top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 4 min read
ree

በውጭ ጉዳይ በቢዝነስ ዲፕሎማሲ ዘርፍ ስሠራ፣ አንድ የጀርመን ኩባንያ ከሀገር ነቅሎ ሲወጣ ለመ/ቤታችን የጻፈው ደብዳቤ ሁልጊዜ ትዝ ይለኛል። “የኢትዮጵያ መንግስት እንደ ሁሉም ኋላ ቀር ሀገራት በሕግ ብዛት ችግሮችን መፍታት የሚቻል የሚመስለው ነው፤ ችግሮች ሲገጥሙ በውይይት እና መፍትሔ ለመፈለግ በሚሆን አዕምሮ ከመሥራት ይልቅ በሕግ ላይ ሕግን ማውጣት ባህሪው ስላደረገ እና በዚህ ሁኔታም ኩባንያችን በዚህ ሀገር ውስጥ ለመሥራት ስለሚቸገር ለቀን ወጥተናል” የሚል ጠንካራ ደብዳቤ ጽፈው ነበር የኩባንያው ኋላፊዎች ከሀገር የወጡት። አንድ የጀርመኖች አባባል አለ “The more laws, the less justice” የሚል።


 ይሄን ያነሳውበት ምክንያት ብዙ ጊዜ የተወሳሰቡ ነገሮች፣ መዋቅሮች፣ ብዛት ያላቸው ሥርዓቶች፣ ትንታኔዎች ይመስለናል ትክክለኛው መልስ ወይም ለችግሮቻችን መፍትሔ። ለዚህም በሁሉም የሕይወታችን ክፍል ውስጥ ማቅለልን ሳይሆን ማክበደን እና ማስጨነቅን፣ ማወሳሰብን የጥራት፣የአዋቂነት መለኪያ አድርገን እንወስደዋለን።


የ14ኛው ክፍለዘመን ቲዎሎጂያን እና የሎጂክ ሰው ዊሊያም ኦክሃም የፈጠረው እና ኦካም ራዛር ተብሎ የተሰየመ የችግሮች መፍቻ ሂደት አለ። ሁልጊዜ ቀላሉ መፍትሔ በጣም ውስብስብ ሆኖ ከቀረበው በላይ ምርጡ መፍትሔ ነው ይላል። (The simplest solution is almost always the best. ... simplicity is better than complexity)።


ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእስራኤል መኃል የተጠየቀውም ይሄን ነበር። በፈሪሳውያን እና ሰዱቃውያን የሕግ እና የሥርዓት ቀንበሮች እና ውስብስብ የአምልኮ ማስመሰሎች መኃል ጌታችን በአንድ የሕግ አዋቂ “ከሕግ ማናቸይቱ ትእዛዝ ታላቅ ናት?” ተብሎ ተጠየቀ። (ማቴ 22፥36)። ከ613 ሕግጋት መካከል የትኛውን እንደሚያስበልጥ ሲጠይቀው ጌታችን እንዴት ባለ መልኩ የሕግጋትን ሁሉ መስፈሪያ ለዚህ ሰው እንደነገረው ተመልከቱ።


613 ሕግጋት መኃል ሁለቱን ምሰሶዎች፣ በጫካው የተሸፈኑ ሁለቱ የሕይወት ዛፎችን አሳየው። “ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስም በፍጹም አሳብህም ውደድ።” እና “ባልጀራህን እንደራስህ ውደድ” የሚለውን።


እነዚህን ሁለቱን ሕግጋት ሳይፈጽም ቀሪዎቹን ሕግጋት ሁሉ ቢፈጽም፤ ለሰው ምንም አይጠቅመውም። እነዚህን ሁለቱን ሕግጋት ብቻ የሚፈጽም ደግሞ ሁሉንም ሕግጋት ይፈጽማል። ለዚህ ነው ቅዱስ አውግስጢኖስ “እግዚአብሔርን ውደዱት ከዛ ሁሉን ማድረግ ትችላላችሁ ያለው።” (Love God and you are allowed to do everything)። ምክንያቱም ፍቅር የተፈቃሪውን ደስታ ከራሱ በላይ የሚሻ እና ተፈቃራዊን ለማስደሰት የሚሰራ ስለሆነ ነው።


ሌላ ጊዜ ደግሞ እንዲሁ ሌላ የሕግ አዋቂ የጌታን እውቀት ሊፈትን መጣ። የሕግ አዋቂዎች ማወቃቸውን የሚያሳዩት የረቀቀ ነገር በመናገር፣ ግልጽ የሆነውን ነገር ሳይቀር በማወሳሰብ፣ ሰው ሁሉ በሚገባው ቋንቋ ሳይሆን ፥ ሁሉ የሚያውቀውን ቋንቋ የውጭ ሀገር ቋንቋ እስኪመስል ድረስ በማራቀቅ ነበርና፣ ታላቅ የሆነን ሰማያዊ እውቀት በቀለለ ቋንቋ፣ ሁሉም በሚረዳው መልኩ የሚያቀርበውን መምህር አልወደደውም። ለሕግ አዋቂዎች ብቻ ተወስኖ የነበረውን፣ ተራው ሕዝብም እንዳይገባው በሚመስል መልኩ የቀረበውን እውቀት፣ ይዘቱ ሳይጓደል ለተራው እስራኤላዊ የሚያስተምረው የዚህ መምህር ዘይቤ ለተኮፈሰው ማንነታቸው አደጋ ነበርና ፥ ይሄ የሕግ አዋቂ ጌታችንን “ባልጀራዬ ማነው?” ብሎ ጠየቀው።


በሉቃስ ወንጌል 10፥30 ላይ “ባልጀራ ማነው?” የሚለውን በደጉ ሳምራዊ ታሪክ ገለጠለት። ባልጀራ ማነው የሚለውን ለማስረዳት አዲስ ሕግ አላወጣም። ረቂቅ ትንታኔ አልሰጠም። በወንበዴዎች ተደብድቦ የወደቀውን አይሁዳዊ እና ሌሎች ሳይረዱት ያለፉትን፤ የእርዳታ እጁን የዘረጋለትን እውነተኛ ባልጀራ ደጉ ሳምራዊን በትረካ አሳየው እንጂ። (በሰዓቱ አይሁድ እና ሳምራዊያን እንደ ጠላቶች ነበሩ)። ጠላቶቻችን ሳይቀሩ የኛ ፍቅር እንደሚገባቸው በማስረዳት ፥ ባልጀራ ማነው የሚለውን በሚደንቅ ቅለት ነገረው።


እውነት ለመናገር አንድ ነገር እንደገባን ማወቅ የሚቻለው ለ6 እና ለ7 ዓመት ሕጻን ልጅ ወይም ለአሮጊት አያታችን ማስረዳት ስንችል ነው። እስከዛ ድረስ እኛም ገና አልገባንም።

አንድን ነገር አቅልሎ የሚያሳይ ሰው የዛ ነገር “essence” ወይም ዋናው አንኳር የገባው ሰው ነው። በተቃራኒው የሚያወሳስቡ ሰዎች አልገባቸውም ወይም ብዙ ጊዜ አጭበርባሪዎች ናቸው።

ከ90 ዓመት በፊት የአሜሪካ ኃያል ባለሀብት የነበረው ጆን ሮክፌለር (ከሀብቱ ብዛት የአሜሪካ መንግስት አስገድዶት ገንዘቡን ተበድሮታል) በጣም የሚታወቅበት ነገር ያልገባውን ነገር በልምድ ወይም ሰዎች ሲያደርጉት ስላየ ፈጽሞ አለማድረጉ ነው። በነዳጅ ማጣሪያው ስፍራ ቆሞ ሲመለከት ሠራተኛው ስምንት ጊዜ ማጣሪያውን ይጫነዋል፣ ይሄ ሂደት ሠራተኞች እይተቀያየሩ የሚከውኑት ነበር። ሮክፌለር አንዱን ኃላፊ “ለምንድነው ስምንት ጊዜ የምታደርጉት፣ ለምን አንድ ጊዜ ብቻ አታደርጉም?” ብሎ ጠየቀው። እሱም “ከዚህ በፊት ስምንት ጊዜ ነበር የምናደርገው” አለው። “ምክንያቱን ግን አላውቅም” ብሎ መለሰለት። “በሚቀጥለው ቀን ምክንያቱን አጥንተ አቅርብልኝ” ብሎት ሄደ። ሰውዬው በጥናቱ የደረሰበት ስምንት ጊዜ የሪፋይነሪ ፓምፑን መጫን እንደማያስፈልግ እና ይሄ በሆነ አጋጣሚ የተከሰተ፣ አሁን ግን ፈጽሞ የማያስፈልግ መሆኑን አጥንቶ አቀረበ። “ለምን” ብሎ በመጠየቁ ብቻ ሮክፌለር ሠራተኞቹ የሚያጠፉትን ሰዓት አዳነ፣ የሪሶርስም ብክነት ቀነሰ።

በየቀን ሕይወታችን የምናደርጋቸው ቀላል የማይባሉ ሥራዎች ያለምክንያት ሊሆኑ ይችላሉ። ሥርዓት ስለሆነ ብቻ፣ ከዚህ በፊት ሌሎች ስላደረጉት ወይም ያን አለመከተል ከሌሎች ሊነጥለን እና ጥፋት ብናጠፋ አደጋ ውስጥ ሊጥለን ይችላል ብለን ስለምናስብ የምናደርጋቸው ነገሮች ብዙ ናቸው።



ይሄ የማይነካው የሕይወት ክፍል የለም። ብዙ ግራ የሚገቡን እና ዓላማውን የሳቱ ወይም ከዓላማው በላይ ሥርዓቱን ዓላማ ያደረጉ ነገሮች በሃይማኖት ስፍራ እናያለን፣ በሥራ ቦታዎቻችን እነዚህ ውስብስብ ሥራዓቶች እና ቢሮክራሲዎች የደካሞች መደበቂያ ሆነው እናገኛለን።

ከወራት በፊት የወዳጄ ቤት ስሄድ፣ በቤቱ ውስጥ አንድ ጉዙፍ ውሻ አለ። ውሻው በአንገቱ ላይ ገመድ አለው። ዓላማው በቀን አንዴ ውጪ ይዞት ሲወጣ፣ እዛ የአንገት ገመድ ላይ ረዥም ሌላ ገመድ አስሮ ለመውጣት ነው። በዚህ ሀገር ውሻን ያለማሰሪያ (leash) መንገድ ላይ ይዞ መወጣት በሕግ ስለሚከለከል ነው። ውሻው ቤት ውስጥ ስለነበረ ይሄን የአንገት ገመት አወለኩለት። ውሻው ግን መታሰሪያውን መልሰ ካላጠለክልኝ ብሎ አበደ። በጣም ገረመኝ። ምንአልባት እንግዳ ስለሆንኩኝ እና እኔ ስላወለኩለት ይሆናል ብዬ፤ እነሱ እንዲያወልቁለት እና እንዴት እንደሚሆን ለማየት ጠየኳቸው። ውሻው ግን ማንም ያን የአንገት ገመድ ከአንገቱ እንዲወስድበት አልፈቀደም። ምክንያቱም ከልጅነቱ ጀምሮ ይሄ ገመድ ዘወትር አንገቱ ላይ ስለነበረ፤ ከዛ ማሰሪያው ገመድ ጋር ከፍተኛ ቁርኝት ፈጥሯል። ነጻ እንዲሆን እና እንዲቀለው የተመኘነውን ሁሉ ሊፈቅድልን አልቻለም።

ይሄ የውሻ ታሪክ ብቻ ከመሰለን በጣም ተሳስተናል። እውነት ለመናገር ያ ውሻ ራሴን እንድፈትሽ ነበር የጋበዘኝ። “በእኔ ሕይወት ውስጥ ምክንያቱን የማላውቃቸው ከልምድ አንጻር፣ ከማህበረሰብ ላለመለየት ስል ብቻ ወይም ሳይገባኝ ሌሎች ስላደረጉት ብቻ የማደርገው ነገር ምንድነው?” ብዬ መጠየቅ ነው የጀመርኩት።



ታላቁ ሳይኮሎጂስት ካርል ዩንግ በዚህ ዓለም ላይ በጣም ከባዱ ነገር አንድን ነገር ማቅለል ነው፤ ራስንም አቅሎ ለማቅረብ ታላቅ ጥበብ ይፈልጋል ይላል። (But simple things are always the most difficult. In actual life, it requires the greatest art to be simple.)።

የትኛውንም ነገር ጠንቅቃችሁ ለማወቅ ትፈልጋላችሁ፣ ያን ነገር አቅልሉት። ውስብስብ ነገሮችን በቀላል ነገር ተኳቸው፣ ሥርዓት የበዛበት ነገር ስታዩ ቆም ብላችሁ ጠይቁ፤ “ምንድነው የዚህ ሥርዓት ዓላማ? ማነው ይሄን የደነገገው? ምን ለማሳካት ታልሞ ይሄ ሥርዓት ወጣ? ዓላማውን ለማሳካት ዛሬ ላይ ከዚህ የተሻለ መንገድ የለም?” ለእነዚህ ጥያቄዎች ውስብስብ መልስ የሚሰጣችሁ ሰው ወይ ራሱ አልገባውም ወይም እያጭበረበረ ነው።



ነገር ግን ያለዕውቀት ለማቅለል የሚሞክር ሰው ሕጻን ነው። ሕጻን ብቻ ነው አንድን ነገር የሚያስከትለውን የተለያዩ መዘዞች በአግባቡ ሳያጤን ለማፍረስ የሚሯሯጠው። ያ ቀላል የሕጻን አዕምሮ ነው።



ማካበድ ደግሞ የጀማሪ አዋቂ ወይም ትንሽ እውቀት ያለው ሰው ባህሪ ነው። ይሄ ሰው በውስብስብ ሕጎች፣ ቢሮክራሲዎች፣ ሥርዓቶች፣ በረቀቁ ትንታኔዎች፣ በከባድ ቋንቋዎች (ቃላቶች) ብቻ ነው ከፍ ማለት የሚችለው፣ መኖር እና አዋቂ ተብሎ መከበር የሚችለው። እነዚህ ዓይነት ሰዎች “ሰንበት ለሰው እንጂ ሰው ለሰንበት የተፈጠረ” አስመስለው ሥርዓት እንደዘረጉት ፈሪሳውያን ናቸው። በማወሳሰብ ብዛት አዋቂ ተብለው ለመኖር የሚቋምጡ።


በእውቀት ላይ ተመስርቶ ቀንበርን ማቅለል ግን የጥበበኛ እና የፍጹም አዋቂ ሰው ባህሪ ነው። እንደዚህ ዓይነት ሰዎች የማንኛውንም ነገር essence ወይም ኮር ዓላማ ወይም ዋነኛ ግብ ለማወቅ የሚጥሩ ሰዎች ናቸው። ያን ጠንቅቀው ካወቁ በኋላ፣ ዓላማውን በተሻለ መንገድ፣ ከድሮው በቀለለ ሂደት ለማሳካት የሚጥሩ ናቸው።

በተለያዩ ርዕሶች ዙሪያ ጹሁፎቼን በቴሌግራም ገጼ ማግኘት ትችላላችሁ።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 3 min read
ree

በዚህ ሰሞን ሁለት ታላላቅ አሜሪካውያን ሞተዋል። አንደኛው የአሜሪካ ቢዝነስ ላይ ኃያል ተጽዕኖ ያሳደረ ሲሆን፣ ሌላኛው ደግሞ የ12 የአሜሪካ ፕሬዝዳንቶች የውጭ ጉዳይ እና የብሔራዊ ደኅንነት ፖሊሲ አማካሪ የነበረ ነው። ቻርሊ መንገር በ99 ዓመቱ ሲሞት፣ ሄነሪ ኪሲንጀር በ100 ዓመቱ ሞቷል።


በኖሩበት ዘመን ልክ ተጽዕኖ የፈጠሩ፣ በተሰማሩበት መስክ አስገራሚ ለውጥ ማምጣት የቻሉ ናቸው። ሕይወታቸው እስከሚያልፍ ድረስ ሰዎች የሚሰሟቸው ነበሩ። ሌላኛው አሜሪካዊ ሙሁር ናሲም ታሌብ ስለቻርሊ እና ኪሲንጀር ሲናገር “አንደኛው ወደ ገነት ሌላኛው ወደ ሲዖል እንደሄዱ የታወቀ ቢሆንም፣ ሁለቱም ግን በዚህ ዓለም ቆይታቸው በሚያዋዥቅ ሙሁራዊ እንቅስቃሴ (athletic activities) ጊዜያቸውን አላጠፉም” ይላል። ከሁለቱም የምንማረው ነገር ቢኖር፤ እኛ ኢትዮጵያውያን በከፍተኛ ደረጀ የጎደለን ነገርን ነው። አንድን ነገር አድምቶ የመረዳት እና ከሥር መሰረቱ የማወቅ፣ ከዛ ሰው ወደደን ጠላን ለሚል ጊዜያዊ ሁካታ ሳይሆን ፥ በጽንአት በዛ አቋም መቆምን ነው። ማለትም ለጊዜያዊ ትክክለኝነት ስንል፣ ከጥልቀት ምርምር እና መረዳት በኋላ የያዝነውን አስተሳሰብ አለመለወጥ። ለዘላቂ ጥቅም ጠላት የሆነ አንድ ነገር አለ፣ ሕዝባዊነት ነው። ለጊዜው ሞኝ እና ስህተተኛ ሆኖ ለመቆጠር ያልደፈረ ሰው፣ ለረጅም ጊዜ የሚዘልቅ ግብን ማሳካት አይቻለውም። ቻርሊም ሆነ ኪሲንጀር በተሰማሩበት ሕይወት እንደዛ ነበሩ።



 ለዛሬ እ.ኤ.አ በሜይ 2023 ዓ.ም. ዋረን በፌት እና ቻርሊ መንገር ከበርክሸር ኢንቬስተሮች ጋር ባደረጉት የሁለት ቀን ስብሰባ ወቅት ከተናገሩት እና በጊዜው ለጥቂት ወዳጆቼ ያጋራውትን አጋራችኋለው። ከድንቁ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ አሳቢ ኪሲንጀር ደግሞ አንድ ከአገራችን ወቅታዊ ሁኔታ ጋር የሚመሳሰል የተናገረውን ነጥብ በቁጥር ዘጠኝ ላይ አክያለሁ። መልካም ንባብ።

ዋረን በፌት 92 ዓመቱ ሲሆን ፥ ቻርሊ መንገር ደግሞ 99 ዓመቱ ነው። ሁለቱም ከ20ዎቹ ዓመታቸው ጀምሮ ኢንቬስተሮች ሲሆኑ ፥ ከ50 ዓመት በላይ ቢሊየነር የሆኑ ጥቂት አሜሪካኖች ውስጥ በመጀመሪያው ረድፍ ስማቸው የሚቀመጥ ነው። ቻርሊ እና ዋረን በርክሽርን (ኮካ ኮላ እና አፕል ስልክን ጨምሮ ትልልቅ ኢንቨስትመንቶች ውስጥ የአንበሳው ድርሻ የያዘ ድርጅት ነው) በሚመሩበት ወቅት፣ ድርጅቱ 2,000,000% መነሻ ኢንቨስትመንቱ ላይ መመለስ ችለዋል። ትላንት ካነሱት ወሳኝ ነጥቦች ፥ በሕይወት እነዚህን ካደረጋቹ ስኬታማ ትሆናላችሁ ብለዋል፤


1) ወጪያቹ ከገቢያችሁ ማነስ አለበት። ቀሪውን ገንዘብ በጥንቃቄ ኢንቬስት አድርጉት፣


2) ከልጅነቴ ጀምሮ የተማርኩት ነገር በሕይወት የሚመጡልኝ ጠቃሚ ዕድሎች ጥቂት እንደሆኑ ነው፣ ጥበቡ እነዚህን ጥቂት ዕድሎች እንዳያመልጡን መዘጋጀት ላይ ነው። ይሄን የኢንቨስትመንት ካውንስል ላይ ሲናገሩ አትሰሟቸውም፣ እነሱ የሚመስላቸው ሚሊዮን ነገሮችን በማጥናት ሚሊዮን ነገሮችን ማግኘት የሚቻል ነው።


3) በየዕለቱ ከመተኛታችሁ በፊት የዛ ቀን ስትነሱ ከነበራችሁ እውቀት ትንሽ አዋቂ ሆናችሁ ለመተኛት ቁረጡ፣ ኃላፊነታችሁን በታማኝነት እና በጥሩ ሁኔታ ተወጡ።


በዚህም ሲስተማቲካሊ ወደፊት ትጓዛላችሁ፤ የግድ በፍጥነት ላይሆን ይችላል። ነገር ግን ይሄን በማድረጋችሁ ጠንካራ ሥነስርዓት (discipline) ስለምትገነቡ ወደፊት በፍጥነት መስፈንጠር ትችላላችሁ። በየቀኑ አንድ እርምጃ ወደፊት ተጓዙ፣ ቀን በቀን ለማደግ ሞክሩ፤ በመጨረሻ ረዥም ዕድሜ ከኖራችሁ በሕይወት የሚገባችሁን ነገር አታጡም። (ቻርሊ ከፈጣን ዕድገት ይልቅ ሰውን ወደ ግቡ የሚያደርሰው ዝግ ያለ ግን የማይቆም ዕድገት ነው የሚል ፍልስፍና አለው። ሲ ኤስ ሉዊስ ስለሰይጣን ስትራቴጂ ሲናገር “የሰውን ልጅ በርግጠኝነት ሲዖል ማስገባት የሚቻለው በፈጣኑ የክህደት ሃዲድ ሳይሆን፣ ዝግ ብሎ በሚሄደው የክህደት መስመር ነው” ይላል። በርግጥስ ከጥንቸል ይልቅ የአሸነፈችው ያለማቋረጥ ግን ደረጃ በደረጃ የተጓዘችው ኤሊ አይደለች። ዊንስተን ቸርችል ስለአሜሪካ ሲናገር “ቶሎ ለውጥን አይቀበሉም ነገር ግን ሁልጊዜ ትክክለኛው ነገር ላይ ይደርሳሉ” ይላል)።


4) ሰዎችን በፍጹም አትውቀሱ ፥ ሰውን ሳትወቅሱ ጥፋታቸውን ማሳየት ትችላላችሁ፣(የከፍተኛ ትምህርት ዘይቤ በሚለው መጽሐፋቸው ሊቁ እጓለ ገብረዮሐንስ፤ “አንድን አሮጌ ቤት አሮጌ ሳትሉ ማርጀቱን መግለጽ ትችላላችሁ” ይላሉ። “ይሄም አጠገቡ አዲስ ቤት በመገንባት ነው። የዛኔ ያንተን አዲስነት፣ የዛን ቤት አሮጌነትም ይናገራል” ይላሉ። “ነቢይ እና ሕጻን ነው በቀጥታ ሰውን የሚወቅሱት። እኔ ደግሞ ሁለቱንም አይደለውም” ይላሉ ሊቁ። ቻርሊ እና ዋረን የሚሉንም ተመሳሳይ ነው)።


5) በሕይወታችሁ መርዛማ ሰዎችን በፍጥነት አሶግዱአቸው (ተንኮልን እወቁ ግን ተንኮል አትስሩ ፥ የጥፋተኝነት ስሜት እንዲሰማችሁ አድርገው ሊበዘብዟችሁ ያሉ ሰዎችን በተቻለ መጠን ከሕይወታችሁ በቶሎ ቆርጦ መጣል ወሳኝ ነው።)


6) በሞታችሁ ጊዜ እንዲነበብላችሁ የምትፈልጉትን ከአሁኑ ጻፉ (obitury) እና በዛ መሰረት ኑሩ። ያኔ በየቀኑ በጥበብ ታድጋላችሁ።


7) ዕዳ ውስጥ ፈጽሞ አትግቡ ፥ አንዴ ከገባችሁ መውጫ የለውም ምን አልባት ቤት መግዛት ላይ በዕዳ ልታደርጉት ትችላላቹሁ ከዛ ውጪ ግን ፈጽሞ።


8. የምታደርጉትን ሁሉ ይሄን ነገር በየቀኑ እያደረኩኝ ብቀጥል የዛሬ አስር ዓመት የት ያደርሰኛል ብላችሁ ጠይቁ። ያኔ ነው ዛሬ ላይ ደደብ የሆነ ነገር ከመስራት የምትቆጠቡት። በሁሉም ነገር የረዥም ጊዜ እይታ ይኑራችሁ።


9) ኪሲንጀር ከጎቴ (Goithe) አዘውትሮ የሚጠቅሰው አባባል አለው፣ “በፍትሕ እና በሥርዓት (order) መካከል ምርጫ ቢሰጠኝ፣ ሥርዓትን ነው የምመርጠው። ምክንያቱም አንዴ ሥርዓት አልበኝነት ከነገሰ ለፍትሕ ቦታ የለውም። (ኪሲንጀር በዚህ ሳምንት ቢሞትም ይሄ አባባሉ ግን በዓብይ ኢትዮጵያ ዛሬ እየኖርነው ነው። ሰው “ምን ነው ሁሉ ነገር ቀርቶብኝ በሰላም ወጥቼ በሰላም በገባው” እያለ ነው፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ መሞቱ ብቻ አይደለም ዛሬ ያማረረው። ገዳዩ መብዛቱ እንጂ። አንድ ገዳይ ቢቻ ቢኖር ያን መንግስት ብሎ ይታዘዝለት እና የሚፈልገውን ያህል ይገብርለት ነበር። ሥርዓት አልበኝነት ባለበት ፍትሕ ሆነ ዲሞክራሲ ቅንጦት ናቸው። ሥርዓት ባለበት ግን ቢያንስ ቢያንስ የተገደበ ፍትሕ በርግጠኝነት አለ)።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 6 min read
ree

የዶ/ር ተቀዳ የተፈጸሙት ትንቢቶች እና እንዳይፈጸም መጸለይ እና መሥራት ያለብን ቀሪው ትንቢት

መምርህ ብርሃኑ አድማስ ሰው በእውነተኛ እውቀት ሲያድግ ከእውነት (ከእግዚአብሔር ጋር) ይገናኛል ፥ ካዛ በፊት የማያውቀው ከሆነ ይላል። ዶ/ር ተቀዳ እንደ እኔ ያ የእውቀት ማማ ላይ የደረሰ ሰው። ዶ/ር ተቀዳ ሁላችን በዓብይ እና ተከትሎት በመጣው ለውጥ ስናብድ፣ ሀገርን ያለአስተዋይ የማይተዋት አለና፣ እምብዛም ለሕዝብ የሚውል ነገር የማይጽፈው እውነተኛው ሙሁር ብዕሩን አነሳ። ለጹሁፍ ርዕስ የከበደችው የዓብይ ኢትዮጵያ ሙሁሩንም አስጨነቀችው መሰለኝ ረዥም ርዕስ ሰጠው ለዚህ ረዥም ጹሁፍ። “የዛሬይቷ ኢትዮጵያ እንቆቅልሽ --- የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ --- ለኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ እና የሀገራዊ ደኅንነት ፍኖተ ካርት ፍለጋ --- የሚል ርዕስ ሰጠው ለዛ ረዥም ማስጠንቀቂያ ጹሁፍ።



በኢትዮጵያ ታሪክ እንደዚህ ዓይነት ከፍተኛ ቅቡልነትን ይዞ፣ ከጫፍ እስከ ጫፍ አስደማሚ ድጋፍ ይዞ የተነሳውን ሰውዬ ፥ “ድንቅ ነው ያገኘኸው ድጋፍ፣ ይሄ ልዩ ነው ግና ተጠንቀቅ፣ የሕዝብ ድጋፍ እንደሸንበቆ ነው ፥ ዘላለም አይቆይም፤ አረ ዘላለም አይደለም ብዙም አይዘልቅም” አለው። አንዳርጋቸው ጽጌ የለ፣ ሻለቃ ዳዊት የለ፣ ዮናስ ብሩ (ኮኪ አቤሴሎም) የለ፣ መስፍን ነጋሽ ወይም አብይ ተክለማርያም፣ ታደሰ ብሩ የለ ኮነሬል ጎሹ ወልዴ፣ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም የለ “ኢትዮጵያ ሆይ ደስ ይበልሽ ፥ ከፈርዖን ቤት አሻጋሪሽን ሙሴሽን አገኘሽ” ሲሏት ፥ ዶ/ር ተቀዳ ግን ንጉሱ ራቆቱን ሊሆን ይችላል አለን።



ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የማነባቸውን ነገሮች በጣም እየተጠነቀኩኝ ነው፤ ጊዜ ካልተረፈኝ በቀር ስለአሁን ሁኔታ የሚተነትኑ የፖለቲካ ጹሁፎችን እያሶገድኩኝ ነው። በተቻለ መጠን የአሁንን ሁኔታ ለመረዳት የዛሬ አስር እና ሃያ ዓመት ተጽፈው አሁን ድረስ መነጋገሪያ የሆኑ ጹሁፎችን እና መጽሐፎችን ነው አንስቼ የማነበው። የምጽፈውንም ነገር ስጽፍ ይሄን የምጽፈውን የዛሬ አስር እና ሃያ ዓመት አንድ ሰው ቢያነበው ምን ያህል ትርጉም ይሰጣል ብዬ በማሰብ ነው። የዶ/ር ተቀዳን ጹሁፍ እንደወጣ ነበር ያነበብኩት። የሙሴ ተከታይ ነበርኩና፣ ምንም እንኳ ምን ዓይነት ኢንቴሌክቿል ካሊበር እና ስብዕና ያለው ሰው መሆኑን ባውቅም ፥ ለውጡን ግን እንዲነካብኝ አልፈለኩም። ስለዚህ ከምር ሳልወስደው ቀረው።



ከጠንካራ ንባብ ዘወር ማለት ስፈልግ ወደትዊተር መንደር ስሄድ በመሐመድ ኡመር የተጻፈውን እና በፎሬን ፖሊሲ ድረገጽ ላይ የወጣውን ጹሁፍ አገኘውት በዚህ ሰሞን። “ኢትዮጵያ እና ኤርትራ ወደ ጦርነት እየሄዱ ነውን?” ይላል መሐመድ፤ አካባቢውን በጥልቀት የሚያውቀው እና የኤርትራ ነጻነት ግንባር የቀድሞ አባል የነበረው መሐመድ፤ ይሄ ጹሁፍ አዲስ መረጃ ባይሰጠኝም፤ ተቀዳን ግን አስታወሰኝ። ዶ/ር ተቀዳ የኖቤል ፕራዝ ኮሚቴ አብይ ከኤርትራ ጋር ለፈጠረው ሰላም በሚል እ.ኤ.አ. በዲሴምበር 2019 ሽልማት ሳይሰጠው በፊት ፥ “ሁለቱ ሀገሮች ድጋሚ ወደ ጦርነት ወይም ወደነበሩበት የቁርሾ ሁኔታ የሚገቡበት መንገድ ዝግ አይደለም!” ብሎ ነበር የመከረው።


ሁለተኛ ትንቢት መሆኑ ነው። የመጀመሪያው “ይሄ የሕዝብ ድጋፋ ይከስማል” አለው፤ “አረ እንደውም ብዙም አይቆይም” አለ። በኢትዮጵያ ታሪክ በዚህ ደረጃ ተደግፎ የማያውቀው ሰውዬ በኢትዮጵያ ታሪክ እንደሱ ተጠልቶ ወደማያውቅ ደረጃ በፍጥነት እየደረሰ ነው (እስካሁንም ካልደረሰ)። ዶ/ር ተቀዳ ሁለተኛ ያለው የኢትዮጵያ እና ኤርትራ ጦርነት ትላንት የተነሳው በአንድ እና አንድ ምክንያት ብቻ ነበር። ግንኙነቱ የሁለት ሀገሮች ግንኙነት ሳይሆን የሁለት መሪዎች፣በዛ ቢባል የሁለት ፓርቲዎች ስለሆነ ነበር። ሰዎች ደግሞ ተቋሞች አይደሉም፤ ለራሳቸው በማይገነዘቡት ሁኔታ ጠዋት ከተፋቀሩት ጋር ማታ ተጣልተው ያድራሉ፤ ስለዚህ ከትላንት ካልተማርን ታሪክን እንደግማለን አለን። ደገምን። መድገም የማይሰለቸን እኛ። ዳንኤል ክብረት 70 ዓመት ይብቃችሁ ብሎ ዲያስፖራዎችን በሚገርም እውነት ተችቷል በዚህ ሰሞን። ዳንኤል ምን አልባትም ዓብይ ከመጣ በኋላ የጻፈው ምርጥ እና ትክክለኛ ጹሁፍ ይሄ ብቻ ይመስለኛል። ዳንኤል ግን እንደዛች ዝንጀሮ በመስታወት ውስጥ ያየው የዲያስፖራን የ70 ዓመት ውድቀት እንጂ ለእኛ የደብተራዎች የ2000 ዓመት ውድቀት እንዴት ኩልል ብሎ እየታየን መሆኑን ዘንግቶታል። ሀገሬ ለሺ ዘመናት እየደጋገመች ከትላንት ስህተት መማር ተስኗት እንድትወድቅ ያደረጋት የዳንኤል ክብረት ዓይነት ሰው የሀገሪቷ መሪ መቀመጫ ሥር ገብቶ፥ ለክርስቶስ መስቀል እና ለቤተክርስቲያን ያለንን እምነት ለቤተመንግስት እንድንሰጥ የበዘበዙን ደብተራዎች በመብዛታቸው እንጂ 70 ዓመት ያስቆጠረው ዲያስፖራ አይደለም።


ዲያስፖራው ስህተት የለበትም እያልኩኝ አይደለም፣ በዛማ ከዳንኤል ክብረት ጋር 100% በተጠጋ መጠን እስማማለሁ፤ ግን ለሺ ዓመት ውድቀት የአክሱም ላሊበላ ስልጣኔ ዕምብርት የነበረችውን ሀገሬን የ፸ ዓመት ዕድሜ ብቻ ያለውን መክሰስ የደብተራነት የንጉሱን ፊት እያዩ የመጻፍ አባዜ ነው። ያ ነው የሀገሬ ገዳይ፤ ያ ነው ኢትዮጵያችንን ደጋግሞ የጣላት። የደብተራነት አድርባይነት። ንጉሱ ራቆቱን ሳለ ለመስቀሉ የሰጠነውን እምነት ራቆቱን ለቆመው ንጉስ እንድንሰጥም እምነታችንን የበዘበዙት የደብተራዎች ሴራ ነው የሀገሬ አንዱ የመክሸፍ ምስጢር። (ብዙ ሰዎች ደብተራዎች ሲባል የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ነው የሚመስላቸው። እውነት ለመናገር ቤተክርስቲያኒቷ ነች ሀገራችን እስካሁን ሳትጠፋ እንድትቀጥል የረዳቻት። በዚህ ጹሁፍ ድብተራዎች የምላቸው የቤተክርስቲያንን እውቀት እና ያገኙትን ትምህርት እውነትን ለማገልገል ሳይሆን የገዢዎች ፍላጎትን ለማርካት ያዋሉትን ነው። ደብተራዎች በቀደመው ጊዜ ከቤተክርስቲያን ነበር የሚወጡት ብቸኛዋ የትምህርት ማዕከል ስለነበረች፤ አሁን ግን እነዚህን intellectual prostitutes እንላቸዋለን።)



ቢያውቀው ዶ/ር ተቀዳ ነበር የዓብይ እውነተኛ ወዳጅ። ይሄ የሕዝብ ድጋፍ ራስህን ልዩ አድርገህ እንድትቆጥር ይፈትንሃል፤ በአግባቡ ከተጠቀምክበት ግን ማለትም በግልጽነት እና በጥበብ ተቋሞችን ለመገንባት ከተጠቀምክበት ኢትዮጵያን ወደ ዲሞክራሲ፣ ወደ ተረጋጋ ሰላም እና ዘላቂ ልማት መውሰድ ትችላለህ አለው (“If this asset is used properly, transparently and wisely—which, among other things, requires prioritizing institution building and eschewal of the temptations of self-aggrandizement”)። ይሄን ምክር በነጻ ሊለግስህ የሚችለው ውለታ የዋልክለት ሰው ብቻ ነው። ዶ/ር ተቀዳ ግን “በኤርትራ ላይ የተጣለውን ማዕቀብ ተቋማዊ ሥርዓትን እና የነገ የኢትዮጵያን ታአማኒነት በማይጎዳ መልኩ ብቻ ነው ማስነሳት ያለብን እንጂ እንደ የሕጻን ልጅ ጨዋታ በብዙ ልፋት የተጣለውን ማዕቀብ በደብዳቤ ብቻ ማንሳት ተገቢ አይደለም” ባለ ፥ በሁለት መስመር ደብዳቤ ከኒውዮርክ አዋራጅ እና ሥርዓትን ባልጠበቀ መልኩ በዓብይ የተነሳ ነበር። መልሶ ጭንቅ ውስጥ ሲገባ ገዱ አንዳርጋቸውን አስልኮበት (በሽማግሌ) ድጋሚ እንዲረዳው ሊጠይቀው ነገር። ዘመኑንን ሁሉ ኢትዮጵያን ያገለገለው ዶ/ር ተቀዳ ግን በዛ ማበድ እና ሳይገባን መከተል ፋሽን በሆነበት ዘመን ነው ፥ “ግድ የለህም ይሄን ነገር ፈር አሲዘው። ተቋማዊ አድርገው። ትላንት ስህተትን ከሰሩ ሰዎች አንተ በምንም አትለይም፣ በእነሱ መንገድ ከሄድክ በመንገዳቸው መጨረሻ እነሱ የገጣማቸውን ነገር ብቻ ነው የምታገኘው” ይለዋል። “ዘላቂ ብሔራዊ ጥቅም እንጂ ዘላቂ ወዳጅ የለም የሚለው የሎርድ ፓልመርስቶን ንግግር ምንም እንኳ አናዳጅ እና ኢሞራላዊ ቢመስልም እውነት መሆኑን ግን መካድ የለብንም” ይላል ዶ/ር ተቀዳ፤ “የኤርትራ ፍላጎት ኢትዮጵያን ዲሞክራሲያዊ ማድረግ ሳይሆን የኢሳያስ የኤርትራ ሕወኃትን የመበቀል ጥማት ነው” ሲለን። እኛ ግን ዜጎቹን ሁሉ አባሮ ሽማግሌ እና አሮጊት ታቅፎ፣ ሲንጋፖር ትሆናለች የተባለችን ሀገር ኦስማን ሳሌ እና የማነ ገብርመስቀል የሚባሉ ሁለት ሰዎች ብቻ አስከትሎ የሚመራን መሪ ለኢትዮጵያ ብርሃን ይሆናል ብለን ተቀበልን።



የሰው ልጅ ከታወረ እና እውነትን ለማየት ካልፈለገ ፤ ሲ ኤስ ሉዊስ እንዳለው ዓለም በፊቱ እንደ ወረቀት እየተጠቀለለች እንኳ እውነትን አይቶ ከማመን ይልቅ አይ ይሄ ሃሉስኔሽን (hallucination) ነው ይላል። የራሱን ሀገር ሰው አልባ ያደረገ መሪ በምን ተዓምር ነው 30 ዓመት መሉ የተዋጋትን ኢትዮጵያ ከሀገሩ በላይ የሚያዝንላት? የኢትዮጵያ መረጋጋት፣ ዲሞክራሲያዊ መሆን እና የኢኮኖሚ ዕድገት ትልቁ አደጋ ለኢሳይያስ መሆኑን ለመዘንጋት እንደ አንዳርጋቸው ጽጌ መታወር ያስፈልጋል።

ዶ/ር ተቀዳ የአሜሪካ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ እና ስትራቴጂ የሚጠነሰስበት “the Council on Foreign Relations” ፕሬዝዳንት የሆነው ሪቻርድ ሀስ “ፎሬን ፖሊሲ የሚጀምረው ከቤት ነው” ብሎ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ መጀመር ያለበት የውስጥን ቤት ሥርዓት በማስያዝ ነው በሚል በ2013 ለመጀመሪያ ጊዜ አዲስ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ እና ስትራቴጂ አስተሳሰብ አስተዋኩኝ ብሎ ከመነሳቱ 9 ዓመት በፊት፤ መለስ ዜናዊ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲያችን እና ስትራቴጂያችን መነሳት ያለበት የውስጥ ቤትን በማቃናት እና ሥርዓት በማስያዝ ነው ብሎን ነበር ይለናል።(እንደአንዳንዶች ዶ/ር ተቀዳ ነበር የጻፈው ያን ድንቅ ፖሊሲ፤ ይሄ ባይሆን እንኳ ትልቅ ግብአት እንደነበረው አልጠራጠርም። ይሄን የምለው መለስ ዜናዊ ያን የማፍለቅ የአዕምሮ አቅም የለውም እያልኩኝ አይደለም። ከዛም በላይ መስራት እንደሚችል ያሳየን ይመስለኛል።)። ዶ/ር ተቀዳ ፖሊሲውን ቢያደንቅም ፥ ያን ፖሊሲ መሬት ለማውረድ የሰነፈውን ኢህአዴግን ግን አልራራለትም። ይሄም ይመስለኛ የዚህ ጹሁፍ ውበት ፥ እውነትን ለራስም ሲሆን አለመሰወር። ለራስም ቢሆን አለመራራት።


በርግጥ ይሄ ጸሐፊ ዓብይ አህመድ ያመጣው የለውጥ ማዕበል ኢትዮጵያ ውስጥ ሲቀጣጠል፤ የሕወኃት አባል ከነበረ አለቃዬ ጋር ዶ/ር ተቀዳን በኒውዮርክ በምሳ ግብዣ ላይ ለማውራት ዕድሉን አግኝተን ነበር። ስለኤርትራ አለቃዬ ሲጠይቀው፤ ዶ/ር ተቀዳ “ችግራችን በዋነኛነት ኤርትራ አይደለችም፤ ወደውጭ መመልከት ተው፤ አሁን ያለውን ነውጥ ራስን በማቃናት እና በመታረም ፈር ማስያዝ ካልቻላቹ ከኤርትራ በላይ ለሀገሪቱ አደጋው ኢህአዴግ ነው” ነበር ያለው። የሚዲያ ሰው ግን ስላልነበረ፣ ይሄን አይነት የእውነት ስብዕናውን የሚያውቁት ጥቂቶች ናቸው። ይሄ ማለት ስህተት የለበትም ወይም ንጹሁ ነው ለማለት አይደለም፤ በዲፕሎማቲክ አገልግሎቱ ኢትዮጵያን ከማስቀደም ጎድሎ አያውቅም ለማለት እንጂ።



ዶ/ር ተቀዳ በመጨረሻ ፥ ስለኢትዮጵያ መጻኢ ዕድል በማሰብ እንቅልፍ አልባ ማታዋችን እንደሚያሳልፍ ገልጾ ፥ በመጨረሻ ትንቢት ጹሁፉን ይዘጋዋል። “ይሄን የለውጥ ዕድል ከበቀል በጸዳ መንፈስ ካልተጠቀምንበት፣ ተቋሞችን ለመገንባት ካላዋልነው፣ ሕወኃት እንዳደረገው ስለተዋጋቸው ብቻ ታላቅ የነበረውን የመከላከያ ሠራዊት እንዳፈረሰው፣ አሁንም ያለው የለውጥ ኃይል ያን ዓይነት ስህተት ከደገመ ‘ኢትዮጵያችን ሁለተኛ ይሄን የመሰለ ዕድል ላታገኝ ትችላለች!’” አለን።



ሀገሬ ዘላለማዊ እንዳልሆነች አውቃለሁ፤ ለእኔም ድንኳኔ እንጂ ዘላቂ ሀገሪ እንዳልሆነች አልዘነጋም፤ ነገር ግን ይሄ የተቀዳ ትንቢት ግን እንዳይሰምር የትላንት ትንቢቱ እንዳይሰምር ከተመኘውበት እጥፍ እመኛለሁ። ኢትዮጵያኖች የገጠመን ነገር የኛም ክፋት ውጤት ነው። ከዚህ መከራ ሊያወጣን እግዚአብሔር የታመነ ነው። ፍቅሩ እና ማዳኑ ግን ያለቅድመ ሁኔታ አይደለም። ሀብታሞች (ነጋዴዎች) በዚህ ደረጃ ጨካኝ ሆነው ፍጹም ለሆነ ስግብግብ ትርፍ የሚራወጡባት፣ የክርስቶስን መስቀል የተሸከሙ አባቶች በዘር እና ጎጥ ተለያይተው እንደ ድንጋይ መግለጫ በሚወራወሩበት ሁኔታ፣ የሀሰት ሌባ ነብዮች በዚህ ደረጃ ሀገሪቷ ላይ ሲፈነጩ እና ትውልድ ሲያከስሙ፤ እኛም የሚናገሩት ለጆሮአችን ደስ ስላለን እየተከተልናቸው፣ የመንግስት ባለስልጣናት የወጣላቸው ዘራፊ ሆነው፣ ወንድማማችነት ጠፍቶ ዘረኝነት የነገሰበት ሀገርን የሚታደግ አምላክ የለንም። ዶ/ር ተቀዳ እንዳለን እሴቶቻችንን እንፈትሽ ፥ “የትኛውም የውጭም ሆነ የሀገር ውስጥ የደህንነት ፖሊሲ የጥንካሬው ደረጃ በቆመባቸው እሴቶቹ (values) ጥንካሬ የሚለካ ነው” ነው ያለን ዶ/ር ተቀዳ።



የሀገራችንን ዘላቂ ጥቅም ማስቀደም ካልቻልን፣ ስለእውነት ለመናገር ካልደፈርን፣ ወገናችንን ለመውደድ ካልፈቀድን ኢትዮጵያን ነገ አናያትም ብቻ አይደለም ሶማሌ እና የመንን ገነት እናስመስላቸዋለን። ለእኔ ዓብይ አህመድ የክፋታችን እና የእውቀት አልባነታችን ውጤት እንጂ ምንጭ አይደለም። ዓብይ አህመድን ለዚህ ውድቀት ማውገዝ ሰውዬው የሌለውን አቅም እና ችሎታ መስጠት ነው። ለመገንባት ብቻ አይደለም ለማፍረስም ችሎታ ይጠይቃል። እሱ ሁሉቱም የሌለው ነው። ላለንበት ሁኔታ ኃላፊነት ወስደን ሀገራችንን እንታደጋት።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page