top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 4 min read

የሰንበት ዕይታ - 7


አንድ ወዳጄ ስለትችት ወይም ሰዎችን ስለመተቸት እንድጽፍ ጠየቀኝ። በርግጥ የወዳጄ ትልቁ ጥያቄ ያለአቅም እና እውቀት ስለመተቸት ነው። እኔ እንደሚገባኝ ትችት ማለት አንድ ነገር ከምንጠብቀው ደረጃ በታች ሲሆን ወይም ትችት የሚቀርብበት ማየት ያለበትን ነገር ሳያይ ሲቀር ወይም የሆነውን ነገር በእውቀትም ሆነ ያለ እውቀት ሲያጣምመው የምናቀርበው ነቀፋ ወይም ስህተትን በጠንካራ ድምጸት ማሳየት ነው። ስለዚህ ለመተቸት እኔም ሆነ ተተቺው የተቀበልነው የጋራ ደረጃ (standard) ሊኖረን ይገባል። ለምሳሌ ይሄ አባት ተሳስተዋል ለማለት ፥ የሆኑትን ወይም የተናገሩትን ነገር ከእኔም ሆነ ከዛ አባት ውጪ ከሆነ ደረጃ (standard) ጋር በማዛመድ ነው ተሳስተዋል ማለት የምችለው። ያ ደረጃ ከሌለ ልል የምችለው ብቸኛ ነገር ያ አባት ተሳስተዋል ሳይሆን ለእኔ አልተመቹኝም ነው።


ምክንያቱም ደረጃው የጋራ ሳይሆን የእኔ ስሜት እና እውቀት ነው፤ ያ ስሜት እና እወቀት ከሌላው ጋር የምጋራው የጋራችን ካልሆነ ፥ እኛን አባት ስህተት ሊያስብል የሚችል ምንም ነገር የለም። በርግጥ ሌላ ክርክር ሊከፈት ይችላል። በራሳቸው ደረጃ (standard) ነው የመዘንኳቸው ሊል ይችላል። ያ ቢሆን ራሱ “የትኛው የራሳቸው ስታንዳርድ?” ትላንት የተናገሩት ወይስ ዛሬ ከተናገሩት ወይም ሆነው በተገኙት ስታንዳርድ? ትላንት ከተናገሩት ከሆነ ስህተቱ የሳቸው ሳይሆን የኛ ነው። ምክንያቱም እየተቸን ያለነው የትላንቱን ሰው ሳይሆን የዛሬውን ሰው ነው። በትላንት ንግግር መተቸት ያለበት የትላንቱ ሰው ነው እንጂ የዛሬው አይደለም። ስለዚህ ዛሬ ከተናገሩት ከሆነ ደግሞ ምንም የሚያስተች ነገር የለም ምክንያቱም ዛሬ የተናገሩት ነው የሳቸው ደረጃ።



ስለዚህ ትችት ትርጉም እንዲኖረው የጋራ የሆነ ሚዛን ያስፈልጋል። ሁለት ሲደመር ሁለት አምስት ነው የሚልን ሰው ልክ አይደለህም የምንለው የትም ቦታ ያ አራት መሆን አለበት ብለን ስለተስማማን ነው። ግን ያ የኛ ስምምነት ብቻ አይደለም፤ ይልቁስ የኛ ስምምነት በራሱ የጸናው በሆነው ነገር ነው። ሁላችን ብንስማማ እንኳ ሁለት ሲደመር ሁለትን አምስት ማድረግ አንችልም። በንድፈ ሀሳብ ተስማምተን ወደ ተግባር ስናወርደው ይከሽፋል። አራት ብርቱካንን ስለተስማማን አምስት ማድረግ ፈጽሞ አንችልም። አምስት ሰው አስቀምጠን አራቱን አንድ አንድ ለአምስቱም ማከፋፋል አንችልም። ስለዚህ ስምምነታችን ከኛ ስምምነት ውጪ ባለ እውነት፣ በራሱ መቆም በሚችል እውነት እስካልተደገፈ ድረስ ይፈርሳል። ማንም ማንንም ከመሬት ተነስቶ መጉዳት የለበትም የሚል ሰው ይሄን ለማለትኽ መሠረትኽ ምንድነው ብንለው፤ እንደዛ ይሰማኛል ብቻ ካለን ፥ ሌላውን ያለምንም ምክንያት የሚጎዳ ሰውም እንደዛ ይሰማኛል ብሎ ቢጎዳ ስህተቱ የቱ ጋር ነው? ነገር ግን ከዚህ የጠለቀ እውነት ሊኖረው ይገባል።



ለምሳሌ በልጅነቱ ከጓደኞቹ ጋር በመሆን የሰው ጓሮ ገብቶ ፍራፍሬ የሰረቀው አውግስጢኖስ ፥ ሌብነት መጥፎ መሆኑን ማንም አስተማሪ ሳይኖር እናውቃለን ይላል። ይሄን ሲመልስ ሌባ እንኳን ሌላ ሰው መጥቶ የእሱን እቃ እንዲሰርቅበት አይፈቅድም። ሌባ ሆኖ ሳለ እንዲሰረቅ አለመፈለጉ የድርጊቱን ሁሉንአቀፋዊ መጥፎነት (universal evilness) ይናገራል። በጎ ነገር ስናደርግ ያን በጎ ነገር ሰዎች ለእኛ እንዲያደርጉልን እንፈልጋለን። ቢያንስ ተመሳሳይ ነገር እንዲመልሱልን ባንፈልግ እንኳ ያ የበጎነት ስሜት ግን ስለእኛም እንዲያድርባቸው እንሻለን። ማናችንም ግን ክፉ ነገር ስናደርግ እነዛ ሰዎች ያን ክፉ ነገር በእኛ ላይ እንዲያደርጉብን አንሻም።



ይሄን ሁሉ ያልኩት ለመተቸት የጋራ የሆነ ደረጃ (standard) ሊኖረን እንደሚገባ ለማሳየት ነው። ድልድይን በሙስና ያለጥራት የሚሰራ መሐንዲስ፤ ሌሎች መሐንዲሶች ግን ድልድዮችን በጥራት እንዲሰሩ ይሻል። ያ ግን የሱ ፍላጎት ብቻ አይደለም። ከሱ ውጪ ያለ ፍላጎት ነው። የሱ ፍላጎትማ በሙስና ለጥራት ባለመጨነቅ መስራት ነው። ግን ከተግባሩ በተቃራኒ ይፈልጋል። ምክንያቱም ያ ፍላጎቱ ተራ ፍላጎት ብቻ አይደለም። ከሱ እና ከሌሎች ውጪ ባለ እውነት ላይ የቆመ እንጂ። ያ እውነት ደግሞ ጥራት ያለው ድልድይ ነው፤ እሱንም ሆነ ቤተሰቦቹን ያለስጋት በዛ ድልድይ የሚያሻግረው። እውነት የምንለው ነገር ከኛ የማድረግ እና ያለማድረግ ተጽዕኖ ውጪ ሕልውና ሲኖረው ነው። ለዚህ ነው እውነት የሆነው። በእኔ ማድረግ እና አለማድረግ ስላልተወሰነ። እኔ በሙስና የምሰራ እንኳ ቢሆን ፥ የእኔ ድርጊት ተግባሩን ጥሩ እንደማያደርገው ከሌሎች በጠበኩት ደረጃ ገለጥኩኝ። ደረጃው የእኔ ቢሆን ኖሮ ፥ ሌሎች እንዲህ ማድረግ አለባቸው ባላልኩኝ ነበር። ያን ብል እንኳ የሚሰማኝ የለም፣ ሰዎች ችላ ለማለትም ስጋት አይገባቸውም። ደረጃው ግን ሁሉን አቀፍ ስለሆነ ካልተሸሸግን በቀር በይፋ አናደርገውም።



ስለዚህ ትችት ሁልጊዜ ከእኛ እና ከዛ ሰውዬ ተራ ፍላጎት ነጻ ሲሆን ነው ትርጉም የሚኖረው። ካሮት ወዳለው የሚልን ሰው እና ካሮት ስላልወደድን ብቻ አንተቸውም። የእኛ ካሮት አለመውደድ የእኛ ወይም የጥቂቶች ብቻ ስለሆነ ግን አይደለም። ካሮትን መብላት ከምግብነት አንጻርም ጥቅም እንዳለው ስለምንገነዘብ እንጂ። ጥቅሙ ደግሞ በሌሎች ተጓዳኝ የፍትሕ እና የመልካም ሕይወት አኗኗር ላይ ጉዳት ስለሌለውም ጭምር ነው። ማለትም ለምግብነት ጥሩ ሆኖ ሌሎች የመልካም ሕይወት ጉዞዎችን የሚያደፈርስ ቢሆን አንቀበለውም። ይሄ የሚያሳየን እኛ ባናረገው ራሱ የማያሳነቅፍ ነገሮችን ስንዳኝ ምን ያህል ከኛ ውጪ ባለ መለኪያ እንደምንመዝን ነው።



ፍትሐዊ ትችት ሚዛኑ ሁልጊዜ ከተቺው ጊዜያዊ ጥቅም እና መሻት የሚሻገር ነው። ይሄ ማለት አንድን ነገር ተቺው ስለወደደው እና ስለጠላው ሳይሆን ከሱ ውጪ ያለ የፍትሕ እና የእውነት ሚዛን ላይ በማስቀመጥ ነው የሚዳኘው። ከኛ ውጪ ያለን ነገር ደግሞ የምንረዳው ባለን የእውነት እና የፍትሕ ዓይኖች የአድማስ ስፋት እና የሕይወት ልምድ ነው። ልጆችን ብዙ ነገር እንዳያደርጉ የምንከለክለው ያ ነገር በራሱ መጥፎ ስለሆነ ብቻ ላይሆን ይችላል፤ የከለከልናቸው ነገር ያለአግባብ ከተጠቀሙበት የሚያመጣውን ጉዳት በማሰብ እንጂ። ለምሳሌ የሦስት እና አራት ዓመት ልጅ ውጪ ወጥቶ መንገድ እንዳያቋርጥ የምንፈልገው፣ መንገድ ማቋረጥ በራሱ መጥፎ ሆኖ አይደለም። ነገር ግን ዕድሜው ግራ ቀኙን የማየት አቅም ስለማይሰጠው፣ ልሻገር ሲል አደጋ ሊደርስበት እንደሚችል ስለምናውቅ እንጂ።



ያ እውቀታችን ደግሞ ከወላጅነት ከሚመጣ ለኛ ግለሰባዊ ከሆነ መሳሳት ብቻ አይደለም። አደጋ ደርሶ ስላየን እና ራሳቸውን ከአደጋ መከላከል የማይችሉትን ልጆቻችንን አለመጠበቅ መጥፎ ወላጅነትም እንደሆነ ስለምንገነዘብ ነው። ይሄ የሚነግረን ከኛ የሕይወት ልምድ፣ እውቀት፣ የሥራ እና የዕድሜ አድማስ ውጪ የሆኑ ነገሮችን መተቸት ምን ያህል ልክ እንዳልሆነ ነው። ምክንያቱም ትችት ከኛ ውጪ ባለ መስፈርት ሲመዘን ብቻ ነው ፍትሐዊ እና ትክክለኛ ትችት የሚሆነው፤ ያ እንዲሆን ደግሞ ፥ ያ ከኛ ውጪ ስላለ ሚዛን እና ደረጃ ከምንተቸው ሰው የማይተናነስ እውቀት ሊኖረን ይገባል። ካለዛ ግን እያልን ያለነው “ለእኔ አልጣመኝም፣ እኔ ካሮትን አልወድም ስለዚህ ካሮትን የሚወድ ሁሉ መጥፎ ነው” ነው። ያ ደግሞ ትችታችንን ኢፍትሐዊ ያደርገዋል። ስለእኛም ግልብነት ይናገራል። በጠባብ የራስ ፍላጎት ላይ የቆመ ስለሆነ ፍጻሜው እፍረት ነው።



ልጅ በሆንባቸው ዘርፎች ወላጅ የሆኑ ሰዎችን መተቸት ትርጉም አይኖረውም። በእነዚህ ጉዳይ ከትችት ይልቅ መጠየቅ እና ያልገቡንን ለመረዳት መጣር ነው ተገቢው እርምጃ። ከአንድ እውነት ጋር ግን መጋፈጥ አለብን። ያለእውቀት እና ያለምንም ልምድ የሚተቹ ደፋሮች በየትኛውም ጊዜ እንደሚኖሩ። ያ ብቻ አይደለም የእነሱን ስሜት እና ከእነሱ ውጪ ያለን ደረጃ (standard) ለይተው ማየት የማይችሉ ሰዎችም አሉ። ይሄ ማለት ለእነሱ ጆሮ ያልጣማቸውን ሙዚቃ መጥፎ መዚቃ የሚሉ፤ እንዲሁም እነሱ የወደዱትን ሙዚቃ ሰዎች ካልወደዱ የምርጫ ጉዳይ ሳይሆን የደረጃ (standard) ጉዳይ አድርገው የሚደባልቁ ሰዎችም በስፋት አሉ። ገበያ ውስጥ እየገቡ ዝምታን መሻት ቅዠት እንደሆነ ሁሉ፤ የአዕምሮ እና የችሎታ ውጤቶቻችንን ለማህበረሰብ ገበያ እያቀረብን ጉራማይሌ ግብረ መልስ አለመጠበቅ የዋህነት ነው። እያደናገሩ ለሚኖሩ እንጂ የማህበረሰብን የምቾት ሀጢያት እና ያለአዋቂነት ስንፍና እየገለጡ ለመኖር ለቆረጡ ክብር እና አድናቆትን ወዲያው መሻት ከረዥሙ የሰው ልጆች የታሪክ እውነት ጋር መጋጨት ነው። ታሪክ ያሳየን ከሚሰክሩ ጋር አብረው ለሰከሩት ብቻ ነው በጋርዮሽ ሀሳብ የሚሄዱ ስብስቦች ቦታ የሚሰጡት። ባልገባቸው ሰዎች የተሳሳታችሁ ተብለው ለመወቀስ እና እንደ ሞኝ እና ጅል ለጊዜው ለመቆጠር የፈቀዱ ናቸው የዘመናት የማሕበረሰብን ዓይነ ጥላ የሚገፉት። እኛ ግን ለማስተዋል የፈጠንን፤ ለመፍረድ እና ለመናገር የዘገየን እንሁን። ታሪክ ያስተማረን ከዛሬ ደስታ ይልቅ የጸጸት ዕድሜ ረጅም መሆኑን ነው። ቸኩሎ መፈረድ እና መተቸት ለረዥሙ ጸጸት ነው የሚዳርገን።

 
 
 

የሰንበት ዕይታ - 13

ree

መሪ እኛን ካልመሰለ መሪዬ ብሎ መቀበል ከባድ ነው፣ መሪ እኛን ከመሰለ ደግሞ ለምን መሪያችን ይሆናል? ከኛ ከልወጣ እኛን እንዴት ያውቀናል፣ ከኛ ከወጣ ደግሞ እኛን ከዚህ እንዴት ያወጣናል? አብሮን ካልበላ፣ አብሮን ካልጠጣ፣ አብሮን ካልተቸገረ፣ አብሮን ካልዘመረ፣ አብሮን ካልጸለየ የኛ ነገር እንዴት ይገባዋል ብለን እንመን? በሁሉ ነገር ከኛ ካልተለየ ከምንም ነገር እኛን ሊለየን አይችልም! የምናውቀው ነገር ብቻ ነው የሚስበን ፥ ልዩ የሆነ ነገር ብቻ ነው የሚማርከን። የምናውቀው ልዩ ካልሆነ፣ ልዩ የሆነው የምናውቀው ካልሆነ ዓይናችንን አይስበውም፣ አዕምሮአችንን አይማርከውም። ራሱን ድኋ ካደረገ ሀብታም ነው ማለት ነው፣ እረኞች ከሰገዱለት የበጎቹ ጌታ እርሱ ነው ማለት ነው፣ ጥበበኞች ከተንበረከኩለት ጥበብ እርሱ ነው ማለት ነው፣ ካህናት ካልሄዱ ራሱ ካህን ነው ማለት ነው፣ በእንግዶች ማደሪያ ስፍራ ከሌለው እርሱ እንግዳ አይደለም ማለት ነው። ስላላወቅነው እርሱ እንደሆነ አወቅነው፣ ስላሳደድነው እውነት እንደሆነ ገባን፣ ወደ ግብጽ በመውረዱ የአባቶቻችን ዘመድ እንደሆነ ተገለጠልን። ወደ ግብጽ ስላልጠራን፣ በግብጽ ስላላገኘነው ከአባቶቻችን የተለየ እንደሆነ አወቅን። በመመሳሰሉ ሳበን፣ ልዩ በመሆኑ ማረከን።



ሕጻን ተወልዶልና ግን የዘላለም አባት ነው፣ የሰላም አለቃ ነው ግን የኛን ሰላም ያናጋዋል፣ ንጉስ ነው ግን እግራችንን ነው የሚያጥበው፣ አምላክ ነው ግን አምላኬ ለምን ተውከኝ ይላል። ወንድ ልጆች ሲገደሉ አባታችን ሙሴ ወደ ገዳዩ ቤት ገባ፣ ወንድ ልጆች ሲገደሉ ወንዱን ልጅ በመጠቅለያ ይዛ ወደ ግብጽ ወረደች።



አካላዊ ቃል ፥ ቃል አልባ ሕጻን ሆነ፤ ቤት ያልተገኘለት ልደት በሁሉ ቤት የሚከበር ልደት ሆነ። ያለእናት የተወለደው ልጅ፣ ያለ አባት ደግሞ ተወለደ። የሰውን ልጅ በኃጢአቱ ምክንያት ከገነት ያሳደደው አምላክ፣ በሰው ልጅ በንጽህናው ምክንያት ከቤተልሄም ተሳደደ። ለካህናት እና ለጠቢባን ረቂቅ የሆነው ልደት ለእረኞች እና ለበጎቹ ግልጽ ሆነላቸው። ቅርብ ለነበሩት የራቀው ልደቱ ለሩቅ ምስራቆቹ ቅርብ ሆነላቸው። ምድራውያን ከልደቱ ሲሸሹ ሰማያዊያን በቤተልሄም ቆሙ። የሚሰግዱት በሄሮድስ ሲያልፉ የሰገዱት ከሄሮድስ ራቁ። አዋቂዎች ሊሰይፉት ሲነሱ ሕጻናት ስለእሱ ተሰየፉ። ምኞታችንን ሕይወት እንድንነሳው ፥ ሕይወት ያለምኞት ተወለደ።



መንግስቱ የማይታየው ንጉስ፣ አሳዳጃችንን ያሳደደልንን ተሳዳጅ፣ ልብስ አልባው አልባሽ፣ በቤት ያኖረን ቤት ያልተገኘለት። ያን ነው ታናሿ ቤተልሄም የሰጠችኝ ታላቁ ጌታ። ከሁሉ አንሶ የተገለጠውን ከይሁዳ ገዢዎች ከቶ አታንሺም የተባለችው ከተማ ሰጠችን። ከሁሉ ለመብለጥ ከሁሉ ታናሽ ሁኑ፣ ለመቅለል ቀንበሬን ተሸከሙ ፣ ዓለምን ለመውረስ ዓለምን ካዱ ፣ ራሳችሁን ለማዳን ራሳችሁን እጡ፣ ፊተኞች ለመሆን ኋለኞች ሁኑ፣ አለቃ ለመሆን ሠራተኞች ሁኑ የሚለን ሕጻኑ አባት፣ ማረፊያ አልባው አሳራፊ፣ ሰላም የነሳነው የሰላም አለቃ፣ ሄሮድስን የሚሸሽ የዘላለም ንጉስ፣ የራሱ የሆኑት ያላወቁት ከርሱ ያልሆኑት ያወቁት በዳዊት ከተማ ተወለደ።



መልካም ገና!!!

 
 
 
ree

የሰንበት ዕይታ - 10


የትኛውም ሰዎች ይሄን አድርጉ ሲባሉ ደስ አይላቸውም። ሰዎች በራሳቸው መወሰን እንደሚችሉ እና ሙሉ ነጻነት እንዳላቸው ማመን ይፈልጋሉ። ልጆች እንኳ እንደሚገረፉ እያወቁ አታድርጉ የሚባሉትን ነገር ነው የሚያደርጉት፤ ይሄም የሰው ልጅ በባህሪው ይሄን አድርግ ወይም አታድርግ ሲባል ስለማይወድ ነው። ለራሱ የሚጠቅም እንኳ ቢሆን ከሚታዘዝ ይልቅ ነጻነቱን ይመርጣል።

የማስታወቂያ ሰዎች ይሄን የሰው ልጅ ባህሪ ጠንቅቀው የተገነዘቡ ናቸው። ለዚህ ነው ጥሩ ማስታወቂያ የሚሰሩ ሰዎች ፥ ሰዎች ያን ዕቃን ግዙ ሳይሆን የሚሏቸው በመግዛት የሚገኘውን ደስታ፣ እርካታ እና ጥቅም ነው የሚያሳዩአቸሁ።


ኢትዮጵያ እያለው የተማረ ሰው ቢዝነስ እንደማይችል ይነገር ነበር። በከፊል እውነት ነው። አሜሪካ ስመጣ ግን ፥ በተለይ ቢዝነስ ስኩል ስገባ የአሜሪካ ኢንቬስተሮች አንዳች ነገር ያለዕውቀት እንደማያደርጉ አየሁ። ለምሳሌ በአሜሪካ ውስጥ ከአንድ እስከ ሦስት ያሉ ባለሀብቶች ሁሉም የIQ መጠናቸው መቶ ሀምሳ ወይም ከዛ በላይ ነው፣ በጣም ምጡቆች ናቸው። ይሄን ለምን አነሳው? ምንም ነገር በእውቀት ሲሰራ የተለየ እና ዘላቂ ውጤት እንዳለው ለማሳየት ነው። ለምሳሌ ቢዝነስ የሰውን ስነ-ልቦና በአግባቡ ማወቅ እና ራስን መግዛት ይጠይቃል። ዴቪድ ኦግሊቪ የተባለ ታዋቂ አሜሪካዊ ጸሐፊ ያሳየውን የቢዝነስ ጥበብ እሱም “አሳይ እንጂ አትንገር - Show but don’t tell” የሚለውን እንይ።



ዴቪድ ከቢሮው ሲወጣ አንድ ዓይነ ስውር ለማኝ ሰው በሚመላለስበት መንገድ ላይ “ዓይነ ስውር ነኝ እርዱኝ - I am blind please help” የሚል በካርቶኒ የተጻፈ ማስታወቂያ ይዞ ቁጭ ብሏል። አንድም ሰው ገንዘብ የሰጠው የለም። ለብዙ ሰዓት እንደተቀመጠ ግን ያስታውቃል። ዴቪድ ዓይነስውሩን ተጠጋው እና “ገንዘብ አልሰጥህም ፥ ይሄ ሁሉ ሰው ግን ገንዘብ እይሰጠ እንዲያልፍ ማድረግ እችላለሁ ፥ ከፈቀድክልኝ” አለው። ዓይነስውሩም የሚያጣው ምንም ነገር ስለሌለ “እሺ” አለ ፥ ዴቪዲም የዓይነስውሩን “ዓይነ ስውር ነኝ እርዱኝ” የሚለውን በራሱ ጹሁፍ ለውጦ ሄደ። በጥቂት ደቂቃ ውስጥ ሰዎች ገንዘብ እና ሳንቲያቸውን ለዓይነስውሩ እየወረወሩ ፥ አንዳንዶቹም ከንፈራቸውን እየመጠጡ ያልፉ ጀመር።



ለማኙ በመደነቅ ፥ የሆነ ሰው ሲያልፍ “ወንድሜ እባክህ የተጻፈው ነገር ምን እንደሆነ ትነግረኛለህ?” አለው።



ሰውዬው ያነበበለትን ከመንገሬ በፊት፤ የመጀመሪያው ጹሁፍ ምን ስህተት እንዳለበት ላሳይ። “ዓይነ ስውር ነኝ እርዱኝ”። “ዓይነ ስውር ነኝ” የሚለው መረጃ ነው ፥ ሰዎች ዓይነ ስውር እንደሆነ እያዩ ነው ምንም የተለየ መረጃ አይሰጥም። ከሚያዩት በላይ የሚነግረው ምንም ነገር የለም። “እርዱኝ!” የሚለው ትዕዛዝ ወይም ማድረግ ያለባቸውን የሚነግር ነው። ሰዎች ደግሞ ይሄን አድርጉ ሲባሉ ደስ አይላቸውም። በራሳችን መወሰን እንችላለን ብለው ነው የሚያምኑት ፥ ሁሉም ሰው ለትዕዛዝ ያምጻል ፥ የእግዚአብሔር ትዕዛዝን የሚጥስ ሰው የሰውን ያከብራል ማለት ሞኝነት ነው።

ዴቪድ ኦግሊቪ ለዓይነ ስውር ለማኙ ምንድነው የጻፈው?


“በጋ (spring) ነው፤ እኔ ግን እዚህ ነኝ - “It is spring but I am here”)፣ በአሜሪካ ውስጥ ስፕሪግ ሰዎች እረፍት የሚወጡበት እና የሚዝናኑበት ወቅት ነው፣ በዚህ ወቅት ውጪ እየወጡ መዝናናት የሁሉም ሰው ናፍቆት ነው ምክንያቱም የበረዶ ዘመን ያለቀበት እና ሀሩር ፀሐይ የሚመጣበት መኃከል ነው ስፕሪንግ ያለው። ሰው ሁሉ በዚህ ሰዓት ምኞቱ መዝናናት ነው። ዴቪዲ በስድስት ቃላት የገለጸው ስለዚህ የሰዎች ምኞት ነው። ሁሉም ሰው በስፕሪንግ ደሀ መሆን እና አለመዝናናት አለመቻል እንዴት እንደሚያም ያውቀዋል ፥ ሁሉም ሰው ግን ዓይነስውር ሆኖ አያውቅም። ስለዚህ ዓይነስውር መሆን ምን እንደሆነ አይረዳም። ስለዚህ ለሁሉም ሰው ቅርብ በሆነ ነገር ነው ዴቪድ የሰውዬውን ሕመም የገለጸው። ሁለተኛው ሰዎች ምን ማድረግ እንዳለባቸው አይገልጽም። ያን ውሳኔ ለሰዎ ትቷል። ማሳየት እንጂ የጥሩ አስተዋዋቂ ተግባር ሰዎች ምን ማድረግ እንዳለባቸው መንገር አይደለም።



ስማርት ነጋዴ ልክ እንደ መርማሪ ፖሊስ ነው። የሞተ ሬሳ ጋር ቆሞ ፥ “ምን ቢፈጠር ነው ይሄ ሰውዬ የተገደለው?” ብሎ የሚጠይቅ ማለት ነው። ነጋዴም የመጨረሻውን መልስ ያውቃል። እሱም “እቃውን በሚፈልገው ትርፍ መሸጥ።” “ይሄን ዕቃ ለመሸጥ ምን መፍጠር አለብኝ ፥ ገዢዎቼ ውስጥ ምን ዓይነት ስሜት መቀስቀስ አለብኝ?” ብሎ የሚጠይቅ እና ለዛ ብዙ ነገሮችን የሚሞክር ማለት ነው።


ሰዎች እቃ የሚገዙት ወይም ሰርቪስ የሚጠቀሙት ለመደሰት ነው። ማንም ሰው ለማዘን ምንም ነገር አያደርግም። ደስታ ማለት በሆነ መጠን ከፍርሃት ነጻ መሆን ነው። ስለዚህ ሰዎች ምንድነው የሚፈሩት የሚለውን ማወቅ ያስፈልጋል። ሰዎች ተመሳሳይ ዕቃ ሆኖ ርካሹን ትተው ውዱን የሚገዙት ፥ ስለሚፈሩ ነው። ይሄ ርካሽ የሆነው እውነተኛ ስላልሆነ ነው ፥ ፌክ ስለሆነ ነው በሚል። ሰዎች ውድ እቃ ከመንገድ ላይ የማይገዙት ፥ በመንገድ ላይ የሚሸጠው ሰው ነገ እዛ ቦታ ላይ ስለማይገኝ ነው። የመንገድ ላይ ነጋዴ ደንበኛ መፍጠር የሚል ነገር አያስጨንቀውም። የሚያስጨንቀው እጁ ላይ ያለውን ዕቃ ሸጦ መገላገል ነው። ስለዚህ አጭበርብሮ ቢሆንም ይሸጣል። ሱቅ ያለው ሰው ግን (ቱሪስት ብቻ የሚሄዱበት ቦታ ካልሆነ) ስለነገ ስሙ ይጨነቃል። ደንበኞቹ ነገም ተመልሰው እሱ ጋር እንዲመጡ ይፈልጋል። ስለዚህ ትርፍና መታመንን አብሮ ነው የሚሸጠው። ስለዚህ የማስታወቂያ አንዱ ዓላማ መታመንን መፍጠር ነው።



ሌላኛው ሰዎች አንድን ነገር የሚያደርጉት በሁለት ነገሮች ግፊት ነው። የመጀመሪያው “በልምድ።” ሁለተኛው “ሌሎች ሰዎች ሲያደርጉ ስላየን።”

ሩዝ ሳይሆን እንጀራ በየቀኑ የምንበላው የእንጀራ ጥቅም ስለሚበልጥ አይደለም። በልምድ ከልጅነት ጀምሮ ስለምንበላ እንጂ። ስለዚህ ማስታወቂያ ሰዎች የምንሸጠውን ነገር እንዲለምዱ ማድረግ ፤ ለማስለመድ ደግሞ ከዚህ በፊት ከሚያደርጉት ነገር ጋር ማያያዝ ያስፈልጋል። አንዱ ልምድ የምንፈጥረው የምንሸጠውን ነገር በተደጋጋሚ በማስተዋወቅ ነው። የዛኔ ሰዎች የኛን እቃ ይለምዱታል።



ሁለተኛው ሌሎች ሰዎች ሲያደርጉት ስናይ ነው። ሰዎች ራሳችንን ምክንያታዊ አድርገን ማሰብ ደስ ይለናል። ያ ግን ውሸት ነው። ብዙ የምንሰራቸው ነገሮች ከምክንያት ጋር የሚጋጩ ናቸው። ብዙ ነገራችን “ሰዎችን ኮፒ” ማድረግ ነው። የምንቀናው ራሱ ከእኛ ከሚበልጠው ነገር ግን ከእኛ ብዙ ባልራቀ ሰው ነው፤ ከኛ በቅርብ ርቀት በሀብት በተለየው ሰው ነው። በቢልጌት አንቀናም። ምክንያቱም አንደርስበትም ብለን ስለምናስብ፤ ከእኛ በጣም ሩቅ ስለሆነ። ነገር ግን በጓደኛችን እንቀናለን። ምክንያቱም እሱ ከኛ ጋር አቻ ነው ብለን እናስባለን። ስማርት ነጋዴዎች ይሄን የሰው ባህሪ ጠንቅቀው ያውቃሉ። ስለዚህ የሚሸጡት ነገር በብዙ ሰዎች የተወደደ እንደሆነ ከማሳየት በተጨማሪ፣ የፉኩኩር መንፈሶችን በመቀስቀስ ስነ-ልቦና የተካኑ ናቸው። የሚሸጡት ነገር በብዙ ሰዎች የተወደደ እንደሆነ ያሳያሉ። ታዋቂ ሰዎች የነሱን ዕቃ ሲጠቀሙ ፥ የነሱን ዕቃ መጠቀም ፋሽን መሆኑን ለሰዎች በማሳየት ፥ ሌሎች ሰዎችም መከተለ እንዳለባቸው በጥበብ ያን ስሜት በሰው ልቡና ያሰርጻሉ።



በእንግሊዝ የማስታወቂያ ጂኒየስ የሚባለው ሮሪ ሰዘርላንድ እንዲህ ይላል “ሰዎችን ወደ ሬስቶራንት በማምጣት በሼፉ (ምግቡን በሚሰራው) እና ወለሉን በሚወለውለው ሰዎች መካከል ምንም ልዩነት የለም።” ወደ ሬስቶራንት ሰዎች የሚሄዱት በዋነኝነት ምግብ ለመብላት ቢሆንም ወለሉ ከቆሸሸ ግን ስለምግቡ ያላቸው ምልከታ ዜሮ ይገባል። እውነታው ግን በወለሉ እና በምግቡ መካከል ምንም ግንኙነት የለም። ወለሉ ሌላ ነገር ፥ ምግቡ ሌላ ነገር። የሰው አዕምሮ ግን እንደዚያ አያስብም። ወለሉ ከቆሸሸ ወዲያው ምግቡም ንጹህ አይደለም ብሎ ያስባል። ሊያስታውክ ሁሉ ይችላል።

ልክ እንደዛው ነጋዴዎች ሁሉ በሰዎች ዓዕምሮ ውስጥ ስለሚፈጥሩት ስዕል በጣም መጨነቅ አለባቸው። ለዚህም ሙያ ያላቸውን ሰዎች መጠየቅ፣ ዕይታ ላይ መስራት፣ ማስታወቂያ መስራት ብቻ ሳይሆን ፥ ያ ማስታወቂያ በሰዎች አዕምሮ ውስጥ ስለሚፈጥረው ምስል ማሰብ እና ጥሩ ምስል ከሳች ነገሮችን መጠቀም ወሳኝ የሚሆነው።



በዚህ ጹሁፍ በትንሹ ያሳየውት እንዴት ቢዝነስ የሰዎችን ስነ-ልቦና የማወቅ ጥበብ እና የአዕምሮ ውጤት መሆን እንዳለበት ነው። ይሄ ግን በቢዝነስ ብቻ ሳይሆን በየትኛውም የሕይወት ክፍላችን እና በተሰማራንበት መስክ መጠቀም ያለብን ብልሃት ነው። የሰዎችን ስነ-ልቦና ማጥናት እና ማወቅ በማንኛውም ተግባራችን ፊት-አውራሪ እንድንሆን የራሱ እገዛ ያደርጋል።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page