- Mulualem Getachew
- 6 days ago
- 5 min read

በሥራዬ ምክንያት በአሜሪካ ዙሪያ ያሉ ብዙ የኢትዮጵያ ቢዝነሶችን በሕግ ዙሪያ የማማከር ዕድሉን አግኝቻለሁ። ብዙዎቹንም የሕግ ጉዳይ እና ችግር ገጥሞአቸው ረድቻቸዋለሁ። ወይም ከሚረዷቸው ሰዎች ጋር አገናኝቻለሁ። የዚህ ጹሁፍ ዓላማ ግን እርሱ አይደለም። የማገኛቸው ብዙ የኢትዮጵያ ቢዝነስ ሰዎች የሚነግሩኝ ነገር ፥ ከሚረዷቸው ኢትዮጵያኖች ባልተናነሰ ብዙ ምቀኛ እና ተንኮለኛ ኢትዮጵያዊ አለባቸው። የሆነ ችግር ሲገጥማቸው ምሳር የሚያበዙባቸው እንጂ የሚበዙት፤ አዲስ ቢዝነስ ሲከፍቱ መደገፍ ወይም ማገዝ እና እንዳይወድቁ የሚረባረቡ ኢትዮጵያኖች አይደለም በብዛት ያሉት።
በሚገርማችሁ አሜሪካ ውስጥ አንድ የኢትዮጵያ ሞል አታገኙም። በዋሽንግተን ዲሲ እና አከባቢው (ቨርጂኒያ እና ሲልቨር ስፕሪንግን ጨምሮ) እስከ 250 ሺ ኢትዮጵያዊ አለ። ሚኒሶታ ትልቁ የሶማሌ ኮሚኒቲ ያለበት ስቴት ነው። ቁጥራቸው ግን ወደ 60 ሺ ብቻ ነው። ይሄ ከኢትዮጵያኖች ጋር ሲነጻጸር በብዙ እጥፍ ያንሳል። ነገር ግን ከአንድም ሁለት ትልልቅ የሶማሌ ሞል በሚኒሶታ አለ። የዚህን ምስጢር ብዙ የሶማሌ ደንበኞቼን ስጠይቃቸው የሚሉኝ “ሶማሌ ከሌላ ሶማሌ ሱቅ ይገዛል። ልብስ ከፈለገ የነጭ ሱቅ ሳይሆን የሚሄደው እዛው አጠገቡ ያለውን የሶማሌ ቢዝነስ ነው የሚደግፈው። ከዛው በመግዛት።” ይሄ በኢትዮጵያኖች ዘንድ እምብዛም አልተለመደም። ብዙ ኢትዮጵያኖች ወገናቸው ከስሮ ፥ ስለክስረቱ ማውራት ያስደስታቸዋል ፥ ያን ሰው ተሯርጠው ደግፈው እንዲሳካለት ከማድረግ ይልቅ።
ስለብዙ ነገር ሳስብ ፥ ወደ መሠረቱ ሄጄ ለመረዳት እሞክራለሁ። ስለ ኢትዮጵያኖችም ይሄ አስገራሚ ራስን የሚጎዳ ባህሪ ሳስብ ፥ ወደ መሠረቱ ሄጀ ለማሰብ ሞክሬያለሁ። ኢትዮጵያኖች የተለየን ሆነን አይደለም እንደዚህ አስገራሚ ባህሪ የምናሳየው። ማለት በጣም ጥልቅ የሆነ የምቀኝነት ባህል እና ባህሪ (ጠልፎ የመጣል ባህል) የኖረን ፥ እጅግ ኋላ ቀር የሆነ የአስተሳሰብ ተሸካሚ ማህበረሰብ ስለሆንን ነው።
ልክ የኢትዮጵያኖች ዓይነት በጣም ኋላ ቀር የምቀኝነት ባህል እጅግ ደሃ የሆኑ ማህበረሰቦች ሁሉ አላቸው። ታላቁ የቲዎሎጂ ሊቅ ሲ ኤስ ሉዊስ “የሰይጣን ትልቁ ተልዕኮ ሰው እንስሳነቱን እንዲረሳ ማድረግ ነው” ይላል።
ሰዎች በትምህርት የጎደልን እና በስሜት የምንመራ ስንሆን እንስሳዊ ባህሪያችን ብቻ ነው የኛ አስተዳዳሪ የሚሆነው። ብዙ ሰው ቅናት እና ምቀኝነት የክፋት ውጤት ይመስለዋል። ይሄ ግን ደካማ ትንታኔ ነው። ቅናትም ሆነ ምቀኝነት እንስሶች ራሳቸውን ለመጠበቅ የሚያመነጩት የሆርሞን መጠበቂያዎች ናቸው። የምንፎካከረው ከኛ በጣም በቅርብ ርቀት ካለ ሰው ጋር ነው። ያ ሰው በሀብት ወይም በማናቸውም ነገሮች ሲበልጠን ፥ እንስሳዊ ባህሪያችን ዕድል (opportunity) አይደለም የሚታየው። ይልቁንስ መሸነፍ፣ ዝቅተኛ መሆን፣ በሌሎች ተፈላጊ አለመሆን እና ብቸኛ መሆን ነው የሚታየው። ስለዚህ ራሱን የሚከላከለው የሚበልጠውን በማጥፋት ነው። ምክንያቱም ሰው ፍጹም የሆነ ሚዛን (objective truth or standard) የለውም። የሚያስበው ሁሌ በአንጻራዊ ሁኔታ ነው። በምሳሌ ላስረዳ። የአሪዞናው ዩኒቨርስቲ ፕሮፌሰር ካልዲኒ አንድ የሰራው አስገራሚ ጥናት አለ። በዚህ ጥናት አምስት ሰዎችን በጣም ቀዝቃዝ የሆነ ክፍል ውስጥ አስገባቸው። ሌሎች አምስት ሰዎችን ደግሞ በጣም የጋለ ሙቀት ያለበት ክፍል ውስጥ ለተወሰነ ደቂቃ አስገባቸው። ከዛ ሁለቱንም ከየክፍላቸው አውጥቶ ወደ ሩም ቴምፕሬቸር (ዓየሩ ወደ ተስተካከል) ክፍል ውስጥ ከተታቸው። በጣም ቀዝቃዛ ከሆነ ክፍል ውስጥ ለመጡ ይሄ ክፍል ሲሞቃቸው፤ በጣም ሙቅ ከሆነ ክፍል ውስጥ ለመጡት ደግሞ ይሄ ክፍል ቀዘቀዛቸው። ይሄ የሚያሳየን የሰው ልጅ የተስተካከል ሚዛን (objective truth/scale) የሌለው መሆኑን ነው። ሁልጊዜ የሚያስበው በንጽጽር ሁኔታ ነው።
ኢለን መስክ በብዙ እጥፍ በሀብት እየበለጠን በርሱ ሳይሆን የምንቀናው፤ የምንቀናው በምናውቀው እና አብሮ አደግ በሆነ ጓደኛችን ነው። ምክንያቱም የዝቅተኛ ስሜት እና የመሸነፍ እና ያለመፈለግ ስሜት በውስጣችን የሚጭረው ያ የምናውቀው አብሮ አደግ ጓደኛችን ሲበልጠን ነው። ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ "ሰው ሀዘን የሚሰማው እንደሚያሸንፈው የሚያስበው ሰው ሲበልጠው ነው።" ይላል። ያ Primordial በሆነው እንስሳዊ ዓለም ውስጥ ፥ በአቻው የተበለጠ እንስሳ የመኖር ተስፋው እና በተቃራኒ ጾታ ተፈላጊነቱ እጅግ ዝቅ ስለሚል ፥ ራሱን በሌላ ዘር የመተካት አቅሙ ሳይቀር ነው የሚቀንሰው። ለምሳሌ ፒኮኮች ያላቸው ቀለማማ ጸጉር ምንም ጥቅም የለውም። ከአንድ ጥቅም ውጪ። ላባቸው እጅግ ቀለማማ ነው ማለት የሚያባክኑት ከፍተኛ የሆነ አቅም (energy) አላቸው ማለት ነው። ያ ደግሞ ለርቢ በጣም ወሳኙ ዘር መሆናቸውን ለተቀራኒው ጾታቸው ያሳውቃሉ። ስለዚህ ብዙ ቀለማት ያላት ፒኮክ ከሌሎች ፒኮኮች ይልቅ በተቃራኒ ጾታ በጣም ተፈላጊ ትሆናለች። በዚህም ለዘር (ለርቢ) ምርጧ መሆኗን ታሳያለች። ይሄ በጣም ዝቅተኛ አስተሳሰብ ባላቸው ሰዎች ዘንድ በተመሳሳይ አለ። ለምሳሌ የእነዚህ ፒኮኮች ባህሪን ልክ እንደ መንሱር ጀማል ያሉ ሰዎች ላይ ታያላችሁ። ብዙ የሚጨነቁት ለሰዎች እና ለማህበረሰቡ ስለሚያሳዩት የሀብት መገለጫዎች ነው። ያ በጣም ዝቅተኛ የሆነው እንስሳዊ ባህሪ ሲያስተዳድረን የምናሳየው ባህሪ ነው።
እጅግ ስማርት የሆነ ሰው፤ ጓደኛው ሀብታም ቢሆን እርሱም ሀብታም የመሆን ዕድሉ በጓደኛው ሀብታም መሆን ብቻ እንደሚጨምር ነው የሚያውቀው። ቢያንስ ለለቅሶ፣ ለምርቃት ወይም ለሆነ ችግር ጓደኛው ሲመጣ ሀብታም ቢሆን ደሃ ከሚሆን ይልቅ የሚሰጠው ገንዘብ ከፍ ይላል። በጓደኛው ኮኔክሽን እና ኔትወርክ ተጠቅሞ እርሱም ወደ ሀብት ከፍ ሊል ይችላል። ይሄ ሁልጊዜ እውነት ባይሆን እንኳን ጓደኛው ሀብታም በመሆኑ ዕድሉን ያሰፋዋል።
በተመሳሳይ ኢትዮጵያኖች በአሜሪካ ውስጥ ያሉ ሌሎች የኢትዮጵያኖችን ቢዝነሶች በስትራቴጂ ቢደግፉ ፥ የመጀመሪያው ለልጆቻቸው እነዚህ ስኬታማ ኢትዮጵያኖች ዓርአያ መሆን ይችላሉ። በአሜሪካ ውስጥ ኢትዮጵያዊ ተኮኖም ሊሳካልን እንደሚችል ማሳያ አገኘን ማለት ነው። የሰው ልጅ ደግሞ በእንስሳዊ ባህሪው ምክንያት የሚቀናው ብቻ ሳይሆን የሚበረታታውም አጠገቡ ባለው ሰው ነው። ለምሳሌ መንገድ ላይ ስትሄዱ ነጭ ብቻ እያለፈ ፥ ድንገት ኢትዮጵያዊ የሚመስል ሰው ሲያልፍ ካያችሁት አንገታችሁን አዙራችሁ ሁሉ ታዩታላችሁ። ለምን? ምክንያቱም በሰው ሀገር ሆናችሁ ፥ አንዳች የሆነ የቡድን እና የመኖር (survivial) ጥያቄያችሁን የሚመልስላችሁ ይሄ እናንተን የሚመስለው ሰው ነው። ልጆቻችሁ የነጭ ትልቅ መሆን አይደለም በአስጨናቂ እና ከባድ ወቅት የሚያጀግናቸው እና እስከመጨረሻው ለመዋጋት የሚያጠነክራቸው። ይልቁንስ ሌላ እነሱን የሚመስል ሰው ስኬታማ መሆን መቻሉን ሲመለከቱ ነው የሚበረታቱት።
የአበበ ቢቂላ የማራቶን ድል ለብዙ ኢትዮጵያኖች በር እንደከፈተ፤ እኛን የመሰሉ ሰዎች የበለጠ ሲሳካላቸው ለኛም በር የበለጠ ይከፈታል። ብዙ ስኬታማ የኢትዮጵያ ቢዝነሶች አሉ ማለት ብዙ ኢትዮጵያኖች የሥራ ዕድል ያገኛሉ ማለት ነው። ብዙ ኢትዮጵያኖች የሥራ ዕድል ሲያገኙ ሀገር ቤት ብዙ ሰው ይታገዛል ማለት ነው። እርሱ ብቻ ሳይሆን ቢዝነሶች በባህሪያቸው ሌሎች ግብአቶችን ይፈልጋሉ። ለምሳሌ የሬስቶራንት ቢዝነስ ስጋ የሚያቀብለው ይፈልጋል። የጥራጥሬ እና የስፓይስ ግብአት ይፈልጋል። የማስታወቂያ ድጋፍ ይፈልጋል። ስለዚህ ስኬታማ የኢትዮጵያ ሬስቶራንት አለ ማለት እነዚህን ግብአቶች ከሌሎች ኢትዮጵያኖች መግዛት ይችላል። ለሌሎች ብዙ ሰዎች የቢዝነስ ዕድል ፈጠረ ማለት ነው። አንድ የማውቀው ኢትዮጵያዊ የሪል ስቴት ባለሀብት አለ። ቢሞት የነጭ ሪሌተር አይቀጥርም። ሁልጊዜ ቤት ሊገዛ ሲፈልግ ብዙ በእውቀት እና በዋጋ የተሻሉ ነጭ ሪሌተሮች እያሉ እርሱ ግን ኢትዮጵያዊ ሪሌተር ነው የሚጠቀመው። ይሄ ለኢትዮጵያኖች አዝኖ ብቻ እንዳይመስላችሁ። ኢትዮጵያዊ ሀብታም በብዛት ቢኖር የመጀመሪያው ተጠቃሚ እርሱ እንደሆነ ስለገባው ነው።
ኢትዮጵያኖች ግን ገና ስትጠይቋቸው የነጭን ሰርቪስ እንደሚጠቀሙ በኩራት እና በጀግንነት ነው የሚነግሯችሁ። “እኔ ኢትዮጵያዊ አልቀጥርም ወይም እኔ ኢትዮጵያዊ ጋር አልሄድም” በማለት ልክ ጽድቅ እንደሰሩ በኩራት ነው የሚናገሩት። በእኔ የሕግ ሥራ ውስጥ ያሉ ብዙ የነጭ ጠበቆች አንዱ በጣም የሚያስገርማቸው ነገር አብዛኛው ስደተኛ ፕሬዝዳንት ትረምፕን መምረጡ ነው። ይሄን ደግሞ በኩራት ነው ብዙ ኢትዮጵያኖች ጭምር የሚያወሩት። ተመልከቱ ፖለቲካ የጥቅም መድረክ ነው። “ማነው የእኔን እና የወገኔን ጥቅም በተሻለ የሚያስጠብቅልኝ” ብለህ አስበ ነው የምትመርጠው። በምን ተዓምር ነው አንደ በነጭ የበላይነት የሚያምን ነጭ እና ኢትዮጵያዊ አንድን የፖለቲካ ተመራጭ በተመሳሳይ ሊመርጡ የሚችሉት?
ለብዙ ኢትዮጵያኖች ሌሎች ኢትዮጵያዊ ስደተኞች ባይመጡ እና ሀገሩ የነጭ ብቻ ሆኖ እነርሱ ግን በሰላም ቢኖሩ ደስ ይላቸዋል። ከዚህ በላይ primordial and lowest thinking (በጣም ዝቅተኛው የእንስሳዊ አስተሳሰብ ማሳያ) ወዴት ይገኝ ይሆን?
በርዕሴ እንደገለጽኩት አይሁዶች ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ የተማሩት አንድ እውነት መተባበር እና በሕብረት ተደጋግፎ መሥራት ብቻ በዚህ ዓለም እንደሚያስከብር ማወቃቸው ነበር። የዛሬ ሁለት ዓመት ከራሺያ የመጣ አንድ አይሁድ ቤቴ ከሚስቱ ጋር ጋብዤው ማውራት ጀመርን። ከዛ “አይሁዳች በጣም አዋቂ እና ጂኒየስ ናችሁ” አልኩት። ስቆ፦ “እንደዛ እንኳን አይመስለኝም። እኛ በሁሉም ቦታ ተበትነን ያለን እና በሄድንበት ሁሉ አናሳ የሆንን ነን። በዚህ ደግሞ ለተከታታይ ጥቃቶች ተጋልጠናል። ስለዚህ መተባበር ብቻ የመኖር ሕልውና ማስከበሪያችን መሆኑን አወቅን አለኝ። ለምሳሌ ልንገርህ። እኔ እዚህ ስመጣ የማላውቃቸው አይሁዶች እየጠሩኝ በተከታታይ ግብዣ ያደርጉልኝ ነበር። በማንኛውም ጊዜ ቢቸግርህ አለን ከጎንህ ይሉኛል። ይሄ የአይሁድ እምነት ልከተል ወይም በፖለቲካ እምነቴ የግራ ዘመም ወይም ቀኝ ዘመም ልሁን ምንም ሳይገዳቸው ነው። ይሄ በየቦታው ባህል ተደርጓል። አይሁዳዊ መሆኑ ብቻ በቂ ነው። ያን ሰው መርዳት እና መደገፍ እና ስኬታማ እንዲሆን አስፈላጊውን ዕድል መፍጠር የሁላችንም ግዴታ ነው። ስለዚህ ይሄ ስሜታዊ ትስስር ስላለ ጥቂትም ብንሆን ትብብሩ ስላለ በቀላሉ ብዙ ቁልፍ ቦታዎችን መቆጣጠር እና ስኬታማ መሆን ችለናል።” አለኝ።
ኢትዮጵያኖች ከዚህ ብዙ መማር ይኖርብናል። እውነት ነው ይሄ ካለ እውቀት እና ቆም ብሎ Reflect ካለማድረግ አይመጣም። ግን ይሄን የምታነቡ ሰዎች ቢያንስ ለመለወጥ አስቡ። ጥቂት ለውጦች እየተጠራቀሙ መጨረሻ ላይ ጠንካራ ባህል ይሆናል።