
“ማርታ ግን አገልግሎት ስለ በዛባት ባከነች፤ ቀርባም። ጌታ ሆይ፥ እኔ እንድሠራ እኅቴ ብቻዬን ስትተወኝ አይገድህምን? እንኪያስ እንድታግዘኝ ንገራት አለችው።
ኢየሱስም መልሶ። ማርታ፥ ማርታ፥ በብዙ ነገር ትጨነቂአለሽ ትታወኪማለሽ፥
የሚያስፈልገው ግን ጥቂት ወይም አንድ ነገር ነው፤ ማርያምም መልካም ዕድልን መርጣለች ከእርስዋም አይወሰድባትም አላት።” ሉቃ 10፥41፡42።
ይሄን ታሪክ ሳነብ ትዝ የሚለኝ ሴኒካ ለሉሲለስ ወዳጁ የጻፈለት ደብዳቤ ነው። እንዲህ ይለዋል “ሉሲለስ ሆይ ካንተ የሚወሰድብህ ነገር ሁሉ ያንተ አይደለም። ያንተ ባልሆነ ነገር መደገፍን አሶግድ።” ጌታችን ለማርታ “ማርያም የማይወሰድባትን መረጠች” ይላታል። መንገድ ላይ ቆመው የሚለምኑ ሰዎችን ሳይ በእኔ አዕምሮ ስለተወሰደባቸው ሀብት እና ክብር ሳይሆን የሚያስበው፤ ስላልተወሰደባቸው ድፍረት ነው። ኑሮን የመቀጠል ድፍረት። በሕይወት የመኖር እና የመቀጠል ጀግንነት።
በያንዳንዱ ቀን ያለኝ ብርታት ሰዎች ከኔ ሊወስዱብኝ የማይችሉት ነገርን ገንዘብ ባደረኩኝ መጠን ነው። ከአምላኳ እግር ሥር ቁጭ ብሎ ማረፍን ማንም ከማርያም የሚወስድባት አይኖርም። ለዛች ነፍስ የክብር ቦታ፣ VIP ወይም ፊትለፊት ላይሰጣት ይችላል። ታላቅ አስተዳዳሪ፣ ታላቅ ሰባኪ ወይም ታላቅ ምናምን ብለው ላይጠሯት ይችላሉ። ግን ከክርስቶስ እግር ሥር ቁጭ ብሎ ፍጹም መደሰትን ማንም አይነጥቃትም።
ከሁለት ዓመት በፊት ውድ ፍራሽ ለጥሩ እንቅልፍ እንዲሆን ገዛው። ግን በሚገርም ሁኔታ ፍራሹን የገዛው ቀን ምንም እንቅልፍ ሊወስደኝ አልቻለም ነበር። በጠዋት ዳውን ታወን ወዳለው ቢሮዬ ልገባ ስል ከሕንጻው ሥር፤ ሰዎች በፍጥነት በሚራመዱበት ሥፍራ አንዱ አስገራሚ እንቅልፍ ተኝቷል። ውድ ፍራሽ አልነበረውም እንቅልፍ ግን ነበረው። ለአምስት ደቂቃ የሚሆን ጊዜ ቆሜ አየውት። የአስር ሺር ዶላር አልጋ ሊኖርህ ይችላል፤ እንቅልፍ ከሌለህ ግን ትርጉም የለውም። ያን እንቅልፍ ፍራሽ እምብዛም አይሰጥህም። ቅዱስ ጳውሎስ እና ሲላስ በእስር ቤት ሆነው በፍጹም ደስታ ይዘምሩ ነበር። በዓለም ላይ ተፈተው ያሉ ሰዎች ግን ያ ደስታ አልነበራቸውም። ጳውሎስ እና ሲላስን በእግረ ብረት ሆኖ መታሰር ያን ደስታ ሊቀማቸው አልቻለም። የማይቀሙን ነገር አለን?
ሰዎች የማይወስዱብን ነገሮች አሉን?
ትረምፕም ሆነ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ የማይቀሙን ነገሮች ይኖሩን ይሆን? እኔ ስለሃይማኖት ወይም በዛ ውስጥ ያሉ ሰዎች ስለሚገባቸው ነገሮች ብቻ እየተናገርኩኝ አይደለም። በጣም ብዙ ድንቅ ሰዎችን በሕይወት ተገናኝቻለው። ማንም የማይወስድባቸው ደግነት፣ መረጋጋት፣ ትህትና፣ እውቀት፣ ማስተዋል፣ ጥበብ፣ ስክነት ያላቸው ሰዎች። መክሰርም ሆነ ማግኘት ምንም ያልነቀነቃቸውን ሰዎች አይቻለው። አንዳንዶቹ ምንም ሃይማኖት የሌላቸው ነበሩ። እነዚህ ማንም የማይቀማቸው ውበት የነበራቸው ሰዎች ነበሩ።
ማርታ ጌታን ለማስደስት በጓዷ ትተጋ ነበር። የጌታ መደሰት በማርታ እጅ ላይ የነበረ አልነበረም። በርሷ ቁጥጥር ውስጥ አልነበረም። እርሷ ግን ብዙ ለፋች። ብዙ ተጨነቀች። ማርያም ደግሞ ነፍሷን አደመጠች። ያ ውብ ጌታ እግር ሥር መቀመጠ እርሷን እንደሚያስደስታት ገባት። ስለዚህ አደረገችው። የእርሷ ደስታ ግን በእጇ ነበር። ጌታ ስለመደሰቱ ሳይሆን የእርሷ ነፍስ ስለማረፏ አሰበች። ያን ራስን ማወቅ ከእርሷ ማን ይወስድባታል?
ሊዮ ቶልስቶይ ስለመደሰት ሲናገር በጣም ቀላል መርህ ነው ያለው። “መደሰት ትፈልጋለህ?” “እንግዲያው ደስተኛ ሁን!” ብቻ ነው የሚለው። ብዙዎቻችን መደሰት ብንፈልግም ደስተኛ የሚያደርገንን ነገሮች ግን አይደለም የምንሰራው። ይልቁንስ ክብር፣ ቦታ፣ ዝና፣ ኢጎ፣ አዋቂ መስሎ መታየት፣ ከቡድን የመነጠል ፍርሃት፣ እንደ ማርታ ሰው ምን ይለኛል የሚል ጭንቀት እና ሌሎች ስሜቶች ነው የሚያስተዳድሩን። የሚቀሙን ነገሮችን ብቻ ነው የምንሰበስበው። ክብር እንደ ጥላችን ነው። አንዳንዴ ከኛ በላይ ትልቅ ነው። አንዳንዴ ከኛ በጣም የሚያንስ ነው። ምክንያቱም የኛ አይደለም።
የማርታ ሃብቶች ሊወሰዱብን የሚችሉ ናቸው። አያስፈልጉም ሳይሆን ብዙ መትጋት ያለብን ግን የማርያም ሃብቶች እንዲበዙልን ነው። የማርያም ሃብት ያለው ሰው የማርታ ሃብትን በሂደት ገንዘቡ ማድረግ ይችላል። የማርታ ሃብት ያለው ሁሉ ግን የማርያም ሃብት አለው ማለት አይደለም። በማንኛውም እና በየትኛውም ቦታ ብንሆን ቀና ብለን የምንሄድበት ጥበብ አለን? በሁሉም ስፍራ አሸናፊ የሚያደርገን ማንም የማይነጥቀን ሰውነት አለን? ያ በማዕበል እና በወጀብ መኃል ቀና እንዳልን የሚያስኬደን ውሳጣዊ ሃብቶች አሉን? የማርያም ሃብቶች።
መስቀል የበዛባቸውን ሰዎች አላያችሁም? ግን ከፊታቸው ይሄ ሕይወት ውብ ነው የሚል ደስታ የማታጡባቸው! ሲመሽ ደስ የሚላቸው ሲነጋም ፀሐይዋን በድጋሚ አወጣት ብለው የሚደሰቱ ሰዎች። ሉሲለስ ሆይ ካንተ የሚወሰድብህ ሁሉ ያንተ አይደለም። አንዳንድ ሰዎች አልገጠሟችሁም? “ወፈርኩኝ አይደል?” ብለው ጠይቀዋችኹ፤ “አዎ” ስትሏቸው የሚያኮርፏችሁ? በሕግ ትምህርት ቤት እያለሁ፤ አንድ ከእንግሊዝ የመጣች ተማሪ ነበረች። ፊቷ በርበሬ መስሎ አንድ ቀን እኔ የማጠናበት ክፍል ከጓደኞቿ ጋር መጣች። “ፊትሽ ምን ሆኖ ነው?” ስላት (እንግዳ ስለሆነብኝ ነበር)፤ አበደችብኝ። ጓደኞቿም “ያን መጠየቅ አልነበረብህም” አሉኝ። ምን አልባት ልክ ናቸው። ግን ተመልከቱ ምን ያህል insecure እንደሆነች! በሽበት፣ በቁመት፣ በእርጅና እና በሌሎች ጉዳዮች እንዲህ የሚሰማን ሰዎች ሞልተናል። የማርታ ሃብቶች ብቻ ያሉን። ማርያም ግን የማይቀሟትን መረጠች።
ሊወዱን ሊጠሉን፣ ለጊዜው ሊያከብሩን ወይም ሊሰድቡን ይችላሉ። ይሄን ሁሉ እንደ ኢምንት ቆጥረን ፥ ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድኅን እንዳለው በዚህ የሙገሳ እና የስድብ ውርጅብኝ ውስጥ ዝም የምንል ምን ያህሎቻችን ነን? የማይቀሙን የውስጥ ጽናት ያለን? የመንፈስ ቅስማችን የማይወሰድብን ምን ያህሎቻችን ነን? የማይቀሙንን እንያዝ። የማይወስዱብንን ገንዘብ እናድርግ። “ሉሲለስ ሆይ ካንተ የሚወሰድብህ ነገር ሁሉ ያንተ አይደለም።”
ፅሁፍን እከታተላለሁ መከታተል ብቻ አይደለም እራሴንም በደንብ እመረምርበታለሁ በህወቴም መርህ ላደርገው እሞክርና በሁለኛው ቀን ይጠፋብኛል
ልክ አባ ጊዮርጊስ በአርጋኖኑ እንዳለው ቃል በቃል ባይሆንም
"ከሀጢያ ለመለየት ሌሊቱን ሁሉ እደክማለሁ አነዋወርን የሚለውጥ ሃሳብ ይመጣብኛል
አመቤቴ ሆይ በጎው ስራ ለመስራት የሚያበረታታውን መንፈስ ይልክልኝ ዘንድ ልጅሽን ለምኝልኝ"
ጌታ ይባርክ ትልቅ መልዕክት የያዘ እውነት ነው!!
ሙልዬ እጅህ ይባረክ።
እይታወችህ ግሩም ናቸዉ!!!!!!!!!!!