top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 4 min read
ree

የሰንበት ዕይታ - 17


የዛሬው ጹሁፍ በውሳኔ አሰጣጥ ጉዳይ እና በሕይወት ወሳኝ የሆኑ ውሳኔዎችን ስንወስን የሚገጥሙን የስነልቦና ዝንፈቶችን (cognitive dissonance) ይዳስሳል።


ስለውሳኔ ስናስብ ስለራሳችን ማሰብ ግድ ይለናል። ምክንያቱም ለራሳችን ያለን ግምት ነው በውሳኔ አሰጣጥ ሂደታችን ላይ ከፍተኛ ጫና የሚያሳድረው። ስለራሳችን ያለን በጎ አመለካከት ለአዕምሮም ሆነ አካላዊ ጤናችን እና በሕይወት ላለን ደስታ ከፍተኛ ሚና ይጫወታል።

ለዚህም ነው ስለራሳችን በጎ እና የማይለዋወጥ ምስል (consistent self-image) እንዲኖረን ብዙ ነገሮችን ስንሰራ የምንታየው።


ይሄን የማንነት ምስል ለመጠበቅ ስኬትን ለራሳችን የመውሰድ ጠንካራ ዝንባሌ ሲኖረን ውድቀትን ደግሞ ለሌሎች እንሰጣለን። ገና ልጅ እያለን በቋንቋችን ሳይቀር የሚዋሃደን ይሄ አስተሳሰብ ነው። ጥሩ ውጤት በትምህርት ስናገኝ “አገኘው!” እንላለን። መጥፎ ውጤት “ሲ” ወይም “ዲ” ስናገኝ “አስተማሪው ሰጠኝ” ነው የምንለው። ይሄ ውድቀትን ለራስ ባለመስጠት ስነልቦናዊ ማንነታችንን እየጠብቅን ነው። በዚህም ራሳችንን ከተራ ሰዎች የተሻልን እንደሆን እናምናለን፣ በእውቀት፣ በውበት፣ በባህሪ፣ በጥረት እና በችሎታ ከብዙ ሰዎች እኛ የተሻልን እንደሆን እናምናለን ወይም ማመን እንፈልጋለን።



ይሄ ስለራስ ያለ የተጋነነ በጎ አመለካከት በጥቂት ሰዎች ላይ የሚስተዋል ሳይሆን ብዙ ሰዎች ያላቸው ማንነት ነው። አንዳንዴ ግን ሕይወት ይሄን ስለራስ ያለንን ግምት ይቀደዋል (smash it)። ከሥራ እንባረራለን፣ ሰዎች ይተውናል፣ ማግኘት ተስፋ ያደረግነውን ነገር እናጣለን ወይም በሰዎች ፊት ከፍተኛ ነቀፋ ይደርስብናል ፥ እነዚህ ነገሮች ሲከሰቱ ደግሞ ለራሳችን ከሰጠነው ግምት ተቃራኒ የሆኑ ውሳኔዎችን እንወስናለን።


ይሄ ስለራስ ባለ ልዩ እና ከእውነታው የተለየ ምስል ምክንያት ፊት ለፊት ያለን ሀቅ ለመቀበል እንቸገራለን። በዚህም ቀላል እና ጊዜያዊ የነበሩ ችግሮቻችን ሥር ይሰዳሉ። ይሄን ስሱ (fragile) የሆነ ስለራስ ያለን ግምት ለመጠበቅ ጊዜያችንን ባልሆኑ ነገሮች እናባክናለን፣ አላስፈላጊ እና ጊዜ አባካኝ ክርክሮች ውስጥ እንጠመዳለን፣ አንዳንድ ሰዎች ወደ ሱስ ወይም ለእነሱ የማይመጥን ግንኙነቶች ውስጥ ይነከራሉ።


ከዚህ ጋር በተያያዘ የቶልስቶይ ወንጀለኞች ለዚህ አመለካከት ገላጭ ምሳሌዎች ናቸው። ቶልስቶይ በልቦለዶቹ ወንጀለኞቹ ሁለት ዓይነት ስነልቦና እንዳላቸው ያሳየናል።

የመጀመሪያው እውነትን ይሸሹታል ፥ በመካድ፤ መካድ የሚከሰተው ስለሕይወት ኃያል እውነት ፊትለፊት ሲገጥመን እና ያን ከመቀበል ይልቅ መካድን ስንመርጥ ነው። ለምሳሌ ልጆቿቸው ከመስመር እየወጡ እና ያልሆነ ሕይወት ውስጥ እየገቡ የሚመለከቱ ወላጆች ይሄን ወዳጆቻቸው ሲነግሯቸው የመጀመሪያው ግብረ መልሳቸው መካድ ነው። እነዛ ያሳደጓቸው ልጆች፣ ከምንም ነገር በላይ የሚወዷቸው ልጆቻቸው በመጥፎ ሕይወት ውስጥ ተገኝተዋለ ብለው ማሰብ አይፈልጉም። ስለዚህ ወሬውን ያመጡላቸውን ሰዎች መንቀፍ ወይም መቀየም ይቀላቸዋል እውነታን ከመጋፈጥ ይልቅ።



በተመሳሳይ ቆዳችን ላይ የሆነ ጥቁር ነጥብ ቢወጣ፣ መጀመሪያ ሊያስደነግጠን ይችላል። ከዛ ግን እንረሳዋለን። ከሳምንታት በኋላ ስናየው የበለጠ ጠቆረ እንጂ የተለወጠ ነገር የለም። ምንአልባት ከዚህ ከሳምንታት መካድ በኋላ የበለጠ መጥቆሩ ከመካድ ሊያወጣን ይችላል። የመጀመሪያው ግብረ መልሳችን ግን መካድ ነው። እንዲሁ እንደወጣ እንዲሁ እንዲጠፋ መመኘት ነው።

ልጃቸው ወደጦርነት የሄደ እና ከዛ ያልተመለሰ ቤተሰብ አውቃለሁ። ጦርነቱ ካለቀ ረጅም ጊዜ ቢሆንም የልጃቸው አለመመለስን ሞቶ ነው ብሎ መቀበል አይፈልጉም፤ ሰው ሁሉ ያን ቢያምንም። ይሄ እውነታ የሚነግረኝ በጣም የምንወደው ነገር ሲሆን በዛ ነገር ላይ የደረሰ ክፍ ነገርን መቀበል ይከብደናል። በጣም የምንጠላው ነገርም ሲሆን ያ ነገር በጎ ነገር እንዳለው መቀበል እንቸገራለን። ስለዚህ ጠንካራ ስሜቶች ሁልጊዜ መካድ ይከተላቸዋል። ለምሳሌ ሂትለር ሕጻናትን የሚወድ እና ለሕጻናት ስሱ ልብ እንዳለው መቀበለ ይከብደናል። ምክንያቱም ሂትለር በብዙ ነገር ክፉ እና አረመኔ ስለሆነ። አንድ የሚሊተሪ ስትራቴጂስት “ጠላቴን አልጠላውም፣ ምክንያቱም ጥላቻ ጠላቴን እንዳላይ ይከልለኛል” ይላል። ጥላቻ የወረረው አዕምሮ ፈጽሞ ስትራቴጂክ ውሳኔዎችን መወሰን አይችልም። ፍቅርም የወረሰው አዕምሮ እውነታን የመጋፈጥ አቅም የለውም።



ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ሱስ (addiction) ነው። የሰው ልዩ ባህሪው ራሱን ፍጹም መውደዱ ነው። በዚህም ማናችንም ደደብ እንደሆንን እና የሆኑ ነገሮችን ማድረግ እንደማንችል መቀበል ይቸግረናል። ለዚህ ነው በሌሎች ላይ ውበት ስናይ የሚቀናን መተቸት ወይም የሚነቀፍ ነገር መፈለግ የሚሆነው። ምክንያቱም ያ ሰው ከኛ የሚያንስበትን ነገር ነው የምንፈልገው። ሱስ ከዚህ የሚመነጭ ነው። ሱሰኛ ሰዎችን ተመልከቱ። (በርግጥ በዚህ የማህበራዊ ሚዲያ ዘመን ማን ሱሰኛ ያልሆነ አለ?) ሁሉም በማንኛውም ሰዓት ያን ሱስ ማቆም እንደሚችሉ ነው የሚያምኑት። ምክንያቱም አልችልም የሚለው ስሜት በከፍተኛ ደረጃ ለራሳቸው የሰጡትን በጎ ስሜት (self-iamge) ይጎዳዋል። ስለዚህ ሰው ሁሉ የሚያውቀውን እውነት ይክዱታል። ከሱ መውጣት እንደከበዳቸው።



ሾፐናወር ለሰው ልጅ መቀበል ከሚከብደው አሉታዊ ስሜት ከሆኑት ትልቁ “ደደብ ነኝ የሚለው ስሜት ነው” ይላል። ይሄ ያለመቻል ስሜት ለራሳችን የሰጠነውን የተጋነነ ስሜት፣ ራስን ከመውደድ እና ስሱ (frgile) የሆነውን ማንነታችን እንዳይጎዳ ከመጠበቅ የመጣ ፍላጎት ስለሆነ ፊት ለፊት ያለውን ሀቅ እንሸሻለን፣ እንክደዋለን። ይሄ የጥሩ ውሳኔዎች ሁሉ የመጀመሪያው እንቅፋት ነው።

ሁለተኛው የቶልስቶይ ወንጀለኞች ባህሪ ምክንያት መስጠት (self-justification) ነው፤

የቶልስቶይ ወንጀለኞች ወንጀል ከፈጸሙ በኋላ ያን ወንጀል በዛ ሁኔታ (context) ውስጥ ወይም በእነርሱ ላይ ከደረሰባቸው አንጻር ተገቢ እንደሆነ ምክንያት ይሰጣሉ። ጉቦ የሚሰጥ ሰው ለዚህ የሚሰጠው ምክንያት ጉቦ ከሚቀበለው ልዩነት የለውም። ሁለቱም ካለጉቦ ምንም ነገር ማድረግ እንደማይቻል ነው የሚናገሩት። ጉቦ ተቀባዩ ያለጉቦ የኑሮ ውጣ ውረድን ማሸነፍ እንደማይችል ሲናገር ፥ ጉቦ ሰጪውም የቢሮክራሲውን ውጣ ውረድ ያለጉቦ ማለፍ እንደማይችል ነው የሚገልጸው።



ሁለቱም ወንጀል እየሰሩ እና በምድርም በሰማይም የሚያስጠይቃቸውን አስነዋሪ ተግባር እየሰሩ መሆናቸውን ማመን አይፈልጉም። ይልቁስ ከመሠረታዊ እምነታቸው ጋር እንዳይጋጭ ለዛ ምክንያት ይሰጣሉ።



ምክንያት የመስጠት (justification) ትልቁ መገለጫ ማቆም ነው። ለምሳሌ ሲጋራ ለማቆም ጥሮ ያልቻለ ግለሰብ የሚያደርገው ሲጋራ መጥፎ ነው ብሎ ማመን ያቆማል። ይልቁስ ሲጋራ እያጨሱ እስከ 90 እና 80 ዓመት የኖሩ ጥቂት ሰዎችን መጥቀስ ይጀምራል ወይም “ሕይወት ማለት ካላጨስክ እና ካልጠጣክ ምኑን ሕይወት ሆነ?” ማለት ይጀምራል። ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም በአገቱኒ መጽሐፉ የነገረን የዚህ ባህሪ ተጠቂ መሆኑን ነበር። አቆመ። ቤተክርስቲያን መሄድ እና ማስቀደስ አቆመ። ንጉሱ “ለምን አቆምክ?” ብለው ሲጠይቁት የመለሰው “መጽሐፍ ቅዱስ አንዱ ጉንጭህን ለሚመታህ ሌላኛውን አዙርለት ይላል፤ እኔ ግን መልሼ ነው የምመታው። ለነገ አትጨነቁ ይላል፣ እኔ ደግሞ ልጆች አሉኝ አለመጨነቅ አልችልም። ስለዚህ አቆምኩኝ” አለ። አለመጨነቅ ጥሩ መሆኑን ሳይሆን ፥ ለመጨነቁ ምክንያት መስጠት ተያያዘ። መታገሰን ገንዘብ ከማድረግ ይልቅ ፥ ታገሱ የሚለውን ስብከት መስማት ማቆም የቶልስቶይ ወንጀለኞች ባህሪ ነው።



በሕይወታችሁ ጥሩ ውሳኔ ለመወሰን ትፈልጋላችሁ? በተቻለ መጠን እውነታን ተጋፈጡ። ሲ ኤስ ሉዊስ ለኦክስፎርድ ተማሪዎቹ የሚላቸው ይሄን ነበር “እውነታን በጥቂቱ ካሳየናችሁ ፥ እውነትን የማየት ድፍረት በጥቂት ከሰጠናችሁ፤ ያን ጊዜ ስኬታማ ፕሮፌሰሮች እንባላለን። የኛ ዓላማ እውነትን የሚያዩ እና ያዩትን እውነት የመናገር ብቃት ያላቸውን ተማሪዎች ማፍራት ነው።”

እውነታው ከምናስበው በላይ ደደቦች ነን። እውነታው ብዙ ነገሮችን ማቆም አንችልም። እውነታው ስሜታዊ ነን። እውነታው ፈሪዎች ነን። እውነታው ከመጠን በላይ በሰዎች መወደድ እንፈልጋለን። እውነታው እንደምናስበው ጥሩዎች አይደለንም። እውነታው ሰንፎች ነን። እውነታው አድሎአዊ እና ዘረኞች ነን። ይሄን ስለራስ መቀበል ያማል፣ ግን ይሄን በጊዜ እንደመቀበል ምንም ፈጣን የመፍትሔ እና የለውጥ መንገድ የለም። አዎ ለዚህ ብዙ ምክንያቶችን መስጠት እንችላለን፤ ግን እውነታውን አይቀይሩትም።



ቻርሊ መንገር ስለወዳጁ ልጅ እና አባቱ ስላለው ነገር እዚህ ጋር ማንሳቱ በጣም ጠቃሚ ነው። ልጁ ከአባቱ የሳንቲም ማጠራቀሚያ “በኋላ እተካለሁ” እያለ ሁልጊዜ ይወስዳል። ይሄን ባህሪ ያስተዋለ አባት “ልጄ! ግድ የለህም ስትወስድ በኋላ እተከዋለሁ እያልክ ተደብቀህ ከምትወስድ ፥ በወሰድክ ቁጥር ሁሉ ራስህን ሌባ እያልክ ጥራ” አለው። ያ ልጅ ዛሬ አድጎ እና ተለውጦ የካሊፎርኒያ ቢዝነስ ስኩል ዲን ሆነ። መጥፎ ነገር ስናደርግ ራሳችንን በዛ ስም እንጥራው። አዎ፣ “ዝሙት እየሰራው ነው። እየሰርኩኝ ነው። ወንጀል እየሰራው ነው።” እንበል። በውሸት ምክንያት የተገነባን የራስ ምስል (self-iamge) ከመጠበቅ ይልቅ፤ ራሳችንን ለዛ ባህሪ ተገቢ በሆነ ስም እንጥራው። ከዛ ባህሪ ለመላቀቀ ትልቅ እርዳታ ይኖረዋል። ከአስርቱ ትዕዛዛት ሁለተኛው “የተቀረጸ ምስል ለራስህ አታኑር” የሚል ነው። ይሄ የተቀረጸ ምስል አንዱ የራስ ምስል (self-iamge) ነው። በምክንያት የምንጠብቀው፣ እውነትን በመካድ ያቆምነው፣ ይሄ ስሱ ምስል (fragile self-image)፣ የሰዎችን መጥፎ ንግግር እና ነቀፋ መቋቋም የማይችለው ፣ በተግሳጽ እና በአሉታዊ ኮሜንት የሚፈርሰው ፣ ላይክ እና አስመሳይ የማሽሞንሞን ቃሎች የሚያለመልሙት የተቀረጸው የራስ-ምስል (carved self-image) ለጥሩ የሕይወት ውሳኔ ሁለተኛው እንቅፋት ነው።


 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 3 min read
ree

የሰው ልጆች በሁሉም ወቅት የሚሰራ መመዘኛ የለንም። መመዘኛችን እና የሞራል እይታችን በደረስንበት የእይታ ጥራት እና አድማስ የሚወሰን ነው። ይሄ ማለት ዘመን እና ድንበር ተሻጋሪ የሞራል ልኬቶች (universal values) የሉንም አይደለም። ለምሳሌ ደግነትን የትኛውም ማህበረሰብ በየትኛውም ስፍራ እንደ ጥሩ እሴት ያከብረዋል። ጥያቄው በአንድ ወቅት ደግነት ተብሎ የሚወሰድ ጉዳይ በሌላ ጊዜ ክፋት ሊሆን ይችላል። ይሄ ተቀያያሪ የሆነ የይዘት ሁኔታዎች የሰው ልጅን የመመዘኛ ድክመት ነው የሚያሳየው። ይሄ ማለት ግን ጽንፎችን የሰው ልጅ አያውቃቸውም ማለት ላይሆን ይችላል። ለአንዱ ሙቀት የሆነ ለሌላው ኖርማል የዓየር ጸባይ ሊሆን ይችላል። ግን የትኛውም የሰው ልጅ ላይኖርበት የሚችል የሙቀት መጠን አለ። በሚዛን ደረጃ ጽንፎችን የማወቅ አቅም አለን ማለት ነው። ፍጹም ምቾትን እና ፍጹም የሆነ ስቃይን የማወቅ አቅምም እንደዚሁ። በፍጽምና መኃል ስላሉት ጉዳዮች ግን በትክክል የሚመዝን አዕምሮ የለንም።



ይሄን በሕመም እንየው። ከእግር በታች ሰውነታችን ሕመም ቢደርስበት፤ በዛ ቦታ ያለው የነርቭ ሥርዓታችን ለአዕምሮአችን መልዕክት ያስተላልፋል። መልዕቱን ተከትሎ አዕምሮአችን ያ ቦታ አደጋ ውስጥ እንዳለ በመግለጽ፤ እዛ ቦታ ላይ እብጭ፣ መቅላት እና ሕመም እንዲኖር ያደርጋል። አዕምሮአችን ያን የሚያስተላልፈው ያን ስፍራ ከመጠበቅ አንጻር ነው። ያ ሕመም ያለበትን አካል በመጠቀም የበለጠ እንዳንጎዳው ያሳብጠዋል ወይም ሕመም ያኖራል። የአዕምሮ ተቀዳሚ ሥራ እኛን ከአደጋ መከላከል ነው። ልክ ነኝ ወይም ልክ አይደለውም የሚለው የአዕምሮ ተቀዳሚ ተልዕኮ አይደለም። ተቀዳሚው ተልዕኮ መጠበቅ (protect) ወይም መከላከል ነው።



አንዳንድ ጊዜ ግን አዕምሮ የተሳሳተ ሲግናል ይልካል። ለምሳሌ Complex Regional Pain Syndrome (CRPS) የሚነግረን ምንም እንኳ የታመመው የሰውነት አካል ቢድንም አዕምሮ ግን እስካሁን እንዳልዳነ ሊቆጥረው ይችላል። ስለዚህ እነዛ የሕመም ምልክቶችን በመላክ እብጠት እና መቅላት፣ ሕመም እንዲቀጥል ሊያደርገው ይችላል። ይሄ መጀመሪያ ከደረሰው የሕመም ከባድነት የተነሳ፤ ሰውነታችን ቢድን እንኳ፤ አዕምሮአችን ግን ሕመሙ ላይ ቀርቷል። ከሰውነታችን ጋር አብሮ ራሱን አላሻሻለም። በዚህም የሕመም ሲግናል (ምልክት) በተከታታይ ይልካል።



ለዚህ አንዱ የሚደረገው አዕምሮ እነዛን የሕመም ሲግናሎች መላክ እንዲያቆም ማሰልጠን ነው። አዕምሮአችን በየዕለት ሕይወታችን የሚያደርገው ይሄንን ነው። እኛን የመጠበቅ ተልዕኮ ስላለው፤ ከዚህ በፊት ውሻ የነከሰው ሰው ፥ ለውሻ የሚኖረው ፍርሃት ወደር አይኖረውም። ሁሉም ሰው ውሻውን እየዳሰሰ እርሱ ግን ከዛ ውሻ ይሸሻል። አዕምሮ ይሄን ሰው በማንኛውም ሁኔታ መጠበቅ ስላለበት፤ ከዚህ በፊት በውሻ የደረሰበትን እንዳይረሳ በማድረግ ይጠብቀዋል። ምንአልባት ሰውዬው ለራሱ ማጽናኛ ቃሎችን ሁሉ ሊጠቀም ይችላል። “ውሻ አይወደኝም ወይም የውሻ መወደድ የለኝም” እና የመሳሰሉት እምነቶችን።



ይሄ ግን በግለሰብ ደረጃ ብቻ እንዳይመስላችሁ። በማህበረሰብ ደረጃም በወል አዕምሮ ውስጥም ተመሳሳይ እሳቤዎች አሉ። በፖሊሲም ሊሆን ይችላል። ለምሳሌ ከዚህ በፊት ይገዛ የነበረን ብሔር ሌሎች የማህበረሰብ አካላት ሊፈሩት እና “ከመጣብን የቀደመውን ይደግማል” በሚል ፍርሃት ሊያሳዱት ይችላሉ። ለምሳሌ በሴፕቴምበር አስራ አንድ የደረሰው የሽብር ጥቃት እንዴት በዓለም ላይ ያሉ ሙስሊም ያልሆኑ ማህበረሰቦችን እይታ እንደቀየረ ተመልከቱ። የጥቂት ሰዎች አውሬነት የብዙ ሰዎች ተደርጎ በፖሊሲ ደረጃ ምንም በዚህ ጉዳይ ላይ የሌሉ የእምነቱ ተከታዮች ለአሰቃቂ ጥቃት ተጋልጠዋል።



አሁን በአሜሪካ ውስጥ የምናየው የኢሚግሬሽን ፖሊሲም የዚህ ስሁት ሪያክሽን ውጤት ነው። ጥቂት ከሌሎች ሀገራት የመጡ ሰዎች በፈጸሙት ወንጀሎች ብዙ መልካም ማንነት ያላቸው ሰዎች በጅምላ ይፈረድባቸዋል። ለሁሉም ጥላቻ ይኖራቸዋል። “ለምን እንደዚህ ታደርጋላችሁ?” ሲባሉ፤ አንድ ሰነድ አልባ ስደተኛ የሆነ ቦታ እና ጊዜ ያደረገውን ወንጀል እንደ ምክንያት ይጠቅሳሉ። ይሄ የሲግናል ግራ መጋባት ነው። ብዙ ጊዜ ለዚህ የሚዳረጉ ሰዎች የተጋላጭነት መጠናቸው በጣም ጠባብ የሆኑ ናቸው።



በቅርብ አንዱ ከኢትዮጵያ ስለ ካቶሊክ ቤተክርስቲያን ለክርስትና መስፋፋት እንቅፋት እንደሆነች ጻፈ። ይሄ ሰው ምን አልባት ከአዲስ አበባ የዘለለ የሕይወት ተጋላጭነት የለው። ስለ ካቶሊክም የሰማው ከኢትዮጵያ ወጥተው በማያውቁ ሰዎች ከተጻፉ መጽሐፎች ይሆናል። አውሮፓ በየሀምሳ ሜትሩ ቤተክርስቲያንን የተከለች፣ በቢሊዮን የሚቆጠር አማኝ ያላት ቤተ እምነት እንደሆነች ምንም እውቀቱ የለውም።



አንድ ወዳጄ ስለነጮች ያለው አመለካከት በጣም ጠባብ ነው። የእኔ ጥያቄ የነበረው “ምን ያህል ነጭ የቅርብ ወዳጅ አሉህ? ወይም በበዓል ቀናቸው የምትሄድበት ነጮች አሉ? ወይም የሴት ጓደኛ ከነጮች ይዘህ ታውቃለህ? የሚል ነበር። መልሱም የሉኝም። አላውቅም ነበር።



ለComplex Regional Pain Syndrome (CRPS) የሚመከረው ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? የተጎዳውን የሰውነት ክፍል ለተለያዩ ቴምፕሬቸሮች፣ ንክኪ እና እንቅስቃሴ ማጋለጥ ነው። በዚህም አዕምሮ ቀስ እያለ ያ ቦታ መዳኑን ይማራል። ስለዚህ ቀስ እያለ የስህተት የሕመም ሲግናሎችን መላክ ያቆማል ማለት ነው።



ትግሬን ወይም አማራን ወይም ኦሮሞን የሚጠላ ሰው የምመክረው፣ ወጥቶ ከእነዚህ ብሔሮች ብዙ ወዳጆች እንዲያፈራ ነው። ቀስ እያለ ያለው አስተሳሰብ ፍጹም ከእውነት የተቃረነ እንደሆነ ይማራል። ለምሳሌ በወንድ የተደፈረች ሴት ሁሉም ወንዶች መጥፎ እንደሆኑ ልታስብ ትችላለች። ከዚህ ስሁት አስተሳሰብ ብቸኛ የሚያወጣት ራሷን ለሌሎች ወንዶች ስታጋልጥ ነው። ፍርሃትህን በመጋፈጥ ብቻ ነው የምታሸንፈው። ይሄም የአዕምሮ ካርታን (GPS/Map) ማደስ ይባላል። አዕምሮአችን የሆነ ቦታ ለመድረስ የሚያውቀው GPS (Map) አለው። ያ GPS (map) አሁን ላይ አይሰራም። ዓለም ተቀያይሯል። ቁስሎች ድነዋል። ግን አዕምሮአችን ያው የጥንቱ GPS (map) ላይ ነው። ያንን እንዲቀይር ማድረግ የሚቻለው ቦታዎቹ ላይ በመሄድ (exposing the brain) የተለወጠውን ነገር በግድ በማሳየት ነው። አለበለዚያ ግን ከእውነት የራቁ እና ለሕይወት እንቅፋት የሆኑ ውሳኔዎችን እየወሰንን እንቀጥላለን።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 3
  • 3 min read
ree

የስነልቦና ሐኪሞች እንዲህ ይላሉ “ለማዳን በጣም ከባዱ በሽተኛ ራሱን ለማዳን የሚጥርን የማዳን ጥረቱን ማስቆም ነው።” ያሉን አስገራሚ ባህሪዎች ራሳችንን ለማከም የወሰድናቸው መድኋኒቶች እንደሆኑ ቢነገረን ምን የምንል ይመስላችኋል?



ማርክ ትዌን ስለዚህ ሲናገር በድመት ነው። ብረትምጣድ ላይ ለመቀመጥ የምትፈራ ድመት ካያችሁ፤ ከዚህ በፊት የጋለ ብረትምጣድ ላይ ተቀምጣለች ማለት ነው። የጋለ ብረትምጣድ ብቻ አይደለም የምታሶግደው ሁሉንም ብረትምጣዶች እንጂ። ሁለት ሦስቴ በሰዎች የተከዳ ሰው የሚክዱ ሰዎችን ብቻ አይደለም የሚያሶግደው፤ ለደስተኛ እና ጤናማ ሕይወት መሠረት የሆነውን ሰውን ማመን ሁሉ እንጂ። በየዓመቱ ከሀገር ወደ ሀገር ከቤተሰቦቹ ጋር እየተዘዋወረ ያደገ ልጅ ፥ ዘላቂ ጓደኝነትን እና ትውስታን መመስረት ይሳነዋል። ሁሉም ነገር ጊዜያዊ ነው የሚመስለው። በጣም በችግር ያደገ ሰው ፤ በጣም ገንዘብ ቢያገኝም ሁልጊዜ ወደ ዛ ችግር የሚመለስ ስለሚመስለው የድህነት ስነልቦና ላይለቀው ይችላል።



ቅናት እና ምቀኝነት እንስሳዊ ማንነታችን ለገጠመን በሽታዎች የለገሰን መድኋኒቶች ናቸው። እንስሳዊ ባህሪያችን በዙሪያችን ያለ ሰው ሲበልጠው ይደነግጣል። በዙሪያችን ያለ ሰው ከበለጠን ወይም ከኛ ትኩረትን ከተጋራ ይፈራል። ምክንያቱም በእንስሳት ዓለም መበለጥ ዋጋ ያስከፍላል። የበለጠን ሰው የኛ የሆነውን ሁሉ ሊወስድ እና ሊያጠፋን ይችላል። ውስጣቸው ነጭ ወረቀት ነው የምንላቸው ሕጻናት በቅናት ይጠቃሉ። የሦስት ዓመት ልጅ አዲስ በተወለደው ሕጻን ልትቀና ትችላለች። አዲሱ ሕጻን የወላጆቹን ትኩረት መሳቡ እንድትጠላው ያደርጋታል። ምክንያቱም ወላጆቿን እንደቀማት አድርጋ ነው የምትቆጥረው። ከወላጆቿ ይልቅ ምንም ራሷን መከላከያ የሌላት ልጅ ይሄን እንደ ትልቅ አደጋ ነው የምትቆጥረው። ስለዚህ በአዲሱ ሕጻን ትቀናለች። ችግሩ የሕጻኗ መቅናት አይደለም፤ አድገንም ሰውነታችን ይሄን መድኋኒት ለመበለጥ እንደ መፍትሔ ሲሰጠን ተቀብለን መዋጣችን ነው። ይሄን ነው ለማዳን ትልቁ ፈተና። ራሳችንን ለማዳን የምንወስደው መድኃኒት።



በሰዎች በልጅነቱ የተጎዳ ሰው ወይም በቤቱ ውስጥ የሌሎችን ትኩረት ለማግኘት የሚቸገር ሰው፤ ሰዎችን ለማስደሰት የሚሰራ ይሆናል። ምክንያቱም በዚህ ቤት ውስጥ ሰው ሆኖ ለመቆጠር ሌሎችን ማስደሰት ነበረበት። በዚህም የራሱን ስሜት የመተው እና የማይፈልገውን ነገር እንቢ የማለት አቅም ያጣል። ብዙ ሰዎች ወደ ሱስ የሚሄዱት በሱስ ውስጥ ያሉ ሰዎች ስለተቀበሏቸው ነው። ሌላ ቦታ ፍቅርን ያጡ እና ቅቡልነት ወይም ትኩረቱን ያላገኙ ሰዎች ሱስ ያን ከሰጣቸው ስሜታቸውን ለማከም ይገቡበታል።



ወላጆቿ ቢዚ ከመሆናቸው የተነሳ ጊዜ የማይሰጧት ልጅ፤ በመጨረሻ ራሷን በምላጭ መቁረጥ የጀመረችበትን ታሪክ አንብቤያለሁ። ምክንያቱም በደማች ቁጥር እናቷ ወይም አባቷ ከሥራ ቤት ቀርተው አብረዋት ይሆኑ ነበር። ራስን የማዳን ተልዕኮ ይሄ ነው። ብዙ የሰዎች ባህሪያት ለስሜት ማከሚያነት የተለበሱ ናቸው።



ራሳቸውን በፍጹም ሥራ የሚወጥሩ ሰዎችን አውቃለሁ። እነዚህ የማሰቢያ ጊዜ ካገኙ ማስታወስ እና ማከም የሚፈሩት ሀሳብ ስለሚወጥራቸው ሊሆን ይችላል። ወይም አንዳች የሚያሳዳቸው ድብቅ በእነርሱ ዓለም ብቻ ያለ አውሬ አለ።


ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድኃን ይሄን ሽሽት “እንዳይነግርህ አንዳች እውነት!” በሚል ግጥሙ ገልጿታል፤


“ደንስ ጎበዝ፦ ደንስ ጀግና


.


.


.


ርገጥ፥ ጨፍር፥ ደንስ ጀግና!


ያን የሙዚቃህን ናዳ፥ የኮንትራባሱን መብረቅ


ልቀቀውና ይደብለቅለቅ


ምንም-ምንም እንዳታስብ፥ ሁሉሉ-ሁሉን እንድትረሳ


ደንስ! ካካታው ይነሳ


ጭንቅላትክን ግዘፍበት፥ እስኪያሰጥመው አጓራበት


ጭንቅላትክን ግዘፍበት፥ ውቀጥበት፥ ውገርበት ....


ዝግ ብሎማ ያስብ እንደሁ፥ ይነግርሃል አንዳች እውነት!”



ብዙ ሰው ለጤናማ እና በአግባቡ ለሚያስብ ሰው ግራ አጋቢ ሕይወት ውስጥ ገብቶ ታገኙታላችሁ። ማህበረሰብን ለማስደሰት ብቻ ወይም ሰው ምን ይለኛል የሚልን ለማስቀረት ብቻ ለራሱ ፍላጎት ተጻራሪ የሆነ ሕይወት ውስጥ የተዘፈቀ ይኖራል። ወይም ከሰው ጋር መቀላቀል፣ ከሌሎች ጋር አብሮ መተባበር እና የተሻለ አካባቢ መኖር ለጤናውም ሆነ ለሕይወቱ የተሻለ ሆኖ ሳለ ፥ መጋፈጥ የማይፈልጋቸው የስሜት ቁስሎች ይዘውት በብዙ ምሽግ ውስጥ ያሉ ሰዎች አሉ። በብቸኝነት ምሽግ ውስጥ፣ ወይም በአልኮል እና እፅ ሱስ ምሽግ ውስጥ፣ በሥራ ማብዛት ምሽግ ውስጥ፣ በገንዘብ ማሳደድ ምሽግ ውስጥ፣ በቅናት እና ምቀኝነት ምሽግ ውስጥ፣ በፍርሃት እና ሁሉን ላስደስት በሚል ምሽግ ውስጥ፣ ሰውን ላለማስቀየም ባለ ምሽግ ውስጥ እና ሌሎች ውስጥ ያሉ አሉ። የማርክ ትዌን ድመት እኛ ውስጥም አለች። በጭቅጭቅ ቤት ውስጥ ያደገ ሰው አውቃለሁ። መከራከር እና ኮስተር ያለ ውይይትን እና ንግግርን ሁሉ ይሸሻል። ጠንከር ብለህ ስለ እንከኑ ልትነግረው ስትል ፥ ከመጋፈጥ ይልቅ ሮጦ ይሄዳል። ምክንያቱም እንደ ድመቷ እንደዚህ ዓይነት ንግግር የሚጭርበት የልጅነቱን ያ ከባድ የአባት እና የእናት ጭቅጭቅ እና ድብድብ ነው።



እኛ ግን እንስሶች ብቻ አይደለንም። ሌላ የምክንያታዊ ክፍልም አለን። ሞኝ የምንሆነው የእንስሳነት ክፍላችንን አሳንሰን ካየን ነው። የእንስሳው ክፍላችን እንደ ዝሆን ግዙፍ ነው። የምክንያት ክፍላችን እንደ አይጥ ድንቢጥ ናት። በኋይል አይጧ ዝሆኑን አትጎትተውም። ግን በጥበብ አይጧ ዝሆኑን ወደ ምትፈልገው ቦታ መምራት ትችላለች። ይሄ በጥበብ እና በትሪክ (trick) ብቻ ነው የሚሆነው።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page