top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 3 min read
ree

በዚህ ሰሞን ሁለት ታላላቅ አሜሪካውያን ሞተዋል። አንደኛው የአሜሪካ ቢዝነስ ላይ ኃያል ተጽዕኖ ያሳደረ ሲሆን፣ ሌላኛው ደግሞ የ12 የአሜሪካ ፕሬዝዳንቶች የውጭ ጉዳይ እና የብሔራዊ ደኅንነት ፖሊሲ አማካሪ የነበረ ነው። ቻርሊ መንገር በ99 ዓመቱ ሲሞት፣ ሄነሪ ኪሲንጀር በ100 ዓመቱ ሞቷል።


በኖሩበት ዘመን ልክ ተጽዕኖ የፈጠሩ፣ በተሰማሩበት መስክ አስገራሚ ለውጥ ማምጣት የቻሉ ናቸው። ሕይወታቸው እስከሚያልፍ ድረስ ሰዎች የሚሰሟቸው ነበሩ። ሌላኛው አሜሪካዊ ሙሁር ናሲም ታሌብ ስለቻርሊ እና ኪሲንጀር ሲናገር “አንደኛው ወደ ገነት ሌላኛው ወደ ሲዖል እንደሄዱ የታወቀ ቢሆንም፣ ሁለቱም ግን በዚህ ዓለም ቆይታቸው በሚያዋዥቅ ሙሁራዊ እንቅስቃሴ (athletic activities) ጊዜያቸውን አላጠፉም” ይላል። ከሁለቱም የምንማረው ነገር ቢኖር፤ እኛ ኢትዮጵያውያን በከፍተኛ ደረጀ የጎደለን ነገርን ነው። አንድን ነገር አድምቶ የመረዳት እና ከሥር መሰረቱ የማወቅ፣ ከዛ ሰው ወደደን ጠላን ለሚል ጊዜያዊ ሁካታ ሳይሆን ፥ በጽንአት በዛ አቋም መቆምን ነው። ማለትም ለጊዜያዊ ትክክለኝነት ስንል፣ ከጥልቀት ምርምር እና መረዳት በኋላ የያዝነውን አስተሳሰብ አለመለወጥ። ለዘላቂ ጥቅም ጠላት የሆነ አንድ ነገር አለ፣ ሕዝባዊነት ነው። ለጊዜው ሞኝ እና ስህተተኛ ሆኖ ለመቆጠር ያልደፈረ ሰው፣ ለረጅም ጊዜ የሚዘልቅ ግብን ማሳካት አይቻለውም። ቻርሊም ሆነ ኪሲንጀር በተሰማሩበት ሕይወት እንደዛ ነበሩ።



 ለዛሬ እ.ኤ.አ በሜይ 2023 ዓ.ም. ዋረን በፌት እና ቻርሊ መንገር ከበርክሸር ኢንቬስተሮች ጋር ባደረጉት የሁለት ቀን ስብሰባ ወቅት ከተናገሩት እና በጊዜው ለጥቂት ወዳጆቼ ያጋራውትን አጋራችኋለው። ከድንቁ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ አሳቢ ኪሲንጀር ደግሞ አንድ ከአገራችን ወቅታዊ ሁኔታ ጋር የሚመሳሰል የተናገረውን ነጥብ በቁጥር ዘጠኝ ላይ አክያለሁ። መልካም ንባብ።

ዋረን በፌት 92 ዓመቱ ሲሆን ፥ ቻርሊ መንገር ደግሞ 99 ዓመቱ ነው። ሁለቱም ከ20ዎቹ ዓመታቸው ጀምሮ ኢንቬስተሮች ሲሆኑ ፥ ከ50 ዓመት በላይ ቢሊየነር የሆኑ ጥቂት አሜሪካኖች ውስጥ በመጀመሪያው ረድፍ ስማቸው የሚቀመጥ ነው። ቻርሊ እና ዋረን በርክሽርን (ኮካ ኮላ እና አፕል ስልክን ጨምሮ ትልልቅ ኢንቨስትመንቶች ውስጥ የአንበሳው ድርሻ የያዘ ድርጅት ነው) በሚመሩበት ወቅት፣ ድርጅቱ 2,000,000% መነሻ ኢንቨስትመንቱ ላይ መመለስ ችለዋል። ትላንት ካነሱት ወሳኝ ነጥቦች ፥ በሕይወት እነዚህን ካደረጋቹ ስኬታማ ትሆናላችሁ ብለዋል፤


1) ወጪያቹ ከገቢያችሁ ማነስ አለበት። ቀሪውን ገንዘብ በጥንቃቄ ኢንቬስት አድርጉት፣


2) ከልጅነቴ ጀምሮ የተማርኩት ነገር በሕይወት የሚመጡልኝ ጠቃሚ ዕድሎች ጥቂት እንደሆኑ ነው፣ ጥበቡ እነዚህን ጥቂት ዕድሎች እንዳያመልጡን መዘጋጀት ላይ ነው። ይሄን የኢንቨስትመንት ካውንስል ላይ ሲናገሩ አትሰሟቸውም፣ እነሱ የሚመስላቸው ሚሊዮን ነገሮችን በማጥናት ሚሊዮን ነገሮችን ማግኘት የሚቻል ነው።


3) በየዕለቱ ከመተኛታችሁ በፊት የዛ ቀን ስትነሱ ከነበራችሁ እውቀት ትንሽ አዋቂ ሆናችሁ ለመተኛት ቁረጡ፣ ኃላፊነታችሁን በታማኝነት እና በጥሩ ሁኔታ ተወጡ።


በዚህም ሲስተማቲካሊ ወደፊት ትጓዛላችሁ፤ የግድ በፍጥነት ላይሆን ይችላል። ነገር ግን ይሄን በማድረጋችሁ ጠንካራ ሥነስርዓት (discipline) ስለምትገነቡ ወደፊት በፍጥነት መስፈንጠር ትችላላችሁ። በየቀኑ አንድ እርምጃ ወደፊት ተጓዙ፣ ቀን በቀን ለማደግ ሞክሩ፤ በመጨረሻ ረዥም ዕድሜ ከኖራችሁ በሕይወት የሚገባችሁን ነገር አታጡም። (ቻርሊ ከፈጣን ዕድገት ይልቅ ሰውን ወደ ግቡ የሚያደርሰው ዝግ ያለ ግን የማይቆም ዕድገት ነው የሚል ፍልስፍና አለው። ሲ ኤስ ሉዊስ ስለሰይጣን ስትራቴጂ ሲናገር “የሰውን ልጅ በርግጠኝነት ሲዖል ማስገባት የሚቻለው በፈጣኑ የክህደት ሃዲድ ሳይሆን፣ ዝግ ብሎ በሚሄደው የክህደት መስመር ነው” ይላል። በርግጥስ ከጥንቸል ይልቅ የአሸነፈችው ያለማቋረጥ ግን ደረጃ በደረጃ የተጓዘችው ኤሊ አይደለች። ዊንስተን ቸርችል ስለአሜሪካ ሲናገር “ቶሎ ለውጥን አይቀበሉም ነገር ግን ሁልጊዜ ትክክለኛው ነገር ላይ ይደርሳሉ” ይላል)።


4) ሰዎችን በፍጹም አትውቀሱ ፥ ሰውን ሳትወቅሱ ጥፋታቸውን ማሳየት ትችላላችሁ፣(የከፍተኛ ትምህርት ዘይቤ በሚለው መጽሐፋቸው ሊቁ እጓለ ገብረዮሐንስ፤ “አንድን አሮጌ ቤት አሮጌ ሳትሉ ማርጀቱን መግለጽ ትችላላችሁ” ይላሉ። “ይሄም አጠገቡ አዲስ ቤት በመገንባት ነው። የዛኔ ያንተን አዲስነት፣ የዛን ቤት አሮጌነትም ይናገራል” ይላሉ። “ነቢይ እና ሕጻን ነው በቀጥታ ሰውን የሚወቅሱት። እኔ ደግሞ ሁለቱንም አይደለውም” ይላሉ ሊቁ። ቻርሊ እና ዋረን የሚሉንም ተመሳሳይ ነው)።


5) በሕይወታችሁ መርዛማ ሰዎችን በፍጥነት አሶግዱአቸው (ተንኮልን እወቁ ግን ተንኮል አትስሩ ፥ የጥፋተኝነት ስሜት እንዲሰማችሁ አድርገው ሊበዘብዟችሁ ያሉ ሰዎችን በተቻለ መጠን ከሕይወታችሁ በቶሎ ቆርጦ መጣል ወሳኝ ነው።)


6) በሞታችሁ ጊዜ እንዲነበብላችሁ የምትፈልጉትን ከአሁኑ ጻፉ (obitury) እና በዛ መሰረት ኑሩ። ያኔ በየቀኑ በጥበብ ታድጋላችሁ።


7) ዕዳ ውስጥ ፈጽሞ አትግቡ ፥ አንዴ ከገባችሁ መውጫ የለውም ምን አልባት ቤት መግዛት ላይ በዕዳ ልታደርጉት ትችላላቹሁ ከዛ ውጪ ግን ፈጽሞ።


8. የምታደርጉትን ሁሉ ይሄን ነገር በየቀኑ እያደረኩኝ ብቀጥል የዛሬ አስር ዓመት የት ያደርሰኛል ብላችሁ ጠይቁ። ያኔ ነው ዛሬ ላይ ደደብ የሆነ ነገር ከመስራት የምትቆጠቡት። በሁሉም ነገር የረዥም ጊዜ እይታ ይኑራችሁ።


9) ኪሲንጀር ከጎቴ (Goithe) አዘውትሮ የሚጠቅሰው አባባል አለው፣ “በፍትሕ እና በሥርዓት (order) መካከል ምርጫ ቢሰጠኝ፣ ሥርዓትን ነው የምመርጠው። ምክንያቱም አንዴ ሥርዓት አልበኝነት ከነገሰ ለፍትሕ ቦታ የለውም። (ኪሲንጀር በዚህ ሳምንት ቢሞትም ይሄ አባባሉ ግን በዓብይ ኢትዮጵያ ዛሬ እየኖርነው ነው። ሰው “ምን ነው ሁሉ ነገር ቀርቶብኝ በሰላም ወጥቼ በሰላም በገባው” እያለ ነው፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ መሞቱ ብቻ አይደለም ዛሬ ያማረረው። ገዳዩ መብዛቱ እንጂ። አንድ ገዳይ ቢቻ ቢኖር ያን መንግስት ብሎ ይታዘዝለት እና የሚፈልገውን ያህል ይገብርለት ነበር። ሥርዓት አልበኝነት ባለበት ፍትሕ ሆነ ዲሞክራሲ ቅንጦት ናቸው። ሥርዓት ባለበት ግን ቢያንስ ቢያንስ የተገደበ ፍትሕ በርግጠኝነት አለ)።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 6 min read
ree

የዶ/ር ተቀዳ የተፈጸሙት ትንቢቶች እና እንዳይፈጸም መጸለይ እና መሥራት ያለብን ቀሪው ትንቢት

መምርህ ብርሃኑ አድማስ ሰው በእውነተኛ እውቀት ሲያድግ ከእውነት (ከእግዚአብሔር ጋር) ይገናኛል ፥ ካዛ በፊት የማያውቀው ከሆነ ይላል። ዶ/ር ተቀዳ እንደ እኔ ያ የእውቀት ማማ ላይ የደረሰ ሰው። ዶ/ር ተቀዳ ሁላችን በዓብይ እና ተከትሎት በመጣው ለውጥ ስናብድ፣ ሀገርን ያለአስተዋይ የማይተዋት አለና፣ እምብዛም ለሕዝብ የሚውል ነገር የማይጽፈው እውነተኛው ሙሁር ብዕሩን አነሳ። ለጹሁፍ ርዕስ የከበደችው የዓብይ ኢትዮጵያ ሙሁሩንም አስጨነቀችው መሰለኝ ረዥም ርዕስ ሰጠው ለዚህ ረዥም ጹሁፍ። “የዛሬይቷ ኢትዮጵያ እንቆቅልሽ --- የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ --- ለኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ እና የሀገራዊ ደኅንነት ፍኖተ ካርት ፍለጋ --- የሚል ርዕስ ሰጠው ለዛ ረዥም ማስጠንቀቂያ ጹሁፍ።



በኢትዮጵያ ታሪክ እንደዚህ ዓይነት ከፍተኛ ቅቡልነትን ይዞ፣ ከጫፍ እስከ ጫፍ አስደማሚ ድጋፍ ይዞ የተነሳውን ሰውዬ ፥ “ድንቅ ነው ያገኘኸው ድጋፍ፣ ይሄ ልዩ ነው ግና ተጠንቀቅ፣ የሕዝብ ድጋፍ እንደሸንበቆ ነው ፥ ዘላለም አይቆይም፤ አረ ዘላለም አይደለም ብዙም አይዘልቅም” አለው። አንዳርጋቸው ጽጌ የለ፣ ሻለቃ ዳዊት የለ፣ ዮናስ ብሩ (ኮኪ አቤሴሎም) የለ፣ መስፍን ነጋሽ ወይም አብይ ተክለማርያም፣ ታደሰ ብሩ የለ ኮነሬል ጎሹ ወልዴ፣ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም የለ “ኢትዮጵያ ሆይ ደስ ይበልሽ ፥ ከፈርዖን ቤት አሻጋሪሽን ሙሴሽን አገኘሽ” ሲሏት ፥ ዶ/ር ተቀዳ ግን ንጉሱ ራቆቱን ሊሆን ይችላል አለን።



ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የማነባቸውን ነገሮች በጣም እየተጠነቀኩኝ ነው፤ ጊዜ ካልተረፈኝ በቀር ስለአሁን ሁኔታ የሚተነትኑ የፖለቲካ ጹሁፎችን እያሶገድኩኝ ነው። በተቻለ መጠን የአሁንን ሁኔታ ለመረዳት የዛሬ አስር እና ሃያ ዓመት ተጽፈው አሁን ድረስ መነጋገሪያ የሆኑ ጹሁፎችን እና መጽሐፎችን ነው አንስቼ የማነበው። የምጽፈውንም ነገር ስጽፍ ይሄን የምጽፈውን የዛሬ አስር እና ሃያ ዓመት አንድ ሰው ቢያነበው ምን ያህል ትርጉም ይሰጣል ብዬ በማሰብ ነው። የዶ/ር ተቀዳን ጹሁፍ እንደወጣ ነበር ያነበብኩት። የሙሴ ተከታይ ነበርኩና፣ ምንም እንኳ ምን ዓይነት ኢንቴሌክቿል ካሊበር እና ስብዕና ያለው ሰው መሆኑን ባውቅም ፥ ለውጡን ግን እንዲነካብኝ አልፈለኩም። ስለዚህ ከምር ሳልወስደው ቀረው።



ከጠንካራ ንባብ ዘወር ማለት ስፈልግ ወደትዊተር መንደር ስሄድ በመሐመድ ኡመር የተጻፈውን እና በፎሬን ፖሊሲ ድረገጽ ላይ የወጣውን ጹሁፍ አገኘውት በዚህ ሰሞን። “ኢትዮጵያ እና ኤርትራ ወደ ጦርነት እየሄዱ ነውን?” ይላል መሐመድ፤ አካባቢውን በጥልቀት የሚያውቀው እና የኤርትራ ነጻነት ግንባር የቀድሞ አባል የነበረው መሐመድ፤ ይሄ ጹሁፍ አዲስ መረጃ ባይሰጠኝም፤ ተቀዳን ግን አስታወሰኝ። ዶ/ር ተቀዳ የኖቤል ፕራዝ ኮሚቴ አብይ ከኤርትራ ጋር ለፈጠረው ሰላም በሚል እ.ኤ.አ. በዲሴምበር 2019 ሽልማት ሳይሰጠው በፊት ፥ “ሁለቱ ሀገሮች ድጋሚ ወደ ጦርነት ወይም ወደነበሩበት የቁርሾ ሁኔታ የሚገቡበት መንገድ ዝግ አይደለም!” ብሎ ነበር የመከረው።


ሁለተኛ ትንቢት መሆኑ ነው። የመጀመሪያው “ይሄ የሕዝብ ድጋፋ ይከስማል” አለው፤ “አረ እንደውም ብዙም አይቆይም” አለ። በኢትዮጵያ ታሪክ በዚህ ደረጃ ተደግፎ የማያውቀው ሰውዬ በኢትዮጵያ ታሪክ እንደሱ ተጠልቶ ወደማያውቅ ደረጃ በፍጥነት እየደረሰ ነው (እስካሁንም ካልደረሰ)። ዶ/ር ተቀዳ ሁለተኛ ያለው የኢትዮጵያ እና ኤርትራ ጦርነት ትላንት የተነሳው በአንድ እና አንድ ምክንያት ብቻ ነበር። ግንኙነቱ የሁለት ሀገሮች ግንኙነት ሳይሆን የሁለት መሪዎች፣በዛ ቢባል የሁለት ፓርቲዎች ስለሆነ ነበር። ሰዎች ደግሞ ተቋሞች አይደሉም፤ ለራሳቸው በማይገነዘቡት ሁኔታ ጠዋት ከተፋቀሩት ጋር ማታ ተጣልተው ያድራሉ፤ ስለዚህ ከትላንት ካልተማርን ታሪክን እንደግማለን አለን። ደገምን። መድገም የማይሰለቸን እኛ። ዳንኤል ክብረት 70 ዓመት ይብቃችሁ ብሎ ዲያስፖራዎችን በሚገርም እውነት ተችቷል በዚህ ሰሞን። ዳንኤል ምን አልባትም ዓብይ ከመጣ በኋላ የጻፈው ምርጥ እና ትክክለኛ ጹሁፍ ይሄ ብቻ ይመስለኛል። ዳንኤል ግን እንደዛች ዝንጀሮ በመስታወት ውስጥ ያየው የዲያስፖራን የ70 ዓመት ውድቀት እንጂ ለእኛ የደብተራዎች የ2000 ዓመት ውድቀት እንዴት ኩልል ብሎ እየታየን መሆኑን ዘንግቶታል። ሀገሬ ለሺ ዘመናት እየደጋገመች ከትላንት ስህተት መማር ተስኗት እንድትወድቅ ያደረጋት የዳንኤል ክብረት ዓይነት ሰው የሀገሪቷ መሪ መቀመጫ ሥር ገብቶ፥ ለክርስቶስ መስቀል እና ለቤተክርስቲያን ያለንን እምነት ለቤተመንግስት እንድንሰጥ የበዘበዙን ደብተራዎች በመብዛታቸው እንጂ 70 ዓመት ያስቆጠረው ዲያስፖራ አይደለም።


ዲያስፖራው ስህተት የለበትም እያልኩኝ አይደለም፣ በዛማ ከዳንኤል ክብረት ጋር 100% በተጠጋ መጠን እስማማለሁ፤ ግን ለሺ ዓመት ውድቀት የአክሱም ላሊበላ ስልጣኔ ዕምብርት የነበረችውን ሀገሬን የ፸ ዓመት ዕድሜ ብቻ ያለውን መክሰስ የደብተራነት የንጉሱን ፊት እያዩ የመጻፍ አባዜ ነው። ያ ነው የሀገሬ ገዳይ፤ ያ ነው ኢትዮጵያችንን ደጋግሞ የጣላት። የደብተራነት አድርባይነት። ንጉሱ ራቆቱን ሳለ ለመስቀሉ የሰጠነውን እምነት ራቆቱን ለቆመው ንጉስ እንድንሰጥም እምነታችንን የበዘበዙት የደብተራዎች ሴራ ነው የሀገሬ አንዱ የመክሸፍ ምስጢር። (ብዙ ሰዎች ደብተራዎች ሲባል የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ነው የሚመስላቸው። እውነት ለመናገር ቤተክርስቲያኒቷ ነች ሀገራችን እስካሁን ሳትጠፋ እንድትቀጥል የረዳቻት። በዚህ ጹሁፍ ድብተራዎች የምላቸው የቤተክርስቲያንን እውቀት እና ያገኙትን ትምህርት እውነትን ለማገልገል ሳይሆን የገዢዎች ፍላጎትን ለማርካት ያዋሉትን ነው። ደብተራዎች በቀደመው ጊዜ ከቤተክርስቲያን ነበር የሚወጡት ብቸኛዋ የትምህርት ማዕከል ስለነበረች፤ አሁን ግን እነዚህን intellectual prostitutes እንላቸዋለን።)



ቢያውቀው ዶ/ር ተቀዳ ነበር የዓብይ እውነተኛ ወዳጅ። ይሄ የሕዝብ ድጋፍ ራስህን ልዩ አድርገህ እንድትቆጥር ይፈትንሃል፤ በአግባቡ ከተጠቀምክበት ግን ማለትም በግልጽነት እና በጥበብ ተቋሞችን ለመገንባት ከተጠቀምክበት ኢትዮጵያን ወደ ዲሞክራሲ፣ ወደ ተረጋጋ ሰላም እና ዘላቂ ልማት መውሰድ ትችላለህ አለው (“If this asset is used properly, transparently and wisely—which, among other things, requires prioritizing institution building and eschewal of the temptations of self-aggrandizement”)። ይሄን ምክር በነጻ ሊለግስህ የሚችለው ውለታ የዋልክለት ሰው ብቻ ነው። ዶ/ር ተቀዳ ግን “በኤርትራ ላይ የተጣለውን ማዕቀብ ተቋማዊ ሥርዓትን እና የነገ የኢትዮጵያን ታአማኒነት በማይጎዳ መልኩ ብቻ ነው ማስነሳት ያለብን እንጂ እንደ የሕጻን ልጅ ጨዋታ በብዙ ልፋት የተጣለውን ማዕቀብ በደብዳቤ ብቻ ማንሳት ተገቢ አይደለም” ባለ ፥ በሁለት መስመር ደብዳቤ ከኒውዮርክ አዋራጅ እና ሥርዓትን ባልጠበቀ መልኩ በዓብይ የተነሳ ነበር። መልሶ ጭንቅ ውስጥ ሲገባ ገዱ አንዳርጋቸውን አስልኮበት (በሽማግሌ) ድጋሚ እንዲረዳው ሊጠይቀው ነገር። ዘመኑንን ሁሉ ኢትዮጵያን ያገለገለው ዶ/ር ተቀዳ ግን በዛ ማበድ እና ሳይገባን መከተል ፋሽን በሆነበት ዘመን ነው ፥ “ግድ የለህም ይሄን ነገር ፈር አሲዘው። ተቋማዊ አድርገው። ትላንት ስህተትን ከሰሩ ሰዎች አንተ በምንም አትለይም፣ በእነሱ መንገድ ከሄድክ በመንገዳቸው መጨረሻ እነሱ የገጣማቸውን ነገር ብቻ ነው የምታገኘው” ይለዋል። “ዘላቂ ብሔራዊ ጥቅም እንጂ ዘላቂ ወዳጅ የለም የሚለው የሎርድ ፓልመርስቶን ንግግር ምንም እንኳ አናዳጅ እና ኢሞራላዊ ቢመስልም እውነት መሆኑን ግን መካድ የለብንም” ይላል ዶ/ር ተቀዳ፤ “የኤርትራ ፍላጎት ኢትዮጵያን ዲሞክራሲያዊ ማድረግ ሳይሆን የኢሳያስ የኤርትራ ሕወኃትን የመበቀል ጥማት ነው” ሲለን። እኛ ግን ዜጎቹን ሁሉ አባሮ ሽማግሌ እና አሮጊት ታቅፎ፣ ሲንጋፖር ትሆናለች የተባለችን ሀገር ኦስማን ሳሌ እና የማነ ገብርመስቀል የሚባሉ ሁለት ሰዎች ብቻ አስከትሎ የሚመራን መሪ ለኢትዮጵያ ብርሃን ይሆናል ብለን ተቀበልን።



የሰው ልጅ ከታወረ እና እውነትን ለማየት ካልፈለገ ፤ ሲ ኤስ ሉዊስ እንዳለው ዓለም በፊቱ እንደ ወረቀት እየተጠቀለለች እንኳ እውነትን አይቶ ከማመን ይልቅ አይ ይሄ ሃሉስኔሽን (hallucination) ነው ይላል። የራሱን ሀገር ሰው አልባ ያደረገ መሪ በምን ተዓምር ነው 30 ዓመት መሉ የተዋጋትን ኢትዮጵያ ከሀገሩ በላይ የሚያዝንላት? የኢትዮጵያ መረጋጋት፣ ዲሞክራሲያዊ መሆን እና የኢኮኖሚ ዕድገት ትልቁ አደጋ ለኢሳይያስ መሆኑን ለመዘንጋት እንደ አንዳርጋቸው ጽጌ መታወር ያስፈልጋል።

ዶ/ር ተቀዳ የአሜሪካ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ እና ስትራቴጂ የሚጠነሰስበት “the Council on Foreign Relations” ፕሬዝዳንት የሆነው ሪቻርድ ሀስ “ፎሬን ፖሊሲ የሚጀምረው ከቤት ነው” ብሎ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ መጀመር ያለበት የውስጥን ቤት ሥርዓት በማስያዝ ነው በሚል በ2013 ለመጀመሪያ ጊዜ አዲስ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ እና ስትራቴጂ አስተሳሰብ አስተዋኩኝ ብሎ ከመነሳቱ 9 ዓመት በፊት፤ መለስ ዜናዊ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲያችን እና ስትራቴጂያችን መነሳት ያለበት የውስጥ ቤትን በማቃናት እና ሥርዓት በማስያዝ ነው ብሎን ነበር ይለናል።(እንደአንዳንዶች ዶ/ር ተቀዳ ነበር የጻፈው ያን ድንቅ ፖሊሲ፤ ይሄ ባይሆን እንኳ ትልቅ ግብአት እንደነበረው አልጠራጠርም። ይሄን የምለው መለስ ዜናዊ ያን የማፍለቅ የአዕምሮ አቅም የለውም እያልኩኝ አይደለም። ከዛም በላይ መስራት እንደሚችል ያሳየን ይመስለኛል።)። ዶ/ር ተቀዳ ፖሊሲውን ቢያደንቅም ፥ ያን ፖሊሲ መሬት ለማውረድ የሰነፈውን ኢህአዴግን ግን አልራራለትም። ይሄም ይመስለኛ የዚህ ጹሁፍ ውበት ፥ እውነትን ለራስም ሲሆን አለመሰወር። ለራስም ቢሆን አለመራራት።


በርግጥ ይሄ ጸሐፊ ዓብይ አህመድ ያመጣው የለውጥ ማዕበል ኢትዮጵያ ውስጥ ሲቀጣጠል፤ የሕወኃት አባል ከነበረ አለቃዬ ጋር ዶ/ር ተቀዳን በኒውዮርክ በምሳ ግብዣ ላይ ለማውራት ዕድሉን አግኝተን ነበር። ስለኤርትራ አለቃዬ ሲጠይቀው፤ ዶ/ር ተቀዳ “ችግራችን በዋነኛነት ኤርትራ አይደለችም፤ ወደውጭ መመልከት ተው፤ አሁን ያለውን ነውጥ ራስን በማቃናት እና በመታረም ፈር ማስያዝ ካልቻላቹ ከኤርትራ በላይ ለሀገሪቱ አደጋው ኢህአዴግ ነው” ነበር ያለው። የሚዲያ ሰው ግን ስላልነበረ፣ ይሄን አይነት የእውነት ስብዕናውን የሚያውቁት ጥቂቶች ናቸው። ይሄ ማለት ስህተት የለበትም ወይም ንጹሁ ነው ለማለት አይደለም፤ በዲፕሎማቲክ አገልግሎቱ ኢትዮጵያን ከማስቀደም ጎድሎ አያውቅም ለማለት እንጂ።



ዶ/ር ተቀዳ በመጨረሻ ፥ ስለኢትዮጵያ መጻኢ ዕድል በማሰብ እንቅልፍ አልባ ማታዋችን እንደሚያሳልፍ ገልጾ ፥ በመጨረሻ ትንቢት ጹሁፉን ይዘጋዋል። “ይሄን የለውጥ ዕድል ከበቀል በጸዳ መንፈስ ካልተጠቀምንበት፣ ተቋሞችን ለመገንባት ካላዋልነው፣ ሕወኃት እንዳደረገው ስለተዋጋቸው ብቻ ታላቅ የነበረውን የመከላከያ ሠራዊት እንዳፈረሰው፣ አሁንም ያለው የለውጥ ኃይል ያን ዓይነት ስህተት ከደገመ ‘ኢትዮጵያችን ሁለተኛ ይሄን የመሰለ ዕድል ላታገኝ ትችላለች!’” አለን።



ሀገሬ ዘላለማዊ እንዳልሆነች አውቃለሁ፤ ለእኔም ድንኳኔ እንጂ ዘላቂ ሀገሪ እንዳልሆነች አልዘነጋም፤ ነገር ግን ይሄ የተቀዳ ትንቢት ግን እንዳይሰምር የትላንት ትንቢቱ እንዳይሰምር ከተመኘውበት እጥፍ እመኛለሁ። ኢትዮጵያኖች የገጠመን ነገር የኛም ክፋት ውጤት ነው። ከዚህ መከራ ሊያወጣን እግዚአብሔር የታመነ ነው። ፍቅሩ እና ማዳኑ ግን ያለቅድመ ሁኔታ አይደለም። ሀብታሞች (ነጋዴዎች) በዚህ ደረጃ ጨካኝ ሆነው ፍጹም ለሆነ ስግብግብ ትርፍ የሚራወጡባት፣ የክርስቶስን መስቀል የተሸከሙ አባቶች በዘር እና ጎጥ ተለያይተው እንደ ድንጋይ መግለጫ በሚወራወሩበት ሁኔታ፣ የሀሰት ሌባ ነብዮች በዚህ ደረጃ ሀገሪቷ ላይ ሲፈነጩ እና ትውልድ ሲያከስሙ፤ እኛም የሚናገሩት ለጆሮአችን ደስ ስላለን እየተከተልናቸው፣ የመንግስት ባለስልጣናት የወጣላቸው ዘራፊ ሆነው፣ ወንድማማችነት ጠፍቶ ዘረኝነት የነገሰበት ሀገርን የሚታደግ አምላክ የለንም። ዶ/ር ተቀዳ እንዳለን እሴቶቻችንን እንፈትሽ ፥ “የትኛውም የውጭም ሆነ የሀገር ውስጥ የደህንነት ፖሊሲ የጥንካሬው ደረጃ በቆመባቸው እሴቶቹ (values) ጥንካሬ የሚለካ ነው” ነው ያለን ዶ/ር ተቀዳ።



የሀገራችንን ዘላቂ ጥቅም ማስቀደም ካልቻልን፣ ስለእውነት ለመናገር ካልደፈርን፣ ወገናችንን ለመውደድ ካልፈቀድን ኢትዮጵያን ነገ አናያትም ብቻ አይደለም ሶማሌ እና የመንን ገነት እናስመስላቸዋለን። ለእኔ ዓብይ አህመድ የክፋታችን እና የእውቀት አልባነታችን ውጤት እንጂ ምንጭ አይደለም። ዓብይ አህመድን ለዚህ ውድቀት ማውገዝ ሰውዬው የሌለውን አቅም እና ችሎታ መስጠት ነው። ለመገንባት ብቻ አይደለም ለማፍረስም ችሎታ ይጠይቃል። እሱ ሁሉቱም የሌለው ነው። ላለንበት ሁኔታ ኃላፊነት ወስደን ሀገራችንን እንታደጋት።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 2 min read
ree

ኖሕ መርከብን ለመገንባት 20 ዓመት ነበር የፈጀበት። 20 ዓመት መሉ ያን ግዙፍ መርከብ ሲገነባ ሰዎች ያሾፉበት ነበር ምክንያቱም ሰማዩ የጠራ ነበር ፥ አንዳች ዝናብ የሌለበት፣ ፀሐይ በሰዓቷ ትወጣለች በሰዓቷ ትገባለች፣ ቀኑ በሰዓቱ ነግቶ በሰዓቱ ይመሻል፣ ዓየሩ የመለወጥ ምልክት አያሳይም፤ ሁሉም ዑደቱን ጠብቆ ነበር የሚጓዘው። የማያቋርጠው ዝናብ መዝነብ እስከሚጀምር ኖሕ ነበር ሞኙ። ኖሕ ነበር ጊዜ አባካኙ፣ ኖሕ ነበር ያልገባው፣ ኖሕ ነበር ያለፈበት፣ ኖሕ ነበር ነቄ ያልነበረው፣ ኖሕ ነበር የሚሾፍበት፥ ያ ዝናብ እስኪጀምር።



 በሕይወትም እንደዛ ነው ፥ ፈተና እስከሚደርስ የማያጠኑ፣ ችግር እስከሚመጣ ገንዘብ የማጠራቀም ጥቅሙ የማይታያቸው፣ ብቸኛ እስከሚሆኑ ዝምድና የማይገነቡ፣ እድሜያቸው ጨምሮ በሽተኛ እስከሚሆኑ ስለሚበሉት ምግብ የማይጨነቁ፣ በዶክተር እስከሚነገራቸው ስፖርት የማይሰሩ ፥ የመከራ ዝናብ እስከሚዘንብ መርከብ የማይገነቡ ሰዎች ብዙ ነን። ዝናቡ አንዴ መዝነብ ከጀመረ ግን ሰርገኛ መጣ በርበሬ ቀንጥሱ ነው ፥ ፋይዳ የሌለው ሩጫ ፥ ትርጉም የሌለው ጭንቀት፣ ሰሚ የሌለው ዋይታ ብቻ ነው።



ከዓመታት በፊት ከአንድ ኢአማኒ ወዳጄ ጋር እንደቀልድ ስንወያይ በዚህ ምድር እንዴት በፍቃዳችን መከራ መቀበል እንዳለብን እና ያ ደግሞ ለሚመጣው ዓለም ዋስትናችን እንደሆነ ስነግረው ፥ “አንተ እኮ የቆጡን አወርድ ብላ የብብቷን እንደጣለችው እየሆንክ ነው፤ ገና ለገና ያን አገኝ ብለህ እጅህ ላይ ያለውን ደስታ አሳልፈ ትሰጣለህ” አለኝ። ፈተነኝ። ከባድ ምት ነበር። ነገር ግን በሕይወታችን ይሄን ወዳጄ ጨምሮ በየቀኑ የምናደርገው በፍቃዳችን የብብታችንን እየጣልን ተስፋ የምናደርገውን ለመያዝ አይደለም የምንዘረጋው?



ቀኑን መሉ እየተራገጠ እና እየቦረቀ ከሚውል (እጁ ላይ ያለውን የዛሬ ደስታ) ይልቅ ነገ መኖሩን እርግጠኛ ላሎነለት ዓለም አይደል እንዴ ተማሪ ዛሬ የሚጨነቀው? ስንቶቻችንስ ዛሬ እጃችን ላይ ያለው ገንዘብ ሊሰጠን የሚችለውን ደስታ ገታ አድርገን (ብብታችን ውስጥ ያለውን ትተን) ነገ ተጠራቅሞ አንድ ቁም ነገር ላይ ለማዋል ገንዘባችንን እናጠራቅም የለ። ይሄስ ተስፋ የምናደርገውን ነገር በዛሬ ስቃይ ለመያዝ መዘርጋት አይደለምን? ስንቶቻችን አይደለን ምራቃችንን እየዋጥን ለነገ ጤናችን ስንል ስንት አሁን ላይ የሚጥመንን ምግብ የምናሳልፈው። እነዚህስ ሁሉ ከተስፋ ውጪ ምን ዋስትና አላቸው? ብዙ ሰዎች ተጠንቅቀው የዛሬን ደስታ አሳልፈው ለነገ ያቆዩትን ሳይጠቀሙ ከመካከላችን እንደተለዩን እያየን እንኳ ፥ መቼ በነገ ተስፋ ቆርጠን እናውቃለን? መቼ የዛሬን ሕይወት በጥቂት ስቃይ ለነገ ከማስተላለፍ ተቆጥበን እናውቃለን? አባካኝ የሚባለው ሰው ሳይቀር በሆነ መጠን ለነገ የዛሬን ደስታ የሚገብርበት ንቃተ ሕሊና ቀርቶለታል።



በመኃል ይሄን የኑሮ እውነት ወደ መግለጽ የገባውት፤ የሰው ልጅ ለዚህ ዓለም የተፈጠረ እንዳልሆነ ተፈጥሮው ራሱ እንዴት እንደሚመሰክርበት ለማሳየት ነው። ሰው ከሃይማኖት የሚፈልገው የዕለት ሕይወቱን ከሚመራበት የምክንያት ሚዛን በላይ ስለሆነ እንጂ፤ የሰው ተፈጥሮ ራሱ ተስፋ ለምናደርገው ነገር ስቃይን ዛሬ በፈቃድ መቀበል ላይ የተመሰረተ ነው።



ወደ ቀደመው ነገር ልመለስ፤ ኖሕ እንዴት በጉብዝናው ወራት የመከራውን ወራት መርከብ እንደሰራ እና በጉብዝናቸው ሰዓት ያሾፉበትን ሰዎች እናያለን። ጠቢቡ ሰሎሞን እንዳለው የጭንቀት ቀን ሳይመጣ፣ ያ መጥፎ የምንለው ወራት ሳይደርስ፣ ሁሉም አልቃሽ፣ ሁሉም ራሱን የማዳን ሩጫ፣ ሁሉም የኩራዝ ጋዛቸው አልቆ ሊገዙ ወደ አደባባይ የመሮጣቸው ወራት ሳይመጣ ፥ የሕይወት መርከባችንን እንስራ። ትላንት መርከብ የሰሩ ሰዎች የዛሬ የመዓት መከራ ላይ ሲንሳፈፉ እያያችሁ ነው። ትላንት ዘረኝነትን የዘሩ፣ ሕዝብን የጨፈጨፉ፣ ሁሉን ማስተንፈስ ስለቻሉ ዘለዓለም የሚገዙ መስሏቸው ሁሉን ፈሪ ብለው ተዘልለው የተቀመጡ እንዴት እንደወደቁ እንዳያችሁ አትዘነጉትንም።



 ከአሁኑ የሕይወት መርከባችንን እንስራ ፥ የመከራ ዝናብ ሳይዘንብ የጥበብ እና የአስተዋዮች ኑሮ እንኑር። ዛሬ አስረስ ምቺው ካሉት ጋር ስላላልን ሞኝ ነን ፥ ነገ ግን እኛን ዛሬ ሞኝ ያሉን ሲጠፉ እኛ በመከራ ዝናብ ላይ እንሳፈፋለን። ዛሬን ሞኝ ለመባል የደፈረ ብቻ የነገ ብልሕ ይሆናል። ዝናቡ እስኪጀምር ሞኝ ሆነን መርከባችንን እንስራ።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page