top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 4 min read

የሰንበት ዕይታ - 3

ree

ካርል ማርክስ እና ሼክስፒር በዚህ ጉዳይ ይለያያሉ። ካርል ማርክስ ሰዎች የሚጣሉት ስለሚለያዩ ነው ይላል። የተለያዩ ግቦች፣ ፍላጎቶች፣ አይዶሎጂ፣ የተለያየ ቁሶች ስላላቸው ነው የሚጣሉት ይላል። ሼክስፒር ግን በሮሚዮ እና ጁሊየት እና በሌሎችም ሥራዎቹ እንደገለጠው ሰዎች የሚጣሉት ስለሚመሳሰሉ ነው ይላል። እኔ ሼክስፒርን በሙሉ ስቀበል ፥ ካርል ማርክስን ደግሞ በከፊል ልክ ነው እላለው።


ብዙ ጊዜ የምንቀናው ከኛ በሀብት እና በንብረት ወይም በሆነ ነገር የሚመሳሰለንን ሰው እንጂ ከኛ በጣም በራቁ ሰዎች አንቀናም። በቢልጌት ወይም በኤለን መስክ እኛ አንቀናም። የምንቀናው ልንደርስበት በምንችለው ወይም አብሮን ከኛ ጋር በነበረ ሰው ነው። ቃዬል በአዳም አልቀናም በመንታ ወንድሙ አቤል እንጂ። ኤሳው በያዕቆብ ፥ የዮሴፍ ወንድሞች ከኛ እሱ በምን በልጦ ነው ብለው በወንድማቸው ዮሴፍ፣ አሮን እና ማርያም በወንድማቸው በሙሴ ቀኑበት ይላል። ይሄ ሁሉ የሚያሳየን ሰዎች የሚጠላሉት ስለሚመሳሰሉ ነው። ኢትዮጵያ ውስጥም በጣም በሚቀራረቡ ብሔሮች መካከል ነው ጥላቻ እና ግጭት ያለው። በትግራይ እና በአማራ፣ በትግራይ እና በኤርትራውያን፣ በኦሮሞ እና አማራ (በቁጥር ስለሚቀራረቡ)፣ በወላይታ እና በሲዳማ፣ በአኝዋክ እና ጉምዝ፣ በኑዌር እና ዲንካ እያለ ይቀጥላል። በዓለም ላይም ጥላቻ እና ግጭት በሚቀራረቡ መካከል እንጂ በሚራራቁ መካከል ጠብ የለም።


የሦስተኛው ክፍለዘመን የመጽሐፍ ቅዱስ ሊቅ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ ሙሴን ለመከራ የዳረገው የሚራራቁት የዕብራውይ እና የግብጻዊ ጠብ ሳይሆን በሁለት ወንድማማቾች ዕብራውያን ጠብ ነው ለስደት የተዳረገው ይላል። ይሄንንም ሲገልጽ የሚለያዩ ነገሮች ጠብ ቀላል እና ውጪያዊ ነው ስለዚህም መገላገል ቀላል ነው ይላል። የሚመሳሰሉ ሰዎች ወይም የወንድማማቾች ጠብ ግን የመረረ ነው ፥ ለዚህም መገላገል እጅጉን ከባድ ነው። ይሄንንም ሲያጠቃልል እንዲህ በሚል ዘመን ተሻጋሪ አባባል ነው የዘጋው “ማንም ሰው ተቀናቃኙ በእርሱ ላይ የድል ኃይል እንዳለው ምልክት ካላገኘ በቀር በእርሱ ላይ ሐዘን አይሰማውም። ” ይሄ ማለት ሰው በሕጻን ልጅ ስድብ አይናደድም ፥ አቻው ወይም ወዳጁ ሲሰድበው ነው የሚናደደው። ማናችንም ተቀናቃኝ የምንላቸው አቻዎቻችንን ነው። በሞተ ሰው ወይም ከኛ በብዙ በሚያንሱ እና በብዙ በሚበልጡ ላይ ንዴት የለንም።



ካርል ማርክስ ደግሞ ያስተዋለው ሰዎች ለግጭት የሚሰጡትን ትንታኔ ነው። አዎ ማንም ሰው ግጭት ውስጥ ሲገባ “ስለቀናው ነው፣ እሱ ያለውን ስለተመኘው ነው፣ እሱን ስለተፎካከርኩት ነው፣ እሱ እንዳይደርስብኝ ነው” አይልም። ምክንያቱም ይሄ ግጭቱን ምክንያት ያሳጠዋል ፥ ተከታይ እና ደጋፊን ይነሳል። ለራሳችንም እንደዛ ብለን ማመን አንፈልግም።


የዚህ ጹሁፍ ዓላማ ምንድነው?


ብዙዎቻችን እንቀናለን ፥ የምንቀናው ደግሞ በጎረቤታችን ወይም በብዙ በሚመስለን ነው።(መጽሐፍም ባልጀራን ውደደው ያለው ፥ ባልንጀራን መውደድ ከባድ ስለሆነ ነው።)ይሄን ለማወቅ ከፈለጋችሁ ዓይናችሁን ጨፍናችሁ ስኬታቸውን ስትሰሙ ወዲያው ደስታ የማይሰማችሁ ሰዎችን አስተውሉ። ወይም በሆነ ነገር ከናንተ ሊያንሱ የሚችሉበትን ነገር ሲያገኛቸው ደስ የሚላችሁ ሰዎች እነማን ናቸው? እነዚህ ሰዎች በብዙዎቻችን ሕይወት ውስጥ አሉ። በእህት እና ወንድም ወይም በእህትማማቾች፣ በጣም በቅርብ ጓደኞች መካከል ነው ባብዛኛው የሚኖረው። ይሄ ስሜት ሲመጣብን ፈጥነን ለማውገዝ አንቸኩል። ይሄ ስሜት ከጥንት ጀምሮ የነበረ ነው። ረጋ ብለን ለምን እንደዛ እንደተሰማን እንጠይቅ፣ እኛ ከቁስ እና ከውድድር በላይ የራሳችን ውበት እንዳለን እናስተውል። ሕይወት ለእያንዳንዳችን የተለየች ናት። ስለዚህ ከዚህ ዓለምም የምናገኘው ነገር እንደዛው የተለያየ ነው። የሌላው ስኬት ሁልጊዜ ለኛ ሊጠቅም ስለሚችልበት ነገር እናስብ። እንድንፎካከራቸው ከሚጋብዙን ሰዎች በብዙ ኬሎሜትር እንራቅ። እንደዛ ስሜት ከሚሰማን ሰዎች ወይም እንዲሰማን ከሚያደርጉን ለጊዜው እንሽሽ ፥ የራሳችን ሕይወት ላይ እናተኩር። ከዛ በተረፈ ግን የምንቀናባቸው ሰዎችን ከኛ መነጠል የማንችል ከሆነ ፥ በተቻለ መጠን በጎ ነገራቸው ላይ ለማተኮር እና ሆን ብለን ለመርዳት እንሞክር። በእነሱ ፊት ላለማስመሰል እንጣር።


የምንቀናባቸው ነገር የምናደንቅላቸው ነገር ስለሆነ እኛ ያ ነገር ቢኖረን እንደምንመኝ እና በዛ ነገራቸው እንደምንቀናባቸው እንንገራቸው። ያ የሚያሳፍር ቢመስለን እንኳ በውስጣችን ያለውን መጥፎ የፉክክር ስሜት ግን ይገለዋል። ስለዚህ ራሳችንን እናድናለን።


በተጨማሪም ቅናት ምን ያህል ፍትሐዊ ስሜት እንዳልሆነ እንገምግመው። ምክንያቱም የምንቀናበትን ሰው ሁሉ ነገሩን አንፈልግም። ያ የምንቀናበትን ጥቂት በጎ ነገር እንጂ። ለምሳሌ የስቲቪ ጆብ (የአፕል ስልክ መስራች) ጓደኛ ሆነን በሱ እንቀናለን እንበል። የምንቀናው በሱ ስኬት ብቻ እንጂ፤ ፈጣሪ ስቲቪ ጆብን ላድርጋችሁ ቢለን ማናችንም እንቢ ነው የምንለው ምክንያቱም ከ40ዎቹ ዕድሜው ጀምሮ በካንሰር በሽታ የተሰቃየውን በ56 ዓመቱ የሞተውን ስቲቪ ጆብን ማናችንም መሆን አንፈልግም፤ የፈለግነው ያ ስኬቱን ብቻ ነው። ሕይወት ግን እንደዚያ አየሰራም። ልጅን ወዶ ንፍጡን ተጠይፈን አይሆንም እንደሚባለው፤ ቅናት እንደዛ ነው። ልጁን ያለንፍጡ መፈለግ። ለዚህ ነው ፍትሐዊ ስሜት እንዳልሆነ እና እኛ የምንቀናበት ሰው የሌለው ውበት በኛ ሕይወት ውስጥ እንዳለ ማየት ያለብን። ይሄ ማለት ግን የኛ ሕይወት ከዛ ሰው የበለጠ ነው ማለት አይደለም። የተለየ እና የራሱ ውበት ያለው ነው ለማለት ነው። ቅናት ግን ይሄን ውበት ያጨልመዋል። ለምሳሌ ሙዚቀኛው ሙሉቀን መለሰ በጥላሁን ገሰሰ ይቀናበታል ይባላል። ያ እውነት ነው እንበል። ሙሉቀን ግን የጥላሁን ገሰሰን ሕይወት ይሰጥኽ ቢባል ፍቃደኛ አይሆንም ምክንያቱም የጥላሁን ሕይወት አንገት መታረድ፣ እግር መቆረጥ፣ በጊዜ መሞትም አለበትና። ለዚህ ነው ቅናት የህሊና ፍትህ መታወር ውጤት የሆነው።



ሌላው የዚህ ጹሁፍ ዓላማ ፥ ወደ ግጭት ስንገባ እንደግለሰብም ሆነ እንደተቋም እና ሀገር ራሳችንን መጠየቅ ያለብን “የሄ ግጭት ከመመሳሰል ከመጣ ቅናት ወይስ ስትራቴጂክ ፍላጎቴን የሚጠቅም ግጭት ነው?” ብለን ነው። ድፍረት አይሆንብኝ እና ከ90% በላይ የሚሆኑት ግጭቶች የቅናት ውጤቶች ናቸው። በዚህም ከመመሳሰል የመጣ፤ የረጅም ዘመን (long-term) ጥቅማችንን ያላማከለ፣ ስሜት የሚነዳው እና በመጨረሻም ሁሉንም ለከፋ ውጤት የሚዳርግ ነው። ምክንያቱም ቅናት ሌላው የሚያጣ ከሆነ በራሱ ማጣት ሀዘን አይሰማውም። ቅናት ሌላው ሁለት ዓይኑን የሚያጣ ከመሰለው የራሱን አንድ ዓይን አሳልፎ ለመስጠት የሚፈቅድ ነው። ቅናት እንደጥንብ አንሳ የሌሎች መቀርናት የሚስበው ፥ መልካም ጠረናቸው የሚገለው ነው። በሚገርም ሁኔታ እንደ ኮሚኒዝም ያሉ የፖለቲካ ፍልስፍናዎች ሳይቀር በቅናት ሞተርነት የተንቀሳቀሱ ድሃውን ከበርቴ ማድረግ ሳይሆን ከበርቴውን ድሃ በማድረግ የተጠናቀቁ ነበሩ። ጥቂቶች በእነዚህ ሥርዓቶች የተደሰቱት ሃብታም ስለሆኑ ሳይሆን ሌሎችን ከእነሱ እኩል ድሃ ስላደረገላቸው ነበር። የሚያስቡ ሰዎች፣ የራሳቸውን ረጅም ጊዜ ጥቅም በጥልቀት ለመመርመር የሚችሉ እና ስሜታቸውን ለመፈተሽ የሚፈቅዱ ግለሰቦችም ሆነ ልሂቃን ግጭቶች በቅናት እንዳይመሩ ወይም እንዳይቀሰቀሱ ለራሳቸው ስሜት መጠበቂያ ያደርጋሉ። ወደ ግጭት ከመግባታቸው በፊት የዛ ሰው፣ ተቋም ወይም ሀገር ስኬት ለእነሱ ምን ማለት እንደሆነ፣ ያ እንዴት ለእነሱ ጥቅም እንደሚውል ያስባሉ። ውድቀቱ የሚያስደስታቸው ከሆነ ያ ግጭት ከቅናት የተነሳ ሊሆን እንደሚችል መጠርጠር ተገቢ ነው።ምክንያቱም ከመመሳሰል የሚነሱ ግጭቶች ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ አጥፊዎች (distractive) ናቸውና።

 
 
 
ree

፩) የኢዮብ ወዳጆች ለመከራ እና ለክፋት መልስ አለን ብለው መቅረባቸው፤

እውነት ለመናገር ብዙዎቻችን ብዙ ነገር አናውቅም። ግን አላውቅም ማለት በጣም ከባድ ነው። መክበዱ ብቻ አይደለም መልስ ሳይኖረን ተረጋግተን መኖር እና መቀጠል ይሳነናል። በተለይ ዓይናችን ሥር ትልቅ ክስተት ስናይ የዛን መንስኤ መተንተን ያስጎመጀናል። በተማሩ ሰዎች መካከል ደግሞ አላውቅም ማለት ነውር ይሆናል። አለማወቅ ተማርን ማለታቸውን ያሳንስባቸዋል። ማህበረሰባዊ ጫናውም ከፍተኛ ነው። አንድ አክስቴ ብዙ ጊዜ ስትጠይቀኝ አላውቅም፣ አላውቅም ስላት “እንዴ የተማርክ አይደለህም እንዴ?” አለችኝ። የዚህ ዓይነት ጫና ስለማናውቀው ነገር ሳይቀር ትንታኔ እንድንሰጥ ይጋብዘናል። ዝም ማለት በትልልቅ ክስተቶች ፊት እጅግ ከባድ ነው። የኢዮብ አዋቂ ወዳጆቹ የተሳናቸው ያ ነበር። በእግዚአብሔር ጉባኤ ተወስኖ በጻዲቁ ኢዮብ ላይ የተከናወነው ነገር ለማናቸውም የሰው ልጆች የተገለጠ አልነበረም። ግን የኢዮብ ወዳጆች ዝም ከማለት ይልቅ ለኢዮብ መከራ ምክንያት ፈለጉለት። ኃጢአተኛ ስለሆንክ ነውና ንስሃ ግባ አሉት። ቢያንስ በሀሳብህ በድለሃል አሉት። ውጤትን ዓይተው መንስኤውን ተነተኑ።



 የደራሲ ዓለማየው ገላጋይን አንድ የተቆረጠ ቪዲዮ ተመለከትኩኝ። ያለንበት ድህነት እና መከራ እረፍት የነሳው ይመስላል። ይሄ አዋቂ ደራሲ ከዛ እንዲህ አለ “እግዚአብሔር ጣልቃ አይገባም በሕይወታችን።” የየቀን ሠሪውን እግዚአብሔርን “ሁሉን ነገር ሠርቶ ጨርሶ ቀድመው ለነቁ ሰዎች አስረክቦናል” አለን። “ለዚህም ነው ከዚህ በፊት የጠፉ ሰዎች ሲያይ ጣልቃ ያልገባው፣ በእኛም ሕይወት ጣልቃ አይገባም፣ ራስህ ሠርተ ለፍተህ ልበስ፣ ብላ፣ ተጋደል። እርሱ ጣልቃ አይገባም፣ ለዚህም ነው የሰለጠኑት፣ ቀድመው የነቁት ሁልጊዜ የሚገዙን” አለ። ይሄ መከራ ላይ፣ ድህነት ላይ፣ ችግር ላይ ቆሞ ስለመንስኤው የማውራት ዝንባሌ እና አባዜ ነው። ጥራት ባለው አስተሳሰብ ዙሪያ ብዙ የተማሩ ሰዎች የሚሰሩት ትልቁ የማሰብ ስህተት ነው፣ መንስኤን ከውጤት ለማግኘት መጣር። ይሄ ጥራት ላለው አስተሳሰብ ጋንግሪን ነው። ከእግዚአብሔር ጋር ስናያይዘው ደግሞ ቁጣው እንደእሳት የሚነድበት የአስተሳሰብ ዝንባሌ ነው። ስለኢዮብ ባይሆን ኖሮ ቁጣዬ እንደ እሣት በልቷቹ ነበር ነው ያለው።



በየቀኑ ይሄን የአስተሳሰብ ስህተት እንሰራለን። የታመመ ሰው እናያለን ፥ እግዚአብሔር ቀጣው እንላለን። ሀብታም እናያለን ፥ እግዚአብሔር ባረከው እንላለን። ድሀ እናያለን ፥ ሰነፍ ነው፣ እግዚአብሔር አልባረከውም እንላለን። ውጤት ላይ ቆሞ መንስኤን የማግኘት አባዜ። እስቲ በሕይወታችሁ አንድን ነገር ስንት ሁኔታዎች ሊያመጡት እንደሚችሉ ጠይቁ እና ያን ለእናንተ የተገለጠውን ብቻ ፈትሹ። በእናንተ ሕይወት እንደዛ ከሆነ፣ እጅግ ውስብስብ በሆነው በዚህ ዓለም አነዋወር ውስጥ የአንድ ነገር መንስኤ ከኛ የማሰብ አቅም ቢያንስ ያለጥልቅ ጥናት የረቀቀ ሊሆን ይችላል ብላችሁ አትገምቱም?


ደራሲ ዓለማየው መንስኤውን ለማወቅ በመቸኮሉ፣ ውጤቱንም በአግባቡ የተረዳው አይመስልም። ለምሳሌ በእውነት ይሄ ዓለም ኃያል የሆነው የሰው ልጅ (በዘመናዊ ቴክኖሎጂ) ደካማ የሆነውን ፍጹም የሚገዛበት ነው ወይስ ብዙ ዓይነት ኃይሎች በሰዎች የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ ላይ እና የነገ ሕይወታችን ላይ ያልተጠበቁ እና ተገማች ያልሆኑ አሻራቸውን እና ተጽዕኖዎችን የሚያሳርፉበት ዓለም ነው? በዚህ ዓለም ሰዎች የፈጠሯቸው ግዙፍ ቴክኖሎጂዎች ፥ በጣም ደካማ በሆኑ ፍጥረታት ወይም ክስተቶች አቅጣጫቸውን ሲቀይሩ እና ሲዘወሩ አላየንምን? ለምሳሌ የኮቪድ ቫይረስ እንዴት የሰው ልጆችን ሁሉ ባህሪ እና አነዋወር በቅጽበት እንደለወጠ ተመልከቱ። ይሄ ክስተት የሚነግረን ይሄ ዓለም በኃያላን ፍላጎት እንደፈለጉት የሚዘወር ዓለም እንዳልሆነ አይደለምን? የታላቋን አሜሪካ የውጪ ጉዳይ እና የሀገር ውስጥ የደኅንነት ፖሊሲ ፍጹም የቀየረው ከደካማዋ ሀገር አፍጋኒስታን የመጣ ጥቃት አልነበረምን? በርግጥስ ይሄ ዓለም ኃያላን እንዳሰቡት የሚኖሩበት ዓለም ነውን?



መሥራትን፣ ለፍቶ ማደርን፣ መፍጠርን ለማበረታታት የግድ ጽንፍ መሄድ አያስፈልገንም። እነዚህ ነገሮች ጥሩ ናቸው። ግን ሌላም እውነት አለ። እነዚህ ብቻ በቂ አይደሉም። እነዚህ ብቻ መልስ አይደሉም። “ሥራ ነጻ ያወጣኻል፣ Arbeit macht frei” የሚለውን መፈክር እናውቀዋለን። ይሄ በፍሬድሪክ ኒቼ ተጠንስሶ ናዚዎች የወረሱት እና በናዚ ካምፖች ሁሉ የተሰቀለ መፈክር ነበር። ሥራ ብቻውን የጥላቻ እና የትዕቢት ባርነት ውስጥ ጀርመኖችን ጨምሮ፣ ውድቀታቸውን አስከተለ እንጂ ነጻ አላወጣቸውም።



ጠቢበኛው ሰሎሞን ስለመንስኤ ሲናገር ከኛ ውጪ ባሉ ኩነቶች ማለትም በጊዜ እና በዕድል የሚወሰኑ እንደሆነ ተናግሯል። እዚህ ላይ የደረሰው ከብዙ ማሰብ በኋላ እንደሆነ ሲያሳይ “እኔም ተመለስሁ” ብሎ ይጀምራል። “እኔም ተመለስሁ፥ ከፀሐይ በታችም ሩጫ ለፈጣኖች፥ ሰልፍም ለኃያላን፥ እንጀራም ለጠቢባን፥ ባለጠግነትም ለአስተዋዮች፥ ሞገስም ለአዋቂዎች እንዳልሆነ አየሁ፤ ጊዜና እድል ግን ሁሉን ይገናኛቸዋል።” መክ 9፥11።


፪) ሁለተኛው ነቀፋ ቲዎሎጂ እና አይዶሎጂ ነው። የኢዮብ ወዳጆች ጠንካራ ቲዎሎጂ ነበራቸው። ያም ክፋት ስለሚሸነፍበት መንገድ ነው። የእነሱ መንገድ ብቻ ኢዮብን ከቁስሉ እንደሚፈውሰው ደሰኮሩ። እየተፈራረቁ የቁስሉ መድኅን እነሱን መስማት መሆኑን ነገሩት። ይሄ በሃይማኖት ሰዎች መካከል በጣም ጠንካራ ዝንባሌ ነው። ለሁሉም ነገር መፍትሔ አለን። ለሁሉም ነገር ስንዱ ነን። የሚገርመው ግን ክፋትን እግዚአብሔር እንዴት እንደሚያሸንፍ ከኛ የተሰወረ ጥበብ መሆኑ ነው። ክፋትን በመስቀሉ እንደሚረታ ለማንም የተሰወረ ነበር በብሉይ ኪዳን። መስቀል ነበር \ የእግዚአብሔር ጥበብ ፥ ክፋትን የረታበት። የሰው ልጆችን ቁስል የፈወሰበት። ያ ግን በድንግዝግዝ ተመለከቱት እንጂ ለአንዳቸውም አበው አልተገለጠላቸውም ነበር። ቲዎሎጂ በፍጥነት አይዶሎጂ ይሆናል፤ ለሁሉም ነገር መልስ አለኝ ብሎ ሲያስብ። ክፋት እና መጥፎ ነገሮች ለምንላቸው ሁሉ መልስ አለኝ ብሎ ሲገምት። ዝምታ እና ለእግዚአብሔር ዕድል እና ጊዜ መስጠት ብዙዎቻችን በየቀኑ መማር ያለቡን ጸጋዎች ናቸው። “ምነው ዝም ብላችሁ ብትኖሩ፦ ይህ ጥበብ በሆነላችሁ ነበር።” ኢዮ 13፥5።


 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 4 min read
ree

በውጭ ጉዳይ በቢዝነስ ዲፕሎማሲ ዘርፍ ስሠራ፣ አንድ የጀርመን ኩባንያ ከሀገር ነቅሎ ሲወጣ ለመ/ቤታችን የጻፈው ደብዳቤ ሁልጊዜ ትዝ ይለኛል። “የኢትዮጵያ መንግስት እንደ ሁሉም ኋላ ቀር ሀገራት በሕግ ብዛት ችግሮችን መፍታት የሚቻል የሚመስለው ነው፤ ችግሮች ሲገጥሙ በውይይት እና መፍትሔ ለመፈለግ በሚሆን አዕምሮ ከመሥራት ይልቅ በሕግ ላይ ሕግን ማውጣት ባህሪው ስላደረገ እና በዚህ ሁኔታም ኩባንያችን በዚህ ሀገር ውስጥ ለመሥራት ስለሚቸገር ለቀን ወጥተናል” የሚል ጠንካራ ደብዳቤ ጽፈው ነበር የኩባንያው ኋላፊዎች ከሀገር የወጡት። አንድ የጀርመኖች አባባል አለ “The more laws, the less justice” የሚል።


 ይሄን ያነሳውበት ምክንያት ብዙ ጊዜ የተወሳሰቡ ነገሮች፣ መዋቅሮች፣ ብዛት ያላቸው ሥርዓቶች፣ ትንታኔዎች ይመስለናል ትክክለኛው መልስ ወይም ለችግሮቻችን መፍትሔ። ለዚህም በሁሉም የሕይወታችን ክፍል ውስጥ ማቅለልን ሳይሆን ማክበደን እና ማስጨነቅን፣ ማወሳሰብን የጥራት፣የአዋቂነት መለኪያ አድርገን እንወስደዋለን።


የ14ኛው ክፍለዘመን ቲዎሎጂያን እና የሎጂክ ሰው ዊሊያም ኦክሃም የፈጠረው እና ኦካም ራዛር ተብሎ የተሰየመ የችግሮች መፍቻ ሂደት አለ። ሁልጊዜ ቀላሉ መፍትሔ በጣም ውስብስብ ሆኖ ከቀረበው በላይ ምርጡ መፍትሔ ነው ይላል። (The simplest solution is almost always the best. ... simplicity is better than complexity)።


ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእስራኤል መኃል የተጠየቀውም ይሄን ነበር። በፈሪሳውያን እና ሰዱቃውያን የሕግ እና የሥርዓት ቀንበሮች እና ውስብስብ የአምልኮ ማስመሰሎች መኃል ጌታችን በአንድ የሕግ አዋቂ “ከሕግ ማናቸይቱ ትእዛዝ ታላቅ ናት?” ተብሎ ተጠየቀ። (ማቴ 22፥36)። ከ613 ሕግጋት መካከል የትኛውን እንደሚያስበልጥ ሲጠይቀው ጌታችን እንዴት ባለ መልኩ የሕግጋትን ሁሉ መስፈሪያ ለዚህ ሰው እንደነገረው ተመልከቱ።


613 ሕግጋት መኃል ሁለቱን ምሰሶዎች፣ በጫካው የተሸፈኑ ሁለቱ የሕይወት ዛፎችን አሳየው። “ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስም በፍጹም አሳብህም ውደድ።” እና “ባልጀራህን እንደራስህ ውደድ” የሚለውን።


እነዚህን ሁለቱን ሕግጋት ሳይፈጽም ቀሪዎቹን ሕግጋት ሁሉ ቢፈጽም፤ ለሰው ምንም አይጠቅመውም። እነዚህን ሁለቱን ሕግጋት ብቻ የሚፈጽም ደግሞ ሁሉንም ሕግጋት ይፈጽማል። ለዚህ ነው ቅዱስ አውግስጢኖስ “እግዚአብሔርን ውደዱት ከዛ ሁሉን ማድረግ ትችላላችሁ ያለው።” (Love God and you are allowed to do everything)። ምክንያቱም ፍቅር የተፈቃሪውን ደስታ ከራሱ በላይ የሚሻ እና ተፈቃራዊን ለማስደሰት የሚሰራ ስለሆነ ነው።


ሌላ ጊዜ ደግሞ እንዲሁ ሌላ የሕግ አዋቂ የጌታን እውቀት ሊፈትን መጣ። የሕግ አዋቂዎች ማወቃቸውን የሚያሳዩት የረቀቀ ነገር በመናገር፣ ግልጽ የሆነውን ነገር ሳይቀር በማወሳሰብ፣ ሰው ሁሉ በሚገባው ቋንቋ ሳይሆን ፥ ሁሉ የሚያውቀውን ቋንቋ የውጭ ሀገር ቋንቋ እስኪመስል ድረስ በማራቀቅ ነበርና፣ ታላቅ የሆነን ሰማያዊ እውቀት በቀለለ ቋንቋ፣ ሁሉም በሚረዳው መልኩ የሚያቀርበውን መምህር አልወደደውም። ለሕግ አዋቂዎች ብቻ ተወስኖ የነበረውን፣ ተራው ሕዝብም እንዳይገባው በሚመስል መልኩ የቀረበውን እውቀት፣ ይዘቱ ሳይጓደል ለተራው እስራኤላዊ የሚያስተምረው የዚህ መምህር ዘይቤ ለተኮፈሰው ማንነታቸው አደጋ ነበርና ፥ ይሄ የሕግ አዋቂ ጌታችንን “ባልጀራዬ ማነው?” ብሎ ጠየቀው።


በሉቃስ ወንጌል 10፥30 ላይ “ባልጀራ ማነው?” የሚለውን በደጉ ሳምራዊ ታሪክ ገለጠለት። ባልጀራ ማነው የሚለውን ለማስረዳት አዲስ ሕግ አላወጣም። ረቂቅ ትንታኔ አልሰጠም። በወንበዴዎች ተደብድቦ የወደቀውን አይሁዳዊ እና ሌሎች ሳይረዱት ያለፉትን፤ የእርዳታ እጁን የዘረጋለትን እውነተኛ ባልጀራ ደጉ ሳምራዊን በትረካ አሳየው እንጂ። (በሰዓቱ አይሁድ እና ሳምራዊያን እንደ ጠላቶች ነበሩ)። ጠላቶቻችን ሳይቀሩ የኛ ፍቅር እንደሚገባቸው በማስረዳት ፥ ባልጀራ ማነው የሚለውን በሚደንቅ ቅለት ነገረው።


እውነት ለመናገር አንድ ነገር እንደገባን ማወቅ የሚቻለው ለ6 እና ለ7 ዓመት ሕጻን ልጅ ወይም ለአሮጊት አያታችን ማስረዳት ስንችል ነው። እስከዛ ድረስ እኛም ገና አልገባንም።

አንድን ነገር አቅልሎ የሚያሳይ ሰው የዛ ነገር “essence” ወይም ዋናው አንኳር የገባው ሰው ነው። በተቃራኒው የሚያወሳስቡ ሰዎች አልገባቸውም ወይም ብዙ ጊዜ አጭበርባሪዎች ናቸው።

ከ90 ዓመት በፊት የአሜሪካ ኃያል ባለሀብት የነበረው ጆን ሮክፌለር (ከሀብቱ ብዛት የአሜሪካ መንግስት አስገድዶት ገንዘቡን ተበድሮታል) በጣም የሚታወቅበት ነገር ያልገባውን ነገር በልምድ ወይም ሰዎች ሲያደርጉት ስላየ ፈጽሞ አለማድረጉ ነው። በነዳጅ ማጣሪያው ስፍራ ቆሞ ሲመለከት ሠራተኛው ስምንት ጊዜ ማጣሪያውን ይጫነዋል፣ ይሄ ሂደት ሠራተኞች እይተቀያየሩ የሚከውኑት ነበር። ሮክፌለር አንዱን ኃላፊ “ለምንድነው ስምንት ጊዜ የምታደርጉት፣ ለምን አንድ ጊዜ ብቻ አታደርጉም?” ብሎ ጠየቀው። እሱም “ከዚህ በፊት ስምንት ጊዜ ነበር የምናደርገው” አለው። “ምክንያቱን ግን አላውቅም” ብሎ መለሰለት። “በሚቀጥለው ቀን ምክንያቱን አጥንተ አቅርብልኝ” ብሎት ሄደ። ሰውዬው በጥናቱ የደረሰበት ስምንት ጊዜ የሪፋይነሪ ፓምፑን መጫን እንደማያስፈልግ እና ይሄ በሆነ አጋጣሚ የተከሰተ፣ አሁን ግን ፈጽሞ የማያስፈልግ መሆኑን አጥንቶ አቀረበ። “ለምን” ብሎ በመጠየቁ ብቻ ሮክፌለር ሠራተኞቹ የሚያጠፉትን ሰዓት አዳነ፣ የሪሶርስም ብክነት ቀነሰ።

በየቀን ሕይወታችን የምናደርጋቸው ቀላል የማይባሉ ሥራዎች ያለምክንያት ሊሆኑ ይችላሉ። ሥርዓት ስለሆነ ብቻ፣ ከዚህ በፊት ሌሎች ስላደረጉት ወይም ያን አለመከተል ከሌሎች ሊነጥለን እና ጥፋት ብናጠፋ አደጋ ውስጥ ሊጥለን ይችላል ብለን ስለምናስብ የምናደርጋቸው ነገሮች ብዙ ናቸው።



ይሄ የማይነካው የሕይወት ክፍል የለም። ብዙ ግራ የሚገቡን እና ዓላማውን የሳቱ ወይም ከዓላማው በላይ ሥርዓቱን ዓላማ ያደረጉ ነገሮች በሃይማኖት ስፍራ እናያለን፣ በሥራ ቦታዎቻችን እነዚህ ውስብስብ ሥራዓቶች እና ቢሮክራሲዎች የደካሞች መደበቂያ ሆነው እናገኛለን።

ከወራት በፊት የወዳጄ ቤት ስሄድ፣ በቤቱ ውስጥ አንድ ጉዙፍ ውሻ አለ። ውሻው በአንገቱ ላይ ገመድ አለው። ዓላማው በቀን አንዴ ውጪ ይዞት ሲወጣ፣ እዛ የአንገት ገመድ ላይ ረዥም ሌላ ገመድ አስሮ ለመውጣት ነው። በዚህ ሀገር ውሻን ያለማሰሪያ (leash) መንገድ ላይ ይዞ መወጣት በሕግ ስለሚከለከል ነው። ውሻው ቤት ውስጥ ስለነበረ ይሄን የአንገት ገመት አወለኩለት። ውሻው ግን መታሰሪያውን መልሰ ካላጠለክልኝ ብሎ አበደ። በጣም ገረመኝ። ምንአልባት እንግዳ ስለሆንኩኝ እና እኔ ስላወለኩለት ይሆናል ብዬ፤ እነሱ እንዲያወልቁለት እና እንዴት እንደሚሆን ለማየት ጠየኳቸው። ውሻው ግን ማንም ያን የአንገት ገመድ ከአንገቱ እንዲወስድበት አልፈቀደም። ምክንያቱም ከልጅነቱ ጀምሮ ይሄ ገመድ ዘወትር አንገቱ ላይ ስለነበረ፤ ከዛ ማሰሪያው ገመድ ጋር ከፍተኛ ቁርኝት ፈጥሯል። ነጻ እንዲሆን እና እንዲቀለው የተመኘነውን ሁሉ ሊፈቅድልን አልቻለም።

ይሄ የውሻ ታሪክ ብቻ ከመሰለን በጣም ተሳስተናል። እውነት ለመናገር ያ ውሻ ራሴን እንድፈትሽ ነበር የጋበዘኝ። “በእኔ ሕይወት ውስጥ ምክንያቱን የማላውቃቸው ከልምድ አንጻር፣ ከማህበረሰብ ላለመለየት ስል ብቻ ወይም ሳይገባኝ ሌሎች ስላደረጉት ብቻ የማደርገው ነገር ምንድነው?” ብዬ መጠየቅ ነው የጀመርኩት።



ታላቁ ሳይኮሎጂስት ካርል ዩንግ በዚህ ዓለም ላይ በጣም ከባዱ ነገር አንድን ነገር ማቅለል ነው፤ ራስንም አቅሎ ለማቅረብ ታላቅ ጥበብ ይፈልጋል ይላል። (But simple things are always the most difficult. In actual life, it requires the greatest art to be simple.)።

የትኛውንም ነገር ጠንቅቃችሁ ለማወቅ ትፈልጋላችሁ፣ ያን ነገር አቅልሉት። ውስብስብ ነገሮችን በቀላል ነገር ተኳቸው፣ ሥርዓት የበዛበት ነገር ስታዩ ቆም ብላችሁ ጠይቁ፤ “ምንድነው የዚህ ሥርዓት ዓላማ? ማነው ይሄን የደነገገው? ምን ለማሳካት ታልሞ ይሄ ሥርዓት ወጣ? ዓላማውን ለማሳካት ዛሬ ላይ ከዚህ የተሻለ መንገድ የለም?” ለእነዚህ ጥያቄዎች ውስብስብ መልስ የሚሰጣችሁ ሰው ወይ ራሱ አልገባውም ወይም እያጭበረበረ ነው።



ነገር ግን ያለዕውቀት ለማቅለል የሚሞክር ሰው ሕጻን ነው። ሕጻን ብቻ ነው አንድን ነገር የሚያስከትለውን የተለያዩ መዘዞች በአግባቡ ሳያጤን ለማፍረስ የሚሯሯጠው። ያ ቀላል የሕጻን አዕምሮ ነው።



ማካበድ ደግሞ የጀማሪ አዋቂ ወይም ትንሽ እውቀት ያለው ሰው ባህሪ ነው። ይሄ ሰው በውስብስብ ሕጎች፣ ቢሮክራሲዎች፣ ሥርዓቶች፣ በረቀቁ ትንታኔዎች፣ በከባድ ቋንቋዎች (ቃላቶች) ብቻ ነው ከፍ ማለት የሚችለው፣ መኖር እና አዋቂ ተብሎ መከበር የሚችለው። እነዚህ ዓይነት ሰዎች “ሰንበት ለሰው እንጂ ሰው ለሰንበት የተፈጠረ” አስመስለው ሥርዓት እንደዘረጉት ፈሪሳውያን ናቸው። በማወሳሰብ ብዛት አዋቂ ተብለው ለመኖር የሚቋምጡ።


በእውቀት ላይ ተመስርቶ ቀንበርን ማቅለል ግን የጥበበኛ እና የፍጹም አዋቂ ሰው ባህሪ ነው። እንደዚህ ዓይነት ሰዎች የማንኛውንም ነገር essence ወይም ኮር ዓላማ ወይም ዋነኛ ግብ ለማወቅ የሚጥሩ ሰዎች ናቸው። ያን ጠንቅቀው ካወቁ በኋላ፣ ዓላማውን በተሻለ መንገድ፣ ከድሮው በቀለለ ሂደት ለማሳካት የሚጥሩ ናቸው።

በተለያዩ ርዕሶች ዙሪያ ጹሁፎቼን በቴሌግራም ገጼ ማግኘት ትችላላችሁ።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page