top of page
Search




በሥራዬ ምክንያት በአሜሪካ ዙሪያ ያሉ ብዙ የኢትዮጵያ ቢዝነሶችን በሕግ ዙሪያ የማማከር ዕድሉን አግኝቻለሁ። ብዙዎቹንም የሕግ ጉዳይ እና ችግር ገጥሞአቸው ረድቻቸዋለሁ። ወይም ከሚረዷቸው ሰዎች ጋር አገናኝቻለሁ። የዚህ ጹሁፍ ዓላማ ግን እርሱ አይደለም። የማገኛቸው ብዙ የኢትዮጵያ ቢዝነስ ሰዎች የሚነግሩኝ ነገር ፥ ከሚረዷቸው ኢትዮጵያኖች ባልተናነሰ ብዙ ምቀኛ እና ተንኮለኛ ኢትዮጵያዊ አለባቸው። የሆነ ችግር ሲገጥማቸው ምሳር የሚያበዙባቸው እንጂ የሚበዙት፤ አዲስ ቢዝነስ ሲከፍቱ መደገፍ ወይም ማገዝ እና እንዳይወድቁ የሚረባረቡ ኢትዮጵያኖች አይደለም በብዛት ያሉት።



በሚገርማችሁ አሜሪካ ውስጥ አንድ የኢትዮጵያ ሞል አታገኙም። በዋሽንግተን ዲሲ እና አከባቢው (ቨርጂኒያ እና ሲልቨር ስፕሪንግን ጨምሮ) እስከ 250 ሺ ኢትዮጵያዊ አለ። ሚኒሶታ ትልቁ የሶማሌ ኮሚኒቲ ያለበት ስቴት ነው። ቁጥራቸው ግን ወደ 60 ሺ ብቻ ነው። ይሄ ከኢትዮጵያኖች ጋር ሲነጻጸር በብዙ እጥፍ ያንሳል። ነገር ግን ከአንድም ሁለት ትልልቅ የሶማሌ ሞል በሚኒሶታ አለ። የዚህን ምስጢር ብዙ የሶማሌ ደንበኞቼን ስጠይቃቸው የሚሉኝ “ሶማሌ ከሌላ ሶማሌ ሱቅ ይገዛል። ልብስ ከፈለገ የነጭ ሱቅ ሳይሆን የሚሄደው እዛው አጠገቡ ያለውን የሶማሌ ቢዝነስ ነው የሚደግፈው። ከዛው በመግዛት።” ይሄ በኢትዮጵያኖች ዘንድ እምብዛም አልተለመደም። ብዙ ኢትዮጵያኖች ወገናቸው ከስሮ ፥ ስለክስረቱ ማውራት ያስደስታቸዋል ፥ ያን ሰው ተሯርጠው ደግፈው እንዲሳካለት ከማድረግ ይልቅ።



ስለብዙ ነገር ሳስብ ፥ ወደ መሠረቱ ሄጄ ለመረዳት እሞክራለሁ። ስለ ኢትዮጵያኖችም ይሄ አስገራሚ ራስን የሚጎዳ ባህሪ ሳስብ ፥ ወደ መሠረቱ ሄጀ ለማሰብ ሞክሬያለሁ። ኢትዮጵያኖች የተለየን ሆነን አይደለም እንደዚህ አስገራሚ ባህሪ የምናሳየው። ማለት በጣም ጥልቅ የሆነ የምቀኝነት ባህል እና ባህሪ (ጠልፎ የመጣል ባህል) የኖረን ፥ እጅግ ኋላ ቀር የሆነ የአስተሳሰብ ተሸካሚ ማህበረሰብ ስለሆንን ነው።



ልክ የኢትዮጵያኖች ዓይነት በጣም ኋላ ቀር የምቀኝነት ባህል እጅግ ደሃ የሆኑ ማህበረሰቦች ሁሉ አላቸው። ታላቁ የቲዎሎጂ ሊቅ ሲ ኤስ ሉዊስ “የሰይጣን ትልቁ ተልዕኮ ሰው እንስሳነቱን እንዲረሳ ማድረግ ነው” ይላል።



ሰዎች በትምህርት የጎደልን እና በስሜት የምንመራ ስንሆን እንስሳዊ ባህሪያችን ብቻ ነው የኛ አስተዳዳሪ የሚሆነው። ብዙ ሰው ቅናት እና ምቀኝነት የክፋት ውጤት ይመስለዋል። ይሄ ግን ደካማ ትንታኔ ነው። ቅናትም ሆነ ምቀኝነት እንስሶች ራሳቸውን ለመጠበቅ የሚያመነጩት የሆርሞን መጠበቂያዎች ናቸው። የምንፎካከረው ከኛ በጣም በቅርብ ርቀት ካለ ሰው ጋር ነው። ያ ሰው በሀብት ወይም በማናቸውም ነገሮች ሲበልጠን ፥ እንስሳዊ ባህሪያችን ዕድል (opportunity) አይደለም የሚታየው። ይልቁንስ መሸነፍ፣ ዝቅተኛ መሆን፣ በሌሎች ተፈላጊ አለመሆን እና ብቸኛ መሆን ነው የሚታየው። ስለዚህ ራሱን የሚከላከለው የሚበልጠውን በማጥፋት ነው። ምክንያቱም ሰው ፍጹም የሆነ ሚዛን (objective truth or standard) የለውም። የሚያስበው ሁሌ በአንጻራዊ ሁኔታ ነው። በምሳሌ ላስረዳ። የአሪዞናው ዩኒቨርስቲ ፕሮፌሰር ካልዲኒ አንድ የሰራው አስገራሚ ጥናት አለ። በዚህ ጥናት አምስት ሰዎችን በጣም ቀዝቃዝ የሆነ ክፍል ውስጥ አስገባቸው። ሌሎች አምስት ሰዎችን ደግሞ በጣም የጋለ ሙቀት ያለበት ክፍል ውስጥ ለተወሰነ ደቂቃ አስገባቸው። ከዛ ሁለቱንም ከየክፍላቸው አውጥቶ ወደ ሩም ቴምፕሬቸር (ዓየሩ ወደ ተስተካከል) ክፍል ውስጥ ከተታቸው። በጣም ቀዝቃዛ ከሆነ ክፍል ውስጥ ለመጡ ይሄ ክፍል ሲሞቃቸው፤ በጣም ሙቅ ከሆነ ክፍል ውስጥ ለመጡት ደግሞ ይሄ ክፍል ቀዘቀዛቸው። ይሄ የሚያሳየን የሰው ልጅ የተስተካከል ሚዛን (objective truth/scale) የሌለው መሆኑን ነው። ሁልጊዜ የሚያስበው በንጽጽር ሁኔታ ነው።



ኢለን መስክ በብዙ እጥፍ በሀብት እየበለጠን በርሱ ሳይሆን የምንቀናው፤ የምንቀናው በምናውቀው እና አብሮ አደግ በሆነ ጓደኛችን ነው። ምክንያቱም የዝቅተኛ ስሜት እና የመሸነፍ እና ያለመፈለግ ስሜት በውስጣችን የሚጭረው ያ የምናውቀው አብሮ አደግ ጓደኛችን ሲበልጠን ነው። ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ "ሰው ሀዘን የሚሰማው እንደሚያሸንፈው የሚያስበው ሰው ሲበልጠው ነው።" ይላል። ያ Primordial በሆነው እንስሳዊ ዓለም ውስጥ ፥ በአቻው የተበለጠ እንስሳ የመኖር ተስፋው እና በተቃራኒ ጾታ ተፈላጊነቱ እጅግ ዝቅ ስለሚል ፥ ራሱን በሌላ ዘር የመተካት አቅሙ ሳይቀር ነው የሚቀንሰው። ለምሳሌ ፒኮኮች ያላቸው ቀለማማ ጸጉር ምንም ጥቅም የለውም። ከአንድ ጥቅም ውጪ። ላባቸው እጅግ ቀለማማ ነው ማለት የሚያባክኑት ከፍተኛ የሆነ አቅም (energy) አላቸው ማለት ነው። ያ ደግሞ ለርቢ በጣም ወሳኙ ዘር መሆናቸውን ለተቀራኒው ጾታቸው ያሳውቃሉ። ስለዚህ ብዙ ቀለማት ያላት ፒኮክ ከሌሎች ፒኮኮች ይልቅ በተቃራኒ ጾታ በጣም ተፈላጊ ትሆናለች። በዚህም ለዘር (ለርቢ) ምርጧ መሆኗን ታሳያለች። ይሄ በጣም ዝቅተኛ አስተሳሰብ ባላቸው ሰዎች ዘንድ በተመሳሳይ አለ። ለምሳሌ የእነዚህ ፒኮኮች ባህሪን ልክ እንደ መንሱር ጀማል ያሉ ሰዎች ላይ ታያላችሁ። ብዙ የሚጨነቁት ለሰዎች እና ለማህበረሰቡ ስለሚያሳዩት የሀብት መገለጫዎች ነው። ያ በጣም ዝቅተኛ የሆነው እንስሳዊ ባህሪ ሲያስተዳድረን የምናሳየው ባህሪ ነው።



እጅግ ስማርት የሆነ ሰው፤ ጓደኛው ሀብታም ቢሆን እርሱም ሀብታም የመሆን ዕድሉ በጓደኛው ሀብታም መሆን ብቻ እንደሚጨምር ነው የሚያውቀው። ቢያንስ ለለቅሶ፣ ለምርቃት ወይም ለሆነ ችግር ጓደኛው ሲመጣ ሀብታም ቢሆን ደሃ ከሚሆን ይልቅ የሚሰጠው ገንዘብ ከፍ ይላል። በጓደኛው ኮኔክሽን እና ኔትወርክ ተጠቅሞ እርሱም ወደ ሀብት ከፍ ሊል ይችላል። ይሄ ሁልጊዜ እውነት ባይሆን እንኳን ጓደኛው ሀብታም በመሆኑ ዕድሉን ያሰፋዋል።



በተመሳሳይ ኢትዮጵያኖች በአሜሪካ ውስጥ ያሉ ሌሎች የኢትዮጵያኖችን ቢዝነሶች በስትራቴጂ ቢደግፉ ፥ የመጀመሪያው ለልጆቻቸው እነዚህ ስኬታማ ኢትዮጵያኖች ዓርአያ መሆን ይችላሉ። በአሜሪካ ውስጥ ኢትዮጵያዊ ተኮኖም ሊሳካልን እንደሚችል ማሳያ አገኘን ማለት ነው። የሰው ልጅ ደግሞ በእንስሳዊ ባህሪው ምክንያት የሚቀናው ብቻ ሳይሆን የሚበረታታውም አጠገቡ ባለው ሰው ነው። ለምሳሌ መንገድ ላይ ስትሄዱ ነጭ ብቻ እያለፈ ፥ ድንገት ኢትዮጵያዊ የሚመስል ሰው ሲያልፍ ካያችሁት አንገታችሁን አዙራሁ ሁሉ ታዩታላችሁ። ለምን? ምክንያቱም በሰው ሀገር ሆናችሁ ፥ አንዳች የሆነ የቡድን እና የመኖር (survivial) ጥያቄያችሁን የሚመልስላችሁ ይሄ እናንተን የሚመስለው ሰው ነው። ልጆቻችሁ የነጭ ትልቅ መሆን አይደለም በአስጨናቂ እና ከባድ ወቅት የሚያጀግናቸው እና እስከመጨረሻው ለመዋጋት የሚያጠነክራቸው። ይልቁንስ ሌላ እነሱን የሚመስል ሰው ስኬታማ መሆን መቻሉን ሲመለከቱ ነው የሚበረታቱት።



የአበበ ቢቂላ የማራቶን ድል ለብዙ ኢትዮጵያኖች በር እንደከፈተ፤ እኛን የመሰሉ ሰዎች የበለጠ ሲሳካላቸው ለኛም በር የበለጠ ይከፈታል። ብዙ ስኬታማ የኢትዮጵያ ቢዝነሶች አሉ ማለት ብዙ ኢትዮጵያኖች የሥራ ዕድል ያገኛሉ ማለት ነው። ብዙ ኢትዮጵያኖች የሥራ ዕድል ሲያገኙ ሀገር ቤት ብዙ ሰው ይታገዛል ማለት ነው። እርሱ ብቻ ሳይሆን ቢዝነሶች በባህሪያቸው ሌሎች ግብአቶችን ይፈልጋሉ። ለምሳሌ የሬስቶራንት ቢዝነስ ስጋ የሚያቀብለው ይፈልጋል። የጥራጥሬ እና የስፓይስ ግብአት ይፈልጋል። የማስታወቂያ ድጋፍ ይፈልጋል። ስለዚህ ስኬታማ የኢትዮጵያ ሬስቶራንት አለ ማለት እነዚህን ግብአቶች ከሌሎች ኢትዮጵያኖች መግዛት ይችላል። ለሌሎች ብዙ ሰዎች የቢዝነስ ዕድል ፈጠረ ማለት ነው። አንድ የማውቀው ኢትዮጵያዊ የሪል ስቴት ባለሀብት አለ። ቢሞት የነጭ ሪሌተር አይቀጥርም። ሁልጊዜ ቤት ሊገዛ ሲፈልግ ብዙ በእውቀት እና በዋጋ የተሻሉ ነጭ ሪሌተሮች እያሉ እርሱ ግን ኢትዮጵያዊ ሪሌተር ነው የሚጠቀመው። ይሄ ለኢትዮጵያኖች አዝኖ ብቻ እንዳይመስላችሁ። ኢትዮጵያዊ ሀብታም በብዛት ቢኖር የመጀመሪያው ተጠቃሚ እርሱ እንደሆነ ስለገባው ነው።



ኢትዮጵያኖች ግን ገና ስትጠይቋቸው የነጭን ሰርቪስ እንደሚጠቀሙ በኩራት እና በጀግንነት ነው የሚነግሯችሁ። “እኔ ኢትዮጵያዊ አልቀጥርም ወይም እኔ ኢትዮጵያዊ ጋር አልሄድም” በማለት ልክ ጽድቅ እንደሰሩ በኩራት ነው የሚናገሩት። በእኔ የሕግ ሥራ ውስጥ ያሉ ብዙ የነጭ ጠበቆች አንዱ በጣም የሚያስገርማቸው ነገር አብዛኛው ስደተኛ ፕሬዝዳንት ትረምፕን መምረጡ ነው። ይሄን ደግሞ በኩራት ነው ብዙ ኢትዮጵያኖች ጭምር የሚያወሩት። ተመልከቱ ፖለቲካ የጥቅም መድረክ ነው። “ማነው የእኔን እና የወገኔን ጥቅም በተሻለ የሚያስጠብቅልኝ” ብለህ አስበ ነው የምትመርጠው። በምን ተዓምር ነው አንደ በነጭ የበላይነት የሚያምን ነጭ እና ኢትዮጵያዊ አንድን የፖለቲካ ተመራጭ በተመሳሳይ ሊመርጡ የሚችሉት?


ለብዙ ኢትዮጵያኖች ሌሎች ኢትዮጵያዊ ስደተኞች ባይመጡ እና ሀገሩ የነጭ ብቻ ሆኖ እነርሱ ግን በሰላም ቢኖሩ ደስ ይላቸዋል። ከዚህ በላይ primordial and lowest thinking (በጣም ዝቅተኛው የእንስሳዊ አስተሳሰብ ማሳያ) ወዴት ይገኝ ይሆን?



በርዕሴ እንደገለጽኩት አይሁዶች ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ የተማሩት አንድ እውነት መተባበር እና በሕብረት ተደጋግፎ መሥራት ብቻ በዚህ ዓለም እንደሚያስከብር ማወቃቸው ነበር። የዛሬ ሁለት ዓመት ከራሺያ የመጣ አንድ አይሁድ ቤቴ ከሚስቱ ጋር ጋብዤው ማውራት ጀመርን። ከዛ “አይሁዳች በጣም አዋቂ እና ጂኒየስ ናችሁ” አልኩት። ስቆ፦ “እንደዛ እንኳን አይመስለኝም። እኛ በሁሉም ቦታ ተበትነን ያለን እና በሄድንበት ሁሉ አናሳ የሆንን ነን። በዚህ ደግሞ ለተከታታይ ጥቃቶች ተጋልጠናል። ስለዚህ መተባበር ብቻ የመኖር ሕልውና ማስከበሪያችን መሆኑን አወቅን አለኝ። ለምሳሌ ልንገርህ። እኔ እዚህ ስመጣ የማላውቃቸው አይሁዶች እየጠሩኝ በተከታታይ ግብዣ ያደርጉልኝ ነበር። በማንኛውም ጊዜ ቢቸግርህ አለን ከጎንህ ይሉኛል። ይሄ የአይሁድ እምነት ልከተል ወይም በፖለቲካ እምነቴ የግራ ዘመም ወይም ቀኝ ዘመም ልሁን ምንም ሳይገዳቸው ነው። ይሄ በየቦታው ባህል ተደርጓል። አይሁዳዊ መሆኑ ብቻ በቂ ነው። ያን ሰው መርዳት እና መደገፍ እና ስኬታማ እንዲሆን አስፈላጊውን ዕድል መፍጠር የሁላችንም ግዴታ ነው። ስለዚህ ይሄ ስሜታዊ ትስስር ስላለ ጥቂትም ብንሆን ትብብሩ ስላለ በቀላሉ ብዙ ቁልፍ ቦታዎችን መቆጣጠር እና ስኬታማ መሆን ችለናል።” አለኝ።



ኢትዮጵያኖች ከዚህ ብዙ መማር ይኖርብናል። እውነት ነው ይሄ ካለ እውቀት እና ቆም ብሎ Reflect ካለማድረግ አይመጣም። ግን ይሄን የምታነቡ ሰዎች ቢያንስ ለመለወጥ አስቡ። ጥቂት ለውጦች እየተጠራቀሙ መጨረሻ ላይ ጠንካራ ባህል ይሆናል።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Apr 13
  • 6 min read




አዋቂው ቻርሊ መንገር እንዲህ ይላል "95% የሚሆነው የስኬት ምንጭ ደደብነትን ከሕይወት በማራቅ የሚመጣ ነው።" ብዙ ሰዎች ስኬት የሚገኘው እጅግ አዋቂ በመሆን ይመስላቸዋል። ባለው የዘር ግንድ ሳይሆን ዓለም ላይ ባሳደረው ተጽዕኖ ምክንያት በዌስት ሚኒስትር ለመቀበር የበቃው ቻርልስ ዳርዊንን ብትጠይቁት እውነቱን ይነግራችዋል። ዳርዊን በሕይወቱ ገና ወጣት እያለ ነበር የIQ መጠኑ ዝቅተኛ እንደነበረ የደረሰበት። ግን ታታሪ ሰው ስለነበረ ከሱ በፊት የነበሩ ሰዎችን ስኬት እና ውድቀት ሲያጠና የደረሰበት እውነት ፥ ስኬት እጅግ ብዙ ጊዜ ደደብነትን በማሶገድ የሚገኝ እንጂ ስማርት በመሆን የሚመጣ እንዳልሆነ ነበር። ስለዚህ በሕይወቱ ሁሉ ደደብ ላለመሆን ብቻ ሠራ። ምንአልባት ዓለም ሁለት ትርክት ቢኖራት ፥ አንዱ ትርክት መሠረቱ የዳርዊን ነው። ደደብነትን በከፍተኛ ደረጃ በመቀነስ የዓለም የትርክት አንደኛው ምንጭ ሆነ።



ትዝ ይላችዋል ልጅ ሆነን ወላጆቻችን ደደብ ብለው ለምን እንደሚሰድቡን? ስማርት ስላልሆንን አልነበረም። ፈጽሞ። ደደብነት ስማርት (ጂኒየስ) ያለመሆን አይደለም። ደደብ የሚሉን የነበረው ብዙ ሰው ዓይቶት እኛ ማየት ስለተሳን ነገሮች ነበር። በቀላሉ ግልጽ ሊሆንልን የሚችሉ ነገሮች ከተሰወሩብን ደደብ ይሉናል። እንደ ሮቢንሰን አዳም ትንታኔ ደደብነት ማለት በጣም ግልጽ የሆነን ነገር ችላ ማለት ወይም መካድ ነው።



ሰው ሁሉ ፍቅረኛዋ እየተጫወተባት እና በአፉ ብቻ እየደለላት እንደሆነ እያወቀ ነገር ግን እርሷ ብቻ ይወደኛል ብላ የምታስብ እና “እርሱ እኮ እንዲህ ስለሆነ ነው” እያለች ምክንያት የምትሰጥ ሴትን ደደብ እንላታለን። ምክንያቱም ሁሉም ማየት የቻለውን ነገር እየካደች ነውና። ይህች ሴት በመስታወት ብቻ የሆነ በር ተመልክታ ነገር ግን በሩ ላይ የመክፈቻ እና መዝጊያ መያዣ ያለውን ሳታይ እንደምትጋጭ ሰው ትመስላለች። መስታወቱ ጥርት ማለቱ የበሩን መያዣ እንዳታይ አድርጓታል፤ ምንም እንኳ ያ በግልጽ ቢታይም።



ደደብነት የሚመነጭባቸው ስምንት ዋነኛ ቦታዎችን እንመልከት፤



1) ከየቀን ሁኔታ እና ከምቾት ዞናችን ስንወጣ፤



ለምሳሌ ታዋቂው የጊታር ተጫዋች እና ቦስተን ስቴት የሚኖረው ዮዮ ማ ለኮንሰርት ኒው ዮርክ ከተማ ሲሄድ ታክሲ ውስጥ ጊታሩን ረስቶ ወጣ። ዮዮ ማ ስለሆነ ከከተማው ከንቲባ እስከ ፖሊሲ አለቃው እና የሕዝብ ሬዲዮ ተረባረበ። ይሄን የሰሙ ሰዎችም ሆነ ሌሎች ጊታር ተጫዋቾች “ዮዮ ማ አደንዣዥ ዕጽ (drug) ወስዶ ነበር ወይ ሰክሮ ነበር” እያሉ አሾፉ።


በሚገርማችሁ ሁኔታ ይሄ እንዴት በራሳቸው ላይ ሊፈጠር እንደሚችል ብዙዎች እምብዛም መፈተሽ አልፈለጉም። እውነታው ግን ኒው ዮርክ ከተማ ውስት ለኮንሰርት ከሚሄዱ ጊታሪስቶች 15% የሚሆኑት ጊታራቸው ከኮንሰርት በፊት ወይ በኋላ ይጠፋባቸዋል። ለምን? ምክንያቱም ከየቀን ውሎህ እና ከምታውቀው ከባቢ ስትነጠል አዕምሮአችን የቱ ጋር መልህቁን እንደሚጥል አያውቅም። አዕምሮአችን የሚደገፍባቸው የልምድ እና የአከባቢ መዘውሮች ይቋረጣሉ። ለዚህም ነው አዲስ ከተማ ሄደን የሆቴላችንን ቁጥር የምንረሳው። ለዚህ ነው አንዳንድ ሰዎች ኤርፖርት ደርሰው ፓስፖርታቸው ግን ኪሳቸው ውስጥ የለም። ለምሳሌ ከክፍላቸው መኪናቸውን እየነዱ ለመሄድ አስበው ወጥተው ፥ የመኪናቸውን ቁልፍ ግን ክፍላቸው ረስተዋል። የመጀመሪያው ይሄን ደደብነት የማሶገጃው መንገድ አዕምሮአችን የልምድ እና የአካባቢ እስረኛ መሆኑን ማወቅ ነው። ለምሳሌ መንገድ የሚሄድ ሰው ፖስፖርቱን ነገ የሚያደርገው ጫማ ውስጥ ቢከት ፥ ይሄን ደደብነት በቀላሉ አሶገደ ማለት ነው። ወይም ቁልፋችንን ሁልጊዜ ተመሳሳይ ቦታዎች ብቻ ማኖር። ሁሉንም ነገር ካላንደር ላይ ማኖር እና የጠዋት የመጀመሪያው ሥራችን ካላንደርን ቼክ ማድረግ ቢሆን


ሰዎች ደደብ ነገር ሲያደርጉ ከማሾፍ እና ከመሳለቅ፤ "እኔ በምን ሁኔታ ብሆን ነው ይሄን የምፈጽመው" ብላችሁ ጠይቁ። ያን ቢጠይቁ ኖሮ ዮዮ ማ የሰራውን ደደብነት ሌሎች ጊታሪስቶች ባልደገሙ ነበር።



2) በቡድን ውስጥ መሆን፤



የናሳ የ1986 ትልቁ አደጋ የዚህ የቡድን (የግሩፕ) ውጤት ነው። በጣም ብዙ ኢንጂነሮች የኦሪንግን (O-ring) ችግር ያውቁ ነበር። ግን በቡድን ስብሰባ ወቅት ሌሎቹ ዝም ስላሉ ሁሉም ፈርተው ዝም አሉ። ምክንያቱም ከላይ ያሉት አለቆቻቸው እና ዋይት ሃውስ የፕሮጀክቱን መሳካት እንዲፋጠን ይፈልጉ ነበር። በሰላማዊ ሰልፍ ወቅት ሰዎች በግል ቢሆኑ መቼም የማያደርጉትን ነገሮች ያደርጋሉ። ለምን? ምክንያቱም በግሩፕ ሲኮን ደደብነት ይደበቃል። ደደብነት ጀግንነት ተደርጎ ይቆጠራል።


ካስ ሰንስቲን በአንድ መጽሀፉ ለመሪዎች ምክር ሲሰጥ በስብሰባ ወቅት መጀመሪያ መሪው ፈጽሞ መናገር የለበትም፤ ምክንያቱም እርሱ ከተናገረ በኋላ መቃረን ከባድ ነው። ያ ብቻ ሳይሆን መሪው ተናጋሪ ሰዎች መጀመሪያ እንዲናገሩም መፍቀድ የለበትም። ዝምተኞች፣ ሰዎች ባሉበት መናገር የሚፈሩ ሰዎችን መጀመሪያ ሀሳባቸውን መጠየቅ አለበት። እውነትን ለማወቅ እና ለድርጅቱ ታላቅነት የሚተጋ መሪ ከሆነ። እነዚህ ዝምተኞች ብዙ ጊዜ ተመልካቾች ናቸው። ስለዚህ ሲጠየቁ እውነትን የመፈንጠቅ አቅም አላቸው። ግን ተናጋሪዎች ወይም መሪው አስቀድሞ ከተናገረ ግን “እርሱ እና እርሷ እንዳለችው” እያለ ነው ሁሉም ነገር የሚቀጥለው።


በዓለማችን ብዙ አይሮፕላን የተከሰከሰበት ኤርላይንስ የደቡብ ኮርያው ነበር። ለዚህም ዋነኛው ምክንያት በባህላቸው አለቃን ወይም ከፍ ያለን ሰው መቃረን በጣም አስቸጋሪ ስለሆነ ነበር። ስለዚህ ጥፋት እንደሆነ እያወቀ እንኳን ኮ-ፓይለቱ (co-pilot) የፓይለቱን ስህተት ዝም ብሎ ያልፋል። አሜሪካን ማናጀሮች መጥተው የደቡብ ኮሪያን ኤርላይንስ ባህል እስከሚቀይሩት ድረስ ይሄ ትልቅ ፈተና ሆኖ ነበር።



3) በሙያ እና በእውቀት ከሚበልጠን ሰው አጠገብ መሆን (ወይም ራሳችን በሙያ ፍጹም ከፍ ስንል)፤



አዲስ ተቀጣሪው የኤክስፐርቱን ግልጽ ስህተት እያየ ዝም ይላል። ምክንያቱም እርሱ ከእኔ የተሻለ ያውቃል ብሎ ያስባል። ዶክተሩ ያውቃል ብሎ ስለሚያስብ ፥ ደደብ የሆነ ነገር በሰውነቱ ላይ ሲደረግ እያየ በሽተኛው ዝም ብሎ ያልፋል። በ2008 የነበረው የአሜሪካ የፋይናስ ውድቀትን ብዙ ሰዎች ያስተዋሉት ቢሆንም ኤክስፐርቶች ስለ ኢኮኖሚው ውብ ስዕል መሳላቸውን ስለቀጠሉ እየመጣ የነበረውን ውድቀት ችላ አሉት። በሃይማኖት ውስጥ ያሉ ሰዎች ፥ "እንደዚህ ያሉ የተመራመሩ እና አዋቂ ሰዎች ይሄ ሃይማኖት ልክ ነው ካሉ ፥ ልክ ነው" ብለው ሲቀበሉ አላያችሁም?


 እኛም በእውቀት እጅግ የሚያንሰን ሰው በጣም ተራ የሆነ ስህተታችንን ሲያሳየን ፥ መቀበል ይከብደናል። ለምን?


ምክንያቱም እውቀታችን አደድቦናል።



4) እጅግ ትኩረት የሚፈልግ ነገር ስንሰራ፤



ቼዝ የምትጫወቱ ሰዎች ታውቃላችሁ፤ በራሳችሁ ስትራቴጂ ላይ በጣም ትልቅ ትኩረት ከጣላችሁ ከየት መጣ የተባለ የተቀናቃኝ ጦር ቼክ ሜት ይለናል። በራሳችን ምርጥ ስትራቴጂ ስለተወሰድን የተቀናቃኛችንን ወደ እኛ መጠጋት ፈጽሞ ማየት ይሳነናል። ይሄ ማለት መነጽሩን አድርገን መነጽሩን መፈለግ ማለት ነው። ልክ አናጺዎች እርሳሱን ጆሮአቸው ላይ አድርገው እርሳሱን እንደሚፈልጉ። ወይም ስልኩን እያናገሩበት ስልኩን ራሱ የት አስቀመጥኩት ብለው እንደሚፈልጉ ሰዎች ማለት ነው። በሕይወት እጅግ ብዙ ደደብ ሥራ የምንሰራው ፥ የራሳችንን ብቻ ነገር ስናይ ነው። ይሄ ዓለም ሌሎችም የሚኖሩበት ነው። የሌሎች ተግባር ለኛ ሕልውና ልክ እንደኛው ተግባር የመጥፊያ ምክንያት ሊሆን ይችላል። የአንተ መስመር እና የትራፊክ ሕግ አክብረህ መሄድ በራሱ ከመጥፎ የትራፊክ አደጋ አይጠብቅህም። ለዚህም ነው የሌሎችን አነዳድ እንድናይ መስታወቶች የተገጠሙሉን። እኛ በጣም ጠንቃቃ ብንሆን ሌላው ጠንቃቃ ካልሆነ ሞታችን ቅርብ ሊሆን ይችላል። በዚህ ዓለም የሌሎችንም ተግባሮች ለሕግ እና ለሥርዓት ለማስገዛት መስራት ተገቢ ነው።



ቀላል የማይባሉ ሰርጅኖች ኦፕራሲዮኑ ላይ ብቻ ትኩረት ሲያደርጉ መቀስ ሆድ ውስጥ ጥለው ይወጣሉ። ለዚህ ነው ክፍል ውስጥ የገባውን እቃ እያንዳንዷን ከኦፕራሲዮኑ በፊት ቆጥረው ልክ ያንን ሰርጀሪ ሲጨርሱ መልሰው የሚቆጥሩት። መርሳት የሰው ልጅ ባህሪ ነው። ስለዚህ በራሳቸው የማስታወስ ብቃት አይደገፉም።



5) የመረጃ መብዛት፤



ብዙ መሪዎች መጥፎ ውሳኔ የሚወስኑት ከመረጃ እጥረት ሳይሆን ከመረጃ ብዛት ነው። ስለ ጦርነት እየወሰነ ያለ መሪ ስለኢኮኖሚው፣ ስለትምህርት ጥራት፣ ስለጤናው ዘርፍ በተመሳሳይ ሰዓት ሪፖርት እንዲቀርብለት ከፈቀደ ፥ መጥፎ ውሳኔ የመወሰኑ ነገር ርግጥ ነው። ወላጆች ከሥራ መጥተው ልጆችን የሚገርፉት ወይም ያለሆነ ውሳኔ የሚወስኑት አዕምሮአቸው በመረጃ ቀኑን ሙሉ ደክሞ አሁንም ሌላ መረጃ ሲመጣለት የውሳኔ ባላንሱን ስለሚያጣ ነው። ኢንቬስተርስ በግልጽ የሚታየውን የኢኮኖሚውን ውድቀት የሚስቱት ብዙ መረጃዎችን ስለ ኢኮኖሚው ስለሚሰሙ ነው። ስቶክ ትሬደሮች ቀዩን መስመር ሳያዩት ይቀራሉ ፥ ምክንያቱም እጅግ ብዙ መረጃዎችን በየቀኑ እንደጎርፍ ይቀበላሉ።



ታላቁ ኢንቬስተር ዋረን ባፌት ይሄን ስላወቀ ነበር ከስቶክ ትሬድ ማዕከል ከሆነችው ኒው ዮርክ ጭር ወዳለችው ኦማሃ ከተማ የሄደው። ምክንያቱም የመረጃ ብዛት አይደለም የጥሩ ውሳኔ ምንጭ። ጥቂት ግን ጥራት ያላቸውን መቀበል ነው የጥሩ ውሳኔ አንዱ ምሰሶ።


6) ድካም፤ ሕመም እና የስሜት ውጥረት፤



ከደከመኝ የደንበኞቼን ስልክ አላነሳም። ካነሳውም በጣም ስለደከመኝ ካስቀይመኳቹ የድካሜ ውጤት ነው ብዬ ማስጠንቀቂያ እሰጣለሁ። የደከመው ዶክተር በጣም ግልጽ የሆነውን መረጃ አሳስቶ አንብቦ ለበሽተኛው ያልሆነ መድኋኒት ሊያዝ ይችላል። ዳንኤል ኮነመን እና ካስ ሰንስቲን በጻፉት ኖይዝ በተባለው መጽሐፍ አሜሪካ ውስጥ ያሉ ዳኞች የከተማቸው የእግር ኳስ ወይም የባስኬት ቦል ቲም ተሸንፎ በማግስቱ ለፍርድ ፊት ለፊቱ ከቀረባችሁ ፥ መጥፎ ውሳኔ የመወሰኑ ዕድል በእጥፍ ይጨምራል። የጨወታው የሽንፈት ንዴቱ የፍትሐዊ ሚዛን አቅሉን ያስተዋል። ወላጆቻችን በማያስገርፍ ጥፋት ደብድበውን ያውቃሉ፤ በሌላ ነገር ተናደው ወይም ደክሟቸው ካገኙን።



ሲ ኤስ ሉዊስ የሰይጣን የመጀመሪያው ሥራ እንስሳነትህን ማስረሳት ነው ይላል። እስቲ እንስሳ ሲበላ ምግቡን ቀማው። እንደሚነክስህ እርግጠኛ ነህ። አንተ ጌታው ብትሆን እንኳን። ሰውም እንደ እንስሳ ነው። ሲደክመው ወይም ሲታመም ወይም ሲበሳጭ ከሚገባው እና ከሆነው በላይ ይጮሃል።



7) መሮጥ እና መፍጠን፤



ይሄን አባባል ብዙዎቻችሁ ታውቁታላችሁ። ፈጥኖ ለመድረስ ቀስ ብሎ መንዳት። በፍጥነት የጫማችሁን ማሰሪያ ስታስሩ የበለጠ ትፈቱታላችሁ። 600 ሰው የሞተበት የ1977 የTenerife Airport Disaster በታሪክ ትልቁ የአውሮፕላን አደጋ የደረሰበት እና ሁለት ፓይለቶች አይሮፕላናቸውን ፈጥነው ወደ መውረጃ ማዕከሉ ጣቢያ ለማስጠጋት ሲሞክሩ የደረሰ ነበር። ይሄ የቼክ ሊስት (checklist) አለመከተል ችግር አልነበረም። ቼክ ሊስትን ብቻ የመከተል ችግር እንጂ። አንዱ የአንዱን ፍጥነት ለመመልከት ሳይሆን ፥ ቼክ ሊስታቸውን ለሟሟላት ነበር የፈጠኑት። መፍጠን እና መቸኮል የደደብ ውሳኔዎች እና ውጤቶች ሥር ነው።



8. ፍቅር እና ጥላቻ፤


ፍቅርም ጥላቻም ያሳውራል። ሁላችንም ከዚህ ከሚያሳውር ስሜት ነጻ አይደለንም። በአንድ ነገር ላይ ፍጹም ስናምን ከኛ የሚቃረኑ ሰዎችን ለመስማት እንጨክን። ለመማር በማሰብ። ዓለሙ ሁሉ እንደሞተ ያመነውን ጦር ሜዳ የሄደውን ልጇን ፥ ጦርነቱ ከተጠናቀቀ ከዓመታት በኋላ እንኳን እናት ልጇ እንደሚመጣ ትጠብቃለች። የልጅ ፍቅር እውነትን የመቀበል አቅሟን አሳጥቷታል። ልጅሽ እየተበላሸ ነው ሲሏት የእናት የመጀመሪያ ምላሽ መካድ ነው። ምክንያቱም ፍቅሯ መስማት የሚፈልገው በጎ በጎውን ብቻ ነው። የምትጠሉትም ነገር ተመሳሳይ ነው። ሂትለር ለልጆች ልዩ ፍቅር እንዳለው ፈጽሞ ማመን አንፈልግም።ስለእሱ የሚታየን ያን ሁሉ አይሁድ እና ሌላውን ማህበረሰብ በግፍ መጨረሱን ነው። ግን የሂትለርን የልጆች ፍቅር ውሸት አያደርገውም።


ሴትን ያፈቀረ ወንድ እንከኗን መስማት አይፈልግም። ዘወትር ምክንያት ይሰጣል (justify ማድረግ)። ከሁሉም በላይ የምንወደው ደግሞ ራሳችንን ነው። ራሳችንን ዘወትር መከላከል (defend ማድረግ) ነው የምንፈልገው። ሰዎች አንዴ ቢሰርቁን የእነሱ ነገር በቃን ለማለት ፍጥነታችን። እራሳችንን ግን ሺ ዕድል ለመስጠት፣ መልሰን እና መላልሰን ለማመን ዝግጁ ነን። ለዚህ ነው ሰዎች አሉታዊ አስተያየት ስለ እኛ ሲሰጡን ይሄ የደደብነት ምንጭ የሆነውን የፍቅር መታወር ለጊዜው ያዝ ማድረግ ያለብን።



አሉታዊ (negative) አስተያየት ለመስማት እንፍቀድ። ቢያንስ ሰዎች ተናግረው እስከሚጨርሱ እንታገስ። ከዛ ደግሞ ይሄን አስተያየት ስለሰጣችሁን እናመሰግናለን እንበላቸው (ልክ ቢሆኑም ባይሆኑም)። ያን የመቀበል እና ያለመቀበል ፈንታ የራሳችን የቤት ሥራ ነው።


 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Apr 6
  • 3 min read


ብሩስ ሊ “በሕይወቴ ረዥም ጊዜ ለመማር የወሰደብኝ ግን ደግሞ ለማሸነፌ መሰረታዊ የሆነው ነገር ርጋታን መጎናጸፍነበር” ብሏል። በዚህ ዘመን ከምንም ነገር በላይ እያጣን ያለነው ነገር ርጋታ ይመስለኛል። ሁሉንም ነገር እኛ ባልነው ሰዓት እና ጊዜ ብቻ ማከናወን መፈለግ። ዛሬ ወይም በጣም አጭር በተባለ ጊዜ ውስጥ ሀብታም መሆን። ወይም አዋቂ መሆን።ወይም ታዋቂ። ይሄን ለመከወን ደግሞ ሁሉንም አቋራጭ መንገዶች ለመጠቀም መፈለግ። በዚህ ፍላጎታችን መስመር ውስጥ እንከን ከገጠመን ሰማይ ምድሩ ነው የሚገለባበጥብን።

 

መስከን የሚባል ነገር ርቆናል። ችግር የመቋቋም እና የመቻል አቅማችን ተሟጧል። ኃይሌ ገብረሥላሴ አንዴ እንዲህ ብሎ ነበር። “ታዋቂ መሆን አልነበረም በጣም ከባዱ ነገር ፥ ታዋቂነትን ያጎናጸፈኽን መልካም ስም ይዞ መቆየት እንጂ።” ጅል ውሳኔዎች የፍጥነት ውጤቶች ናቸው። ቶማስ ጀፈርሰን እንዲህ ይላል “ከተናደድክ እስከ አስር ቁጠር። በጣም ከተናደድክ ግን እስከ መቶ ቁጠር።” ይሄ ታላላቅ ተግባራትን የሰሩ ሰዎች ንግግር የሚነግረን የሰው ልጅ አዕምሮ ሁልጊዜ የምንመካበት እንዳልሆነ ነው። በፍጥነት ወቅት ባላንሱን ይስታል።

 

የሆነ ሰው ሲያናደኝ ራሴን የምጠይቀው “በዚህ ምድር ላይ ይሄ ሰው የተናገረውን ንግግር ሰምተው ምንም የማይመስላቸው ሰዎች የሉም? ልክ እኔን የተናገረኝን ቢናገራቸው ፥ ምንም እንዳልተፈጠረ የሚያልፉ የሉም? መልሴ ሁልጊዜ ማለት በሚቻል መጠን “አለ!” ነው። ስለዚህ ይሄ ነገር ግለሰባዊ (subjective) ነው ማለት ነው። የእኔ የዕይታ አድማስ መጥበብ እና የቆዳዬ ስሱነት እንጂ የሰውዬው ንግግር አይደለም ማለት ነው። ያ subjective የሆነ ግብረ መልሴ ዓለምን ከሌላ ሰው አንግል እንዳየው ያግዘኛል። ይሄ ማለት ቀላል ነው ማለት አይደለም። ፈጽሞ። ያልተገራ ውሻ ዘወትር ውስጣችን አለ።ውሻ እየበላ ያለውን ብታነሳበት ይነክስሃል። ምግቡን የሰጠኸው እና ነገም የምትሰጠው አንተ ብትሆን እንኳ።በተመሳሳይ ክብራችን፣ እንጀራችን፣ ኢጎአችን፣ ድንበራችን ፥ ተነካ ስንል ፥ እንናከሳለን። ለውሻው ራስን መግዛት እና ስለነገ ማሰብ ከባድ እንደሆነው ሁሉ ፥ እኛም ያን ማሰብ በጣም ይከብደናል።

 

ይሄ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ያልቆመ ነገር አለ። ሰውን በንዴት እና በቅናት ተነሳስቶ ማጥቃት። ምንም እንኳ ይሄን የሚያደርጉ ሰዎች መጨረሻቸው ጸጸት እንደሆነ እያወቅን እንኳን ዛሬም ያን የሚያደርጉ ሰዎች እልፍ ናቸው።

 

የሒሳብ ሊቁ ብሌዝ ፓስካል “የሰው ልጅ ችግር ሁሉ የሚመነጨው ፥ ሰው ብቻውን በርጋታ አንድ ክፍል ውስጥ ለመቀመጥ ባለመፍቀዱ ነው” ይላል። ሊቁ ጸጋዬ ገብረመድኅን ይሄን ግብዣ ነው ለሁላችንም ያቀረበልን። “አብረን ዝምእንበል” በሚለው ግጥሙ። “አጉል ነው ብለን ሳንፈርድ ድንቅም ነው ብለን ሳናደንቅ አስቲ ለአንድ አፍታ ዝም እንበል” ፥ መገዳደል እና መፍክር ማብዛት ለተጣባው ፖለቲካችን ምክር ሰጠን።

 

ዳንኤል ኮነመን “ብዙ ሰው የሚወደው ስፖርት ፥ ውሳኔ ላይ በፍጥነት መዝለል ነው (jumping to conclusion)” ይላል። ምንአልባት ያን አለማድረግ አንችል ይሆናል። ለሆነ ሰው ስልክ ደውለን ሳያነሳልን ሲቀር ፥ ንቆኝ ነው ማለት ይሆናል መጀመሪያ የሚቀለን። ምን አልባት የሆነ ነገር ፈልገን ስናጣ ፥ እከሌ ሰርቆን ነው ማለት ይሆናል የመጀመሪያው ውሳኔያችን። መጥፎ መጥፎውን ይሆናል መጀመሪያ አዕምሮአችን የሚያሳስበን። እንዲህ አስቤ ከዛ ውጤቱ ሌላ ሲሆን ፥ ራሴን “አየ አይደል!ትቸኩላለህ። ይሄ የመጀመሪያህ አይደለም። ብዙ ጊዜ እንዲህ ብለህ ከጠበከው ውጪ ሆኗል። ስለዚህ ተጠንቀቅ እለዋለሁ።” ከራሳችን ጋር መወቃቀስ እና ራሳችንን ሰው ሳይታዘበን በፊት እንታዘበው። ትላንት ተሳስተሃል። አሁንስ ልትሳሳት ብትችልስ? ስለዚህ ታገሰ። ተረጋጋ እንበለው።

 

ብሩስ ሊ እንዳለው ርጋታን መላበስ ፥ የትኛውንም ውጊያ የማሸነፊያ ጥበብ ነው። በሀገራችን መሪዎች ውስጥ እጅግብዙ ያሳኩ መሪዎቻችን አብዛኛው ጊዜ የሚታወቁት በታጋሽነታቸው ነው። በአጭር ሕይወታቸው የተቀጩ እንደ ቴዎድሮስ፣ ዮሐንስ፣ ኢያሱ እና መንግስቱ ኃይለማርያም ያሉት ደግሞ ቁጡዎች እና ፈጥነው ውሳኔ መስጠት የሚወዱ ነበሩ። እነዚህ ረጅም አልመው በአጭር የተቀጩ  መሪዎች ናቸው። በዘመናቸው ለሕዝባቸው ጦርነትን አብዝተው የሰጡ ነበሩ።

 

ታሪክ የሚነግረን መረጋጋት እና መታገስ የስኬት ጨው መሆኑን ነው። መረጋጋት ማለት ግን ውሳኔ ለመወሰን የሚቸገርን ሰው አይወክልም። የተረጋጋ ሰው መወሰን ተቸግሮ አይደለም። ይልቁንስ ውሳኔው ነው ያረጋጋው። በአዕምሮ ውስጥ ቀጣይ የሚወስዳቸው ርምጃዎች ሁሉ ግልጽ ስለሆኑለት ወይም በርጋታ ውስጥ ያልተገለጡ እና በቅርብ ሊያውቃቸው የሚገቡ መረጃዎችን እየጠበቀ ስለሆነ ነው የተረጋጋው። ንድፈ ሀሳቡን በርጋታ ውስጥ በተግባር እየፈተሸው ነው። ርጋታ ማለት ጉዞ አልባነት አይደለም። ይልቁንስ ርጋታ ማለት የድብቅ እና የስውር ሩጫ ማለት ነው። ርጋታ ማለት ንፋሱን ቁጡ እና ቀበጥባጣው ሰው እንዲሰብረው ግን አንተ ከኋላ ሆነ የደውሉን ፍጻሜ የምትጠባበቅበት ስፍራ ማለት ነው። ርጋታ ማለት ነብር በሆዱ እየቧጠጠ ወደ ሚያድነው ታርጌት ከእይታ ተሰውሮ የሚቀርበብት ሁኔታ ማለት ነው።


ርጋታ ማለት እዩኝ የሌለበት ፈጣን እድገት ማለት ነው።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page