top of page
Search

የጠፋነው ፥ ራምበረንት

Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew


September 2023


የሁለት ሺ ዓመት ታሪክን በሚደንቅ ውበት የሳለ፣ በታላቁ የስዕል ጠቢብ በቪንሰንት ቫን ጎ “ይሄን ስዕል መሳል የቻለ ሰው ብዙ ሞትን ራሱ የሞተ ነው” ተብሎ የተመሰከረለት ፥ በዚህ ምድር ሁሉን ነገር አግኝቶ ያጣ ፥ የ17ኛው ክፍለ ዘመን የደች የምን ጊዜም ምርጥ ሰዓሊ ራምበረንት እና የጠፋው ልጅ ታሪክ።



ራምበረንት በ17ኛው ክፍለ ዘመን የነበረ ታዋቂ ሰዓሊ ነበር። በጊዜው ሀብታም ሰው ሁሉ ለሱ ማንኛውንም ክፍያ ከፍሎ በሱ መሳልን ፥ የሱን የቡርሽ አሻራ በቤቱ ማኖር የሚፈልጉ ሁሉም ከበርቴዎች እና ባላባቶች ነበሩ። በዚህ ዝናው በሚመጣ ሀብት እና ክብር ራምበረንት የጉብዝናውን ወራት ፍጹም በተጋነነ የዝሙት እና የስካር ሕይወት ማሳለፍ ጀመረ። ደንበኞቹን መስደብ እና ማመናጨቅ፣ የጠመዳቸውን ሰዎች ከፍተኛ ገንዘብ ከፍሎ የሚያሳስር፣ የአዕምሮ ሕክምና ጣቢያ ውስጥ የሚያስጨምር ሆነ። ያን ረምበረንት ነበር ዓለም እስከመጨረሻው የሚያውቀው ፥ ለራሱ ክፋት ሁለተኛ ዕድል የሚሰጠው የሰው ልጅ ሌላ ሰው ሲሳሳት እና ሲበድል ቢያየው ግን የወደፊቱን ብቻ ሳይሆን የቀደመውንም ጽድቅ ነው የሚነሳው። ድሮም ሲያስመስል ነበር ይላል። ወደፊትም በጎ ይሰራል ብሎ አይቀበልም።



ራምበረንት ያን ፍርድ ነው ከዓለም ያገኘው። በሉቃስ ወንጌል (15፥12) የምናገኘው ታናሹ ልጅ ልክ እንደ ራምበረንት ከአባቱ ሀብት ተካፍሎ (ጸጋ ወስዶ) ወደ ሩቅ ሀገር ሄደ ይላል መጽሐፍ ቅዱስ። በዚህ የሉቃስ ወንጌል ላይ ጥናት የሰራው የሀርቫርዱ ሄነሪ ኖዌን በየትኛውም የዓለማችን ክፍል ባሉ ማህበረሰቦች ባህል አባት ሳይሞት ፥ ልጅ የአባቱን ንብረት አይጠይቅም ይላል። በሌላ አነጋገር ታናሹ ልጅ ያለው “አባቴ ሆይ አትሞትም እንዴ? የማትሞት ከሆነ ቆሜ አልጠብቅህም” ነው። ሞቱን ተመኝቶ ንብረቱን ተካፍሎት ርቆ ሄደ።



ራምበረንት ይሄን ልቅ ሕይወት ሲመራ የመጀመሪያ ወንድ ልጁን በ1635 በሞት ተነጠቀ። ከመቼውም ጊዜ በላይ ለቀሪ ልጆቹ መራራት እና ከሚስቱ ሳሲካ ጋር በሀዘኑ ምክንያት ቅርበትን ፈጠረ። ራምበረንት ግን የመጀመሪያ ሴት ልጁን በ1638 በሞት ተነጠቀ። ብዙም አልቆየም በ1640 ኮሪኒላ የተባለች ሴት ልጁ በሞት ተለየችው። በዚህ ጊዜ የራምበረንት ዝና እና ክብር ወርዶ ፥ ሕይወቱ መመሰቃቀል ጀመረ። የገንዘብ ዕዳ ውስጥ እየተነከረ መጣ። በዚህ ወቅት ነበር ሚስቱ ሳሲካ የዘጠኝ ወር ልጅ አሳቅፋው በ1642 በሞት የተለየችው። ከልጁ ሞግዚት ጋር ግንኙነት ቢመሰርትም ፥ በክስ እና በመጨረሻም እሷ በአዕምሮ ሕክምና ጣቢያ ውስጥ በሚያሳስር ፍርድ ተጠናቀቀ። ስቶፈል ከተባለች ሴት ጋር ተጋባ ፥ ሁለት ልጆች ወለደችለት። ነገር ግን አሁንም የወለደችለት ወንድ ልጁ በ1652 ሞተበት። በዚህ ወቅት ቤቱ እና ስዕሎቹ ሁሉ በሀራጅ ተሸጡበት። በዚህ ሰዓት የሳላቸው ስዕሎች በጣም ልዩ እንደሆኑ እና “ሰውን እና ተፈጥሮን በሚደንቅ መነጽር ማየት የጀመረበት፣ ከዚህ በፊት በስዕሉ የሚታዩ ውጪያዊ ጫጫታዎች የራቁት ነበሩ” ይላል ስለሱ የጻፈው ጃኮብ ሮዘንበርግ። ሁለተኛ ሚስቱ በ1663 ሞተችበት። ከዓምስት አመት ቆይታ በኋላ ራምበረንት ከመጀመሪያ ሚስቱ የወለደው ብቸኛ ወንድ ልጁ እና በጣም የሚወደው ቲተስ ሞተ። ራምበረንት በዚህ ወቅት ነበር ፥ ቡሩሹን አንስቶ ማንም ስሎት በማያውቀው ጥልቀት የጠፋውን ልጅ ታሪክ የሳለው።



የእርያዎችን አሰር መብላት ሲከለከል የአባቱ ቤት ሕይወት እንደታወሰው የጠፋው ልጅ ብቻ አይደለም ራምበረንት አሁን እግዚአብሔርን ያወቀው። ይልቁስ በጠፋው ልጅ ታሪክ የተሰወረውን የአባት ፍቅር ነበር ራምበረንት በስዕሉ አውጥቶ ያሳየው። የጠፋው ልጅ ልሂድ ሲል ፥ እንደ ወላጅ “አትሂድ አላለውም” ያ አባት። ታናሹ ልጅ ለመሄድ የሚያስፈልገውን ሁሉ ሰጠው እንጂ። ከዚህ ቤት ውጪ ደስታ እንደሌለ ቢያውቅም ፥ ደስታን ከአባቱ እቅፍ ውጪ ለፈለገች ነፍስ በዓለም የሚያስፈልጋትን ሁሉ ሰጥቶ ሸኛት። ያ ሀብት እንደሚያልቅ፣ መቁሰል እና መጎዳት እንዳለ ቢገነዘብም ፥ ያ አባት ግን አደጋን ለመጋፈጥ ለፈቀደች ነፍስ ነጻነትን ሰጣት። ራምበረንት “ታናሹ ልጅ ከአባቱ ቤት ሲሄድ ብቻ ሳይሆን ወደ አባቱ ቤት ሲመጣም አባቱን እንዳላወቀው ስለገባው” ነበር ፥ የጠፋውን ልጅ ጭንቅላት የሕጻን ልጅ ሰውነቱን የአዋቂ አድርጎ የሳለው። አባቱ ቤት ሲመለስ ንግግር እየተለማመደ፣ ምን መናገር እንዳለበት እያሰበ ነበር የመጣው። የሱ ንግግር የአባቱን ልብ የሚያራራ መስሎት። ከእግዚአብሔር ፍቅር በላይ የኛ ቃላት ፍቅር የተሸከሙ ይመስለናል። አባቱ ግን ገና ሩቅ ሳለ አዘነለት። ልጁ ንስሐውን ሳይጨርስ አባቱ ልጁን አለበሰው፣ እጁን በቀለበት እግሩን በጫማ አሳመረው።



ራምበረንት ወደ እግዚአብሔር መንግስት እንደ ልጅ ካሎናችሁ አትገቡም የሚለውንም አሳየን።የጠፋውን ልጅ ጭንቅላት ከማህፀን የወጣ ጭንቅላት አስመስሎ ስሎ። አባቱን ሁለት ዓይነት እጆች ያሉት፥ የሴት እና የወንድ አድርጎ ሳለው። እንደምንጎዳ እያወቀ ለነጻ ፍቃዳችን እሺታውን የሚሰጥ አባት (ልቤ ጨከነ እንዳለ ዳዊት)፥ ስንመለስ ደግሞ በፍቅር ሮጦ የሚቀበለን እናት ነው እግዚአብሔር። ራምበረንት ግን ታላቁንም ሳለው። በውስጥ ሳለ የጠፋውን ፥ ከጠፋው ይልቅ በውስጡ መራራነትን ያዘለውን። ከወንድሙ መዳን ይልቅ የሰባው ፍሪዳ መታረድ ያስጨነቀው ፥ መመለሱ ሳይታወቅ ታሪኩ የተጠናቀቀው ታላቁ ልጅ። ባለፈው ዓመት በሀገራችን ያየነው ይሄን የታላቁን ልጅ ማንነት ነበር።



ታላቁ ልጅ በልቡ በታናሹ ልብ ውሳኔ የሚደሰት ሰው ነበር። የሚጠብቀው አባቱ ሞቶ ታናሹን ማስቀናት፣ ከሱ የበላይ ሆኖ መኖር ነበር። ሁልጊዜ ከአባቱ ጋር መሆኑ አላስደሰተውም ፥ የሚጠባበቀው አንድ ቀን የአባቱን ሁሉን መውሰድ እንጂ። ስለዚህ ከአባቱ ምንም እንዳይጎድል በስስት ይጠብቅ ነበር። የክህነት ቀሚስ ገድቧቸው እንጂ እንደታናናሿቹ መጋደል ያማራቸው፣ ታናናሾቹ ሲታረቁ ሞተን እንገኛለን ብለው የአባታችንን ቤት ቆልፈው የሄዱ ታላላቆችንም ያየነው ባለፈው ዓመት ነበር።



ለምን እንደሆነ አላውቅም ፥ ስለራምበረንት እስከማውቅ ድረስ የጠፋው ልጅ ያባከነው ‘ገንዘብ እና ጸጋ’ ብቻ ነበር የሚመስለኝ። ለካ ሁሉም ነገር ስጦታ ነው። ማለትም ራምበረንት ልጆቹን እና ሚስቱን አጣ ፥ እነዚህ ሁሉ የእግዚአብሔር ስጦታ ነበሩ። ኢዮብ ልጆቹን እንዳጣ፣ ኑኃሚን ከባሏ እና ከሁለት ልጆቿ ጋር ከእስራኤል ወጥታ ፥ ባሏን እና ሁለት ልጇቿን አጥታ ባዶ እጇን እንደተመለሰች ፥ የሚወሰደብን ነገር ምን እንደሆነ አናውቀውም። ሁሉም ግን የሱ ስጦታ ነው። ከሱ በተለየን መጠን የሚጠፉ ፥ የሚባክኑ፣ የሚያልቁ ናቸው።



ራምበረንት የመጨረሻ ልጁን ባጣ በሁለት ዓመት ውስጥ እሱም ሞተ። በሉቃስ ወንጌል 2፥28 እንደምናገኘው ስምዖን “እርሱ ደግሞ ተቀብሎ አቀፈው እግዚአብሔርንም እየባረከ እንዲህ አለ። ጌታ ሆይ፥ አሁን እንደ ቃልህ ባሪያህን በሰላም ታሰናብተዋለህ”፤ ራምበረንት በክርስቶስ እቅፍ ውስጥ በመጨረሻ አረፈ። ከሩቅ ያየው አምላኩ ከሱ ብዙ አልጠበቀምና ወደራሱ ሰበሰበው። የራምበረንት የመጨረሻ ስዕልም የነበረው ይሄ የአዛውንቱ ስምዖን ነበር። "አሰናብተኝ ፥ ነፍሴ የተጠማችሁን በመጨረሻ አየውት" የሚለው የአዛውንቱ የስምዖን ስዕል ነበር የራምበረት ፍጻሜ።



አዲሱ ዓመት ወደ ልቦናችን የምንመጣበት ዓመት ይሁነን። የእግዚአብሔር ፍቅር ይግባን። እሱም ወንድምን ከፍሪዳዎች በላይ መውደድ እና አባታችን እኛን በፍጹም ፍቅሩ እንደሚወደን ማወቅ ነው። “ይሄ የምወደው ልጄ ነው” የሚለው ድምጽ ከእርሱ ጋር ሕብረት ቢኖረን ለኛም ነው። የፈረድንባቸው እና ከመጠን በላይ የምንጠላቸው ሰዎች ሁሉ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸው። የሰባውን ፍሪዳ የሚያርድላቸው፣ አንባር የሚያጠልቅላቸው ፥ ጫማ የሚያደርግላቸው አንገታቸውን አቅፎ የሚስማቸው ናቸው። ይሄን ስናውቅ በወንድሞቻችን ላይ ጥላቻ ሊኖረን እንደምን ይችላል? ይሄ ፍቅር ካለበትስ ቤት ወዴት እንሄዳለን?

89 views0 comments

Recent Posts

See All

የሰንበት ዕይታ - 16

እንቢ ማለትን በምግብ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አከራካሪ ከሆኑ ነገሮች አንዱ እና የተለያዩ ሊቃውንትም ግራ ከሚጋቡበት ነገሮች ውስጥ ንጹሁ የሆኑ እና ንጹሁ ያልሆኑ ተብለው እንስሳት ለምግበ እስራኤል መለየታቸው ነው።...

የሰንበት ዕይታ - 14. የኢዮብ መጽሐፍ እንቆቅልሾች

January 20, 2024 ዊሊያም ብሌክ እንዳለው “በሞኝነቱ የጸና ሞኝ ጠቢብ ይሆናል።” “ያለጽናት አይደለም ጥሩ አማኝ፤ ጥሩ ኢአማኒም መሆን አይቻልም” እንደሚባለው ማለት ነው። አንዴ ያየኸውን ነገር አውቃለሁ...

Commentaires


  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page