top of page
Search
Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew


ከውድ ጓደኛዬ ጋር በቅርብ በስልክ ስናወራ አንዱ ርዕሳችን ሰዎች ማጣትን እና መተውን የሚወስዱበት መንገድ ነበር። ሰው በተፈጥሮ ማጣት ከማግኘት በላይ ይሰማዋል። አስር ሺ ብር ያጣ ሰው እና 12 ሺ ብር ያገኘ ሰው የሀዘን እና የደስታ መጠናቸው በጣም የተለያየ ነው። ያጣው ሰው የሚያዝነው ካገኘው ሰው ደስታ ይልቅ በብዙ እጥፍ ነው። ለምሳሌ ጠዋት ላይ 10 ሺ ብር አግኝተን ከሰዓት 5 ሺ ብር ብናጣ ፥ እጦታችን ሁሉመናችንን ይቆጣጠረዋል። በዚህም የተነሳ ሰዎች ብዙ ጊዜ በከሰረ ነገር ላይ ተጨማሪ ጊዜያቸውን ማጥፋት ይቀላቸዋል፤ ያ ነገር ላይ ተስፋ ከመቁረጥ ይልቅ።

 

የዚህ አንዱ ማሳያ በመጥፎ ግንኙነቶች ውስጥ የምናጠፋው ጊዜ ነው። ቀላል የማይባሉ ሰዎች ብዙ ጊዜ ከጎዷቸውሰዎች ጋር ወዳጅነታቸውን ይቀጥላሉ። እየጠቀማቸው ካለ ወዳጅነት ይልቅ፣ የተጣመመን ለማቅናት የሚወስዱት ጊዜ ይበልጣል። ስኬት ማለት ግን የሚሰራን ነገር በብዛት ማድረግ ፥ የማይሰራን ነገር በቶሎ መተው ነው። ለዚህ ደግሞ መጨከን ያስፈልጋል። ግራ የሚያጋቡንን ሰዎች፣ ፍላጎታቸውን በግልጽ ማኖር የከበዳቸውን እና ለወዳጅነታችን ያላቸው አክብሮት እምብዛም የሆኑ ግለሰቦችን መቁረጥ ፥ ስሜታችንን ከመጥቀሙ ባሻግር ለጥሩ ግንኙነቶች የበለጠ ጊዜ እና ዕድል እንድንሰጥ ያደርገናል። ይሄን ማድረግ ግን ቀላል አይደለም። ምክንያቱም ተፈጥሮአችን ማጣትን ከማግኘት በላይ ይፈራል። ስለዚህ ከተፈጥሮ ተቃራኒ መቆምን ይጠይቃል።

 

በኢኮኖሚክስ opportunity cost የሚባል ጽንሰ ሀሳብ አለ። ይሄ ማለት እያንዳንዱ ድርጊታችን እና ምርጫችን opportunity cost አለው። ከመጥፎ ወይም አሉታዊ ወዳጅነት ጋር የማሳለፍ opportunity cost ከጥሩ ወዳጅነት ጋር የማሳለፍ ነው። ከዛ ሰው ጋር የምናሳልፈው ሰዓት opportunity costቱ ጥሩ መጽሐፍ የማንበብ፣ ስሜታችንን የሚጠግኑ ነገሮችን የመስራት ሊሆን ይችላል። ግን ይሄን በማግኘት አናስበውም። በማክበር፣ በፍቅር፣ በታማኝነት እና በመልካም ቃላት ከጎናችን ሊሆኑ የማይችሉ ሰዎችን መተው (መቁረጥ) አለመቻል የሚያሳጣንን ነገር ማሰብ ለተፈጥሮአችን የተመቸ አስተሳሰብ ይሆናል። በመጥፎ ወዳጅነት ላይ የሚጠፉ እያንዳንዱ ደቂቃዎች ከጥሩ ወዳጅነት ጋር ልናሳልፋቸው የምንችላቸው ሰዓቶች እንደሆኑ ካሰባችሁ ፥ ለውሳኔ አሰጣጥ ይቀለናል።

 

ማቋረጥ፣ መተው፣ መልቀቅ፣ ተስፋ መቁረጥ የሚሉ ቃላት አሉታዊ (negative) ስሜት ብቻ ነው ያላቸው ብዙ ጊዜ። ለዚህ ነው አብረውን የሚሰሩ ሰዎችን፣ ወዳጆቻችንን ወይም የቅርብ ሰዎቻችን መተው እና ከእነሱ ጋር ማቆም የሚያስፈራን። ግን ለጥሩ ነገር ጅማሮ መጥፎ ነገር መቋረጥ ይኖርበታል። የበጎ ነገር መንደርደሪያ የመጥፎ ነገር ማብቂያ ነው። መጥፎ ነገር ወይም ለእነሱ የማይሰራን ነገር መተው ያልቻሉ ሰዎች ለእነሱ የሚሰራ እና በጎ የሚሆንላቸውን ለመጀመር አይችሉም። ቅድም እንዳልኩት በምንም መስክ ያለ ስኬት ማለት የሚሰራን ነገር አብዝቶ መስራት እና የማይሰራን ነገር መተው ነው።

 

በማይሰራ ነገር ላይ የምናጠፋው ጊዜ ከሚሰራ ነገር ላይ እየተቀነሰ እንደሆነ ካልገባን፤ ስለ አለን ውስን ሰዓቶች እና ሪሶርሶች ብዙ ግንዛቤ የለንም ማለት ነው። ሌላው ሰብአዊ ባህሪያችን የታዳጊነት እና ሰዎችን የመቀየር ስነልቦና እንዲኖር አድርጓል። እውነታው ግን ይሄን አስተሳሰብ የምንጠቀመው ሰዎች ከኛ የዓለም እይታ ጋር የሰመረ ባህሪ እንዲኖራቸው ነው። ወዳጆቻችን በራሳቸው ለራሳቸው የሚሆን ባህሪ ይዘው ይሆናል። ጥሩ ጓደኛ፣ ጥሩ ሚስት ወይም ጥሩ ቤተሰብ ላይሆኑ ይችላሉ። ግን እንደዛ የመሆን መብት እንዳላቸው መዘንጋት የለብንም። ብቸኛው ምርጫችን ያ ሰው ለኛ የሚሆን nurturing (ጠጋኝ) ባህሪ እንደሌላቸው መወሰን እና ያን ወዳጅነት ማብቃት ነው። ያ ሰው መጥፎ ስለሆነ ላይሆን ይችላል። ከኛ ጋር የሚስማማ ማንነት ግን እንዲኖረው ስላልመረጠ፤ የታዳጊነት እና ነገ ይሻሻላል የሚለው ባህሪያችን ያን ሰው ከኛ ጋር እንዲስማማ በማድረግ ጊዜያችንን በከንቱ እናጠፋለን።

 

በሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ 15 ከቁጥር 11 ጀምሮ ያለው አፍቃሪው አባት ታሪክ ብዙ አስተማሪ የሕይወት ምክሮች አሉት። አንዱ ትምህርት ልጁ ወደ ሞት ቀጠና እንደሚሄድ እያወቀ ገንዘቡን ከፍሎ ሰጥቶ መሸኘቱ ነው። እኛ ብንሆን የምናደርገውን ተመልከቱ። ፈጽሞ ልጃችንን አደጋ ውስጥ አንከተውም። በሽማግሌ ማስመከር፣ ማሳፈር፣ በጭቅጭቅ እና በኃይል ፍላጎቱን እንዲተው ማድረግ ነው። ያ ምን ያህል ልቡ የከጀለን ሰው ያስቆመዋል? መቼም የሚሰራ ስትራቴጂ ግን አይደለም።


ሲ ኤስ ሉዊስ እንዲህ ይላል “እየሰመጠ ያለን ሰው ለመርዳት እስከሚሰምጥ መታገስ ያስፈልጋል። ያለመስመጥ ትግሉን ሳይጨርስ የእርዳታ እጅ መዘርጋት ፥ ራስን ለአደጋ ማጋለጥ ነው።” በተመሳሳይ ሰዎች የውሳኔያቸውን ክፉ ውጤት በአግባቡ ተመልክተው፣ ሪፍሌክት አድርገው፣ የኛን እርዳታ ለመቀበል እጃቸውን እስከሚዘረጉ ድረስ ለመርዳት እና ለመታደግ መጣር የመማርን እና ፍጹም የመቀየርን ዕድል ነው የሚዘጋው። ለዚህ ነው የታዳጊነት ፓራሹታችንን ያለ ሰዓቱ ላለመክፈት መጠንቀቅ ያለብን።

 

ሰዎች ለምርጫቸው ኃላፊነት የሚወስዱ እና ከዛ የሚማሩ ካልሆኑ፤ ከእነዚህ ሰዎች ጋር የምናሳልፈው ጊዜ ጉዳቱ ለኛ ብቻ አይደለም፤ ለእነዛም ሰዎች የመማርን እና የመለወጥን ዕድል ነው የሚነሳው።

355 views0 comments
Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew




ጥንታዊ መጽሐፎች የሚነግሩን ይሄ ሕይወት ጦርነት እንደሆነ ነው። እስቲ በደንብ ይሄን ለመረዳት አሁን እየተካሄደ ያለ ጦርነት እንመልከት። ለምሳሌ ሩሲያ እና ዩክሬን ጦርነት ውስጥ ናቸው። ጦርነቱ ገና አልተጠናቀቀም። እምብዛም የተገመተው ውጤት አልተገኘም። በጦርነቱ እስካሁን በሁለቱም ወገን ያሉት የጠበቁት አልሆነም። ብዙ ውጊያዎች እስካሁን ተካሂደዋል። ለምሳሌ በአንቶኖቭ ውጊያ፣ በካርኪቪ ውጊያ፣ በኬርሰን ውጊያ፣ በሉናስክ ውጊያ እና ሌሎች ሩሲያ ስታሸንፍ ፥ በቮዝነሰስኪ ውጊያ፣ በሚካሪ ውጊያ፣ በኢርፒን ውጊያ፣ በሰሚ ውጊያ እና ሌሎች ዩክሬን አሸንፋለች። ውጤታቸው ገና ያልታወቁ ውጊያዎች አሉ። እንደቀጠሉ ያሉ። ጦርነቱ በመጨረሻ እንደሁሉም ጦርነቶች አንዱ በአንዱ ላይ የበላይ ሆኖ ይጠናቀቃል። ግን አሸናፊው የሚፈልገውን በመጨረሻ ላያገኝ ይችላል።



ሕይወትም ልክ እንደዚ ጦርነት ናት። ዩክሬን ከሩሲያ ጎረቤት መሆኗ ተፈጥሮአዊ ሁኔታ ነው። ጎረቤት ሀገርህን መምረጥ አትችልም። በሕይወትም ብዙ ማንመርጣቸው ነገሮች አሉ። ዕድል ብቻ የሆኑ፣ ከኛ ቁጥጥር ውጪ ያሉ ክስተቶች አሉ። በሚገርም ሁኔታ ግን የሕይወትን ደስታ እና ስኬት የሚወስነው ከማንመርጣቸው ነገሮች በላይ የምንመርጣቸው ጉዳዮች ናቸው።


የመጀመሪያው የሆነውን ነገር እንደሆነ የመቀበል ምርጫ ነው። ሪያሊቲን (ነባራዊ እውነታን) እንዳለ የማየት ምርጫ።



ምንም ሩሲያ ኃያል ብትሆን ሁሉንም ውጊያዎች ማሸነፍ አትችልም። ከሩሲያ አንጻር ዩኩሬን ምንም ትንሽ ብትሆን ሁሉንም ውጊያዎች አትሸነፍም። በኛም ሕይወት ሁሉንም አውደ ውጊያዎች አናሸንፍም። ይሄ ሕይወት የልጅ አውደ ውጊያ አለው፣ የገንዘብ አውደ ውጊያ አለው፣ የጓደኝነት አውደ ውጊያ አለው፣ የጤና አውደ ውጊያ አለው፣ የመንፈሳዊነት አውደ ውጊያ አለው፣ የታዋቂነት እና የማህበረሰባዊ ክብር አውደ ውጊያ አለው፣ የውበት አውደ ውጊያ አለው፣ የጥበብ እና የእውቀት አውደ ውጊያ አሉት፣ የትዳር እና የፍቅር አውደ ውጊያ አሉት፣ የጥሩ ቤተሰብ አውደ ውጊያ አለው፣ የሥራ እና የሙያ አውደ ውጊያ አሉት፣ የመኖሪያ አከባቢ አውደ ውጊያ አለው። እነዚህ እና ሌሎች የውጊያ አውዶች ናቸው በሕይወት ጦርነት ውስጥ ያሉት። ስኬታማ ሕይወት ማለት ሁሉንም አውደ ውጊያዎች ማሸነፍ ማለት አይደለም። እንደዛ የሚያስብ ሁሉ በዚህ የሕይወት ፍልሚያ በፍጥነት ከጫወታ ውጪ የሚሆን ነው። የመጀመሪያው እውነት ሁሉንም ውጊያዎች እንደማናሸንፍ ማወቅ ነው። ሁለተኛው ትልቁ ጥበብ ግን የትኛው ውጊያ ወገብ ሰባሪ እንደሆነ መረዳት ነው። ማለትም በፍጹም መሸነፍ የሌለብን ውጊያ የትኛው ነው የሚለውን ማወቅ። ያን ውጊያ የተሸነፈ ሁሉንም አውደ ውጊያዎች ቢያሸንፍ እንኳ ጦርነቱን ይሸነፋል።



ታላቁ የጦር አዋቂ ሰን ዙ እንዳለው የምርጥ ጄኔራል መለያው ይሄን አውደ ውጊያ ማወቅ ነው። ምርጥ ጄኔራል ብዙ ውጊያዎችን ተሸንፎ እንኳ ጦርነቱን ግን ያሸንፋል። ሁሉም ውጊያዎች ላይ ያለንን አቅም በእኩል መጠን ማፍሰስ አንችልም። ስለዚህ አንዳንዶቹን ለመሸነፍ መተው አለብን። ለአንዳንዶቹ ውጊያዎች ተፈጥሮ ሳይቀር ለሽንፈት የሚሆን ማንነት ሰጥታናለች። ስለዚህ ያንን መቀበል ያስፈልጋል። ዩኩሬን ምርጫዋ ቢሆን ከሩሲያ አጠገብ ጎረቤት ባትሆን ይሻላት ነበር። ግን አንዳንድ ምርጫዎች በዚህ ዓለም ዝግ ናቸው። የመቀበል እና የለውጥ ሚዛን ነው በጦርነቱ አሸናፊ የሚያደርገን።



የሆነን ግለሰብ ሕይወት አይታችሁ የእናንተ ሕይወት እንደዛ ሰው እንዲሆን መመኘት የመጀመሪያው የሽንፈት ፕሮፓጋንዳ ሰለባ መሆኛ መንገድ ነው። ሰን ዙ እንደሚለው ጦርነትን ሳትዋጋ ማሸነፍ ከቻልክ የምንጊዜም ምርጥ ጄኔራል ነህ። እንዴት ነው ሳትዋጋ የምትሸነፈው? (ለጊዜው ሳንዋጋ ማሸነፉን እንተወው እና!)። እንደ ሌሎች እኛም እንድንሆን በመመኘት። የሕይወት ምርጫችን እኛን ብቻ ነው ሊመስል የሚገባው። ተመሳሳይ መጽሐፍ እያነበቡ፣ ተመሳሳይ ምግብ እየበሉ፣ በተመሳሳይ ቤተሰብ እና በተመሳሳይ አካባቢ ያደጉ ሁለት መንትያ ልጆች ሳይቀር በዚህ ምድር ላይ ለሚገጥማቸው ነገር የሚሰጡት ግብረ መልስ ለየቅል ነው። ልጆች እንደእነ እከሌ ልጆች እንዲሆኑ መመኘት ልጆችን ለሽንፈት ማሰልጠን ነው። ያ ልክ ለጠላት ፕሮፓጋንዳ ተላልፎ እንደመሰጠት ነው። እውነት ነው ሰው በመሆናችን ከሌሎች ጋር የምንጋራቸው ብዙ ጉዳዮች አሉ። ግን በዚህ ሕይወት ያለን ጥልቅ ደስታ እና ሀዘንን አስመልክቶ ከማንም ጋር አንጋራም። በጦርነት መኃል አሰቃቂን መከራ ተቀብሎ የሚስቅ እንዳለ ሁሉ ፥ ፌሽታ በበዛበት መኃል የሚቆዝም አለ። “ለምን?” ካልን መልሱ ያን ሰው ብቻ ነው የሚመስለው። ሕይወትን በሌሎች መነጽር ብቻ ለማየት የሚደክም ማንም ምንም ነገርን አጥርቶ የማየት እርከን ላይ አይደርስም።



በመጨረሻም የሰው ልጅ ትልቁ ሀብቱ የማሰብ እና የማሰላሰል አቅሙ ነው። ያም አውደ ውጊያ ነው። በነጻነት የማሰብ እና ነገሮችን በጥልቀት የማየት አቅምን ማዳበር የሕይወትን ጦርነት ለኛ በሚስማማ መልኩ ለማጠናቀቅ ጥቅም አለው። ይሄ ሕይወት የኛ ሕይወት ነው። ባንተ ሕይወት መዝገብ ውስጥ ያለፈው እና ያለው ያንተ ነው። ስለዚህ ኃላፊነት እንውሰድ። ሁሉን ልታሸንፍ አትችልም። ዓላማህ በጦርነቱ ማብቂያ ጫፍ ላይ ስትደርስ ፥ የአንድ ደቂቃ ዕድል ብታገኝ ፥ ይሄ ሕይወት ውብ ነበር ለማለት ነው። በስንፍና ያለፍከው ነገር እንደሌለ በማየት፣ የራስህን ጀርባ እየመታህ "በራሴ ሕይወት ላይ ምርጥ ጄኔራል ነበርኩኝ" ለማለት መብቃት ነው። ምክንያቱም ይሄ ሕይወት ያንተ ሕይወት ነው። ሽንፈቱም ድሉም ያንተ ነው።

394 views0 comments
Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew




ድሮ የምሰራበት የስፖርት ቦታ በትልቁ “NO PAIN NO GAIN ወይም ካለሕመም ምንም የምታገኘው ነገር የለም!” የሚል የተጻፈ መፈክር ነበረው። አንዳንዴ ወደ ኋላ በመሄድ በሕይወቴ ያሳለፉኳቸውን ከባባድ ጊዜዎችን ለማስታወስ እጥርና “ምናለ እንደ ዛ ባልሆን” ልል ይቃጣኛል ፥ ሕመሙን በማስታወስ። ግን ያ ሀሳብ ከአንዱ የአዕምሮ ክፍሌ ሳያልፍ ነው ያን የመስቀል ጉዞ “እሰይ ሆነ ፥ እሰይ ደረሰብኝ” ብዬ በድጋሚ የማፈቅረው። ብዙዎቻችን ያለ መስቀል ትንሣኤ ፈጽሞ እንደማይኖር አይገለጽልንም። እሁድን የሚናፍቅ ቢኖር አርብን መታገስ ይጠበቅበታል።


ሕመምን የምንታገሰው ጀግና  ፥ ስለሆንን ወይም የተለየ ፍጡር ስለሆንን አይደለም።


እንደሚሞት፣ ለዛውም የመስቀል ሞትን እንደሚሞት ራሱ ጭምር እየተናገረ የመጣው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሳይቀር መስቀሉን በቅርብ ርቀት ሲያየው ፥ “ይሄ ጽዋ ፈቃድህ ቢሆን ከእኔ ይራቅ” ብሎ ጸልዪል። የጌታችን ያልተሰማ ጸሎት ይሄ ብቻ ነበር። “ዋጠው፣ ይሄን ጽዋ ጠጣው” ብሎ አባቱ ጨከነበት። አጽናኞችን ግን ላከለት። እውነተኛ አባት የሚያደርገው ይሄን ነው። የሕመምን ጽዋ ለልጆቹ ያስጎነጫል። እውነተኛም እናት ከዚህ የአባት ጭካኔ ጋር ትስማማለች። ምክንያቱም የልጇን ትንሣኤ ትፈልጋለች እና። ልጇ ሁልጊዜ ልጅ ሆኖ እንዲቀር አትፈልግም። ለዚህ ነው እመቤታችን ድንግል ማርያም አንድም ጊዜ ጌታን ከመስቀል ሞት እንደ ሐዋርያው ጴጥሮስ “ልጄ ሆይ ፥ አትሙትብኝ” ብላ ስትከላከል ያልታየችው። ያልተሰማችው። ያ ሞት ያለጊዜው ሲመጣ ብቻ ልጇን ካለጊዜው ከሆነ ሕመም ጠበቀችው እንጂ ፥ በዕድሜው ለሆነው አርብ ግን ድንጋል ማርያም ተባባሪ ነበረች። ይሄ ትንሣኤን ለራሱ ለሚሻ ፥ ለልጆቹ ለሚመኝ ሰው ሁሉ የተጻፈ ታሪክ ነው።



አሁን አሁን ሕይወትን ካለብዙ ነገሮች ማሰብ እያቃተን ነው። በተለይ በምዕራቡ ሀገራት። መብራት፣ ኮምፒውተር፣ ጉግል፣ ፍርጅ፣ መኝታ ቤት የተቀመጠ መጸዳጃ ቤት ፥ ሕይወትን ካለእነዚህ የማያውቅ ትውልድ ነው ያለው። አንዱ ለልጄ “በኛ ጊዜ ጉግል (Google) አልነበረም ስለው አላመነኝም” ብሏል። ምክንያቱም ካለ ጉግል የሰው ልጅ ምን ያህል መረጃን ለማግኘት እንደሚደክም ይሄ ልጅ ፈጽሞ የማይረዳበት ዘመን ነው።



አሁን አሁን ወደ ሕክምና ስፍራ ብትሄዱ የመጀመሪያው የሚሰጣችሁ ነገር ሕመም ማስታገሻ ነው። በየቤቱ የተለያዩ ዓይነት የሕመም ማስታገሻዎች አሉ። መውሰድ ባንፈልግ እንኳ ቢያንስ ከራስ ምታት ማስታገሻ እስከ ተለያዩ ኦፒዎዶች ቤታችን አሉ። እንቅልፍ እንቢ ካለንም ብዙ መጨናነቅ አሁን አያስፈልገንም። በተለያዩ መልኮች የእንቅልፍ ማስተኛ ሽሮፖች እና ክኒን ሞልተውልናል። የሰው ልጅ ብዙ ታሪኩ ግን እንዲህ አልነበረም። እስከ አስራዘጠነኛው ክፍለዘመን መጨረሻ ድረስ የሕመም ብቸኛ ምርጫ ጥርስን ነክሶ መቻል ነበር። ምን አልባት ትንሽ ማደንዘዣ አልኮል ይሰጥሃል ወይም የምትነክሰው ነገር ያቀብሉህና ፥ የሰውነትህ አካል ሳይቀር ያለማደንዘዣ ይቆረጥ ነበር። ልክ እንደ ክርስቶስ አጠገብህ የሚያጽናኑህ ይኖሩ ይሆናል እንጂ ያን ሕመም ስለ ሕመሙ ብቻ ተብሎ የሚያስቀረው አልነበረም። ምክንያቱም ለረዥሙ የሰው ልጅ ታሪክ ሕመም የሰው ታሪክ አካል ነበር። የሕክምና ባለሙያዎች እና ተመራማሪዎች ሳይቀር ፥ ሕመምን ለማስቀረት ያደረጉት ጥረት የረዥም ጊዜ ታሪክ አልነበረም። ትልቁም የሳይንስ ትኩረት አልነበረም።



ጆናን በርክ በStory of Pain በሚለው መጽሐፉ እንደጻፈው ኬሚስት ሀምፍሬ ዴቪይ የLaughing Gasን (ላፊንግ ጋዝን) የሕመም የማስታገሻ ባህሪውን ካገኘ በኋላ እንኳ በሕክምናው እና በሳይንሱ ዓለም እንደ ትልቅ ግኝት ተቆጥሮ በቶሎ ወደ ተግባር አልተገባም። ለሕመም ማስታገሻነት በስፋት ጥቅም ላይ እስኪውል መቶ ዓመታት ፈጅቷል ። ሌሎችም የሕመም ማስታገሻዎች፣ ለምሳሌ እንደ ኒትረስ ኦክሳይድ ሲገኝም የሕክምናው ዘረፍ እንደ ዛሬው ተሯርጦ ወደ መጠቀም አልገባም። ጆናን በርክ እንደሚለው የሕመም ትርክት ለብዙ ሰዎች ለመቀበል የሚቸገሩት አልነበረም። ሕመም ለዶክተሮችም ሆነ ለታካሚዎች የሕክምናው እና የመዳን ሂደት አካል ነበር። እንደውም አንዳንድ ሰርጅኖች ያለ ታካሚው የስሜት እንቅስቃሴዎች እና ጩኸት ሕክምናውን ማድረግ አይፈልጉም ነበር።



ከሁሉም በላይ ግን ለብዙ ሰዎች ለብዙ የታሪክ ዘመን ሕመምን ራስን በመቆጣጠር፣ በመግዛት እና በክብር ጨክኖ ማለፍ የማንነት መገለጫቸው እና የጀግንነት ጌጣቸው ነበር። ሕመም የጀግንነት፣ የወንድነት እና የታላቅ ስብዕና መገለጫ ነበር። ሕመምን ሳይመጣ ይለማመዱት ነበር። በሚበሉት ነገር ሳይቀር የሚያቃጥል፣ የሚለበልብ እና ጎምዛዛ ነገር በማብዛት የሕመም የመታገስ ሐሞታቸውን ያጠነክሩ ነበር። በእኔ ዕድሜ ሳይቀር የሚያቃጥል ቃሪያ በምግብ ጠቅልሎ አባቴ ያጎርሰኝ ነበር። ፈጽሞ ያን እንድተፋው አይፈቀድልኝም ነበር። ጨክኜ አኝኬ እድውጠው እንጂ። ከዛ የሚብስ ነገር ሊመጣ ስለሚችል ያን ቃጠሎ ቃሪያ አኝኬ እውጠዋለሁ። የአባትነት ሥራ ልጅን ከሕመም መጠበቅ አልነበረም። ይልቁንስ በየደረጃው ለሕመም ማጋለጥ እንጂ።



ዛሬ ግን የሕክምናው ዘርፍም ተለውጧል። በአሜሪካ ዶክተሮች የሚገመገሙት ታካሚዎች የሕክምናው ፕሮሲጀር ሲካሄድ በተሰማቸው የሕመም መጠን ሆኗል። ምንም ሕመም ካልተሰማቸው ያ ዶክተር ትልቅ እና በጎ ሬቲንግ ያገኛል። ያም ለደሞዝ እና ለእርከን ዕድገት አስተዋጽኦ አለው። ስለዚህ ዶክተሮች ምን ያደርጋሉ? ሱስ እንደሚያሲዝ እያወቁ የተለያዩ የሕመም ማስታገሻዎችን ለታካሚዎቻቸው ያስቅማሉ። ዛሬ አሜሪካ ውስጥ መጨነቅ መድኃኒት አለው። መወፈር መድኃኒት አለው። ትኩረት ማጣት የሚቃም መድኃኒት አለው። ያለመድኃኒት የማይንቀሳቀሱ ጥቂት መጤዎች ብቻ ቢሆኑ ነው። ከ1980ዎች ጀምሮ የዓለም የጤና ድርጅት ሳይቀር እነዚህ የሕመም ማስታገሻ ኦፒዶዎች በስፋት እንዲመረቱ እና ጥቅም ላይ እንዲውሉ መግፋት እና ማበረታታት ጀምረዋል።



የሚገርመው ግን የሕመም ማስታገሻዎች የረዥም ጊዜ ጥቅም እንዳላቸው የሚያሳይ ምንም ሳይንቲፊክ የሪሰርች ውጤቶች አለመኖሩ ነው። ያ ብቻ ሳይሆን አሁን በስፋት እየወጡ ያሉ ጥናቶች እንደሚያሳዩት የሕመም ማስታገሻዎች የቁስሎች የመዳንን ሂደት በጣም እንደሚያዘገዩት ነው። ልክ ነው አንዳንድ የቀዶ ጥገና ሕክምናዎች የግድ የሕመም ማስታገሻዎች (anesthesia) ያስፈልጋቸው ይሆናል። ግን ከየት ወዴት እንደመጣን ብቻ እዩት?



የሰው ልጅ ትልቁ ሀብቱ ለራሱ የሚነግረው ትርክት ነው። ብዙ ጊዜ እንደጻፉኩት የደስተኛ ሕይወት ምንጭ ትርጉም ያለው ሥራ መሥራት እንጅ ምቾት አይደለም። ደሃ ራሱን አጠፋ ሲባል መስማት በጣም ዝቅተኛ ነው። ራስን ማጥፋት እንደ ፊንላንድ፣ ደቡብ ኮሪያ እና መሰል የምቾት መጠናቸው ከፍ ባሉ ሀገራት ላይ ነው የሚብሰው። የሰው ልጅ ሕመምን እና መከራን ለማለፍ የሚታገለው ትግል እና በዚህ ወቅት ለራሱ የሚነግረው ትርክት ነው የደስታው መሠረት። ትርጉም ያለው ሕይወት ማለት ይሄን ሕመም ጥርስ ነክሶ ሲታለፍ ነው። ይሄ ሕመም የትውስታ ማህደራችን (memory) ውስጥ ካልተቀበረ ፥ የምናገኘው ጥሩ ነገሮች እና ምቾቶች ሁሉ አያስደስቱንም። መስቀሉ ነው የትንሣኤው ውበት። ያ ትንሣኤ ውበት የሚኖረው ፥ ልብሳችንን ተከፋፍለው፣ በጦራቸው አይነሳም ብለው ወጋግተው፣ በተሳለቁብን እና ባሾፉብን መኃል ከዛ ሕመም በላይ ሆነን ፥ ከቀናት መሰወር በኋላ ላያስቆሙን ብድግ ስንል ነው። እነዛ ሕመሞች የትንሣኤው ዘላለማዊ ጌጦች ናቸው። ኢዮብ ያለ ሕመሙ እና ጥርሱን ነክሶ ራሱን ሳያዋርድ ሕመሙን መታገሱ ነበር ዖፅ ከምትባል መንደር በላይ ለዘላለም ገዝፎ እንዲታይ፣ እንዲተረክለት ያደረገው። ሰው እንዴት ነው ጌጦቹን የሚርቀው? እንዴት ይሄን የደስታ ምንጭ ከልጆቻችን እናርቃለን?

417 views0 comments

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page