top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 3
  • 3 min read
ree

የስነልቦና ሐኪሞች እንዲህ ይላሉ “ለማዳን በጣም ከባዱ በሽተኛ ራሱን ለማዳን የሚጥርን የማዳን ጥረቱን ማስቆም ነው።” ያሉን አስገራሚ ባህሪዎች ራሳችንን ለማከም የወሰድናቸው መድኋኒቶች እንደሆኑ ቢነገረን ምን የምንል ይመስላችኋል?



ማርክ ትዌን ስለዚህ ሲናገር በድመት ነው። ብረትምጣድ ላይ ለመቀመጥ የምትፈራ ድመት ካያችሁ፤ ከዚህ በፊት የጋለ ብረትምጣድ ላይ ተቀምጣለች ማለት ነው። የጋለ ብረትምጣድ ብቻ አይደለም የምታሶግደው ሁሉንም ብረትምጣዶች እንጂ። ሁለት ሦስቴ በሰዎች የተከዳ ሰው የሚክዱ ሰዎችን ብቻ አይደለም የሚያሶግደው፤ ለደስተኛ እና ጤናማ ሕይወት መሠረት የሆነውን ሰውን ማመን ሁሉ እንጂ። በየዓመቱ ከሀገር ወደ ሀገር ከቤተሰቦቹ ጋር እየተዘዋወረ ያደገ ልጅ ፥ ዘላቂ ጓደኝነትን እና ትውስታን መመስረት ይሳነዋል። ሁሉም ነገር ጊዜያዊ ነው የሚመስለው። በጣም በችግር ያደገ ሰው ፤ በጣም ገንዘብ ቢያገኝም ሁልጊዜ ወደ ዛ ችግር የሚመለስ ስለሚመስለው የድህነት ስነልቦና ላይለቀው ይችላል።



ቅናት እና ምቀኝነት እንስሳዊ ማንነታችን ለገጠመን በሽታዎች የለገሰን መድኋኒቶች ናቸው። እንስሳዊ ባህሪያችን በዙሪያችን ያለ ሰው ሲበልጠው ይደነግጣል። በዙሪያችን ያለ ሰው ከበለጠን ወይም ከኛ ትኩረትን ከተጋራ ይፈራል። ምክንያቱም በእንስሳት ዓለም መበለጥ ዋጋ ያስከፍላል። የበለጠን ሰው የኛ የሆነውን ሁሉ ሊወስድ እና ሊያጠፋን ይችላል። ውስጣቸው ነጭ ወረቀት ነው የምንላቸው ሕጻናት በቅናት ይጠቃሉ። የሦስት ዓመት ልጅ አዲስ በተወለደው ሕጻን ልትቀና ትችላለች። አዲሱ ሕጻን የወላጆቹን ትኩረት መሳቡ እንድትጠላው ያደርጋታል። ምክንያቱም ወላጆቿን እንደቀማት አድርጋ ነው የምትቆጥረው። ከወላጆቿ ይልቅ ምንም ራሷን መከላከያ የሌላት ልጅ ይሄን እንደ ትልቅ አደጋ ነው የምትቆጥረው። ስለዚህ በአዲሱ ሕጻን ትቀናለች። ችግሩ የሕጻኗ መቅናት አይደለም፤ አድገንም ሰውነታችን ይሄን መድኋኒት ለመበለጥ እንደ መፍትሔ ሲሰጠን ተቀብለን መዋጣችን ነው። ይሄን ነው ለማዳን ትልቁ ፈተና። ራሳችንን ለማዳን የምንወስደው መድኃኒት።



በሰዎች በልጅነቱ የተጎዳ ሰው ወይም በቤቱ ውስጥ የሌሎችን ትኩረት ለማግኘት የሚቸገር ሰው፤ ሰዎችን ለማስደሰት የሚሰራ ይሆናል። ምክንያቱም በዚህ ቤት ውስጥ ሰው ሆኖ ለመቆጠር ሌሎችን ማስደሰት ነበረበት። በዚህም የራሱን ስሜት የመተው እና የማይፈልገውን ነገር እንቢ የማለት አቅም ያጣል። ብዙ ሰዎች ወደ ሱስ የሚሄዱት በሱስ ውስጥ ያሉ ሰዎች ስለተቀበሏቸው ነው። ሌላ ቦታ ፍቅርን ያጡ እና ቅቡልነት ወይም ትኩረቱን ያላገኙ ሰዎች ሱስ ያን ከሰጣቸው ስሜታቸውን ለማከም ይገቡበታል።



ወላጆቿ ቢዚ ከመሆናቸው የተነሳ ጊዜ የማይሰጧት ልጅ፤ በመጨረሻ ራሷን በምላጭ መቁረጥ የጀመረችበትን ታሪክ አንብቤያለሁ። ምክንያቱም በደማች ቁጥር እናቷ ወይም አባቷ ከሥራ ቤት ቀርተው አብረዋት ይሆኑ ነበር። ራስን የማዳን ተልዕኮ ይሄ ነው። ብዙ የሰዎች ባህሪያት ለስሜት ማከሚያነት የተለበሱ ናቸው።



ራሳቸውን በፍጹም ሥራ የሚወጥሩ ሰዎችን አውቃለሁ። እነዚህ የማሰቢያ ጊዜ ካገኙ ማስታወስ እና ማከም የሚፈሩት ሀሳብ ስለሚወጥራቸው ሊሆን ይችላል። ወይም አንዳች የሚያሳዳቸው ድብቅ በእነርሱ ዓለም ብቻ ያለ አውሬ አለ።


ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድኃን ይሄን ሽሽት “እንዳይነግርህ አንዳች እውነት!” በሚል ግጥሙ ገልጿታል፤


“ደንስ ጎበዝ፦ ደንስ ጀግና


.


.


.


ርገጥ፥ ጨፍር፥ ደንስ ጀግና!


ያን የሙዚቃህን ናዳ፥ የኮንትራባሱን መብረቅ


ልቀቀውና ይደብለቅለቅ


ምንም-ምንም እንዳታስብ፥ ሁሉሉ-ሁሉን እንድትረሳ


ደንስ! ካካታው ይነሳ


ጭንቅላትክን ግዘፍበት፥ እስኪያሰጥመው አጓራበት


ጭንቅላትክን ግዘፍበት፥ ውቀጥበት፥ ውገርበት ....


ዝግ ብሎማ ያስብ እንደሁ፥ ይነግርሃል አንዳች እውነት!”



ብዙ ሰው ለጤናማ እና በአግባቡ ለሚያስብ ሰው ግራ አጋቢ ሕይወት ውስጥ ገብቶ ታገኙታላችሁ። ማህበረሰብን ለማስደሰት ብቻ ወይም ሰው ምን ይለኛል የሚልን ለማስቀረት ብቻ ለራሱ ፍላጎት ተጻራሪ የሆነ ሕይወት ውስጥ የተዘፈቀ ይኖራል። ወይም ከሰው ጋር መቀላቀል፣ ከሌሎች ጋር አብሮ መተባበር እና የተሻለ አካባቢ መኖር ለጤናውም ሆነ ለሕይወቱ የተሻለ ሆኖ ሳለ ፥ መጋፈጥ የማይፈልጋቸው የስሜት ቁስሎች ይዘውት በብዙ ምሽግ ውስጥ ያሉ ሰዎች አሉ። በብቸኝነት ምሽግ ውስጥ፣ ወይም በአልኮል እና እፅ ሱስ ምሽግ ውስጥ፣ በሥራ ማብዛት ምሽግ ውስጥ፣ በገንዘብ ማሳደድ ምሽግ ውስጥ፣ በቅናት እና ምቀኝነት ምሽግ ውስጥ፣ በፍርሃት እና ሁሉን ላስደስት በሚል ምሽግ ውስጥ፣ ሰውን ላለማስቀየም ባለ ምሽግ ውስጥ እና ሌሎች ውስጥ ያሉ አሉ። የማርክ ትዌን ድመት እኛ ውስጥም አለች። በጭቅጭቅ ቤት ውስጥ ያደገ ሰው አውቃለሁ። መከራከር እና ኮስተር ያለ ውይይትን እና ንግግርን ሁሉ ይሸሻል። ጠንከር ብለህ ስለ እንከኑ ልትነግረው ስትል ፥ ከመጋፈጥ ይልቅ ሮጦ ይሄዳል። ምክንያቱም እንደ ድመቷ እንደዚህ ዓይነት ንግግር የሚጭርበት የልጅነቱን ያ ከባድ የአባት እና የእናት ጭቅጭቅ እና ድብድብ ነው።



እኛ ግን እንስሶች ብቻ አይደለንም። ሌላ የምክንያታዊ ክፍልም አለን። ሞኝ የምንሆነው የእንስሳነት ክፍላችንን አሳንሰን ካየን ነው። የእንስሳው ክፍላችን እንደ ዝሆን ግዙፍ ነው። የምክንያት ክፍላችን እንደ አይጥ ድንቢጥ ናት። በኋይል አይጧ ዝሆኑን አትጎትተውም። ግን በጥበብ አይጧ ዝሆኑን ወደ ምትፈልገው ቦታ መምራት ትችላለች። ይሄ በጥበብ እና በትሪክ (trick) ብቻ ነው የሚሆነው።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jul 13
  • 4 min read
ree

በዚህ ሥራ ላይ የመሰማራት ስቃይ ከሀገሬ ርቄ የሀገሬን ችግር በቅርብ በየቀኑ ማስተዋሌ ነው። ብዙ ኢትዮጵያኖች ወደ ሀገራቸው ተመለሱ ከሚባሉ መሞትን ይመርጣሉ። በተቃራኒው ከሌሎች ሀገሮች የመጡ ስደተኞች የአሳይለም ኬዛችሁ ተቀባይነት አላገኘም ሲባሉ፤ እየሳቁ ነው ወደ ሀገራቸው የሚመለሱት። ያነሰ ምቾት እና ተስፋ እንደሚጠብቃቸው ቢያቁ እንኳ ሀገር ግን እንዳላቸው ያውቃሉ። ሊኖሩበት እና ጠንክረው ደግሞ ከሰሩ ሊለወጡበት የሚችሉበት ሀገር እንዳላቸው ያውቃሉ። የኛ ግን ይለያል። ከሀገር የወጣን ሰዎች መጀመሪያ የምናደርገው ልክ እንደ ስፓን የጦር ጄኔራል ኸርናን ኮርቴዝ መርከባችን ኢትዮጵያን ማቃጠል ነው። እስቲ ስንት የዩትዩብ እና የሶሻል ሚዲያ አካውንት አለ ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ልጆች የምዕራባውያንን እውቀት፣ ቴክኖሎጂ እና የታላቅነት ምስጢር ሊያስቀስም የሚችል መልዕክት የሚያስጨብጡ?


ይልቁንስ ጦርነት የሚያፋፍሙ፣ ነፍጥ አንስተው የደሃ ልጅ የደሃ ልጅን እንዲገድል የሚያደርግ እና አንዱ ዘር አንዱን ዘር ለጠብ የሚያነሳሳ የይቱዩብ ቻናል ነው እንደ እንጉዳይ የበዛው። ዲያስፖራው የሚሰባሰበው እና ገንዘብ የሚያዋጣው፣ መቀነቱን የሚፈታው መመለሻ ሀገር እንዲኖረው የሚያስችል ቴክኖሎጂዎችን እና አውታሮችን ለመገንባት ሳይሆን ፥ መመለሻ ሀገር እንዳይኖረው የሚያስችል ጦርነቶችን ፈንድ ለማድረግ ነው።



ኢትዮጵያውያን ባለንበት ሀገር ገነባን ቢባል ራሱ ቢበዛ የምንገነባው የሃይማኖት ተቋማት (ቤተክርስቲያን) እና ሬስቶራንት ነው። ከ10 ሺ የማይበልጥ ምዕመን ባለበት ከተማ ሰባት እና ስምንት ቤተክርስቲያ ታገኛላችሁ። ይሄ እንዴት አያሳፍረንም?! እነዚህን የቤተክርስቲያን ሕንጻዎች ራሱ ከሰኞ እስከ ዓርብ ወላጆች ተረጋግተው ሥራቸውን እንዲሰሩ እና ገንዘብ እንዲያከማቹ የልጆቻቸው መዋያ ወደ ማድረግ እንኳ መቀየር አልተቻለም። ባሉት የአንድ እምነት ቤተእምነቶች መካከል ያለው የዘር ልዩነት እና የመገፋፋት መጠን ፥ የትኛው አምላክ በዚህ እንደሚከብርበት ግር ይላል።



ምንድ ነው ግን የነካን?



ለእኔ ሁልጊዜ መልሱ “ሥር የሰደደ መኃይምነት እና ድንቁርና ነው።” ከዚህ በፊት በሰንበት ዕይታዬ አተኩሬ እንደጻፍኩት የአይሁድ ማህበረሰብ ያለውን ሕብረት ተመልከቱ። አሜሪካ ውስጥ ካጠቃላይ ማህበረሰቡ 2.4 ፐርሰንት ብቻ ናቸው። ከዚህ ውስጥ ሊብራል አሉ። ቀኝ ዘመም አሉ። እስራኤልን አስመልክቶ ግን አንዳቸውም ወለም ዘለም የለም። ይሄ 2.4 ፐርሰንት የሚሆን አስደናቂ ሕዝብ ነው የአሜሪካንን ፖለቲካ እና ኢኮኖሚ የሚዘውረው። ልጆቻቸውን በማስተማር ወደር የላቸውም። ሲያስተምሩ ደግሞ ለጋራ ነው። ብቻ የሚባል ነገር የላቸውም። በሁሉም መስክ የበላይነትን ለመያዝ ይሰራሉ። የጉግል ባለቤት አይሁዳዊ ነው። የቻት ጂፒቲ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አይሁዳዊ ነው። የፌስቡክ እና ኢንስታግራም ባለቤት ዙከበርግ አይሁዳዊ ነው። ዋል ስትሪት ላይ እነሱ ናቸው። የኢንተርቴመንት ማዕከሉን ይዘውታል። ይሄ ግን እንደ ማህበረሰብ ስለሰሩ እና ዓለም አይሁዳዊያን ላይ ምን ያህል ጨካኝ እንደነበረ ስላዩት ነው። ስለዚህ ከአይሁድ ውጪ ለአይሁድ ሌላ ማንም እንደ ሌለ ገባቸው። ደካማ ሆነው በታዩ ወቅት አጥንታቸውን ለመፍጨት የሚጨክን ዓለም እንዳለ እና ያንንም ስለ ፍትሕ ብሎ ለማስቆም የፈቀደ ታላቅ ሀገር እንደ ሌለ ስለተመለከቱ ነው።



መጽሐፉ ቅዱስ ላይ ከአብርሃም እስከ ኤልያስ፤ ከኢዮብ እስከ ጳውሎስ አንድ ንግግር ተናግረው ነበር። “ብቻዬን ነኝ። ብቻዬን ቀረው።” የሚል። የእስራኤል አምላክ መልስ ግን ሁልጊዜ አንድ ነበር። “ብቻህን አይደለህም” የሚል ተግሳጽ ነበር ለእነዚህ ቅዱሳን የሚደርሳቸው ድምጽ። ብቻ ተኮኖ የሚሰራ ምንም ዓይነት ጽድቅ የለም። የምስጋና ጥማት ይዞት የፈጠረን አምላክ የለም። ፍቅሩን የማጋራት ፍላጎት ነው ፍጥረትን ሕያው ያደረገው።



ኢትዮጵያኖች ትልቁ መኃይምነታችን እዚህ ጋር ነው። ብቻ የመድመቅ ፍላጎት። ተልይቶ የመጥገብ እና የማብለጭለጭ ዝቅተኛ አስተሳሰብ አለን። ባህላችን ምቀኝነት መገለጫው እስኪሆን ድረስ። ይሄን መኃይምነት የምለው ማናችንም ቢሆን በመጨረሻ ጠንካራ እና በኢኮኖሚ ያደገ ማህበረሰብ ከሌለን በቀር ብዙ ርቀት መሄድ እንደማንችል ስለምንዘነጋ ነው። ብቻችን ፈጥነን ለጊዜው መሄድ እንችል ይሆናል። ሩቅ ግን አንሄድም። ቤተሰባችን ውስጥ ያሉ ታናናሾቻችንን ለመርዳት የማንፈጥን ካልሆነ፣ ማህበረሰባችን ውስጥ ሩቅ አስበን፣ ስትራቴጂክ ሆነን ወጣቶች ላይ መስራት ካልቻልን ነገ አደጋ ቢደርስብን ጠንካራ ሆኖ ሊቆምልን የሚችል ማህበረሰብ አይኖረንም።



ፖለቲካውን ይሄው ለባለፈው አርባ እና ሃምሳ ዓመት ሞከርነው። ቢያንስ ለምድነው በረጅም ጊዜ ውስጥ ለውጥ ሊያመጣ የሚችል ስትራቴጂዎችን ማሰብ የማንችለው? በታላላቅ የምዕራባውያን ተቋማት ውስጥ ያለንስ ሰዎች ገፈን መጣል የምንችለው ማንነት ያለን ይመስል ያልሆነውን ለመሆን ከምንጥር ፥ ቢያንስ እኛ ከደረስንበት በላይ የነገው ትውልድ እንዲደርስ ጥቂት ግን ዘላቂ ነገሮች ላይ አተኩረን ለምን አንሰራም? በሞታችን አልጋ ላይ ሆነን ፥ በዚህ ዓለም ላይ ብቻችን እና ራሳችንን ብቻ አበልጽገን እና አዋቂ አድርገን ማለፋችን አይቆጨንም?


እንዴት ሁላችንም መፍትሔ የሌለው የዘር ፖለቲካ ውስጥ ራሳችንን ሁልጊዜ ነክረን እንሞታለን? የነበረንን አንድ ሕይወት፣ አንድ ሰማንያ እና ሰባ ዓመት አሁን ስልጣን የያዘው ትግሬ ነው፣ አማራ ነው፣ ኦሮሞ ነው ብለን ስንነታራክ ብቻ ጨርሰነው ስንሄድ እንዴት አያሳፍረንም? ወይም ቤተመቅደስ ብቻ በየቦታው እየገዛን ፥ ለትውልድ ግን ችግርን እና መከፋፈልን አስረክበን ስናልፍ እንዴት አያሳፍረንም?



አንዳንድ ጅሎች ደግሞ አሉ። ይሄን ጹሁፍ ሲያነቡ እኔ ምን ላድረግ፣ የኔ አቅም ደካማ ነው፣ ስልጣን የለኝ ወይም ፖሊሲ ላይ ያሉ ሰዎች ይሄን ካለወጡ እኔ ምንም አቅም የለኝም የሚሉ። እንደዚህ ዓይነት ጅሎች በሕይወት ይገጥሙናል። መስራት የማይወዱ። ስልጣን ሲይዙ ብቻ መስራት የሚችሉ የሚመስላቸው። ወይም ሁሉን የመቀየር ስልጣን ካልተሰጣቸው በቀር የእነሱ ኃላፊነት የማይታያቸው። ልክ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ አንድ ሺ ዲናር ተሰጥቶ ፥ የተሰጠው አንድ ሺ ብቻ መሆኑ ላይ አተኩሮ ጌታው እንደ መጣበት ሰነፍ ያሉ።



ማዕበሉ ብዙ አሣዎችን እየገፈተረ ወደ አሸዋው ያወጣቸዋል። በዚህ ሰዓት በዚህ ዓለም ላይ ብቻውን እንዳልሆነ የገባው አንድ መልካም ሰው የሚችለውን አሣዎች እያነሳ ወደ ባህሩ ይመልሳቸዋል። ማዕበሉ ባያቋርጥም የእርሱ ድርሻ ግን የሚችለውን ማድረግ እንጂ የማይችለውን ማዕበል ማስቆም እንዳልሆነ ስለገባው አሣዎችን ወደ ባህሩ መመለሱን ቀጠለ። በዚህ ሰዓት ሁልጊዜ ብቻውን እንደሆነ የሚታየው አንድ ሰነፍ ተከሰተ። እየገላመጠው ፥ “ምን ሆነሃል?” አለው። “ምን ሆኛለው?” አለው። “ይሄ ሁሉ አሣ በማዕበሉ ተገፍትሮ እየወጣ ያንተ ሁለት አሣዎች እያነሱ ወደ ባህሩ መመለስ ምን ሊፈይድ ነው?” አለው! ቂልነቱ እያሳዘነው ፥ ወደ እጆቹ ወዳሉት አሣዎች እያመለከተው ፥ “የማደርገው ነገር ለእነዚህ አሣዎች ይረባል” አለው።



የችግሮችን ማዕበሎች እያሳዩን በእጃችን ያሉትን ፥ እርዳታችንን ልንሰጣቸው የምንችላቸው ሰዎችን ሳይቀር እንድንተዋቸው የሚነግሩን ሰነፎች አሉ። እነዚህ ሰነፎች ሁልጊዜም አሉ። በኛ ማህበረሰብ ደግሞ በብዛት አሉ። ከእነዚህ ጋር ያለን ትግል ጥቅም የለውም። በመካከላችን የተማርን እና የነቃን ካለን ፥ ቤተሰቦቻችን ውስጥ የእህት ልጅ፣ የአክስት ልጅ፣ የአጎት ልጆች ካሉ ፥ እነርሱን መርዳት፣ ከቲክቶክ እና ኢንስታግራም ይልቅ መጽሐፍት ላይ እንዲያተኩሩ፣ የተሻለ የትምህርት እድል እንዲያገኙ ካደረግን ቢያንስ በእጃችን ላይ ያሉ ነፍሳትን አድነናል። በዚህ ቤተሰብ ስኬት ብዙ ሌሎች ነገ ይነቃቃሉ። አካባቢያችን የኢትዮጵያኖች ቢዝነሶች ካሉ እነርሱን እናበረታታ። ነገ ልጆቻችን የሚያዩት እና የሚነሳሱት በኢትዮጵያዊ ስኬት ነው። ተስፋ ያላቸውን ሰዎች ለመርዳት እና ከፍ ለማድረግ እንጣር። ጦርነትን፣ መለያየትን ለሚያበረታቱ የገንዘብ መቀነታችን አይፈታ። የእምነት ተቋሞቻችን ሕንጻ ቤተክርስቲያን ማስፋፋት ላይ ሲያተኩሩ እንቢ እንበል። ይልቁንስ ትምህርት ቤት እንዲሰሩ ወይም እንዲገዙ እናስገድዳቸው። እኔ በበኩል በዚህ ጉዳይ ፍጹም አቋም አለኝ። ይሄ ባህል መቆም አለበት። ለምንድነው የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያኖች ልክ እንደ ካቶሊክ ቤተክርስቲያን ትምህርት ቤት እና የነገው ትውልድ የሚፈጠሩበት ተቋሞች ላይ ማትሰራው? ኢትዮጵያዊ ተሰባሰበ ማለት ቤተክርስቲያን መግዛት እና መስራት ላይ ብቻ ለምን ያተኩራል? ይሄን ለባለፉት አርባ እና ሃምሳ ዓመታት አደረግን። ስደትን አላቆመ። ረሃብን አላቆመ። ከመንፈሳዊነት አንጻር ራሱ መከፋፈልን አላቆመ ወይም አንድነትን አልፈጠረ። ምክንያቱም መኃይምነትን የሚቀንሱ ተቋሞች ላይ ስለማንሰራ ነው። እንደዚህ ዓይነት ሃሳብ ለማንሳት ደግሞ ብቻችን ነን ብለን እናስባለን።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jul 6
  • 2 min read
ree

አሌክሳንደር ሶልዠኒስተን በአርክ ፕሌጎ ቅጾቹ ከነገርን እውነት ትልቁ የሰው ተፈጥሮ ነው። የሰው ልጅ እንዴት በቀላሉ ክፋትን፣ ፍጹም ክፋትን ወደ ማድረግ ልቡን እንደሚያሳምን ነው የሚያስረዳን። ለብዙ ጊዜ የያዝኩት አመለካከት የጀርመን ናዚዎች ያን ሁሉ አይሁዳዊ እና ከእነርሱ ውጪ ያለውን ማህበረሰብ ያጠፉበት የክፋት ጥግ ልዩ ፍጥረት እንደሆኑ አድርጌ እንድቆጥራቸው አድርጎኝ ነበር። ግን አልነበሩም። በገዳይ እና በተገዳይ መካከል ሰብአዊነትን አስመልክቶ እምብዛም ለውጥ አልነበረም። ለውጥ የነበረው አይዶሎጂው ላይ ነበር። ገዳዮች ጭልጥ ብለው በአንድ ልዩ ነን በሚል አይዶሎጂ እየተመሩ ነበር። የሚገርመው ነገር በጀርመን የሚኖሩ አይሁዶች ሳይቀሩ የሂትለርን ፓርቲ መርጠው ነበር። Appeasement ወይም ማባበል የሚባለውን ፖሊሲ ተከትለው ማለት ነው። ብንመርጠው ጥላቻውን ይቀንስልናል በሚል እምነት።



ግን አንድ ሰው አዕምሮው በጥላቻ ፖለቲካ ከታወረ በኋላ የሚያቆመው ነገር አይኖርም። ያ አይዶሎጂ ለጊዜው እስካልተሸነፈ ድረስ ጠላት ብሎ የፈረጀውን ከማጥፋት አይመለስም። በናዚ ጀርመኖች እና በአይሁዶች መካከል የአይዶሎጂ እንጂ የሰብአዊነት ልዩነት አልነበረም። ሁለቱም የሰው ልጆች ናቸው። በዛ ዓይነት ሰቆቃዊ መከራ ያለፉ አይሁዶች ዛሬ ደግሞ ሕጻናትን ለመግደል ምንም ርህራሄ ሳይኖራቸው ስታዩ ይሄ እውነት በግልጽ ይታየናል። ሳውዲ አረቢያ የመኖችን እንዴት ባለ ጭካኔ እንደጨፈጨፈቻቸው ለተመለከትን ደግሞ ተመሳሳይ ሃይማኖት ውስጥ መኖር ምንም ይሄን የሰው ክፋት የማለዘብ አቅም እንደሌለው ታያላችሁ። በትግራይ ጦርነት ወቅት የደረሰው ግፍም አንድ ሃይማኖት በሚጋሩ ሕዝቦች መካከል የተፈጸመ ግፍ ነበር።



ዛሬ አሜሪካ ውስጥ የክርስቲያን ቀኝ ዘመም ነው ስልጣን የያዘው። የክርስትና መሠረቱ ደግሞ ገና ከልጅነቱ በአምባገነኑ ሄሮድስ ተሰዶ ወደ ግብጽ ሕይወቱን ለማትረፍ የተሰደደውን ክርስቶስን ማምለክ ነው። ግን እነዚህ ክርስቲያን ነን የሚሉ የፖለቲካ ኃይሎች ናቸው አንደኛ ስደተኛ ጠል የሆኑት። ሲግመንድ ፍሮይድ ሰው የሚራመድ ተቃርኖ ነው ይላል። ክርስትና እና ስደተኛ ጠል መሆን ምንም ሳይጋጩበት መራመድ የሚችለው ሰው ብቻ ነው። የሰው ልጅን በምንም ነገር እንዲያምን ማድረግ ትችላላችሁ። ሕንድ ብትሄዱ እጅግ ብዙ የተማሩ፣ እስከ ዶክትሬት ዲግሪ የጫኑ ሰዎች ለከብት ሲሰግዱ ታያላችሁ። በሆነ ጉዳይ በእውቀት መራቀቁ በሆነ ጉዳይ ጅል ከመሆን የሰው ልጅን አያድነውም።



ቆሞ እያንዳንዱ የሚያደርገውን ድርጊቶች ለመፈተሽ እና በሌሎች ለመመከር ወይም ሌሎችን ለመስማት ያልፈቀደ ሰው እንደ ሸንበቆ ወጥቶ ወጥቶ በድንገት ይሰበራል። ጉደኛ ቴክኖሎጂዎችን መፍጠር የቻለ የሰው አዕምሮ ፥ ጅል በሆኑ የጥላቻ ስብከቶች ተወስዶ በክፋት ሥራዎች ሲዝረከረክ ታዩታላችሁ። የክፋት ጥግ የፍቅር ልብ ባለው ሰው ውስጥ እንዳለ እንዘነጋለን። ሂትለር ለሕጻናት አስገራሚ ፍቅር ነበረው። ግን ይሄ ልብ አይሁዶችን ጨምሮ ሌሎች የሰው ዘሮችን ለማጥፋት የሚሆን የክፋት ጥጉን ለመፈተሽ እና ለመግራት ስላልቻለ ፥ ስልጣን ሲያገኝ መራራ ታሪክን ሠርቶ አለፈ።



ብዙዎቻችን የምንስተው የሰው ልጆች ያን የክፋት ስነልቦና አልፈውታል ብለን ነው። ያን እንዳልተሻገርነው፣ መቼምም መሻገር እንደማንችል ለማየት ጋዛ መሄድ ነው። በፍሎሪዳ ስቴት በአዞ እና አሊጌተር የተከበበው እና ስደተኞች ይታሰሩበታል በሚባለው እስር ቤት መገንበት የሚደሰተውን የነጭ ብዛት ለተመለከተ ፥ ዓለም ዲሞክራሲ እና ሰብአዊ መብት የሚሉ ሥርዓቶችን ከመዝገቡ ሊሰርዝ እየተቃረበ መሆኑን እናስተውላለን። የጠቅላይ ፍርድ ቤቷ ዳኛ ጀስቲስ ጃክሰን እንዳለችው ዛሬ ይሄን ማስቆም ካልቻልን ፥ የአሜሪካ ሕገመንግስታዊ ሪፖብሊክ ነገ ታሪክ ይሆናል። ብዙዎቻችን ከዚህ ቀደም የነበሩ በጎ ሥርዓቶች እና ትውፊቶች እንክብካቤ እና ጥበቃ የሚያስፈልጋቸው ተክሎች አይመስሉንም። ያ ግን ስህተት ነው። ነቅተን ክፋት የዓለምን ብርሃን እንዳያጨልም የራሳችንን ጥረት ካላደረግን ፥ ባርነት ታሪክ ብቻ አይሆንም። ተመልሶ ይመጣል። ውሻ እና ጥቁር እዚህ አይገባም የሚለው ቀስ እያለ ስደተኛ አይገባም በሚል የስም ለውጥ እየመጣ ነው። ከዛ ከአብዛኛው ሰው በመልክ የተለየው ሁሉ ስደተኛ ይባላል። ኢለን መስክ ሲቃወማቸው ደቡብ አፍሪካነቱን እንዳስታወሱት ፥ ይሄ ማዕበል እስካልተገታ ድረስ ቅኝ ግዛት የድሮ ታሪክ ብቻ አይሆንም። ከታሪክ መጽሐፍት ወጥቶ ነገ ዜና ይሆናል። የክፋትን አቅም አቅሎ እንደማየት ሞኝነት የለም።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page