይደለም። በማንኛውም እና በየትኛውም ቦታ ብንሆን ቀና ብለን የምንሄድበት ጥበብ አለን? በሁሉም ስፍራ አሸናፊ የሚያደርገን ማንም የማይነጥቀን ሰውነት አለን? ያ በማዕበል እና በወጀብ መኃል ቀና እንዳልን የሚያስኬደን ውሳጣዊ ሃብቶች አሉን? የማርያም ሃብቶች።



መስቀል የበዛባቸውን ሰዎች አላያችሁም? ግን ከፊታቸው ይሄ ሕይወት ውብ ነው የሚል ደስታ የማታጡባቸው! ሲመሽ ደስ የሚላቸው ሲነጋም ፀሐይዋን በድጋሚ አወጣት ብለው የሚደሰቱ ሰዎች። ሉሲለስ ሆይ ካንተ የሚወሰድብህ ሁሉ ያንተ አይደለም። አንዳንድ ሰዎች አልገጠሟችሁም? “ወፈርኩኝ አይደል?” ብለው ጠይቀዋችኹ፤ “አዎ” ስትሏቸው የሚያኮርፏችሁ? በሕግ ትምህርት ቤት እያለሁ፤ አንድ ከእንግሊዝ የመጣች ተማሪ ነበረች። ፊቷ በርበሬ መስሎ አንድ ቀን እኔ የማጠናበት ክፍል ከጓደኞቿ ጋር መጣች። “ፊትሽ ምን ሆኖ ነው?” ስላት (እንግዳ ስለሆነብኝ ነበር)፤ አበደችብኝ። ጓደኞቿም “ያን መጠየቅ አልነበረብህም” አሉኝ። ምን አልባት ልክ ናቸው። ግን ተመልከቱ ምን ያህል insecure እንደሆነች! በሽበት፣ በቁመት፣ በእርጅና እና በሌሎች ጉዳዮች እንዲህ የሚሰማን ሰዎች ሞልተናል። የማርታ ሃብቶች ብቻ ያሉን። ማርያም ግን የማይቀሟትን መረጠች።



ሊወዱን ሊጠሉን፣ ለጊዜው ሊያከብሩን ወይም ሊሰድቡን ይችላሉ። ይሄን ሁሉ እንደ ኢምንት ቆጥረን ፥ ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድኅን እንዳለው በዚህ የሙገሳ እና የስድብ ውርጅብኝ ውስጥ ዝም የምንል ምን ያህሎቻችን ነን? የማይቀሙን የውስጥ ጽናት ያለን? የመንፈስ ቅስማችን የማይወሰድብን ምን ያህሎቻችን ነን? የማይቀሙንን እንያዝ። የማይወስዱብንን ገንዘብ እናድርግ። “ሉሲለስ ሆይ ካንተ የሚወሰድብህ ነገር ሁሉ ያንተ አይደለም።”

465 views4 comments
Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew


 

ሙያተኛ ስትሆኑ ሰዎች በእናንተ ላይ ሊደገፉ ይፈልጋሉ። የመጨረሻውን ውሳኔ እናንተ እንድትሰጡላቸው ይመኛሉ። ግንበእውቀት እና በልምድ ከፍ ስትሉ እርግጠኝነት የእውቀት እና የልምድ እጥረት ውጤት መሆኑን ታውቃላችሁ። ስለዚህ ያን የበለጠ ታሶግዳላችሁ። ከእናንተ በእውቀት የሚያንሱ ሰዎች ያን እርግጠኝነት ሲያጡ ፥ ከእውቀት እና ልምድ ጋር ያያይዙታል። ስለዚህ ለአጭበርባሪዎች ወይም ላነሰ እውቀት ላላቸው ይሰጣሉ።

 

ወደ ጌታችን የፍጻሜ ዘመን ስብከት ሂዱ። ከሁሉ አዋቂ አባቱ ዘንድ የመጣው ልጅ ፥ ስለፍጻሜው ዘመን ምልክት እንጂ እርግጠኝነት በርሱ ቃላት ውስጥ አልነበረም። ያ በእውቀት ማነስ የመጣ ግን አልነበረም በእውቀት መብዛት እንጂ።ከርሱ እውቀት ጋር የማይነጻጸሩት የሐዋርያትን የፍጻሜ ዘመን ስብከት ደግሞ ተመልከቱ ፥ “ጌታ አሁን ይመጣል” ነበር ያሉን። ምንአልባትም በእነርሱ የእድሜ ዘመን ወይም ከእነርሱ በጥቂት ዘመን ተሻግሮ ክርስቶስ እንደሚመጣ ይሰብኩ ነበር። ያም እርግጠኝነት በተሞላበት መልኩ ነበር። ያ ግን አልሆነም። ከሦስት ሺ ዘመን በኋላም ያን ክስተት እየጠበቅን ነው። በሌላም ዘርፍ እርግጠኝነት አንድን ነገር በጥልቀት የመረዳት እጥረት ነው።

 

ሪስክ የሚወስዱ ሰዎች ናቸው በብዛት የሚያተርፉት። በተመሳሳይ ሪስክ የሚወስዱ ሰዎች ናቸው የሚከስሩት። አሉታዊያን በሕይወት ላይ ብዙ ጊዜ ልክ ናቸው። አዎንታዊያን ግን በሕይወት ደስተኛ ናቸው። ምክንያቱም እነሱ የማይቻል የነበረውን የሚቀይሩ ናቸውና። እርግጠኝነትን መፈለግ የውሳኔ ሽባነትን ያመጣል። ሕይወት ልንሞክራት፣ የማይቻል የሚመስለውን ነገር ፈራ ተባ እያልን ልንገፋው የተሰጠን ስጦታ ናት። ይሄ ሕይወት አንድ ብቸኛ ዕድላችን ናት። አንድ ብቸኛ ዕድል ከዚህ በፊት የነበሩ ሰዎች ባስቀመጡልን ሥሪት ብቻ በመመራት ማለቅ የለበትም። ትንሽ ድንበሮችን መግፋት፣ ትንሽ የተገነቡ ነገሮችን አፍርሶ በተሻለ ለማቆም የምንጥርበትም መሆን አለበት። ለዛ ደግሞ ከእርግጠኝነት ይልቅ የመሆን ዕድልን (probability) ነው ማጤን ያለብን። የመሆን ዕድሉ ከፍ ያለን ነገር እርግጠኛ ስላልሆንን ብቻ ማቆም የበጎ ለውጥ መቅሰፍት ነው።

 

አንገት የሚያጎነብሱ ሰዎችን ሳይሆን አንገትን ቀና የሚያደርጉ ትውልዶችን ስለማፍራት ነው ማሰብ ያለብን። በሆነ መጠን በእውቀት እና በድፍረት እንቢ የሚሉ ሰዎች ብቻ ናቸው ድንበር የሚሻገሩ፣ አይቻልም የሚባሉ ተግባሮችን አስችለው ያሳዩን። እነዚህ ሰዎች እርግጠኝነት ደባሪ የሆነባቸው እና መሞከር የሚያረካቸው ናቸው።

 

ስለሚመጣው ነገር በርግጠኝነት የምናውቅ ቢሆን፤ ሕይወታችን ከሕይወት የተላቀቀ ይሆን ነበር። መደነቅ እና ደስታ የጎደለው፣ መደንገጥ እና መረበሽ የራቀው ፥ መሳቅ እና መቦረቅ የሸሸው ይሆን ነበር። አለማወቅ ነው ተራራ ጫፍ የወሰደን። አለማወቅ ነው ያስወደደን ያስከዳን። እርግጠኝነትን የሚሰጠን ሁሉ ከእውነትም ከሕይወትም የተጣላ ነው። ወይም የኛን ደካማ ጎን ለጥቅሙ የሚያውል ነው። በዚህ ዓለም ላይ ሞት ሳይቀር እርግጠኛ እንዳልሆነ ፥ ሔኖክ እንዳልሞተ መጽሐፍ ቅዱስ ሲነግረን እናያለን። እንደ ብራየን ጆንሰን ያሉ ሰዎች የሞትን እርግጠኝነት እየተጋፉ ነው። ምን አልባት ይሳካላቸው ይሆናል፤ ግን ይሄ ድንበርን መግፋት ነው የሰው እውነተኛ ተፈጥሮ። ማመጽ የሰው ልጅ ተፈጥሮ ነው። የሚጠቅመው ቢሆን እንኳ የሆነን ነገር በአታድርግ ትዕዛዝ መቀበል እንደማይፈልግ የመጀመሪያው ሰው አሳይቷል።

 

ውሳኔ ስንወስን የማይታወቅ ሪስክ ካለው ልምድ እና እውቀት ላይ እንደገፍ፤ የሚታወቅ ሪስክ ከሆነ ደግሞ የመሆን ዕድል (probability) እና አመክንዮ ላይ እንመርኮዝ። እንጂ ከእርግጠኝነት ወዳጅ አንሁን።

 

353 views0 comments

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page