top of page
Search
Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew




ለምንድነው የሶቅራጦስ “ያልተመዘነ ሕይወት እንዳልተኖረ ይቆጠራል ወይም the unexamined life is not worth living” አባባል ከሶስት ሺ ዘመናት በላይ ትርጉም ለሰው ልጅ ውሳጣዊ ልቦና የሰጠው?


ግን ብዙዎቻችን ይሄን አባባል ምን ማለት እንደሆነ አናውቀውም ወይም ልምምዱ የለንም። በሕግ ትምህርት ቤት እያለው ሁለት ሦስት ፕሮፌሰሮቼ ስለዚህ አባባል በተደጋጋሚ ሲነግሩኝ ግራ ይገባኝ ነበር። ሪፍሌክሽን። “ሪፍሌክት አድርግ” ሲሉኝ። እንዴት አድርጌ ነው ሪፍሌክት የማደርገው? ምንድነው እነዚህ ሰዎች እያሉኝ ያሉት? የምን ሪፍሌክሽን?



ሪፍሌክሽን ሳይሆን ዶግማ፣ መመራመር ሳይሆን ማመን፣ መጠየቅ ሳይሆን መታዘዝ፣ ለምን ማለት ሳይሆን እሺ ማለት፣ ፍለጋ ሳይሆን መረጋጋት የማህበረሰቡ እሴት ከሆነበት ሀገር ለፈለቀ ሰው ሪፍሌክሽን እንግዳ ነገር ነው። በዛ ወቅት ከሃይማኖት ልቦናዬ በጣም የራኩበት ዘመን ቢሆንም የአስተሳሰብ መዋቅሬ ግን ሁሌም ሃይማኖተኛ ነበር። ስለዚህ እነዚህ ሰዎች ስለእኔ ሪፍሌክት ቢያደርጉልኝ ራሱ እመርጥ ነበር።



የሰው ልጅ አዕምሮ በተቀረጸበት ማህበረሰብ መነጽር ነው የሚያየው። ከዚህ የዕይታ ግርዶሽ ተሻግሮ ማየት ለሰው እጅግ ፈተኝ ነው። የመኖር እና የመመሳሰል፣ ማህበረሰብ የሚያስቀምጠውን ደረጃ የመያዝ ፍላጎት ፥ ከእንስሳዊ ባህሪው ጋር ማለትም ከሞት ራስን የመከላከል ፍላጎት ጋር ተጣምሮ መጠየቅን ይፈራል። የራሱን አዕምሮ ጭምር ይፈራዋል። የተጠየቅ ቀስቶች ሲወረውርበት በእምነት ማህተም ይመክተዋል። ስለዚህ ሪፍሌክሽን እንዲርቀው ያደርጋል።



ያልተመዘነ ሕይወት እንዳልተኖረ ይቆጠራል ያለው፣ በመጠየቅ አቅሙ የማንንም የእምነት እና ያልተፈተነ ሰንፋፋ የእውቀት ዝናር በቀላሉ የሚያራግፈው ሶቅራጦስ ሳይቀር በዚዎስ ያምን ነበር። ዛሬ ማንም ስላለመኖሩ የማይጠራጠረው ዚዎስ ከሞት በኋላ ለእውነት በመቆሙ እንደሚሸልመው ያምን ነበር። ይሄ በቀላሉ የሚነግረን ሰው ምን ያህል የቆመበትን የፍልስፍና መሠረቶች የመጠየቅ አቅሙ ደካማ እንደሆነ ነው።



ሪፍሌክሽን ከራሳችን እውነተኛ ተፈጥሮ ጋር ለመገናኘት የድልድዩ ጅማሬ ነው። ሩጫን፣ እምነን፣ ግን፣ ዓላማን፣ ተግባን፣ ቃን ከዛም ራን የመጠየቅ እና በጥልቅ የመፈተሽ ከዛም የመታዘብ ልምምድ ነው ሪፍሌክሽን። ብሌዝ ፓስካል እንዳለው “የሰው ልጅ ችግር ሁሉ የሚነሳው ብቻውን በአንድ ክፍል ውስጥ ለመቀመጥ ካለመቻል ነው።” ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድኅን ለዚህ ነው “እንዳይነግርህ አንዳች እውነት አናፋበት ፥ ሸልልበት፤ ሆይ፡ሆይ! በል ጩኽበት፤ ጭንቅላትክን ግዘፍበት ፥ ውቀጥበት ፥ ውገርበት፤ ዝግ ብሎማ ያስብ እንደሁ ፥ ይነግርሃል አንዳች እውነት!” ያለው።



የሰው ልጅ አዕምሮ እንደ እውነት የሚፈራው ነገር የለውም። አዕምሮውን ካሳረፈው ያን እውነት እንደሚደርስበት ስለሚያውቅ፤ በዶግማ፣ በሽምደዳ፣ በመደዴ ትንታኔ፣ በአይዶሎጂ ይሞላዋል። ምክንያቱም ዝግ ካደረገው ያጋፍጠዋል። ያጋፍጠዋል ከባከነው ዕድሉ ጋር፣ ያጋፍጠዋል ከከንቱ እና ከውሸት እምነቱ ጋር። ካልተኖረው የአስመሳይነት መርሁ ጋር። ስለዚህ ያን ከመጋፈጥ ፥ በላይ በላይ ይግተዋል ይሄን መረጃ። ጭንቅላቱን ይገዝፍበታል። አዕምሮውን ከማህበራዊ ሚዲያ እስከ ዜና በሚገኝ ብጣሽ እና ቅራቅንቦ ይሞላዋል። በዚህም ሕይወትን እንደሸሻት ፥ የራሱን ሕይወት ሳይኖር ይሞታል። ለዚህ ነው ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድኅን “እስቲ ለአንድ አፍታ እንኳ ዝም እንበል። አጉል ነው ብለን ሳንፈረድ፣ ድንቅም ነው ብለን ፈጥነን ሳንወድ፣ መንጋነትን አርቀን እስቲ ዝም እንበል። ብቻ ይሄን አለማድረግ ነው ሞት” ይለናል። ዳግመኛ ሞት መሞት ፥ የአዲስ ኪዳን ጨለማ ማለት ይሄ ነው። ራስን ለመፈተሽ ፥ ተረጋግቶ ለማሰብ ፥ ከዛም ለመታዘብ አለመፍቀድ።

327 views1 comment
Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew




“ፍላጎት ገደብ የለውም ፥ ሀብት ግን ገደብ አለው” ወይም “demand is unlimited but all resources are scarce” የሚለው የእንግሊዘኛ ዓረፍተ ነገር የኢኮኖሚክስ ክላስ ሁሉ ሀ ሁ ነው። እጥረት ማለት አንድን ፒዛ ለመቶ ሰው ለማከፋፈል እንደመጣር ነው። በኢኮኖሚክስ እጥረት ማለት ብዙ ሰው የሚፈልገው ነገር በተመጠነ ቀጥር ብቻ ሲኖር ማለት ነው። በተመጠነ ቁጥር ያለ ግን ብዙ ሰው የማይፈልገው ነገር ዋጋው በጣም ዝቅተኛ ወይም ርካሽ ነው። በተመሳሳይ ብዙ ሰው የሚፈልገው ነገር ፥ ግን በብዛት ያለ ነገርም ዋጋው ርካሽ ነው። እጥረት የሰዎችን የመወሰን አቅም ይቀርጻል። ማለትም በሆነ ጊዜ በጣም ያጠረን ነገር ዘወትር ባህሪያችንን ሊመራው ይችላል። ለምሳሌ በልጅነቱ በጣም ደሃ የሆነ እና የተቸገረ ሰው ፥ በኋላ ላይ ገንዘብ ቢኖረውም አላስፈላጊ የሆነ ስግብግብነት ወይም የገንዘብ ስስት ሊያሳይ ይችላል። ምክንያቱም ወደ ዛ ችግር እመለሳለው የሚለው ፍራቻ አሁን ላይ ተትረፍርፎት ቢሆን እንኳ አላስፈላጊ የተጋነነ ቁጠባ ውስጥ ራሱን ሊከት ይችላል።



በሚገርም ሁኔታ ግን እጥረት በራሱ መጥፎ ነው ማለት አይደለም። ይልቁንስ መትረፍረፍ የበለጠ ሊጎዳን ይችላል። በዓለም ላይ በረሃብ ከሚሞተው በላይ በውፍረት ከሚመጣ በሽታ የሚሞት ሰው ይበዛል። የዛሬ አስር ዓመት አካባቢ በነበረኝ የስደተኞች ጉዳይ ጥናት ባህር እየተሻገሩ የሚሰደዱ እና የሚሞቱ ሰዎች ድኇች እንዳልሆኑ የደረስንበት ጥናት ነው። ምክንያቱም በሰዓ ያንን ስደት ለማድረግ ከሰባት ሺ እስከ አስራ አምስት ሺ የአሜሪካ ዶላር ያስፈልግ ነበር። ያ ገንዘብ የኢትዮጵያ ድሃ ኖሮት አያውቅም። ስለዚህ ድህነትን ተላቀው የወጡ ሰዎች ነበ ይሄን ስደት የሚመርጡት። ምክንያቱም ሀብታም ለመሆን። ድህነትን ለማምለጥ ሳይሆን።


የብዙ ስህተቶች ምንጭ ከእጥረት በላይ መትረፍረፍ ነው።



የዚህ ጹሁፌ ዓላማ በዚህ የኢኮኖሚክስ ጽንሰ ሀሳብ ላይ አተኩሬ መጻፍ አይደለምይልቁንስ እንዴት እጥረትን እኛ መጠቀም እንደምንችል እና እኛ ራሳችን እጥረት መሆን እንደምንችል ማሳየት ነው።


እጥረት የፈጠራ ምንጭ ነው። የገንዘብ እጥረት ነው ለብዙ መፍትሔዎች መሰረት። ነጋ የሆነ ነገር እንደምናጣ ስናስብ ነው ሰውን በአግባቡ መጠየቅ፣ መልካም መሆን የምንጀምረው። ነገ ገንዘብ ሊያጥረን እንደሚችል ስናስብ ተጨማሪ ሙያ መማር እንጀምራለን። ነገ ብቸኛ ልንሆን እንደምንችል ስናስብ እና ስንሰጋ ወደ ትዳር፣ ልጅ ወደ መውለድ ወዳጆቻችንን ወደ መጠየቅ እንገባለን። እጥረትን በሆነ መጠን ስንቀምሰው ወዲያው ባህሪያችንን መቀየር እንጀምራለን። ጤና የተትረፈረፈ ነገር እንዳልሆነ የምናውቀው የጤና እጥረት ሲገጥመን ነውከዛ ስለጤናችን ማሰብ፣ ጥሩ ምግብ መብላት እና ስፖርት ወደ መስራት እንሄዳለን። “በእጅ ያለ ወርቅ እንደ መዳብ ይቆጠራል" እንላለን። ሁልጊዜ ከእኛ ጋር ያሉ ሰዎች ድንገት ሲለዩን ፥ እነሱ በሕይወት እያሉ ያሳየነው መዘናጋት እንደ እግር እሳት ይለበልበናል። ብዙ ሰው ግን በመትረፍረፍ ውስጥ እንዴት መኖር እንደሚቻል አያውቅም። ስለዚህ እጥረትን እስከሚቀምስ ድረስ ማሰብ አይችልም።



በተያያዘ ደግሞ እጥረት ያላቸው ነገሮች እና ሰዎች የሚፈልጉት ነገር ዋጋው ውድ ነው። ለምሳሌ ወርቅን ተመልከቱ። በየቦታው እንደ ልብ ያለ ቢሆን በዚህ ደረጃ ዋጋው አይወደድም ነበር። እጥረት ነው ዋጋውን ያስወደደው። ለዚህ ነው አንዳንድ ኩባንያዎች ምርታቸውን በጣም ትንሽ ብቻ በማድረግ ዋጋውን ሰማይ ይሰቅሉታል። ለምሳሌ እንደ ሬንጅ ሮቨር ያሉ መኪኖች ከቶዮታ አንጻር ጥንካሬያቸው እና የመገልገያ ዘመናቸው በጣም ያነሰ ቢሆንም ኩባንያው ግን በጣም ትንሽ ቁጥር ያለው ሬንጅ ሮቨር በማምረት ፥ ዋጋውን ሰማይ ይሰቅሉታል፤ በዚህም የክላስ ጉዳይ ያደርጉታል። ይሄ ለሰውም ይሰራል። እጅግ ጥሩ እና መልካም ብትሆኑንም ዘወትር ካላችሁ፣ በቀላሉ የምትገኙ ከሆነ ግን ሰዎች ዋጋችሁን ዝቅ ያደርጉታል። ሁሌ እንደምትገኙ ካሰቡ ላቀረባችሁት መልካምነት የሚሰጡት ዋጋ እጅግ ዝቅተኛ ይሆናል።



ለዚህ ነው እጥረት በራሱ መጥፎ ያልሆነው። ለምሳሌ ታማኝ ናችሁ፣ በዚህ ላይ ጠንካራ ሰራተኛ እና እጅግ ስማርት ናችሁ እንበል። በዚህ ዓለም ላይ እነዚህን ሦስት ባህሪዎች ገንዘብ ያደረገ ሰው በጣም ጥቂት ነው። ታማኝ ሰው ስታገኙ ሥራ አይችልም። ነገር አይገባውም። ነገር የሚገባው ብሩህ አዕምሮ ያለው ሰው ስታዩ ደግሞ ጥቂት ጠጋ ብላችሁ ስትፈትሹት ጠንካራ ሰራተኛ አይደለም። ወይም ታማኝ አይደለም። ስለዚህ እነዚህን ሦስት ማንነቶች ታማኝነትን ከብሩህ አዕምሮ ጋር ፥ ብሩህ አዕምሮን ከትጋት እና ዲሲፕሊን ከሆነ ሰራተኝነት ጋር አዋህደን ከያዝን በዚህ ዓለም ላይ መቼም ሥፍራ አናጣም። የኛ ዋጋ ሁልጊዜ ከፍ ያለ ነው። እንደ እንቁ ውድ ነን። በአንድ ነገር ላይ ምርጥ መሆን ብቻ አይደለም ግን ብዙ ነገሮችን አዋህዶ መያዝን እንጂ። ለዚህ ነው “እጥረት እንሁን” ያልኩት። ምርጥ አይደለም፤ የማንተካ እንሁን። የኛ መጉደል ትልቅ ክፍተት የሚፈጥር ይሁን። ያን በተንኮል ሳይሆን በብቃታችን እንፍጠር። የኛ መጉደል በነካነው ቦታ ላይ ሁሉ በጎ ትውስታን የሚፈጥር ከሆነ የዛኔ እጥረት ነን ማለት ነው።



ጻድቁ ኢዮብ እጥረት ነበር። ፍጹምና ቅን፥ እግዚአብሔርንም የሚፈራ፥ ከክፋትም የራቀ ነበረ። እነዚህን ሦስቱንም የሆነ ሰው አልነበረም። ፈሪያ እግዚአብሔር የሌላቸው ግን ቅን ሰዎች አሉ። እግዚአብሔርን የሚፈሩ ግን ከክፋት መራቅ ያልቻልን አለን። ኢዮብ ግን እጥረት ነበር። ሦስቱንም አካቶ የያዘ።



እጥረትን በጥልቀት እናስብበት። ለኛ ጥቅም እናውለው። በእጥረት ግን እንዳንነዳ እንጠንቀቅ። ምክንያቱም አንዳንድ እጥረቶች የውሸት፣ ሆን ተብለው የተፈጠሩ ወይም አሁን ላይ የሌሉ ናቸው።

349 views0 comments
Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew



አልበርት አንስታይን የህሊና አድማስ (ኢማጅኔሽን) የሌለው ሰው እና የሞተ ሰው እኩል ነው ይል ነበር። የእናንተን አላውቅም የእኔ አዕምሮ ግን በሆነ ነገር ላይ ሲመሰጥ ራሱን የዛ አካል አድርጎ በምልዓት ጠልቆ ይገባል። በዚህ ሳምንት በትንቢተ ኢሳይያስ ምዕ 6 ከቁጥር 1 ጀምሮ ያለው ታሪክ የህሊና አድማሴን ይዞት ሄዷል።



 ረጅሙ እና ከፍ ያለው ዙፋን ላይ የተቀመጠው አምላክ። ፍጹም አስፈሪው ግን ፍጹም ውበት ያለው፤ ያ የተፈራው ዖዝያን ከሞተ በኋላም እርሱ ግን በረዥሙ እና ከፍ ባለው ዙፋን ላይ ተቀምጧል። ይሄን የሚናገረው ስለዙፋን እና ንጉሶች እነሱን በማገልገል እውቀት የነበረው ነቢዩ ኢሳይያስ ነበር። ከዛ ትልቁ እና ውቡን ዝማሬን ሰማ። “ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ” የሚለውን። እንደሚዳሰስ ፍቅር፣ እንደሚነካ የምህረት ፏፏቴ አምላካቸውን በማየት የረኩ ከልብ ደስ ብሏቸው “ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ” እያሉ ከዙፋኑ ሥር ወደቁ። ፍጹም ፍቅር ያለበት ግን ፍርሃት ያልተለየው ያ ምስጋና።



“የመድረኩም መሠረት ከጭዋኺው ድምፅ የተነሣ ተናወጠ።” ይሄ ክብር የሰው ልጅ ክብር ነው። ነቢዩ ይሄን ሲያይ የጠፋ ነበር የመሰለው። ነገር ግን ከሱራፌልም አንዱ እየበረረ ወደ እርሱ መጥቶ ፥ የዚህ ደስታ አካል እንዲሆን ተመኝቶ በፍሙ አነጻው።


ተመሳሳይ ደስታ የምናየው በራዕይ ላይ ነው። ራዕይ ምዕ 4። ሃያ አራት ሽማግሌዎች ዙፋኑን ከበውት ፥ ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ የሚለውን የምስጋና ጅረት ሲሰሙ ወድቀው “አንተ ሁሉን ፈጥረሃልና ስለ ፈቃድህም ሆነዋልና ተፈጥረውማልና ክብር ውዳሴ ኃይልም ልትቀበል ይገባሃል።” ይሉታል።



ይሄ ውበት፣ ይሄ ሞገስ፣ ይሄ ከፍታ የሰው ልጅ የሕሊና አድማስ ነው። ይሄን የውበት ወንዝ እየሳልን ፥ የተጠራነው ከዚህ ፍጹም ሞገስ ጋር አንድ ለመሆን እንደሆነ እንድናውቅ ነው።



ሲ ኤስ ሉዊስ “ሰይጣን ሥርዓት ያለው ዘፈን ሳይቀር ይረብሸዋል” ይላል። እስቲ ሂዱ እና እነዚህ ሰማያዊ መዝሙሮችን ተመልከቱ። ስሜት አልባ እኮ አይደሉም። ድምጽ፣ እሳት፣ ነጎድጓድ አላቸው። ግን ደግሞ ፍጹም ሥርዓትም አላቸው። የመሬት መናወጥ አላቸው ግን ረጋ ብሎ መደፋት እና ሞገስ እና እርከንም (hierarchy) አላቸው። ዙፋኑን የከበቡበት መንገድ፣ ቤቱ በጢስ መሞላቱን ስታዩ ምን ያህል ሕይወት ያለው መዝሙር እና የዛ አካል መሆንን የሚያጓጓ እንደሆነ ታያላችሁ። በተቃራኒው የትህትናው ብዛትን ተመልከቱ። ዓይናቸውን፣ እግራቸውን እየሸፈኑ ግን ደግሞ እየበረሩ የሚያመሰግኑ ነበሩ። ት ህትና ብቻ ነው ወደ ላይ ከፍ የማለት ክንፍ ያለው። ራሱን የሚሸፍን ብቻ ነው የተገለጠውን የሚያየው። ግን ደግሞ ባዶን ነገር መሸፈን አይቻልም። የእውቀት ዓይኖች ፥ የጽናት እግሮች ሲኖሩን ብቻ ነው የሚሸፈን ነገር የሚኖረን። መኖሩ የታወቀ ገንዘብ እንደሚበዘበዝ፣ እንደሚመነዘር ፥ የተደበቀው ግን ወደ በለጠው ክብር ይበራል።



ዙፋኑ ያን ትህትና በሚያሳይ መልኩ ነበር የተዘጋጀው። ረጅም እና ከፍ ያለ ነበር።



ሲ ኤስ ሊዊስ “እንስሳት መሆናችንን ማስረሳት ነው የሰይጣን ተልዕኮ” ይል ነበር። ማለትም ትህትና ዝም ብሎ የሚመጣ ነገር ይመስለናል። በፍጹም። ትህትና በየቀኑ ትንሽነታችንን በሚያስታውስ ነገር ራሳችንን ካልከበብን እየራቀን ይሄዳል። ከድንኮች ጋር ከዋልን ከትዕቢት ውጪ አማራጭ የለንም።



 ሌላ ደግሞ ሽማግሌዎችን እዩአቸው። በዘመን አርጅተዋል። በልምድ ሸብተዋል። ከዚህም የተነሳ ነጭ ለብሰው፣ ከወርቅ የተሰራ አክሊል አጥልቀው እንዲቆሙ ሳይሆን እንዲቀመጡ ነበር የተፈቀደላቸው። ነገር ግን የዙፋኑ መሠረት ኃያል በሆነ ድምጽ ሲመታ እና የምስጋናው ድምጽ ሲሰማ እነዚህ ሃያ አራት አባቶች በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ፥ የሰው ልጅ ቋንቋ የማይገልጸው ውበት ለተላበሰው ወደቁ ፥ ተንበርክከውም ፈቃዱን አደነቁ።



ሥርዓት፣ ሕይወት ያለው ምስጋና፣ ፍጹም ትህትና፣ ንጽህና እንዴት ባለ ገመድ ተሳስረው በሰማያዊው ቤተመቅደስ እንደተገለጡ ተመልከቱ። በዚህ ምድር ላይ እነዚህን ነገሮች ገንዘብ ያደረገ ተቋም የማይበገር ነው። ሥርዓት ያለ ሕይወት (passion) ድብርትን ይጋብዛል። ስሜት (passion) ያለ ትህትና ውድቀትን ይስባል። ንጽህና ደግሞ የዚህ ውበት እና ደስታ ተካፋይ እንድንሆን ያደርጋል። አካል፣ ተካፋይ እንድንሆን ያደርገናል። ይሄን አዕምሮዬ ተመሰጠበት። ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ ፥ የሚለው ዖዝያንም ሞቶ ይቀጥላል። ሃያ አራቱ ሽማግሌዎች በፊቱ ወድቀው ፥ አክሊላቸውን ለርሱ አኖሩ።



በመጨረሻም ዖዝያን ይሞታል። ግድ የላችሁም ፥ እርሱን ግን ነገም በዛ ረዥም እና ከፍ ባለ ዙፋኑ ላይ እናየዋለን።

371 views0 comments

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page