top of page
Search
Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew

እንቢ ማለትን በምግብ


በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አከራካሪ ከሆኑ ነገሮች አንዱ እና የተለያዩ ሊቃውንትም ግራ ከሚጋቡበት ነገሮች ውስጥ ንጹሁ የሆኑ እና ንጹሁ ያልሆኑ ተብለው እንስሳት ለምግበ እስራኤል መለየታቸው ነው። በተለይ በዘፍጥረት ምዕራፍ አንድ ላይ እግዚአብሔር የፈጠራቸው ፍጥረታት ሁሉ መልካም መሆናቸው በይፋ ተገልጾልን፣ ፍጥረቱን እንደሚወድ እና እንደሚመግባቸው በብዙ የመጽሐፍ ክፍል ተነግሮን ሳለ፣ እንደገና ንጹሁ የሆኑ እና ንጹሁ ያልሆኑ ተብለው መለየታቸው እስራኤሎችን ሳይቀር ግራ የሚያጋባ ነው።


ከክርስቶስ ልደት በፊት በግብጽ አሌክሳንደሪያ ብዙ ግብጾች ይኖሩ ነበር፤ በአይሁድ የአመጋገብ ምርጫ የሚደነቁ ሄለናዊያን እና ግሪኮች እነዚህን አይሁዶች ለምን ንጹሁ እና ንጹሁ ያልሆነ ምግቦች በማለት አንዳንድ እንስሳትን እንደማይበሉ ጠይቀዋቸው ነበር። ፋይሎ የሚባል ሊቅ በሰዓቱ ለዚህ ምክንያት ነው ያላቸውን ዘርዝሮ ጽፎ ነበር። የአርስጣጢለስ ደብዳቤ ለአሌክሳንደርም ይሄን ጉዳይ ያብራራል። እውነታው ግን በርግጠኝነት ማናቸውም ምክንያቱን እንደማያውቁት ነው የሚያሳየው።


ይሄ በዘሌዋውያን ምዕራፍ 11 እስራኤል እንዲበሉት ተብለው የተጠቀሱት እንስሶች አንዳንዶቹ በእንደዚህ ባህሪያት ተለይተዋል፤


፩) የተሰነጠቀ ሰኮና ያለውንና የሚያመሰኳውን እንስሳ ሁሉ ብሉ።

፪) በባሕሮችና በወንዞች ውስጥ ክንፍና ቅርፊት የሌላቸው ሁሉ በእናንተ ዘንድ የተጸየፉ ናቸው።

፫) በአራት እግሮቹ ከሚሄድ እንስሳ ሁሉ በመዳፎቹ ላይ የሚሄድ በእናንተ ዘንድ ርኩስ ነው፤

፬) በሆዱ የሚሳብ፥ በአራትም እግሮች የሚሳብ፥ ብዙ እግሮችም ያሉት፥ በምድርም ላይ የሚንቀሳቀሱ ተንቀሳቃሾች ሁሉ የተጸየፉ ናቸውና አትብሉአቸው።


ስለሚበሩ ወፎች የተነገረ መለያ ሕግ ባይኖርም፤ የማይበሉት እንደ ቁራ፣ ዳክዬ፣ ጥንብ አንሳ ተዘርዝረዋል።


በብሉይ ሕግ ስለንጽህና በምግብ ብቻ ሳይሆን በአልባሳትም ተጠቅሷል። ለምሳሌ ሁለት ዓይነት ቀለማት ያሉት ልብስ መልበስ ንጹሁ አይደለም። የሞተ እንስሳ መንካትም እንዲሁ ከንጽህና ያሶጣል። እነዚህን ነገሮች ማድረግ ኃጢአት ነው ሳይሆን፣ ወደ ተቀደሰው ቤት እና ወደ መቅደሱ ለመግባት ግን የመንጻት ሥርዓትን መፈጸም ያስፈልጋል።


አንዱ የሊቃውንት መከራከሪያ እነዚህ ንጹሁ አይደሉም የተባሉ እንስሶች በጣዖት በሚያመልኩ ሕዝቦች ዘንድ የአማልክቶቻቸው ወካይ ናቸው ተብሎ መጠቀሱ ነው ይላሉ። ለምሳሌ በዮሐንስ ራዕይ ሰይጣን በእንቁራሪት ተመስሏል፣ እንቁራሪት ደግሞ ንጹሁ አይደሉም ስለዚህ አትብሏቸው ከተባሉት ነው ወገኑ። ሌላኛው መከራከሪያ ደግሞ ንጹሁ የተባሉ እንስሳት የወገኖቻቸው ወካይ ናቸው፤ ለምሳሌ በውሃ ውስጥ የሚኖር እንስሳ ክንፍና ቅርፊት ከሌለው የአሣን መስፈረት አያሟላም ፥ ስለዚህ ያን ዘር (የአሣን) አጉዳይ ስለሆነ ንጹሁ እንዳልሆነ ይቆጠራል የሚል ነው።

በስፋት በሀገራችን ሊቃውንት ሳይቀር የምንሰማው መከራከሪያ ደግሞ ዝምድና ነው። ለምሳሌ አሳማ ሁሉን የሚበላ፣ የሚከረፋ፣ ሆዳም ስለሆነ ያንን እንደ ኃጢአተኛ እና ከክብሩ እንደተዋረደ ማንነት አድርጎ በምሳሌ በማቅረብ፤ ለመብላት ንጹሁ ያልተባለው ለዛ ነው የሚል ነው። ጥንብ አንሳም ከዚህ ምሳሌ የሚካተት ነው።


ሌሎች ደግሞ ንጹሁ የተባሉት እንስሳት ለፈጣሪ በመሥዋዕት መልክ የሚቀርቡ በመሆናቸው፤ የፈጣሪ ምግብ ናቸው፣ በዚህም ንጹሁ ተባሉ። በተቃራኒው አሳማ፣ ግመል ደግሞ ለመሥዋዕት ስለማይቀርቡ፣ የሰው ልጆችም መብላት የለባቸውም የሚል ነው።


ሌሎች ደግሞ እንደ ጠንካራ መከራከሪያ አድርገው የሚያነሱት ከጤና አንጻር ነው። እንደ እንቁራሪት፣ አሳማ ያሉ እንስሶች ከውሏቸው እና አመጋገባቸው አንጻር ለጤና አደገኛ ስለሆኑ (ሁሉን የሚያግበሰብሱ በመሆናቸው) ለዛ ነው አትብሉ የተባልነው ይላሉ።

እውነት ለመናገር ከላይ የተጠቀሱት ምሳሌዎች እምብዛም አሳማኝ አይደሉም። ለምሳሌ ቀላል የማይባሉ ንጹሁ የተባሉ እንስሶች የክፋት ምሳሌዎች፣ የባዕድ አምልኮ ምልክቶች ነበሩ። በንጽህናም ከወሰድን ፍየል እምብዛም ከአሳማ የሚለይ የአመጋገብ ሥርዓት የለውም። ዶሮም ሁሉን የሚመገብ ነው። ከጤናም አንጻር የሚነሳው ክርክር ውሃ የሚቋጥር አይደለም። አሳማ ከምግባር አንጻር በመጥፎ እና በሁሉ አግበስባሽነት ቢመሰልም፣ በምንም ክፋት የማይመሰሉ እንስሶችም ንጹሁ አይደሉም እና አትብሏቸው ተብሏል። ለምሳሌ ዳክዬ፣ ሎብሰተር፣ ፈረስ እና ሌሎችም። ስለዚህ የክፋት ምሳሌ ናቸው መባሉም አሳማኝ መከራከሪያ አይደለም። ለፈጣሪ ምግብነትም (ከመሥዋዕት አንጻር) ተብሎ የሚቀርበው ምክንያት መሻገር የማይችሏቸው ነጥቦች አሉት። ለምሳሌ ለመብላት ንጹሁ ሆነው ለእግዚአብሔር ግን በመሥዋዕትነት ማቅረብ የማይፈቀዱ እንስሶች ነበሩ። አጋዘን አንዱ ነው። ይበላል ግን አይሠዋም።


ከበሽታ እና ከንጽህና አንጻርም እስራኤሎች የተለየ ጤናማ ሕዝቦች አልነበሩም። ንጹሁ የተባሉ እንስሳትን ብቻ በመብላታቸው ያተረፉት የተለየ የጤና ጉዳይ የለም። ሌሎች በሚጠቁበት በሽታ ሁሉ ተጠቅተዋል። ረዥም ዕድሜ በመኖር በአርኬዎሎጂ ጥናት መሠረት ሩቅ ምስራቆች የተሻሉ ናቸው። እነዚህ ደግሞ በአመጋገብ ባህላቸው ከእስራኤሎች የተለዩ ነበሩ።

አንድ መገንዘብ ያለብን ነገር መጽሐፍ ቅዱስ ንጹሁ እንስሳት እና ንጹሁ ያልሆኑ ብሎ ለመብል ሲከፍላቸው ፈጽሞ ከሰውነት ጤና እና ከረዥም ዕድሜ ጋር እንዳላያያዛቸው ነው።

በዚህ ክርክር ውስጥ እግዚአብሔር ለእስራኤላውን ንጹሁ እና ንጹሁ ያልሆኑ እንስሳት፣ አዕዋፋት እና የባህር እንስሶች ብሎ ሲለይ በምን ምክንያት ነው የሚለውን ከዳሰሱ እና አሳማኝ ሆነው ያገኘውትን ነጥቦች ልዘርዝር፤


1) መገደብን፣ እንቢ ማለትን ማስተማር፤


ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፥ “ሁሉ ተፈቅዶልኛል፥ ሁሉ ግን አይጠቅምም። ሁሉ ተፈቅዶልኛል፥ በእኔ ላይ ግን አንድ ነገር እንኳ አይሠለጥንብኝም።” እግዚአብሔር ሁሉን መልካም አድርጎ ከፈጠረ በኋላ፣ በገነት ውስጥ መታዘዝን፣ የሰውን በፍጥረቱ ውስጥ ያለውን ቦታ እና ከእግዚአብሔር ጋር ያለውን ግንኙነት የምታሳይ ያለመብላት ሕግ አውጥቶ ነበር። ያ ፍሬ በገነት ውስጥ ከነበሩት ፍሬዎች የተለየ ውበት ወይም ማስቀየም እንዳለው የተነገረን ነገር የለም። ሔዋን ለመብላት ስታስብ ፍሬው ያማረ እንደሆነ ከማየቷ በቀር። ይሄ ግን ሌሎቹ የሚበሉ ፍሬዎች ከዛ ዛፍ ያነሰ ውበት ወይም አስጎምጅነት እንዳላቸው ምንም አልተገለጸም። አንድ ነገር ግን ተነግሮናል፣ ያ ዝፍ የሞት ፍሬ መሆኑ። ምክንያቱም እርሱን መብላት ያለመታዘዝ ምልክት ነው። የአመጽ ምሳሌ ነው። በተመሳሳይ ለእስራኤል ንጹሁ እንስሳት ተብለው የተዘረዘሩትን በመስመር ማስቀመጥ እና ሁሉንም በሆነ መስፈረት ማኖር አይቻልም (arbitrariness አለባቸው)። ይሄ የሚነግረን ጉዳዩ ከመብልነት እጅጉን የተሻገረ እንደሆነ ነው።


እስራኤል እንቢ ማለትን፣ ለእግዚአብሔር ሲል መተውን፣ በዚህም ራስን መግዛትን እንዲማር የወጡ ሕጎች ናቸው። የሥጋ ትልቁ ፍላጎት እና ፈተና የሆነውን መብላት በመገደብ ፥ እንቢ ማለትን እና የፍቃድ ጡንቻን ማጠንከርን ለእስራኤል አስተማረው። እስራኤል እነዚህ የኛ ምግቦች አይደሉም፣ ለኛ አይሆኑም በማለት በሕይወት ራስን መገደብን እና ኃጢአት እንኳ ባይሆን ለእኛ የተፈቀደ አይደለም በማለት እንቢ ማለትን በሕይወት እንዲማሩ የተተከለ የፍቃድ (will power) ጡንቻ ማጎልበቻ ናቸው። ለእግዚአብሔር ስንል ምክንያት እንኳ ባይኖረው እንቢ ማለትን እንዲማሩ አደረጋቸው። በዚህም በሕይወት ነገሮች ስላጓጓቸው እና ስሜታቸው ስላሻው ብቻ እንዳያደርጉ ፥ ለምኞታቸው እንቢ የማለትን ጡንቻ ገና በጊዜ እንዲያዳብሩ አደረጋቸው።


የአይሁድ ቤተሰቦች በዚህ ዘመን ሳይቀር ይሄን የምግብ ባህል በጥንቃቄ ይከተላሉ። ተመልከቱ ይሄ ራስን የመግዛት፣ በዚህም የሕይወት ስኬትን የመቆናጠጥ ማንነት ከአይሁድ ዘር በላይ በዚህ ዓለም ማን ምሳሌ ሊሆን ይችላል። የኖቤል ሽልማትን ብቻ ውሰዱ። እስከዛሬ ከ965 የኖቤል ተሸላሚዎች ውስጥ፣ 214 አይሁዶች ናቸው። በአሜሪካ ውስጥ የአይሁድ ቁጥር 2.4% ነው፤ በአሜሪካ ቢዝነስም ሆነ ፖለቲካ ግን 71% ከሚሆነው የነጩ ማህበረሰብ ምንም ያልተናነሰ ተጽዕኖ የአይሁድ ማህበረሰብ ነው ያለው። በዚህ ዓለም ላይ ከቁጥሩ አንጻር የአይሁዶችን ያህል ስኬት የተጎናጸፈ አንድ ዘር መጥራት የሚችል ይኖራል? የትኛውንም የስኬት ሜትሪክሶችን አምጡ እና የአይሁድን ማህበረሰብ አስቀምጡ፤ ይሄ ማህበረሰብ ካለው ቁጥር አንጻር እጅግ አስገራሚ ስኬት የተጎናጸፈ ሆኖ ታገኙታላችሁ።

ማንንም ጠይቁ ፥ ለጊዜያዊ ፍላጎቱ እንቢ ማለት የቻለ ሰው፣ ራሱን መቆጣጠር እና መግዛት የሚችል ሰው በምንም ዘርፍ በመጨረሻ ያሸንፋል። ይሄን ነበር በምግብ እግዚአብሔር ለእስራኤል ያስተማራቸው። በዚህ ሕግ ሕይወታቸውን ሁሉ አበራላቸው። እንቢ የማለትን ማንነት አጸናላቸው።


2) ሥርዓትን ያስተምራል ፦ መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን ላይ “ዓላማ ይዞ እንደ ተሰለፈ ሠራዊት የምታስፈራ ማን ናት?” እንዳለው ጠቢቡ፤ በሕይወት ሥርዓት ያለው ትንሽ ሠራዊት ሥርዓት የሌለውን እልፎች ይረታል። ዛሬም ስለእስራኤላውን ይሄ እውነት ነው። ጎረቤቶቻቸው በቁጥር በስንት እጥፍ እየበለጧቸው፣ ራሳቸውን የለዩ፣ በሥርዓት ማንነታቸውን ያሰለጠኑ በመሆናቸው በእልፍ የሚበልጧቸው በፊታቸው ይርዳሉ። (You develop an ordered soul that says no to certain things).


3) ማንነት ነው ፦ እነዚህን ምግብ እኛ እስራኤላውያን በመሆናችን አንበላም በማለታቸው ፥ ራሳቸውን ሁሉን ከሚበላው ዓለም ለዩ። በዚህም በቁጥር በብዙ እጥፍ ከሚበልጡአቸሁ ጎረቤቶቻቸሁ ማንነታቸውን ጠብቀው ማቆየት ቻሉ።


4) የእግዚአብሔርን ንጽሕ እና ቅድስና የሚያሳይ ነው። ለምሳሌ ሴቶች በወራዊ ልማዳቸው ወቅት ወደ ቅዱሱ ስፍራ ወንዶችም ዘራቸው የፈሰሰ እንደሆነ ወደ እግዚአብሔር መቅደስ እንዳይገቡ በብሉይ ሕግ ተደንግጎ ነበር። ሴቶች ወራዊ ልማዳቸውን ማስቀረት የሚችሉት ነገር አይደለም፤ ስለዚህም ኃጢአት አይደለም። ነገር ግን ወደ ቅድስናው ስፍራ በዚህ ወቅት መቅረብ አይችሉም፤ ለምን? ይሄ የእግዚአብሔርን ቅድስና እና ንጽህና የሚናገር ነው። “እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ነኝና፤ ሰውነታችሁን ቀድሱ፥ ቅዱሳንም ሁኑ፥ እኔ ቅዱስ ነኝና፤ በምድርም ላይ በሚሳብ ተንቀሳቃሽ ሁሉ ሰውነታችሁን አታርክሱ።” ዘሌዋውያን 11፥44። ኃጢአትን አለመስራት አንድን ሰው ቅዱስ አያደርገውም። ቅድስና የዓላማ ተግባር ነው (affirmative action)። ቅድስና መተግበርን ይሻል፣ መራቅን ብቻ አይደለም። አንድ ሰው ኃጢአት መሥራት እየቻለ፣ ስለእግዚአብሔር ብቻ ሲል ከተወ ያ ቅድስና ነው። ምክንያቱም የዓላማ ተግባር ነውና። ቤቱ ውስጥ ምግብ የሞላለት እና ምንም ያልጎደለበት ሰው ላይሰርቅ ይችላል። አለመስረቁ ቅዱስ አያደርገውም። ከመጸወተ ግን ያ ቅድስና ነው። ሰይጣን ስለኢዮብ ያለው ይሄን ነበር። “እርሱ ስለሞላለት፣ ምንም ስላልጎደለበት፣ ዙሪያውንም ከክፍ ስላጠርክለት እንጂ ምንም ጽድቅ የለውም” ነበር ያለው። ሰይጣን ሳይቀር ከኃጢአት መራቅ በራሱ የጽድቅ ምልክት እንዳልሆነ ያውቃል ማለት ነው። እነዚህ ምግቦች ለእግዚአብሔር ሲባል ብቻ መተውን፣ በዚህም መቀደስን የሚያስተምሩ ምልክቶች ናቸው።

በአዲስ ኪዳን እነዚህ ምግቦች ያላቸው ቦታ ግልጽ ነው። በቤተክርስቲያናችንም እንዴት እንደሚታዩ ብጹዑ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የቤተክርስቲያን ታሪክን በጻፉበት መጽሐፋቸው ዳሰውታል።

14 views0 comments

January 20, 2024


ዊሊያም ብሌክ እንዳለው “በሞኝነቱ የጸና ሞኝ ጠቢብ ይሆናል።” “ያለጽናት አይደለም ጥሩ አማኝ፤ ጥሩ ኢአማኒም መሆን አይቻልም” እንደሚባለው ማለት ነው። አንዴ ያየኸውን ነገር አውቃለሁ እንደማለት አላዋቂነት የለም። የኢዮብ መጽሐፍ ጥናት የገለጠለኝ ያን እውነት ነው። ሁሉን ነገር ለማወቅ ከሚጥር ይልቅ አንድን ነገር በጥልቀት ለማወቅ የሚጥር ሰው ስለሁሉም ነገር ሁሉን ነገር ለማወቅ ከሚጥሩት በላይ የተሻለ ግንዛቤ ይኖረዋል።


በተለይ ለዚህ ዘመን የማህበራዊ ሚዲያ ዜና አጋባሾች ለሆን ይሄ መርሳት የሌለብን ሐቅ ነው። እግዚአብሔርን ለማወቅ ትጥራለህ፣ እርሱን ብቻ ለማወቅ ከጣሩ ቅዱሳን አንዱን ምረጡ፤ የዛን ቅዱስ ሕይወት በጥልቀት መመርመርን የሕይወት ግባችሁ አድርጉት። በእውቀት ውቅያኖስ ላይ በሁሉም አቅጣጫ ለመሄድ የምትጥረው መርከባችሁ፣ የዛኔ ወደቧን ታገኛለች። ወደዛ ቅዘፉ። ወደ-ዛ አንድ አቅጣጫ ብቻ። በሁሉም አቅጣጭ ለመሄድ ከሚጥሩት በላይ ስለውቅያኖሱም ሆነ ስለወደቦቹ የበለጠ እውቀት ይኖራችዋል። በመንፈሳዊ ሕይወት ዕድገት ከውቅያኖሶቹ ወደቦች በአንዱ የደረሰው፣ ከዛም እግዚአብሔርን የመምሰልን ሕይወት በሚገርም ልዕልና ያቀላጠፈው የአራተኛው ክፍለዘመን የኑሲሱ ጻድቁ አባታችን ቅዱስ ጎርጎርዮስ ፤ ስለመንፈሳዊ ሕይወት ምከረን ብሎ ለጠየቀው መነኩሴው ቄዛርያስ እና ከሱ ጋር ለሚኖሩ ጽፎ የላከላቸው ስለሙሴ ሕይወት ነበር። የሙሴን ሕይወት ችክ ብሎ ያጠና ሞኝ፣ በመጨረሻ ያ ጽናት ብልህ ያደርገዋል።


በዚህ ወደ ኢዮብ መጽሐፍ እንቆቅልሾች እንሂድ። የኢዮብ መጽሐፍ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ካሉ መጽሐፎች (በተለይ ከብሉይ ኪዳን) አስጨናቂው እና ከባዱ ነው። ከባድ የሆነው ግን ቀላል ስለሆነም ነው። ማለትም ከባዱ ፈተና በጣም ቀለል ያለ መልስ ያለው ነው። በርግጥ በሕይወት በጣም ከባዱ ነገር መቅለል ነው።


የኢዮብን መጽሐፍ የሚያነብ ሁሉ፤ በተለይ ሁለት ሦስቴ ብቻ አንብቦ የተወ፤ ራሱን የኢዮብ ወዳጆች ጎራ ያገኘዋል። ብዙ ጊዜ ይሄ የሚሆነው ሳናውቀው ነው። በጣም መጥፎ ስለሆነ በዚህ ምድር ላይ የመጨረሻ ከባድ የሆነውን ቅጣት የተቀበለ ሰው ሳይሆን፤ በጣም ጥሩ ስለሆነ የመጨረሻ ክፉ ነገርን የተቀበለን ሰው ነው በኢዮብ መጽሐፍ የምንገናኘው። ያ ነው የመጀመሪያው እንቆቅልሽ። ወለፈንዲዎች ያለመጠፋፋት የተዋሃዱበት ታሪክ። ይሄን ወለፈንዲ በአግባቡ ቢረዱት ኖሮ አይሁዶች ክርስቶስን ለመቀበል ባልቸገራቸው ነበር። የኢዮብ መጽሐፍ በርግጥም ጎልጎቷ ነው። መንስኤ እና ውጤት (cause and effect) ሁልጊዜ ቢሰራ፤ ከመጽሐፍ ቅዱስ በላይ ቻርልስ ዳርዊን ልክ ነበር። ፍትሕ ቢሆን የዚህ ዓለም ብቸኛ ሕግ ከኢዮብ በላይ የኢዮብ ወዳጆች ጠቢባን ነበሩ። በርባን በነጻ በሚለቀቅበት ዓለም ላይ ነው የምንኖረው፣ ግን የወጣላቸው ክፉ ወንጀለኞችም በጎልጎቷ ተሰቅለዋል። ዓይናችንን ብናምን በመኃከል ያለው የወንጀለኞቹ አለቃ መሆን አለበት። ለቀረበው ግን፣ ወደ መስቀሉ ለተጠጋው ግን ይሄ ዓለም አንዳች እንቆቅልሽ እንደሆነ ይረዳል።

የኢዮብን መጽሐፍ የሚያነብ ደጋግሞ ራሱን ማስታወስ የሚያስፈልገው፤ ኢዮብ ጻድቅ፣ እግዚአብሔርን የሚፈራ እና ክፋትን ሁሉ ያስወገደ መሆኑን ነው። ይሄን መሰረት የለቀቀ ሰው፤ ያን መጽሐፍ በማንበቡ ምንም የሚጨምረው ነገር የለም። የውሸት የአዋቂነት ስሜትን ካልሆነ በቀር። መጽሐፉ መግቢያውን ያደረገው በዚህ ነው፣ ድምዳሜውም የኢዮብ ቅንነት ነው። ካለዛ በሕይወት ላስጨነቃችሁም ሆነ ለሚያስጨንቃችሁ ጥያቄ ከዚህ መጽሐፍ የተለየ መገለጥን አታገኙም።

የማንኛውም ትንታኔ ዋነኛው አንጓ የትንታኔው መሠረት (premises) ነው። የትንታኔው መሠረት (premises) ውሸት ከሆነ፤ ትንታኔው ሦስት ገጽም ይፍጅ ሦስት መቶ ገጽ ሁሉም ነገር ውሸት ነው። ለዚህ ነው የኢዮብ መጽሐፍን የሚያነብ ሁሉ የዚህ መጽሐፍ መሠረት የሆነውን ፈጽሞ መልቀቅ የሌለበት። ያም ኢዮብ በእግዚአብሔር የተመሰከረለት ጻድቅ እና ክፋትን ሁሉ ያስወገደ መሆኑን ነው።

ለዛሬ ሰይጣን ስለኢዮብ የተናገረውን ልለፈው፤ በሌላ ጊዜ እመለስበታለሁ። ኢዮብ በመጨረሻ በደረሰበት ነገር የተጋፈጠው ከሕይወት ትርጉም ጋር ነበር። ሰባት ቀን ሙሉ በዝምታ ከአሁን አሁን ንስሐ ይገባል፣ ከአሁን አሁን ኃጢአቱን ተናዞ ፈውስ ይለምናል ብለው ለሚጠብቁት ወዳጆቹ፤ ኢዮብ መናገር ሲጀምር እምነታቸውን ነቀነቀባቸው፤ ቲዎሎጂያቸውን ደመሰሰው፣ ስለእግዚአብሔር ያላቸውን ዕይታ አፈረሰባቸው። ከዛ በኋላ ወዳጆቹ ታስሮ እንደተፈታ በሬ የኢዮብን ቃል ሁሉ በእውር ድንብር መተሩ፣ ለማጽናናት የሄዱት ወዳጆቹ ስለሃይማኖታቸው ክርክር ገጠሙ። የሚያምኑት ከሚፈርስባቸው፣ ኢዮብን አሳልፈው መስጠት መረጡ።


“መቃብርን ባገኙ ጊዜ በእልልታ ደስ ለሚላቸው፥ ሐሤትንም ለሚያደርጉ ሕይወት ስለ ምን ተሰጠ?

፤ መንገዱ ለተሰወረበት ሰው፥ እግዚአብሔርም በአጥር ላጠረው ብርሃን ስለ ምን ተሰጠ?” ምዕ 3፥22

ይሄ አይደል የብዙ ሰው ጥያቄ?! መደስት ካልቻልን “ለምን ሕይወት?” አይደለም የምንነው! በውሃ መርካት ካልቻልን ለምን ውሃ? ብርሃን ጨለማን ገፎ ከጥሻ ውስጥ እንድንወጣ ካልሆነ ፥ ምንድነው ጥቅሙ? ልጅ ልጅ ካልሆነ ለምን ሕይወትን ሰጠኸን? ሀብት ካልሰጠኸን ለሀብት የመጎምዠትን ፍላጎት ለምን አሳደርክብን? የምንወደውን ሰው አግኝተን በዛ መርካት ካልቻልን ለምን ይሄን ስሜት በኛ ውስጥ አኖርክ? ይሄ ነው ሌላው የኢዮብ መጽሐፍ እንቆቅልሽ። መከራ እና ስቃይ ነው ከዚህ የሕይወት ትርጉም ጋር እንድንጋፈጥ የሚያደርገን።


ዮሐንስ በወንጌሉ ብርሃን ያለው ክርስቶስን ነው፤ ኢዮብም የሚጠይቀው ምንድነው ፈጣሪን ማምለክ ከመከራ የማያወጣ ከሆነ (ብርሃን በአጥር ለታጠረው ስለምን ተሰጠ፤ አንተን ማወቅ ከዚህ ዓይነት ስቃይ የማያላቅቅ ከሆነ ምንድነው ፋይዳው?) ነበር ያለው።

ይሄ በአንድ ቅዱስ የቀረበ ታላቅ ጥያቄ ነው። የብዙ ሰው ጥያቄ። በተለይ ኢዮብ በምዕራፍ 21 ላይ በጣም ግልጽ በመሆን የምናየውን እውነት ይጋፈጣል፤ ይሄን የየዕለት እውነት መጋፈጥ ፈርተው ኢዮብ ላይ “ጽድቅ በረከት እንዲሁም ኃጢአት መርገምን ሁልጊዜ ይወልዳል” ለሚሉ ወዳጆቹ ይሄ ውስልትና ነው ይላቸዋል። “አታዩም እንዴ ኃጢአተኞች ሆነው እስከ እርጅና ድረስ በደስታ፣ በብልጽግና፣ በልጆች በረከት የሚደሰቱትን፤ ልጆቻቸው ላይ ግፍ ይደርሳል ትሉኛላችሁ፤ ‘የክፋታቸውን መጠን ያውቁ ዘንድ ለምን ለራሳቸው አይከፍልም?’ ፥ ወደ እግዚአብሔር እንጸልይ ዘንድ ምን ይጠቅመናል ብለው በተድላ ዕድሜ ጠግበው ሞቱ። ኃጢአተኞች ይጠፋሉ ትላላችሁ፤ ስንቱ ኃጢአተኛ ነው የጠፋው?” እያለ ኢዮብ ባልተለመደ መልኩ ብዙ ሰው መልስ የለውም ብሎ ስለሚያስብ አይቶ እንዳላየ የሚያልፈውን፣ ለህሊና ጥያቄም የራሱን እንቶ ፈንቶ እንደሚመልሰው ሆኖ ኢዮብ አላለፈም፤ እውነትን ፊት ለፊት ተጋፈጠው እንጂ።


የአክስቴ ልጅ በቅርብ አንድ መጽሐፍ አንብባ እንደሁልጊዜው የመጽሐፍ ግምገማዋን ላከችልኝ። በዚህ ውስጥ ቀልቤን የሳበው እንዲህ የሚለው አገላለጿ ነበር “በዚህ ዓለም እውነትን በፍጥነት ከተጋፈጥካት ፥ የደረሰብኅን ነገር በፍጥነት ማከም ትችላለ፤ ያን በፍጥነት ካደረክ ደግሞ ጉዳቱን መቀነስ ትችላለ።” ኢዮብ ያደረገው ያን ነበር፤ መራራውን እውነት በሰው ቲዎሎጂ እና ፍልስፍና ሳያለባብሰው ፊት ለፊት ተጋፈጠው፣ የወዳጆቹን ኑፋቄ እና የፍልስፍና መጋረጃ ቀደደው። መራራውን እውነት ተጋፈጠው። ያም ፍትሕ ማለት በጎ ለሠራ በዚህ ምድር ሁልጊዜ በጎ ክፋያ እንዳልሆነ፣ ክፉንም ላደረገ መከራ ሁልጊዜ እንደማይዘንብለት ነበር።

የኢዮብ ወዳጆች ይሄን ነው መታገስ ያቃተቸው። ልክ እንደ ኢዮብ ወዳጆች በዚህ መሠረታዊ የሕይወት ትርጉም ጥያቄ ፊት ብዙ ሰዎች ሲበረግጉ፣ በዚህ ጥያቄ ፊት የጥቅስ መዓት ሲያዥጎደጉዱ አይቻለሁ።


“ጽድቅ ትሰራለህ ከዛ እግዚአብሔር ለጽድቅህ በረከት ይሰጠኸል የሚለው ትምህርት ነው” ስንቱን ከእውነተኛው ሃይማኖት ነቅሎ የወሰደው። ሌላም ትምህርት አለ። በንጽሐ ባህሪው በእግዚአብሔር ፊት “የአንተ መልካም ሥራ ምንም ነው፣ በመልካም ሥራ ለእርሱ ምን ትጨምርለታለህ?” የሚል፤ እግዚአብሔር ኃያል ስለሆነ ብቻ ተገዛለት ብሎ የሚያስተምር፤ ሰውን በእርሱ ፊት ትርጉም አልባ የሚያደርግ አፍራሽ አመለካከት። ኢዮብ መልስ የጠየቀው ለዚህ ነው። የዚህን እንቆቅልሽ ፍቺ ነው ከወዳጆቹ ማግኘትን የወደደው።


የዚህ መጽሐፍ አስደናቂው ነገር፣ ከኢዮብ ይልቅ እግዚአብሔር ስለኢዮብ የተናገረው ልክ ነበረ። ምንም እንኳ የዘሩትን የማሳጨድ ፍትሕ (retributive justice) አተገባበሩ ግር ቢለውም፤ ከዚህ ፍትሕ የሚጋጭ እውነትን በየቀኑ ቢያስተውልም፤ በመሠረቱ ግን የኢዮብ እምነት “ሰው ሁሉ የዘራውን ያጭዳል” ከሚለው የወዳጆቹ እምነት እምብዛም አይለይም ነበር። ያልዘራው መከራ እስከሚወረው ድረስ። ለዚህ ነው “እናንተ የምታውቁትን እኔ ደግሞ አውቃለሁ፣ ከእናንተ የማንስ አይደለሁም”፤ “የምትናገሩት ነገር እኮ እኔ የምናገረው ነገር ነው፤ የምናገረውን’ማ አምኜ፤ እሱም ለሰዎች ቅን ሆንኩኝ፣ እግዚአብሔርን ፈራውኝ፣ ክፋትን አሶገድኩኝ ግን የደረሰብኝ ነገር፣ የተሰጠኝ ነገር እናንተ የምትሉት አይደለም። በበረከት ፈንታ መርገንም፣ በእረፍት ፈንታ ስቃይን፣ በደስታ ፈንታ ሐዘንን አከናነበኝ፤ ስለዚህ መልሱልኝ የዚህ ፍቺው ምንድነው?” ነበር ያላቸው።

በሚገርም ሁኔታ ግን ይሄን ጥያቄ የሚጠይቀው ኢዮብ በአምላኩ ላይ ያለው እምነት ፍንክች አላለችም ነበር። ይልቁስ “ቢገድለኝ ስንኳ እርሱን በትዕግሥት እጠባበቃለሁ፤” ይላል። (ኢዮ 13፥15)። ፍጻሜው ሞት ቢሆን እንኳ ከእግዚአብሔር ውጪ ለእርሱ የተሻለ ተስፋ እንደሌለ አመነ። የዚህ መጽሐፍ አጠቃላይ መሠረት አንድ ይሄ ነው። “እግዚአብሔርን እንዲሁ ሊወድ የማይፈቅድ እና ያልወሰነ ሰው የመከራን ባህር አይሻገርም” የሚል ነው። እንዲሁ መውደድ።


ጄ ኬ ቼስተርትሮን “ኢዮብ ቧሏን ከምትወድ ሚስት ማብራሪያ እንደምትጠይቅ ሚስት፣ ከእግዚአብሔር ማብራሪያ ጠየቀ” ይላል። ምክንያቱም ከአንደበቱ በላይ ውስጡ “እግዚአብሔር ሁልጊዜ ልክ ነው!” ብሎ አምኗልና።


የዚህ መጽሐፍ ትልቁ እንቆቅልሽ ግን የእግዚአብሔር መልስ ነው። በልጁ ድል አድራጊነት በሰው ሁሉ ፊት ቀና ብሎ በደስታ እንደሚሄድ አባት፤ በኢዮብ ጽድቅ ፍጹም የተደሰተው እግዚአብሔር “ይህ ማነው ፥ ያለ እውቀት በሚነገር ቃል ምክርን የሚያጨልም?” በማለት ተገለጠ። ለኢዮብ የሕይወት ትርጉም መልስ፣ ለስቃዩ ምክንያት (ቢያንስ እኛ በምዕራፍ አንድ እና ሁለት የምናውቀውን የሰማይ ቤት ጉባኤ) ይነግረዋል ብለን ስንጠብቅ፣ ስለፍጥረቱ ገለጸለት። ጥልቀቱ የማይመረመረውን የሰማያዊውን የፍርድ አሰራር ከመጠየቅህ በፊት፤ በተለይ ሞኝ ስለሚመስሉ ፍጥረታቱ፣ “ትልቅ ክንፍ ኖሯት መብረር ስለማትቸለዋ ሰጎን፣ ስለፍጹም ሰላማዊው ግን ማንም የቤት እንስሳ ስለማያደርገው የበርሃ አህያ፣ ጉልበቱ ኃያል ስለሆነው ግን ማንም ስለማይጠምደው ጎሽ፣ በላይ በደመናት ተቋጥሮ ስለሚፈሰው ዝናብ” ይገባሃል ፥ ትረዳዋለ ብሎ ጠየቀው?

ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለው ከሰው ጥበብ ይልቅ የእግዚአብሔር ሞኝነት ይጠበባል፣ ከሰው ጉልበት ይልቅ የእግዚአብሔር ድካም ይበረታል። ይሄ ሞኝነት ጥበብ ከሆነብን፤ ይሄ ከረቀቀብን፤ ዓለምን ከፈጠረበት ጥበብ በላይ የሚልቀው የማዳኑ ጥበብማ እንደምን ይርቀቅብን? ይሄ ሞኝነት የሆነለት ጥበቡን ካልተረዳን፣ ጥበቡ የሆነውን የሕይወት ትርጉም እንደምን ያስረዳን?

ለእኛ እንጂ ለእርሱ የፍጥረቱ በኩር የሆነው ቤሂሞስ፣ ሌቫያተን እንደማያስፈራው ነገረው። ለእኛ እንጂ ኃያልነቱ ለእርሱ በጣቶቹ የሚጫወትበት ፍጥረቱ መሆኑን አሳወቀን።

ኢዮብ ግን በመጨረሻ ተጽናና። የፈለገው እግዚአብሔርን ነበርና አገኘው። ይቀጥላል።

22 views0 comments
Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew



ጎርጎሪዮስ ዘኑሲስ ነው ይሄ ሩጫ የፍጽምና ሩጫ ነው ያለው። መጨረሻው የሌላ ነገር መጀመሪያ እንጂ በርግጥም መጨረሻ አይደለም ያለው። በዚህ ሕይወት እስካለን ድረስ እያንዳንዱ ግብ ፥ የሌላ ሕይወት መጀመሪያ ነው። እያንዳንዱ መጨረሻ ፥ የሌላ ሕይወት መነሻ ነው።

 

ቻርልስ ቢኮወስኪ “ይሄ ሕይወት፦ ያሁኑ፤ ያለፈው ሁሉ ያንተ ነው” ሲል ፥ በዚህ ሕይወት ለውድቀትህም ሆነ ለድልህ ከአንተ በላይ ተጠያቂ የለም እያለህ ነው። ያንተ እና ያንተ ብቻ ነው። ያነሰ ኃላፊነት አትውሰድ። ለዚህ ነው በዚህ ሕይወት በሌሎች ፍልስፍና፣ በሌሎች አረዳድ እና በሌሎች የመገንዘብ ችሎታ የራስን ሕይወት መምራት ሕይወትን ማባከን ነው። ሰው ምን ይለኛል ብለህ ይሄን አንድ ሕይወት፣ ይሄን ያንተ የሆነውን ስጦታ ሕይወት ለማህበረሰብ አትስጥ። “ለምን ይሉኛል” ባርነት አትንበርከክ። በዚህ ዓለም  የመኖሪያ ማብቂያ ሰዓት ላይ እንዴት ያለ ጅል እንደነበርክ የሚገባህ ፥ ስለራሱ እንጂ ስለአንተ ግድ ስለማይሰጠው ዓለም ስትጨነቅ ህልምህን አለመኖርህ ሲገለጥልህ ነው።

 

ቆም ብለህ አስብ። የትኛው ኢንዶክትርኔሽን ነው ጨፍልቆህ ያለው? ደስተኛ ያልሆነ ሕይወት እና ኑሮ ውስጥ የነከረ? ለምን? ምንአልባት ያለህበትን ሁኔታ መቀየር አትችል ይሆናል። በርግጠኝነት ግን ላለህበት ሁኔታ ባሪያ አለመሆን ትችላለህ። በሚዲያ፣ በማጉያ፣ በቲዎሎጂ፣ በፖለቲካ፣ በቡና ወሬ አንተን የስብስባቸው ቁጥር፣ የእነርሱ ህልውና ማስረጃ፣ የእንጀራቸው ማብሰያ ከሚያደርጉህ ተላቀ፤ በማፈር እና በፍርሃት የሸመቀቃትን ነፍስ ነጻ ስታወጣት ብቻ ፥ የፍልስፍናቸው ኦናነት ይገለጥልሃል። ለራስህ እውነተኛ ስትሆን ፥ ብዙዎችን ትማርካለህ። ከዘመንህም መሻገር ትችላለህ።

 

271 views0 comments

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page