top of page
ree

የንጉሱን ልብስ ታሪክ ብዙዎቻችን (the emperor cloth) እናውቀዋለን። ታሪኩ ረዘም ቢልም በጥቅሉ ግን የንጉሱ ልብስ ሰፊዎች ለንጉሱ ታይቶ የማይታወቅ ልብስ እንሰፋለን ብለው ተነሱ። ያን ልብስ ማየት የማይችል ሰው በፈጣሪ ርጉም የሆነ እና ኃጢያተኛ ነው አሉ። ንጉሱ ልብሱን ለማየት ቸኮለ። ሕዝቡ ንጉሱ ያን ልብስ ለብሶ ለማየት ቋመጠ። ንጉሱን ልብስ ሰፊዎቹ ለኩት። በወሩ ተመልሰው ልብሱን ይዘን መጣን አሉ። ንጉሱ የለበሰውን ልብስ ሁሉ አሶለቁት። ከያዙት ሳጥን ልብስ እንደሚያወጡ መስለው፤ ከፈቱት። ማንም በዛ ያለ ልብስ አልታየውም። ግን ማን ደፍሮ ይናገራል። ልብሱን ማየት የማይችል ሰው የኃጢያት እና የርግማን ግርዶት ነው ተብሏል። ንጉሱም ልብሱን ማየት አልቻለም። ግን በልቡ ኃጢያተኛ እና በፈጣሪ የተረገምኩኝ መሆን አለብኝ አለ። ንጉሱን ያለበሱት መስለው ተሸከረከሩት። አለበስነው ብለው እልል አሉ። ሁሉም የልብሱን ማማር በአድናቆት ዋው እያለ ገለጸ። የአድናቆት ማዕበል እና ዶፍ ወረደ። ንጉሱ በቤተሰቡ እና በአጃቢዎቹ ተከቦ በአስር ሺዎች ለሚቆጠሩ ሕዝቦቹ ከዚህ አስገራሚ ልብስ ጋር ወደ ሰገነቱ ወጣ። ያን አስገራሚ ልብስ ያየ አንድም የለም። የንጉሱን ሁሉ መላ ከነመላመሉ ግን ሁሉም እያዩ ነው። ግን ሁሉም አስደናቂ ይሆናል ብለው ለተመኘቱ እና ማየት ግን ላልቻሉት ልብስ ከመጀመሪያ ጫፍ እስከ እስከመጨረሻ ጫፍ የአድናቆት ናዳ አወረዱ። በዚህ መኃል በአባቱ ትከሻ ላይ ያን አስደናቂ ልብስ ለማየት እሽኮኮ የወጣ ልጅ ፥ እየሳቀ “ንጉሱ ራቆቱን ነው” አለ። ከዛ ከላይ እስከ ታች ያለው ሕዝብ “ሕጻኑ እኮ ንጉሱ ራቆቱን ነው አለ!” እያሉ ሁሉም ያዩትን፣ የሚያውቁትን እውቀት ለሁሉም ማሰራጨት ጀመሩ። ከላይ እስከ ታች በሕጻኑ አይን ያዩትን የተገለጠ እውነት ማስተጋባት ጀመሩ።



እውቀት ብዙ ዓይነት ነው። አንዱ ግን መጀመሪያ ያወቅነውን ያን እውቀት እንደ ምናውቅ በድፍረት መግለጽ ነው። የታወቀ እውቀት ግን መግለጽ የተፈራ ነገራ ካልታወቀ እውቀት ወይም እውነት ጋር እምብዛም ልዩነት የለውም። ለባለፉት አራት ዓመታት የአሜሪካ ማህበረሰብ ጆይ ባይደን እንዳረጀ፣ የማሰብ እና የማገናዘብ አቅሙ ለሀገር መሪነት ብቁ እንደማያደርገው ያውቅ ነበር። ግን ያን መናገር ለዲሞክራቶች ፓርቲያቸውን መክዳት ነበር የሆነው። ስለዚህ የታወቀውን እውነት ካልታወቀ እውቀት ጋር አቻ አደረጉት። መደበቅ የማይቻልበት ደረጃ ሲደርስ ግን ሁሉም ነገር ከእጃቸው አምልጦ ነበር። በቲቪ ለዓለም በሚታይ መልኩ ከፕሬዝዳንት ትረምፕ ጋር ሲከራከር ትረምፕ “የሚናገረውን ራሱ እንኳ የሚያውቅ አይመስለኝም” ብሎ አሾፈበት። ከዛ ያን የተገለጠ እውነት በሕጻኑ ዓይን አሁን ሁሉም ተቀባበለው። የደረሰውን ውድቀት ግን መቀነስ አልተቻለም።



አሁን ደግሞ ፕሬዝዳንት ትረምፕን ተመልከቱ። ካቢኔው ሲሰባሰብ ሰውዬውን ልክ የአብይ አህመድ ካቢኔ ይመስል አስደናቂ መሪ፣ ባለራዕይ መሪ፣ በአሜሪካ ታሪክ ተፈጥሮ የማያውቅ መሪ፣ ስኬት በስኬት የሆነ መሪ በሚል ነው የሚጀምሩት። በቀደም ለት የቴክ መሪዎችን ሰብስቦ የአፕል ሲኢኦ የሆነው ቲም ኩክ በሦስት ደቂቃ ንግግሩ ትረምፕን ስምንት ጊዜ አስደናቂ መሪ እያለ አመሰገነው። እውነታው ግን የሌበር ዲፓርትመንቱ እንደጠቀሰው ከ2001 ዓ.ም. በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የሥራ አጥ ቁጥር ሪከርድ ደረጃ ዝቅ ብሏል። የአሜሪካ ወዳጅ የነበረችው ሕንድ ከቻይና ጋር ገጥማለች ወይም እየሸሸች ነው። የአሜሪካ ወዳጆች አሜሪካንን እየራቋት ነው። ትረምፕ ሲመጣ ቃል ከገባው የፓናማ፣ የካናዳ እና የግሪን ካርድ ጥቅለላ አንዱም የተሳካ ውጥን የለም። ሀገሪቷ ከመቼውም ጊዜ በላይ ተከፋፍላለች። የኑሮ ውድነት ከባይደን ዘመን በላይ የማይቻል ሆኗል። እውነት ነው ድንበሩ ተዘግቷል። በሕገ ወጥ መልኩ የሚገቡ ኢሚግራንቶች የሉም። ግን ደግሞ የዲፖርቴሽን ሂደቱ ጽንፍ ሄዶ ወንጀል ያለባቸውን ብቻ ሳይሆን ንጹሀንን እና ለኢኮኖሚው ትልቅ አስተዋጽኦ የሚያደርጉትን ሁሉ እያጠቃ ነው። በዚህ ውስጥ ሆነን ነው የንጉሱ ልብስ አስደናቂ ነው የሚሉ የካቢኔ አባላትን የምንሰማው።



በሕይወት እውነትን ግቡ ያላደረገ ሰው የሚያጠፋቸው ጥፋቶች የትየለሌ ነው። ንጉሱ ራቆቱን መሆኑን ሁሉም አይቷል። ያን መናገር ግን ኃጢያተኛ የሚያስብል ከሆነ ወይም ቅጣት ካለው ያን ሪስክ ለመውሰድ ብዙ ሰው አይፈቅድም። መወደድ የመጀመሪያ ግባችን ሲሆን፥ ከሰዎች ጋራ ላለመስማማት እንጥራለን። ሪስክ ከመውሰድ እንሸሻለን። ድንበር ላለመግፋት እንጥራለን። የሌሎች ሰዎች ጥበቃ እስረኛ እንሆናለን።


እውነት ግቡ የሆነ ሰው ከሌሎች ጋር ለመለያየት ብዙ አይፈራም። ሪስክ ከመውሰድ አይሸሽም። ያለ ሪስክ እውነትን መግለጥ አይቻልም እና። ከሁሉም በላይ የሌሎች ሰዎች ፍላጎት እስረኛ አይሆንም።


ይሄ በኛም ግለሰባዊ ሕይወት ውስጥ ያለ ነገር ነው። የምናውቀው፣ ብዙ ዳታዎች ያሉን እውነቶች አሉ። ግን ያን ማወቅ እና መግለጥ አንፈቅድም። ለምን? ከምኞታችን ተቃራኒ ስለሆነ። የምንመኘው እና የምናውቀው ለየቅል ሲሆን፤ ለምኞታችን እንሸነፋለን። ምኞታችን እውቀትን እና እውነትን መግለጥ ከሚፈልገው ክፍላችን በላይ ጠንካራ ነው። ስለዚህ እውነትን በድፍረት የሚነግሩን ሰዎችን በዙሪያችን መክበብ አለብን።



ዛሬ አሜሪካ ውስጥ ስለ ቻይና ያለው አመለካከት ተመሳሳይ ነው። ቻይና በብዙ መንገድ ተመንድጋለች። በብዙ የቴክኖሎጂ ብቃት ከአሜሪካ በልጣለች። ይሄን ማመን ግን የፖለቲካ ሱሳይድ ነው። ስለዚህ ቻይና ሰርቃ ነው፣ አጭበርብራ ነው ወይም ብዙ ደሃ ቻይናዎች አሉ በሚሉ ፕሮፖጋንዳዎች ተጠምደዋል። እውነታውን ማመን ግን ችግሩን ለመቅረፍ የመጀመሪያ መንገድ ነበር። የሰው ልጅ እውነትን መቀበል ዋጋ የሚያስከፍለው ሆኖ ካገኘው፤ ማስደሰትን ይመርጣል።



በዙሪያችን ያሉትን ሰዎች እንገምግማቸው። እውነታን በምንም ዋጋ የሚነግሩን ናቸው ወይስ እኛን ለማስደሰት የሚጥሩ ናቸው። በሚያስደስቱን ሰዎች ራሳችንን ከከበብን የቀን ጉዳይ ነው፤ ከኛ ጋር መሆን አስፈሪ እና የማያስደስት በሆነበት ቀን ጥለውን የሚሄዱ የመጀመሪያ ሰዎች እነርሱ ናቸው። ለዚህ ነው በጆራችን ላይ ሙገሳን ዲቴክት የሚያደርግ ሳይረን ሊኖር የሚገባው። እውነታን ቢመረንም ለሚነግሩን ቀና መንፈስ እና ምቹ ሁኔታን እንፍጠርላቸው። እነርሱ ያድኑናል።




 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 24
  • 3 min read
ree

አንዱ ፍላጎታችን መሉ በኩልሄ መልስ ማግኘት ነው። የትኛውንም ጉዳይ ብንችል በአንድ ሳጥን ውስጥ መክተት እና መረዳት እንፈልጋለን። የምናቃቸውን ሰዎች በምድብ ከፍለን ጥሩ እና መጥፎ ብቻ ወይም ወዳጅ እና ጠላት እንዲሆኑልን እንፈልጋለን። ስለሕይወትም ያለን አረዳድ ሕይወት ትግል ወይም ሕይወት ከባድ እንደሆነ ብቻ ነው። ስለ መንግስትም ሥርዓቶች ያለን ግንዛቤ ጨቋኝ፣ በዝባዣ፣ ፋሺስት ወይም ከኛ የሆነ እና ስህተቱ ይቅርታ የሚባልለት ወይም ነጻ እና ተራማጅ የሆነ ጥቅል ሳጥኖች ናቸው። በመንፈሳዊ ዓለምም የሚድን እና የማይድን፣ ሲዖል ወይም ገነት የሚገባ ብቻ ነው ያለን።


አሁን ላይ በጣም እየተረዳውት የመጣውት ነገር ለሰው ልጅ አዕምሮ ሪያሊትን መረዳት በጣም ከባድ ነገር እንደሆነ ነው። ይሄ ዓለም ከአዕምሮአችን የመረዳት አቅም በላይ በጣም እና እጅግ ውስብስብ ነው። ለምሳሌ ከሰዎች ጋር ስንኖር ግንኙነታችን እከሌ የሚባለው ሰው ሁልጊዜ ጥሩ ስለሆነ አይደለም ወዳጃችን የሚሆነው። ይልቁንስ እኛ የምህረት አቅም ለእርሱ ስላለን ጭምር ነው ወዳጅነት የሚጸናው። ወዳጅ ያልነው ሰው ስለእኛ የሆነ ጊዜ ክፉ ያስባል። እኛም ከዛ ክፋት ነጻ አንሆንም። ከቅናት ወይም ከሌሎች ያልተገናዘቡ ስሜቶች ተነስተን ያን ሰው የሚያሳዝን ባህሪ ወይም ንግግር ልናሳይ፣ ልናወጣ እንችላለን። ለዚህ ነው የምህረት እና የይቅር ባይነት አቅም ያላቸው ሰዎች ብቻ ዘላቂ የሆነ ወዳጅነት የሚገነቡት። እራሱ ውስጥ ያሉትን የክፋት ባህሪዎች እና ሀሳቦች ማስተዋል ያልቻለ ሰው ከሌሎች ጋር ጤናማ ግንኙነት ሊኖረው አይችልም።


ዴቭ ሻፔል ስለ ቢል ኮዝቢ አንድ ያለው ነገር ነበር። ከገደለው ይልቅ ያዳነው ይበልጣል። ከሰዎች ጋር ስንኖር ይሄ ይመስለኛል ውሃ ልኩ። ከሚገለው ይልቅ የሚያድነው ይበልጥ እንደሆነ መጠየቅ። ለብዙ ነገሮች ውሃ ልኩን ማግኘት ነው ወሳኝ። በሕይወት ውስጥም ብዙ ሰዎች የተዛባ ሕይወት የሚኖራቸው ውሃ ልክ ሳይኖራቸው ሲቀር ነው። ወይ አብልጠው ከብዙ ነገር ይልቅ ገንዘብ ይወዳሉ። ወይ ፍጹም አባካኝ ይሆናሉ። ፍጹም የሥራ ፍቅር ይይዛቸው እና ሁሉን ችላ ይላሉ ወይም ሰነፍ ሆነው የሰው ጥገኛ ይሆናሉ። ወይም ፍጹም ሰውን ያምኑና ሲታለሉ ይኖራሉ ወይም ሁሉን ተጠራጣሪ ሆነው ለደስተኛ ሕይወት መሠረት የሆነውን ሰውን ማመን ይሳናቸዋል። በእንግሊዘኛ ይሄ Adjusted ያልሆነ ሕይወት ይባላል።



አጀስት ያልሆነም እውቀት አለ። ሁሉን ነገር በኛ የፕሮፌሽን ዓይን የማየት ብቻ እውቀት። ወይም ጥቂት መጽሐፍ ብቻ በሕይወት ያነበበ ሰው ዓለምን በእነዛ መርሕሆች ብቻ ለመዳኘት እንደሚሞክረው ማለት ነው። በቅርብ የሠላሳ ዓመት ሴት ልጅ ያላት አንድ የሰባ ስድስት ዓመት ነጭ ጋር እያወራን፤ ሴት ልጇ የእርሷን ምክር ለመስማት ምንም ፈቃደኛ አለመሆኗ ገርሟት ታወራኛለች። የስነ ልቦና ባለሙያ ስለነበረች የሴት ልጇ ችግርን ከነ መፍትሔው ታውቀዋለች። ግን መች ለመስማት ፈቅዳ። ሕይወትን ተዋግታ ሕይወትን የኖረች ሴትዮ ፊት ለፊቷ እያለች ሴት ልጇ የርሷ የዓለም ዕይታ የተሻለ ጥራት እንዳለው ታስባለች። አስባ ስኬታማ ብትሆን አንድ ነገር ነው። ግን በሕይወት ከውድቀት ወደ ውድቀት ነው እየሄደች ያለችው።



አንድ ጥሩ የሚያነብ በአስራዎቹ መጨረሻ ያለ የዘመድ ልጅ አለ። ከእኔ ጋር ሲያወራ የእርሱ ፍላጎት የእርሱ የዓለም ምልከታ ትክክል እንደሆነ ለማሳየት ነው ጥረቱ። አንዳንዴ እገረማለሁ። የምገረመው በወጣቶች አዕምሮ ነው። ሁላችንም ያለፍንበት ዓለም ነው። የእኔም የዛ የሃያ ዓመቶቼ አዕምሮ ጭምር ነው የሚደንቀኝ። የሆነ መስመር አንበን ወይም ሰምተን ሁሉን ነገር በዛ የመመዘን ፍጥነታችን እና ከኛ ተለቅ ያሉ ሰዎች የሚያሳዩንን የሕይወት ዝግታ እንደ ሞኝነት የመቁጠራችን ዝንባሌ ማለቴ ነው።



ትልቁ ጥበብ ራስን መግዛት የሆነው ለዚህ ነው። ራስን መግዛት በራሱ እውቀት ሆኖ ሳይሆን ራሱን የገዛ ሰው ብዙ ውሳኔዎችን ማዘግየት ስለሚችል ነው። ያዘገየው ተገዶ ሳይሆን ፈቅዶ ሲሆን ማለቴ ነው። ያን የሚያደርግ ሰው እውነትን ለማግኘት ጥረቱን ስለማያቆም በትግስቱ ውጤቱን ይለውጠዋል።



ሕይወት በነጠላ አትሰራም። እያንዳንዱ ነገር የተያያዘ ነው። አንድ ሰው አንዳች ጥሩ ነገር ሲያደርግ ለኛ በጎ ብቻ አስቦ አይደለም። ለራሱም አስቦ ነው። መጥፎ የሚያደርግም ሰው ለራሱ ብቻ ጥሩ ስላሰበ አይደለም። በዛ ውስጥ የተጎደለ ፍትሕን በራሱ መንገድ ለማሻሻልም በመጣር ነው። በአንድ ጊዜ ብዙ ነገሮች አብረው እንደ ድር ይሰራሉ። ሕይወት ስትሰራ ይሄ ባይሎጂ ነው፣ ይሄ ኬሚስትሪ ነው፣ ይሄ ፊዚክስ ነው፣ ይሄ ቲዎሎጂ እያለች አትንቀሳቀስም። ሕይወት ጭራሽ እነዚህን ክፍፍሎች አታውቅም። ለምሳሌ አንድ መጥፎ ነገር የሚያደርግ ሰው በአንድ ጊዜ የሞራሉ ስንኩልነት፣ የዓየር ጸባዩ መጥፎ መሆን፣ መጥፎ ከማድረጉ በፊት የገጠመው ሕይወት፣ ጥሩ እንቅልፍ አለመተኛቱ በትክክል እንዳያስብ አድርጎት እና ሌሎች ተጨማሪ ጉዳዮች በአንድ ላይ መጥተው ሊሆን ይችላል። ብዙ ጊዜም እውነታው ይሄ ነው። ለዚህ ነው ብዙ ነገሮችን የሚያውቁ ሰዎች በጣም ጥሩ ውሳኔ የመወሰን አቅማቸው ከፍ የሚለው። ምክንያቱም ሪያሊትን በተሻለ የመረዳት አቅም አላቸው እና።


የተገናዘበ ሕይወት ማለት ውጪውን ከመረዳት በላይ ውጪውን የምንረዳበት እና የምናይበትን መንገድ በጥልቀት ማወቅ ነው። በሌሎች ላይ ለመፍረድ እና ለመጨከን የሚሮጥ ሰው ከፈረደባቸው ሰዎች ስብዕና በላይ ስለራሱ ማንነት ይነግረናል። የተገናዘበ ስብዕና ላይ የደረሰ ሰው በውስጡ የሚርመሰመሱ ስሜቶችን ሁሉ ያለ ማፈር እና መሸማቀቅ እውቅና ይሰጣቸዋል። የዚህ ዓለም ዕይታው እና ነገሮችን የመረዳት አቅሙ ከእነዚህ ከውስጡ ከሚመነጩ የስሜት ውጊያዎች ነጻ እንደማይሆን ይረዳል። ዓለሙን የመረዳት አቅሙ ራሱን በተረዳበት መጠን የተወሰነ እንደሆነ ስለሚያውቅ፤ ሪያሊትን የማወቅ ውስንነቱ ገደብ እንዳለበት ያለጥርጥር ይገባዋል። ለዚህ ነው የሕይወት የፍጽማና አቅጣጫ ለሰው ልጅ በባላንስ ብቻ የሚደረስበት የሚሆነው።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 5 min read

የሰንበት ዕይታ - 16

ree

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አከራካሪ ከሆኑ ነገሮች አንዱ እና የተለያዩ ሊቃውንትም ግራ ከሚጋቡበት ነገሮች ውስጥ ንጹሁ የሆኑ እና ንጹሁ ያልሆኑ ተብለው እንስሳት ለምግበ እስራኤል መለየታቸው ነው። በተለይ በዘፍጥረት ምዕራፍ አንድ ላይ እግዚአብሔር የፈጠራቸው ፍጥረታት ሁሉ መልካም መሆናቸው በይፋ ተገልጾልን፣ ፍጥረቱን እንደሚወድ እና እንደሚመግባቸው በብዙ የመጽሐፍ ክፍል ተነግሮን ሳለ፣ እንደገና ንጹሁ የሆኑ እና ንጹሁ ያልሆኑ ተብለው መለየታቸው እስራኤሎችን ሳይቀር ግራ የሚያጋባ ነው።



ከክርስቶስ ልደት በፊት በግብጽ አሌክሳንደሪያ ብዙ ግብጾች ይኖሩ ነበር፤ በአይሁድ የአመጋገብ ምርጫ የሚደነቁ ሄለናዊያን እና ግሪኮች እነዚህን አይሁዶች ለምን ንጹሁ እና ንጹሁ ያልሆነ ምግቦች በማለት አንዳንድ እንስሳትን እንደማይበሉ ጠይቀዋቸው ነበር። ፋይሎ የሚባል ሊቅ በሰዓቱ ለዚህ ምክንያት ነው ያላቸውን ዘርዝሮ ጽፎ ነበር። የአርስጣጢለስ ደብዳቤ ለአሌክሳንደርም ይሄን ጉዳይ ያብራራል። እውነታው ግን በርግጠኝነት ማናቸውም ምክንያቱን እንደማያውቁት ነው የሚያሳየው።


ይሄ በዘሌዋውያን ምዕራፍ 11 እስራኤል እንዲበሉት ተብለው የተጠቀሱት እንስሶች አንዳንዶቹ በእንደዚህ ባህሪያት ተለይተዋል፤


፩) የተሰነጠቀ ሰኮና ያለውንና የሚያመሰኳውን እንስሳ ሁሉ ብሉ።

፪) በባሕሮችና በወንዞች ውስጥ ክንፍና ቅርፊት የሌላቸው ሁሉ በእናንተ ዘንድ የተጸየፉ ናቸው።

፫) በአራት እግሮቹ ከሚሄድ እንስሳ ሁሉ በመዳፎቹ ላይ የሚሄድ በእናንተ ዘንድ ርኩስ ነው፤

፬) በሆዱ የሚሳብ፥ በአራትም እግሮች የሚሳብ፥ ብዙ እግሮችም ያሉት፥ በምድርም ላይ የሚንቀሳቀሱ ተንቀሳቃሾች ሁሉ የተጸየፉ ናቸውና አትብሉአቸው።


ስለሚበሩ ወፎች የተነገረ መለያ ሕግ ባይኖርም፤ የማይበሉት እንደ ቁራ፣ ዳክዬ፣ ጥንብ አንሳ ተዘርዝረዋል።


በብሉይ ሕግ ስለንጽህና በምግብ ብቻ ሳይሆን በአልባሳትም ተጠቅሷል። ለምሳሌ ሁለት ዓይነት ቀለማት ያሉት ልብስ መልበስ ንጹሁ አይደለም። የሞተ እንስሳ መንካትም እንዲሁ ከንጽህና ያሶጣል። እነዚህን ነገሮች ማድረግ ኃጢአት ነው ሳይሆን፣ ወደ ተቀደሰው ቤት እና ወደ መቅደሱ ለመግባት ግን የመንጻት ሥርዓትን መፈጸም ያስፈልጋል።


አንዱ የሊቃውንት መከራከሪያ እነዚህ ንጹሁ አይደሉም የተባሉ እንስሶች በጣዖት በሚያመልኩ ሕዝቦች ዘንድ የአማልክቶቻቸው ወካይ ናቸው ተብሎ መጠቀሱ ነው ይላሉ። ለምሳሌ በዮሐንስ ራዕይ ሰይጣን በእንቁራሪት ተመስሏል፣ እንቁራሪት ደግሞ ንጹሁ አይደሉም ስለዚህ አትብሏቸው ከተባሉት ነው ወገኑ። ሌላኛው መከራከሪያ ደግሞ ንጹሁ የተባሉ እንስሳት የወገኖቻቸው ወካይ ናቸው፤ ለምሳሌ በውሃ ውስጥ የሚኖር እንስሳ ክንፍና ቅርፊት ከሌለው የአሣን መስፈረት አያሟላም ፥ ስለዚህ ያን ዘር (የአሣን) አጉዳይ ስለሆነ ንጹሁ እንዳልሆነ ይቆጠራል የሚል ነው።



በስፋት በሀገራችን ሊቃውንት ሳይቀር የምንሰማው መከራከሪያ ደግሞ ዝምድና ነው። ለምሳሌ አሳማ ሁሉን የሚበላ፣ የሚከረፋ፣ ሆዳም ስለሆነ ያንን እንደ ኃጢአተኛ እና ከክብሩ እንደተዋረደ ማንነት አድርጎ በምሳሌ በማቅረብ፤ ለመብላት ንጹሁ ያልተባለው ለዛ ነው የሚል ነው። ጥንብ አንሳም ከዚህ ምሳሌ የሚካተት ነው።


ሌሎች ደግሞ ንጹሁ የተባሉት እንስሳት ለፈጣሪ በመሥዋዕት መልክ የሚቀርቡ በመሆናቸው፤ የፈጣሪ ምግብ ናቸው፣ በዚህም ንጹሁ ተባሉ። በተቃራኒው አሳማ፣ ግመል ደግሞ ለመሥዋዕት ስለማይቀርቡ፣ የሰው ልጆችም መብላት የለባቸውም የሚል ነው።


ሌሎች ደግሞ እንደ ጠንካራ መከራከሪያ አድርገው የሚያነሱት ከጤና አንጻር ነው። እንደ እንቁራሪት፣ አሳማ ያሉ እንስሶች ከውሏቸው እና አመጋገባቸው አንጻር ለጤና አደገኛ ስለሆኑ (ሁሉን የሚያግበሰብሱ በመሆናቸው) ለዛ ነው አትብሉ የተባልነው ይላሉ።


እውነት ለመናገር ከላይ የተጠቀሱት ምሳሌዎች እምብዛም አሳማኝ አይደሉም። ለምሳሌ ቀላል የማይባሉ ንጹሁ የተባሉ እንስሶች የክፋት ምሳሌዎች፣ የባዕድ አምልኮ ምልክቶች ነበሩ። በንጽህናም ከወሰድን ፍየል እምብዛም ከአሳማ የሚለይ የአመጋገብ ሥርዓት የለውም። ዶሮም ሁሉን የሚመገብ ነው። ከጤናም አንጻር የሚነሳው ክርክር ውሃ የሚቋጥር አይደለም። አሳማ ከምግባር አንጻር በመጥፎ እና በሁሉ አግበስባሽነት ቢመሰልም፣ በምንም ክፋት የማይመሰሉ እንስሶችም ንጹሁ አይደሉም እና አትብሏቸው ተብሏል። ለምሳሌ ዳክዬ፣ ሎብሰተር፣ ፈረስ እና ሌሎችም። ስለዚህ የክፋት ምሳሌ ናቸው መባሉም አሳማኝ መከራከሪያ አይደለም። ለፈጣሪ ምግብነትም (ከመሥዋዕት አንጻር) ተብሎ የሚቀርበው ምክንያት መሻገር የማይችሏቸው ነጥቦች አሉት። ለምሳሌ ለመብላት ንጹሁ ሆነው ለእግዚአብሔር ግን በመሥዋዕትነት ማቅረብ የማይፈቀዱ እንስሶች ነበሩ። አጋዘን አንዱ ነው። ይበላል ግን አይሠዋም።



ከበሽታ እና ከንጽህና አንጻርም እስራኤሎች የተለየ ጤናማ ሕዝቦች አልነበሩም። ንጹሁ የተባሉ እንስሳትን ብቻ በመብላታቸው ያተረፉት የተለየ የጤና ጉዳይ የለም። ሌሎች በሚጠቁበት በሽታ ሁሉ ተጠቅተዋል። ረዥም ዕድሜ በመኖር በአርኬዎሎጂ ጥናት መሠረት ሩቅ ምስራቆች የተሻሉ ናቸው። እነዚህ ደግሞ በአመጋገብ ባህላቸው ከእስራኤሎች የተለዩ ነበሩ።


አንድ መገንዘብ ያለብን ነገር መጽሐፍ ቅዱስ ንጹሁ እንስሳት እና ንጹሁ ያልሆኑ ብሎ ለመብል ሲከፍላቸው ፈጽሞ ከሰውነት ጤና እና ከረዥም ዕድሜ ጋር እንዳላያያዛቸው ነው።

በዚህ ክርክር ውስጥ እግዚአብሔር ለእስራኤላውን ንጹሁ እና ንጹሁ ያልሆኑ እንስሳት፣ አዕዋፋት እና የባህር እንስሶች ብሎ ሲለይ በምን ምክንያት ነው የሚለውን ከዳሰሱ እና አሳማኝ ሆነው ያገኘውትን ነጥቦች ልዘርዝር፤


1) መገደብን፣ እንቢ ማለትን ማስተማር፤


ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፥ “ሁሉ ተፈቅዶልኛል፥ ሁሉ ግን አይጠቅምም። ሁሉ ተፈቅዶልኛል፥ በእኔ ላይ ግን አንድ ነገር እንኳ አይሠለጥንብኝም።” እግዚአብሔር ሁሉን መልካም አድርጎ ከፈጠረ በኋላ፣ በገነት ውስጥ መታዘዝን፣ የሰውን በፍጥረቱ ውስጥ ያለውን ቦታ እና ከእግዚአብሔር ጋር ያለውን ግንኙነት የምታሳይ ያለመብላት ሕግ አውጥቶ ነበር። ያ ፍሬ በገነት ውስጥ ከነበሩት ፍሬዎች የተለየ ውበት ወይም ማስቀየም እንዳለው የተነገረን ነገር የለም። ሔዋን ለመብላት ስታስብ ፍሬው ያማረ እንደሆነ ከማየቷ በቀር። ይሄ ግን ሌሎቹ የሚበሉ ፍሬዎች ከዛ ዛፍ ያነሰ ውበት ወይም አስጎምጅነት እንዳላቸው ምንም አልተገለጸም። አንድ ነገር ግን ተነግሮናል፣ ያ ዝፍ የሞት ፍሬ መሆኑ። ምክንያቱም እርሱን መብላት ያለመታዘዝ ምልክት ነው። የአመጽ ምሳሌ ነው። በተመሳሳይ ለእስራኤል ንጹሁ እንስሳት ተብለው የተዘረዘሩትን በመስመር ማስቀመጥ እና ሁሉንም በሆነ መስፈረት ማኖር አይቻልም (arbitrariness አለባቸው)። ይሄ የሚነግረን ጉዳዩ ከመብልነት እጅጉን የተሻገረ እንደሆነ ነው።


እስራኤል እንቢ ማለትን፣ ለእግዚአብሔር ሲል መተውን፣ በዚህም ራስን መግዛትን እንዲማር የወጡ ሕጎች ናቸው። የሥጋ ትልቁ ፍላጎት እና ፈተና የሆነውን መብላት በመገደብ ፥ እንቢ ማለትን እና የፍቃድ ጡንቻን ማጠንከርን ለእስራኤል አስተማረው። እስራኤል እነዚህ የኛ ምግቦች አይደሉም፣ ለኛ አይሆኑም በማለት በሕይወት ራስን መገደብን እና ኃጢአት እንኳ ባይሆን ለእኛ የተፈቀደ አይደለም በማለት እንቢ ማለትን በሕይወት እንዲማሩ የተተከለ የፍቃድ (will power) ጡንቻ ማጎልበቻ ናቸው። ለእግዚአብሔር ስንል ምክንያት እንኳ ባይኖረው እንቢ ማለትን እንዲማሩ አደረጋቸው። በዚህም በሕይወት ነገሮች ስላጓጓቸው እና ስሜታቸው ስላሻው ብቻ እንዳያደርጉ ፥ ለምኞታቸው እንቢ የማለትን ጡንቻ ገና በጊዜ እንዲያዳብሩ አደረጋቸው።


የአይሁድ ቤተሰቦች በዚህ ዘመን ሳይቀር ይሄን የምግብ ባህል በጥንቃቄ ይከተላሉ። ተመልከቱ ይሄ ራስን የመግዛት፣ በዚህም የሕይወት ስኬትን የመቆናጠጥ ማንነት ከአይሁድ ዘር በላይ በዚህ ዓለም ማን ምሳሌ ሊሆን ይችላል። የኖቤል ሽልማትን ብቻ ውሰዱ። እስከዛሬ ከ965 የኖቤል ተሸላሚዎች ውስጥ፣ 214 አይሁዶች ናቸው። በአሜሪካ ውስጥ የአይሁድ ቁጥር 2.4% ነው፤ በአሜሪካ ቢዝነስም ሆነ ፖለቲካ ግን 71% ከሚሆነው የነጩ ማህበረሰብ ምንም ያልተናነሰ ተጽዕኖ የአይሁድ ማህበረሰብ ነው ያለው። በዚህ ዓለም ላይ ከቁጥሩ አንጻር የአይሁዶችን ያህል ስኬት የተጎናጸፈ አንድ ዘር መጥራት የሚችል ይኖራል? የትኛውንም የስኬት ሜትሪክሶችን አምጡ እና የአይሁድን ማህበረሰብ አስቀምጡ፤ ይሄ ማህበረሰብ ካለው ቁጥር አንጻር እጅግ አስገራሚ ስኬት የተጎናጸፈ ሆኖ ታገኙታላችሁ።


ማንንም ጠይቁ ፥ ለጊዜያዊ ፍላጎቱ እንቢ ማለት የቻለ ሰው፣ ራሱን መቆጣጠር እና መግዛት የሚችል ሰው በምንም ዘርፍ በመጨረሻ ያሸንፋል። ይሄን ነበር በምግብ እግዚአብሔር ለእስራኤል ያስተማራቸው። በዚህ ሕግ ሕይወታቸውን ሁሉ አበራላቸው። እንቢ የማለትን ማንነት አጸናላቸው።


2) ሥርዓትን ያስተምራል ፦ መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን ላይ “ዓላማ ይዞ እንደ ተሰለፈ ሠራዊት የምታስፈራ ማን ናት?” እንዳለው ጠቢቡ፤ በሕይወት ሥርዓት ያለው ትንሽ ሠራዊት ሥርዓት የሌለውን እልፎች ይረታል። ዛሬም ስለእስራኤላውን ይሄ እውነት ነው። ጎረቤቶቻቸው በቁጥር በስንት እጥፍ እየበለጧቸው፣ ራሳቸውን የለዩ፣ በሥርዓት ማንነታቸውን ያሰለጠኑ በመሆናቸው በእልፍ የሚበልጧቸው በፊታቸው ይርዳሉ። (You develop an ordered soul that says no to certain things).


3) ማንነት ነው ፦ እነዚህን ምግብ እኛ እስራኤላውያን በመሆናችን አንበላም በማለታቸው ፥ ራሳቸውን ሁሉን ከሚበላው ዓለም ለዩ። በዚህም በቁጥር በብዙ እጥፍ ከሚበልጡአቸሁ ጎረቤቶቻቸሁ ማንነታቸውን ጠብቀው ማቆየት ቻሉ።


4) የእግዚአብሔርን ንጽሕ እና ቅድስና የሚያሳይ ነው። ለምሳሌ ሴቶች በወራዊ ልማዳቸው ወቅት ወደ ቅዱሱ ስፍራ ወንዶችም ዘራቸው የፈሰሰ እንደሆነ ወደ እግዚአብሔር መቅደስ እንዳይገቡ በብሉይ ሕግ ተደንግጎ ነበር። ሴቶች ወራዊ ልማዳቸውን ማስቀረት የሚችሉት ነገር አይደለም፤ ስለዚህም ኃጢአት አይደለም። ነገር ግን ወደ ቅድስናው ስፍራ በዚህ ወቅት መቅረብ አይችሉም፤ ለምን? ይሄ የእግዚአብሔርን ቅድስና እና ንጽህና የሚናገር ነው። “እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ነኝና፤ ሰውነታችሁን ቀድሱ፥ ቅዱሳንም ሁኑ፥ እኔ ቅዱስ ነኝና፤ በምድርም ላይ በሚሳብ ተንቀሳቃሽ ሁሉ ሰውነታችሁን አታርክሱ።” ዘሌዋውያን 11፥44። ኃጢአትን አለመስራት አንድን ሰው ቅዱስ አያደርገውም። ቅድስና የዓላማ ተግባር ነው (affirmative action)። ቅድስና መተግበርን ይሻል፣ መራቅን ብቻ አይደለም። አንድ ሰው ኃጢአት መሥራት እየቻለ፣ ስለእግዚአብሔር ብቻ ሲል ከተወ ያ ቅድስና ነው። ምክንያቱም የዓላማ ተግባር ነውና። ቤቱ ውስጥ ምግብ የሞላለት እና ምንም ያልጎደለበት ሰው ላይሰርቅ ይችላል። አለመስረቁ ቅዱስ አያደርገውም። ከመጸወተ ግን ያ ቅድስና ነው። ሰይጣን ስለኢዮብ ያለው ይሄን ነበር። “እርሱ ስለሞላለት፣ ምንም ስላልጎደለበት፣ ዙሪያውንም ከክፍ ስላጠርክለት እንጂ ምንም ጽድቅ የለውም” ነበር ያለው። ሰይጣን ሳይቀር ከኃጢአት መራቅ በራሱ የጽድቅ ምልክት እንዳልሆነ ያውቃል ማለት ነው። እነዚህ ምግቦች ለእግዚአብሔር ሲባል ብቻ መተውን፣ በዚህም መቀደስን የሚያስተምሩ ምልክቶች ናቸው።


በአዲስ ኪዳን እነዚህ ምግቦች ያላቸው ቦታ ግልጽ ነው። በቤተክርስቲያናችንም እንዴት እንደሚታዩ ብጹዑ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የቤተክርስቲያን ታሪክን በጻፉበት መጽሐፋቸው ዳሰውታል።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page