top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 5 min read

የሰንበት ዕይታ - 16

ree

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አከራካሪ ከሆኑ ነገሮች አንዱ እና የተለያዩ ሊቃውንትም ግራ ከሚጋቡበት ነገሮች ውስጥ ንጹሁ የሆኑ እና ንጹሁ ያልሆኑ ተብለው እንስሳት ለምግበ እስራኤል መለየታቸው ነው። በተለይ በዘፍጥረት ምዕራፍ አንድ ላይ እግዚአብሔር የፈጠራቸው ፍጥረታት ሁሉ መልካም መሆናቸው በይፋ ተገልጾልን፣ ፍጥረቱን እንደሚወድ እና እንደሚመግባቸው በብዙ የመጽሐፍ ክፍል ተነግሮን ሳለ፣ እንደገና ንጹሁ የሆኑ እና ንጹሁ ያልሆኑ ተብለው መለየታቸው እስራኤሎችን ሳይቀር ግራ የሚያጋባ ነው።



ከክርስቶስ ልደት በፊት በግብጽ አሌክሳንደሪያ ብዙ ግብጾች ይኖሩ ነበር፤ በአይሁድ የአመጋገብ ምርጫ የሚደነቁ ሄለናዊያን እና ግሪኮች እነዚህን አይሁዶች ለምን ንጹሁ እና ንጹሁ ያልሆነ ምግቦች በማለት አንዳንድ እንስሳትን እንደማይበሉ ጠይቀዋቸው ነበር። ፋይሎ የሚባል ሊቅ በሰዓቱ ለዚህ ምክንያት ነው ያላቸውን ዘርዝሮ ጽፎ ነበር። የአርስጣጢለስ ደብዳቤ ለአሌክሳንደርም ይሄን ጉዳይ ያብራራል። እውነታው ግን በርግጠኝነት ማናቸውም ምክንያቱን እንደማያውቁት ነው የሚያሳየው።


ይሄ በዘሌዋውያን ምዕራፍ 11 እስራኤል እንዲበሉት ተብለው የተጠቀሱት እንስሶች አንዳንዶቹ በእንደዚህ ባህሪያት ተለይተዋል፤


፩) የተሰነጠቀ ሰኮና ያለውንና የሚያመሰኳውን እንስሳ ሁሉ ብሉ።

፪) በባሕሮችና በወንዞች ውስጥ ክንፍና ቅርፊት የሌላቸው ሁሉ በእናንተ ዘንድ የተጸየፉ ናቸው።

፫) በአራት እግሮቹ ከሚሄድ እንስሳ ሁሉ በመዳፎቹ ላይ የሚሄድ በእናንተ ዘንድ ርኩስ ነው፤

፬) በሆዱ የሚሳብ፥ በአራትም እግሮች የሚሳብ፥ ብዙ እግሮችም ያሉት፥ በምድርም ላይ የሚንቀሳቀሱ ተንቀሳቃሾች ሁሉ የተጸየፉ ናቸውና አትብሉአቸው።


ስለሚበሩ ወፎች የተነገረ መለያ ሕግ ባይኖርም፤ የማይበሉት እንደ ቁራ፣ ዳክዬ፣ ጥንብ አንሳ ተዘርዝረዋል።


በብሉይ ሕግ ስለንጽህና በምግብ ብቻ ሳይሆን በአልባሳትም ተጠቅሷል። ለምሳሌ ሁለት ዓይነት ቀለማት ያሉት ልብስ መልበስ ንጹሁ አይደለም። የሞተ እንስሳ መንካትም እንዲሁ ከንጽህና ያሶጣል። እነዚህን ነገሮች ማድረግ ኃጢአት ነው ሳይሆን፣ ወደ ተቀደሰው ቤት እና ወደ መቅደሱ ለመግባት ግን የመንጻት ሥርዓትን መፈጸም ያስፈልጋል።


አንዱ የሊቃውንት መከራከሪያ እነዚህ ንጹሁ አይደሉም የተባሉ እንስሶች በጣዖት በሚያመልኩ ሕዝቦች ዘንድ የአማልክቶቻቸው ወካይ ናቸው ተብሎ መጠቀሱ ነው ይላሉ። ለምሳሌ በዮሐንስ ራዕይ ሰይጣን በእንቁራሪት ተመስሏል፣ እንቁራሪት ደግሞ ንጹሁ አይደሉም ስለዚህ አትብሏቸው ከተባሉት ነው ወገኑ። ሌላኛው መከራከሪያ ደግሞ ንጹሁ የተባሉ እንስሳት የወገኖቻቸው ወካይ ናቸው፤ ለምሳሌ በውሃ ውስጥ የሚኖር እንስሳ ክንፍና ቅርፊት ከሌለው የአሣን መስፈረት አያሟላም ፥ ስለዚህ ያን ዘር (የአሣን) አጉዳይ ስለሆነ ንጹሁ እንዳልሆነ ይቆጠራል የሚል ነው።



በስፋት በሀገራችን ሊቃውንት ሳይቀር የምንሰማው መከራከሪያ ደግሞ ዝምድና ነው። ለምሳሌ አሳማ ሁሉን የሚበላ፣ የሚከረፋ፣ ሆዳም ስለሆነ ያንን እንደ ኃጢአተኛ እና ከክብሩ እንደተዋረደ ማንነት አድርጎ በምሳሌ በማቅረብ፤ ለመብላት ንጹሁ ያልተባለው ለዛ ነው የሚል ነው። ጥንብ አንሳም ከዚህ ምሳሌ የሚካተት ነው።


ሌሎች ደግሞ ንጹሁ የተባሉት እንስሳት ለፈጣሪ በመሥዋዕት መልክ የሚቀርቡ በመሆናቸው፤ የፈጣሪ ምግብ ናቸው፣ በዚህም ንጹሁ ተባሉ። በተቃራኒው አሳማ፣ ግመል ደግሞ ለመሥዋዕት ስለማይቀርቡ፣ የሰው ልጆችም መብላት የለባቸውም የሚል ነው።


ሌሎች ደግሞ እንደ ጠንካራ መከራከሪያ አድርገው የሚያነሱት ከጤና አንጻር ነው። እንደ እንቁራሪት፣ አሳማ ያሉ እንስሶች ከውሏቸው እና አመጋገባቸው አንጻር ለጤና አደገኛ ስለሆኑ (ሁሉን የሚያግበሰብሱ በመሆናቸው) ለዛ ነው አትብሉ የተባልነው ይላሉ።


እውነት ለመናገር ከላይ የተጠቀሱት ምሳሌዎች እምብዛም አሳማኝ አይደሉም። ለምሳሌ ቀላል የማይባሉ ንጹሁ የተባሉ እንስሶች የክፋት ምሳሌዎች፣ የባዕድ አምልኮ ምልክቶች ነበሩ። በንጽህናም ከወሰድን ፍየል እምብዛም ከአሳማ የሚለይ የአመጋገብ ሥርዓት የለውም። ዶሮም ሁሉን የሚመገብ ነው። ከጤናም አንጻር የሚነሳው ክርክር ውሃ የሚቋጥር አይደለም። አሳማ ከምግባር አንጻር በመጥፎ እና በሁሉ አግበስባሽነት ቢመሰልም፣ በምንም ክፋት የማይመሰሉ እንስሶችም ንጹሁ አይደሉም እና አትብሏቸው ተብሏል። ለምሳሌ ዳክዬ፣ ሎብሰተር፣ ፈረስ እና ሌሎችም። ስለዚህ የክፋት ምሳሌ ናቸው መባሉም አሳማኝ መከራከሪያ አይደለም። ለፈጣሪ ምግብነትም (ከመሥዋዕት አንጻር) ተብሎ የሚቀርበው ምክንያት መሻገር የማይችሏቸው ነጥቦች አሉት። ለምሳሌ ለመብላት ንጹሁ ሆነው ለእግዚአብሔር ግን በመሥዋዕትነት ማቅረብ የማይፈቀዱ እንስሶች ነበሩ። አጋዘን አንዱ ነው። ይበላል ግን አይሠዋም።



ከበሽታ እና ከንጽህና አንጻርም እስራኤሎች የተለየ ጤናማ ሕዝቦች አልነበሩም። ንጹሁ የተባሉ እንስሳትን ብቻ በመብላታቸው ያተረፉት የተለየ የጤና ጉዳይ የለም። ሌሎች በሚጠቁበት በሽታ ሁሉ ተጠቅተዋል። ረዥም ዕድሜ በመኖር በአርኬዎሎጂ ጥናት መሠረት ሩቅ ምስራቆች የተሻሉ ናቸው። እነዚህ ደግሞ በአመጋገብ ባህላቸው ከእስራኤሎች የተለዩ ነበሩ።


አንድ መገንዘብ ያለብን ነገር መጽሐፍ ቅዱስ ንጹሁ እንስሳት እና ንጹሁ ያልሆኑ ብሎ ለመብል ሲከፍላቸው ፈጽሞ ከሰውነት ጤና እና ከረዥም ዕድሜ ጋር እንዳላያያዛቸው ነው።

በዚህ ክርክር ውስጥ እግዚአብሔር ለእስራኤላውን ንጹሁ እና ንጹሁ ያልሆኑ እንስሳት፣ አዕዋፋት እና የባህር እንስሶች ብሎ ሲለይ በምን ምክንያት ነው የሚለውን ከዳሰሱ እና አሳማኝ ሆነው ያገኘውትን ነጥቦች ልዘርዝር፤


1) መገደብን፣ እንቢ ማለትን ማስተማር፤


ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፥ “ሁሉ ተፈቅዶልኛል፥ ሁሉ ግን አይጠቅምም። ሁሉ ተፈቅዶልኛል፥ በእኔ ላይ ግን አንድ ነገር እንኳ አይሠለጥንብኝም።” እግዚአብሔር ሁሉን መልካም አድርጎ ከፈጠረ በኋላ፣ በገነት ውስጥ መታዘዝን፣ የሰውን በፍጥረቱ ውስጥ ያለውን ቦታ እና ከእግዚአብሔር ጋር ያለውን ግንኙነት የምታሳይ ያለመብላት ሕግ አውጥቶ ነበር። ያ ፍሬ በገነት ውስጥ ከነበሩት ፍሬዎች የተለየ ውበት ወይም ማስቀየም እንዳለው የተነገረን ነገር የለም። ሔዋን ለመብላት ስታስብ ፍሬው ያማረ እንደሆነ ከማየቷ በቀር። ይሄ ግን ሌሎቹ የሚበሉ ፍሬዎች ከዛ ዛፍ ያነሰ ውበት ወይም አስጎምጅነት እንዳላቸው ምንም አልተገለጸም። አንድ ነገር ግን ተነግሮናል፣ ያ ዝፍ የሞት ፍሬ መሆኑ። ምክንያቱም እርሱን መብላት ያለመታዘዝ ምልክት ነው። የአመጽ ምሳሌ ነው። በተመሳሳይ ለእስራኤል ንጹሁ እንስሳት ተብለው የተዘረዘሩትን በመስመር ማስቀመጥ እና ሁሉንም በሆነ መስፈረት ማኖር አይቻልም (arbitrariness አለባቸው)። ይሄ የሚነግረን ጉዳዩ ከመብልነት እጅጉን የተሻገረ እንደሆነ ነው።


እስራኤል እንቢ ማለትን፣ ለእግዚአብሔር ሲል መተውን፣ በዚህም ራስን መግዛትን እንዲማር የወጡ ሕጎች ናቸው። የሥጋ ትልቁ ፍላጎት እና ፈተና የሆነውን መብላት በመገደብ ፥ እንቢ ማለትን እና የፍቃድ ጡንቻን ማጠንከርን ለእስራኤል አስተማረው። እስራኤል እነዚህ የኛ ምግቦች አይደሉም፣ ለኛ አይሆኑም በማለት በሕይወት ራስን መገደብን እና ኃጢአት እንኳ ባይሆን ለእኛ የተፈቀደ አይደለም በማለት እንቢ ማለትን በሕይወት እንዲማሩ የተተከለ የፍቃድ (will power) ጡንቻ ማጎልበቻ ናቸው። ለእግዚአብሔር ስንል ምክንያት እንኳ ባይኖረው እንቢ ማለትን እንዲማሩ አደረጋቸው። በዚህም በሕይወት ነገሮች ስላጓጓቸው እና ስሜታቸው ስላሻው ብቻ እንዳያደርጉ ፥ ለምኞታቸው እንቢ የማለትን ጡንቻ ገና በጊዜ እንዲያዳብሩ አደረጋቸው።


የአይሁድ ቤተሰቦች በዚህ ዘመን ሳይቀር ይሄን የምግብ ባህል በጥንቃቄ ይከተላሉ። ተመልከቱ ይሄ ራስን የመግዛት፣ በዚህም የሕይወት ስኬትን የመቆናጠጥ ማንነት ከአይሁድ ዘር በላይ በዚህ ዓለም ማን ምሳሌ ሊሆን ይችላል። የኖቤል ሽልማትን ብቻ ውሰዱ። እስከዛሬ ከ965 የኖቤል ተሸላሚዎች ውስጥ፣ 214 አይሁዶች ናቸው። በአሜሪካ ውስጥ የአይሁድ ቁጥር 2.4% ነው፤ በአሜሪካ ቢዝነስም ሆነ ፖለቲካ ግን 71% ከሚሆነው የነጩ ማህበረሰብ ምንም ያልተናነሰ ተጽዕኖ የአይሁድ ማህበረሰብ ነው ያለው። በዚህ ዓለም ላይ ከቁጥሩ አንጻር የአይሁዶችን ያህል ስኬት የተጎናጸፈ አንድ ዘር መጥራት የሚችል ይኖራል? የትኛውንም የስኬት ሜትሪክሶችን አምጡ እና የአይሁድን ማህበረሰብ አስቀምጡ፤ ይሄ ማህበረሰብ ካለው ቁጥር አንጻር እጅግ አስገራሚ ስኬት የተጎናጸፈ ሆኖ ታገኙታላችሁ።


ማንንም ጠይቁ ፥ ለጊዜያዊ ፍላጎቱ እንቢ ማለት የቻለ ሰው፣ ራሱን መቆጣጠር እና መግዛት የሚችል ሰው በምንም ዘርፍ በመጨረሻ ያሸንፋል። ይሄን ነበር በምግብ እግዚአብሔር ለእስራኤል ያስተማራቸው። በዚህ ሕግ ሕይወታቸውን ሁሉ አበራላቸው። እንቢ የማለትን ማንነት አጸናላቸው።


2) ሥርዓትን ያስተምራል ፦ መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን ላይ “ዓላማ ይዞ እንደ ተሰለፈ ሠራዊት የምታስፈራ ማን ናት?” እንዳለው ጠቢቡ፤ በሕይወት ሥርዓት ያለው ትንሽ ሠራዊት ሥርዓት የሌለውን እልፎች ይረታል። ዛሬም ስለእስራኤላውን ይሄ እውነት ነው። ጎረቤቶቻቸው በቁጥር በስንት እጥፍ እየበለጧቸው፣ ራሳቸውን የለዩ፣ በሥርዓት ማንነታቸውን ያሰለጠኑ በመሆናቸው በእልፍ የሚበልጧቸው በፊታቸው ይርዳሉ። (You develop an ordered soul that says no to certain things).


3) ማንነት ነው ፦ እነዚህን ምግብ እኛ እስራኤላውያን በመሆናችን አንበላም በማለታቸው ፥ ራሳቸውን ሁሉን ከሚበላው ዓለም ለዩ። በዚህም በቁጥር በብዙ እጥፍ ከሚበልጡአቸሁ ጎረቤቶቻቸሁ ማንነታቸውን ጠብቀው ማቆየት ቻሉ።


4) የእግዚአብሔርን ንጽሕ እና ቅድስና የሚያሳይ ነው። ለምሳሌ ሴቶች በወራዊ ልማዳቸው ወቅት ወደ ቅዱሱ ስፍራ ወንዶችም ዘራቸው የፈሰሰ እንደሆነ ወደ እግዚአብሔር መቅደስ እንዳይገቡ በብሉይ ሕግ ተደንግጎ ነበር። ሴቶች ወራዊ ልማዳቸውን ማስቀረት የሚችሉት ነገር አይደለም፤ ስለዚህም ኃጢአት አይደለም። ነገር ግን ወደ ቅድስናው ስፍራ በዚህ ወቅት መቅረብ አይችሉም፤ ለምን? ይሄ የእግዚአብሔርን ቅድስና እና ንጽህና የሚናገር ነው። “እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ነኝና፤ ሰውነታችሁን ቀድሱ፥ ቅዱሳንም ሁኑ፥ እኔ ቅዱስ ነኝና፤ በምድርም ላይ በሚሳብ ተንቀሳቃሽ ሁሉ ሰውነታችሁን አታርክሱ።” ዘሌዋውያን 11፥44። ኃጢአትን አለመስራት አንድን ሰው ቅዱስ አያደርገውም። ቅድስና የዓላማ ተግባር ነው (affirmative action)። ቅድስና መተግበርን ይሻል፣ መራቅን ብቻ አይደለም። አንድ ሰው ኃጢአት መሥራት እየቻለ፣ ስለእግዚአብሔር ብቻ ሲል ከተወ ያ ቅድስና ነው። ምክንያቱም የዓላማ ተግባር ነውና። ቤቱ ውስጥ ምግብ የሞላለት እና ምንም ያልጎደለበት ሰው ላይሰርቅ ይችላል። አለመስረቁ ቅዱስ አያደርገውም። ከመጸወተ ግን ያ ቅድስና ነው። ሰይጣን ስለኢዮብ ያለው ይሄን ነበር። “እርሱ ስለሞላለት፣ ምንም ስላልጎደለበት፣ ዙሪያውንም ከክፍ ስላጠርክለት እንጂ ምንም ጽድቅ የለውም” ነበር ያለው። ሰይጣን ሳይቀር ከኃጢአት መራቅ በራሱ የጽድቅ ምልክት እንዳልሆነ ያውቃል ማለት ነው። እነዚህ ምግቦች ለእግዚአብሔር ሲባል ብቻ መተውን፣ በዚህም መቀደስን የሚያስተምሩ ምልክቶች ናቸው።


በአዲስ ኪዳን እነዚህ ምግቦች ያላቸው ቦታ ግልጽ ነው። በቤተክርስቲያናችንም እንዴት እንደሚታዩ ብጹዑ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የቤተክርስቲያን ታሪክን በጻፉበት መጽሐፋቸው ዳሰውታል።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 4 min read

የሰንበት ዕይታ - 3

ree

ካርል ማርክስ እና ሼክስፒር በዚህ ጉዳይ ይለያያሉ። ካርል ማርክስ ሰዎች የሚጣሉት ስለሚለያዩ ነው ይላል። የተለያዩ ግቦች፣ ፍላጎቶች፣ አይዶሎጂ፣ የተለያየ ቁሶች ስላላቸው ነው የሚጣሉት ይላል። ሼክስፒር ግን በሮሚዮ እና ጁሊየት እና በሌሎችም ሥራዎቹ እንደገለጠው ሰዎች የሚጣሉት ስለሚመሳሰሉ ነው ይላል። እኔ ሼክስፒርን በሙሉ ስቀበል ፥ ካርል ማርክስን ደግሞ በከፊል ልክ ነው እላለው።


ብዙ ጊዜ የምንቀናው ከኛ በሀብት እና በንብረት ወይም በሆነ ነገር የሚመሳሰለንን ሰው እንጂ ከኛ በጣም በራቁ ሰዎች አንቀናም። በቢልጌት ወይም በኤለን መስክ እኛ አንቀናም። የምንቀናው ልንደርስበት በምንችለው ወይም አብሮን ከኛ ጋር በነበረ ሰው ነው። ቃዬል በአዳም አልቀናም በመንታ ወንድሙ አቤል እንጂ። ኤሳው በያዕቆብ ፥ የዮሴፍ ወንድሞች ከኛ እሱ በምን በልጦ ነው ብለው በወንድማቸው ዮሴፍ፣ አሮን እና ማርያም በወንድማቸው በሙሴ ቀኑበት ይላል። ይሄ ሁሉ የሚያሳየን ሰዎች የሚጠላሉት ስለሚመሳሰሉ ነው። ኢትዮጵያ ውስጥም በጣም በሚቀራረቡ ብሔሮች መካከል ነው ጥላቻ እና ግጭት ያለው። በትግራይ እና በአማራ፣ በትግራይ እና በኤርትራውያን፣ በኦሮሞ እና አማራ (በቁጥር ስለሚቀራረቡ)፣ በወላይታ እና በሲዳማ፣ በአኝዋክ እና ጉምዝ፣ በኑዌር እና ዲንካ እያለ ይቀጥላል። በዓለም ላይም ጥላቻ እና ግጭት በሚቀራረቡ መካከል እንጂ በሚራራቁ መካከል ጠብ የለም።


የሦስተኛው ክፍለዘመን የመጽሐፍ ቅዱስ ሊቅ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ ሙሴን ለመከራ የዳረገው የሚራራቁት የዕብራውይ እና የግብጻዊ ጠብ ሳይሆን በሁለት ወንድማማቾች ዕብራውያን ጠብ ነው ለስደት የተዳረገው ይላል። ይሄንንም ሲገልጽ የሚለያዩ ነገሮች ጠብ ቀላል እና ውጪያዊ ነው ስለዚህም መገላገል ቀላል ነው ይላል። የሚመሳሰሉ ሰዎች ወይም የወንድማማቾች ጠብ ግን የመረረ ነው ፥ ለዚህም መገላገል እጅጉን ከባድ ነው። ይሄንንም ሲያጠቃልል እንዲህ በሚል ዘመን ተሻጋሪ አባባል ነው የዘጋው “ማንም ሰው ተቀናቃኙ በእርሱ ላይ የድል ኃይል እንዳለው ምልክት ካላገኘ በቀር በእርሱ ላይ ሐዘን አይሰማውም። ” ይሄ ማለት ሰው በሕጻን ልጅ ስድብ አይናደድም ፥ አቻው ወይም ወዳጁ ሲሰድበው ነው የሚናደደው። ማናችንም ተቀናቃኝ የምንላቸው አቻዎቻችንን ነው። በሞተ ሰው ወይም ከኛ በብዙ በሚያንሱ እና በብዙ በሚበልጡ ላይ ንዴት የለንም።



ካርል ማርክስ ደግሞ ያስተዋለው ሰዎች ለግጭት የሚሰጡትን ትንታኔ ነው። አዎ ማንም ሰው ግጭት ውስጥ ሲገባ “ስለቀናው ነው፣ እሱ ያለውን ስለተመኘው ነው፣ እሱን ስለተፎካከርኩት ነው፣ እሱ እንዳይደርስብኝ ነው” አይልም። ምክንያቱም ይሄ ግጭቱን ምክንያት ያሳጠዋል ፥ ተከታይ እና ደጋፊን ይነሳል። ለራሳችንም እንደዛ ብለን ማመን አንፈልግም።


የዚህ ጹሁፍ ዓላማ ምንድነው?


ብዙዎቻችን እንቀናለን ፥ የምንቀናው ደግሞ በጎረቤታችን ወይም በብዙ በሚመስለን ነው።(መጽሐፍም ባልጀራን ውደደው ያለው ፥ ባልንጀራን መውደድ ከባድ ስለሆነ ነው።)ይሄን ለማወቅ ከፈለጋችሁ ዓይናችሁን ጨፍናችሁ ስኬታቸውን ስትሰሙ ወዲያው ደስታ የማይሰማችሁ ሰዎችን አስተውሉ። ወይም በሆነ ነገር ከናንተ ሊያንሱ የሚችሉበትን ነገር ሲያገኛቸው ደስ የሚላችሁ ሰዎች እነማን ናቸው? እነዚህ ሰዎች በብዙዎቻችን ሕይወት ውስጥ አሉ። በእህት እና ወንድም ወይም በእህትማማቾች፣ በጣም በቅርብ ጓደኞች መካከል ነው ባብዛኛው የሚኖረው። ይሄ ስሜት ሲመጣብን ፈጥነን ለማውገዝ አንቸኩል። ይሄ ስሜት ከጥንት ጀምሮ የነበረ ነው። ረጋ ብለን ለምን እንደዛ እንደተሰማን እንጠይቅ፣ እኛ ከቁስ እና ከውድድር በላይ የራሳችን ውበት እንዳለን እናስተውል። ሕይወት ለእያንዳንዳችን የተለየች ናት። ስለዚህ ከዚህ ዓለምም የምናገኘው ነገር እንደዛው የተለያየ ነው። የሌላው ስኬት ሁልጊዜ ለኛ ሊጠቅም ስለሚችልበት ነገር እናስብ። እንድንፎካከራቸው ከሚጋብዙን ሰዎች በብዙ ኬሎሜትር እንራቅ። እንደዛ ስሜት ከሚሰማን ሰዎች ወይም እንዲሰማን ከሚያደርጉን ለጊዜው እንሽሽ ፥ የራሳችን ሕይወት ላይ እናተኩር። ከዛ በተረፈ ግን የምንቀናባቸው ሰዎችን ከኛ መነጠል የማንችል ከሆነ ፥ በተቻለ መጠን በጎ ነገራቸው ላይ ለማተኮር እና ሆን ብለን ለመርዳት እንሞክር። በእነሱ ፊት ላለማስመሰል እንጣር።


የምንቀናባቸው ነገር የምናደንቅላቸው ነገር ስለሆነ እኛ ያ ነገር ቢኖረን እንደምንመኝ እና በዛ ነገራቸው እንደምንቀናባቸው እንንገራቸው። ያ የሚያሳፍር ቢመስለን እንኳ በውስጣችን ያለውን መጥፎ የፉክክር ስሜት ግን ይገለዋል። ስለዚህ ራሳችንን እናድናለን።


በተጨማሪም ቅናት ምን ያህል ፍትሐዊ ስሜት እንዳልሆነ እንገምግመው። ምክንያቱም የምንቀናበትን ሰው ሁሉ ነገሩን አንፈልግም። ያ የምንቀናበትን ጥቂት በጎ ነገር እንጂ። ለምሳሌ የስቲቪ ጆብ (የአፕል ስልክ መስራች) ጓደኛ ሆነን በሱ እንቀናለን እንበል። የምንቀናው በሱ ስኬት ብቻ እንጂ፤ ፈጣሪ ስቲቪ ጆብን ላድርጋችሁ ቢለን ማናችንም እንቢ ነው የምንለው ምክንያቱም ከ40ዎቹ ዕድሜው ጀምሮ በካንሰር በሽታ የተሰቃየውን በ56 ዓመቱ የሞተውን ስቲቪ ጆብን ማናችንም መሆን አንፈልግም፤ የፈለግነው ያ ስኬቱን ብቻ ነው። ሕይወት ግን እንደዚያ አየሰራም። ልጅን ወዶ ንፍጡን ተጠይፈን አይሆንም እንደሚባለው፤ ቅናት እንደዛ ነው። ልጁን ያለንፍጡ መፈለግ። ለዚህ ነው ፍትሐዊ ስሜት እንዳልሆነ እና እኛ የምንቀናበት ሰው የሌለው ውበት በኛ ሕይወት ውስጥ እንዳለ ማየት ያለብን። ይሄ ማለት ግን የኛ ሕይወት ከዛ ሰው የበለጠ ነው ማለት አይደለም። የተለየ እና የራሱ ውበት ያለው ነው ለማለት ነው። ቅናት ግን ይሄን ውበት ያጨልመዋል። ለምሳሌ ሙዚቀኛው ሙሉቀን መለሰ በጥላሁን ገሰሰ ይቀናበታል ይባላል። ያ እውነት ነው እንበል። ሙሉቀን ግን የጥላሁን ገሰሰን ሕይወት ይሰጥኽ ቢባል ፍቃደኛ አይሆንም ምክንያቱም የጥላሁን ሕይወት አንገት መታረድ፣ እግር መቆረጥ፣ በጊዜ መሞትም አለበትና። ለዚህ ነው ቅናት የህሊና ፍትህ መታወር ውጤት የሆነው።



ሌላው የዚህ ጹሁፍ ዓላማ ፥ ወደ ግጭት ስንገባ እንደግለሰብም ሆነ እንደተቋም እና ሀገር ራሳችንን መጠየቅ ያለብን “የሄ ግጭት ከመመሳሰል ከመጣ ቅናት ወይስ ስትራቴጂክ ፍላጎቴን የሚጠቅም ግጭት ነው?” ብለን ነው። ድፍረት አይሆንብኝ እና ከ90% በላይ የሚሆኑት ግጭቶች የቅናት ውጤቶች ናቸው። በዚህም ከመመሳሰል የመጣ፤ የረጅም ዘመን (long-term) ጥቅማችንን ያላማከለ፣ ስሜት የሚነዳው እና በመጨረሻም ሁሉንም ለከፋ ውጤት የሚዳርግ ነው። ምክንያቱም ቅናት ሌላው የሚያጣ ከሆነ በራሱ ማጣት ሀዘን አይሰማውም። ቅናት ሌላው ሁለት ዓይኑን የሚያጣ ከመሰለው የራሱን አንድ ዓይን አሳልፎ ለመስጠት የሚፈቅድ ነው። ቅናት እንደጥንብ አንሳ የሌሎች መቀርናት የሚስበው ፥ መልካም ጠረናቸው የሚገለው ነው። በሚገርም ሁኔታ እንደ ኮሚኒዝም ያሉ የፖለቲካ ፍልስፍናዎች ሳይቀር በቅናት ሞተርነት የተንቀሳቀሱ ድሃውን ከበርቴ ማድረግ ሳይሆን ከበርቴውን ድሃ በማድረግ የተጠናቀቁ ነበሩ። ጥቂቶች በእነዚህ ሥርዓቶች የተደሰቱት ሃብታም ስለሆኑ ሳይሆን ሌሎችን ከእነሱ እኩል ድሃ ስላደረገላቸው ነበር። የሚያስቡ ሰዎች፣ የራሳቸውን ረጅም ጊዜ ጥቅም በጥልቀት ለመመርመር የሚችሉ እና ስሜታቸውን ለመፈተሽ የሚፈቅዱ ግለሰቦችም ሆነ ልሂቃን ግጭቶች በቅናት እንዳይመሩ ወይም እንዳይቀሰቀሱ ለራሳቸው ስሜት መጠበቂያ ያደርጋሉ። ወደ ግጭት ከመግባታቸው በፊት የዛ ሰው፣ ተቋም ወይም ሀገር ስኬት ለእነሱ ምን ማለት እንደሆነ፣ ያ እንዴት ለእነሱ ጥቅም እንደሚውል ያስባሉ። ውድቀቱ የሚያስደስታቸው ከሆነ ያ ግጭት ከቅናት የተነሳ ሊሆን እንደሚችል መጠርጠር ተገቢ ነው።ምክንያቱም ከመመሳሰል የሚነሱ ግጭቶች ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ አጥፊዎች (distractive) ናቸውና።

 
 
 
ree

፩) የኢዮብ ወዳጆች ለመከራ እና ለክፋት መልስ አለን ብለው መቅረባቸው፤

እውነት ለመናገር ብዙዎቻችን ብዙ ነገር አናውቅም። ግን አላውቅም ማለት በጣም ከባድ ነው። መክበዱ ብቻ አይደለም መልስ ሳይኖረን ተረጋግተን መኖር እና መቀጠል ይሳነናል። በተለይ ዓይናችን ሥር ትልቅ ክስተት ስናይ የዛን መንስኤ መተንተን ያስጎመጀናል። በተማሩ ሰዎች መካከል ደግሞ አላውቅም ማለት ነውር ይሆናል። አለማወቅ ተማርን ማለታቸውን ያሳንስባቸዋል። ማህበረሰባዊ ጫናውም ከፍተኛ ነው። አንድ አክስቴ ብዙ ጊዜ ስትጠይቀኝ አላውቅም፣ አላውቅም ስላት “እንዴ የተማርክ አይደለህም እንዴ?” አለችኝ። የዚህ ዓይነት ጫና ስለማናውቀው ነገር ሳይቀር ትንታኔ እንድንሰጥ ይጋብዘናል። ዝም ማለት በትልልቅ ክስተቶች ፊት እጅግ ከባድ ነው። የኢዮብ አዋቂ ወዳጆቹ የተሳናቸው ያ ነበር። በእግዚአብሔር ጉባኤ ተወስኖ በጻዲቁ ኢዮብ ላይ የተከናወነው ነገር ለማናቸውም የሰው ልጆች የተገለጠ አልነበረም። ግን የኢዮብ ወዳጆች ዝም ከማለት ይልቅ ለኢዮብ መከራ ምክንያት ፈለጉለት። ኃጢአተኛ ስለሆንክ ነውና ንስሃ ግባ አሉት። ቢያንስ በሀሳብህ በድለሃል አሉት። ውጤትን ዓይተው መንስኤውን ተነተኑ።



 የደራሲ ዓለማየው ገላጋይን አንድ የተቆረጠ ቪዲዮ ተመለከትኩኝ። ያለንበት ድህነት እና መከራ እረፍት የነሳው ይመስላል። ይሄ አዋቂ ደራሲ ከዛ እንዲህ አለ “እግዚአብሔር ጣልቃ አይገባም በሕይወታችን።” የየቀን ሠሪውን እግዚአብሔርን “ሁሉን ነገር ሠርቶ ጨርሶ ቀድመው ለነቁ ሰዎች አስረክቦናል” አለን። “ለዚህም ነው ከዚህ በፊት የጠፉ ሰዎች ሲያይ ጣልቃ ያልገባው፣ በእኛም ሕይወት ጣልቃ አይገባም፣ ራስህ ሠርተ ለፍተህ ልበስ፣ ብላ፣ ተጋደል። እርሱ ጣልቃ አይገባም፣ ለዚህም ነው የሰለጠኑት፣ ቀድመው የነቁት ሁልጊዜ የሚገዙን” አለ። ይሄ መከራ ላይ፣ ድህነት ላይ፣ ችግር ላይ ቆሞ ስለመንስኤው የማውራት ዝንባሌ እና አባዜ ነው። ጥራት ባለው አስተሳሰብ ዙሪያ ብዙ የተማሩ ሰዎች የሚሰሩት ትልቁ የማሰብ ስህተት ነው፣ መንስኤን ከውጤት ለማግኘት መጣር። ይሄ ጥራት ላለው አስተሳሰብ ጋንግሪን ነው። ከእግዚአብሔር ጋር ስናያይዘው ደግሞ ቁጣው እንደእሳት የሚነድበት የአስተሳሰብ ዝንባሌ ነው። ስለኢዮብ ባይሆን ኖሮ ቁጣዬ እንደ እሣት በልቷቹ ነበር ነው ያለው።



በየቀኑ ይሄን የአስተሳሰብ ስህተት እንሰራለን። የታመመ ሰው እናያለን ፥ እግዚአብሔር ቀጣው እንላለን። ሀብታም እናያለን ፥ እግዚአብሔር ባረከው እንላለን። ድሀ እናያለን ፥ ሰነፍ ነው፣ እግዚአብሔር አልባረከውም እንላለን። ውጤት ላይ ቆሞ መንስኤን የማግኘት አባዜ። እስቲ በሕይወታችሁ አንድን ነገር ስንት ሁኔታዎች ሊያመጡት እንደሚችሉ ጠይቁ እና ያን ለእናንተ የተገለጠውን ብቻ ፈትሹ። በእናንተ ሕይወት እንደዛ ከሆነ፣ እጅግ ውስብስብ በሆነው በዚህ ዓለም አነዋወር ውስጥ የአንድ ነገር መንስኤ ከኛ የማሰብ አቅም ቢያንስ ያለጥልቅ ጥናት የረቀቀ ሊሆን ይችላል ብላችሁ አትገምቱም?


ደራሲ ዓለማየው መንስኤውን ለማወቅ በመቸኮሉ፣ ውጤቱንም በአግባቡ የተረዳው አይመስልም። ለምሳሌ በእውነት ይሄ ዓለም ኃያል የሆነው የሰው ልጅ (በዘመናዊ ቴክኖሎጂ) ደካማ የሆነውን ፍጹም የሚገዛበት ነው ወይስ ብዙ ዓይነት ኃይሎች በሰዎች የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ ላይ እና የነገ ሕይወታችን ላይ ያልተጠበቁ እና ተገማች ያልሆኑ አሻራቸውን እና ተጽዕኖዎችን የሚያሳርፉበት ዓለም ነው? በዚህ ዓለም ሰዎች የፈጠሯቸው ግዙፍ ቴክኖሎጂዎች ፥ በጣም ደካማ በሆኑ ፍጥረታት ወይም ክስተቶች አቅጣጫቸውን ሲቀይሩ እና ሲዘወሩ አላየንምን? ለምሳሌ የኮቪድ ቫይረስ እንዴት የሰው ልጆችን ሁሉ ባህሪ እና አነዋወር በቅጽበት እንደለወጠ ተመልከቱ። ይሄ ክስተት የሚነግረን ይሄ ዓለም በኃያላን ፍላጎት እንደፈለጉት የሚዘወር ዓለም እንዳልሆነ አይደለምን? የታላቋን አሜሪካ የውጪ ጉዳይ እና የሀገር ውስጥ የደኅንነት ፖሊሲ ፍጹም የቀየረው ከደካማዋ ሀገር አፍጋኒስታን የመጣ ጥቃት አልነበረምን? በርግጥስ ይሄ ዓለም ኃያላን እንዳሰቡት የሚኖሩበት ዓለም ነውን?



መሥራትን፣ ለፍቶ ማደርን፣ መፍጠርን ለማበረታታት የግድ ጽንፍ መሄድ አያስፈልገንም። እነዚህ ነገሮች ጥሩ ናቸው። ግን ሌላም እውነት አለ። እነዚህ ብቻ በቂ አይደሉም። እነዚህ ብቻ መልስ አይደሉም። “ሥራ ነጻ ያወጣኻል፣ Arbeit macht frei” የሚለውን መፈክር እናውቀዋለን። ይሄ በፍሬድሪክ ኒቼ ተጠንስሶ ናዚዎች የወረሱት እና በናዚ ካምፖች ሁሉ የተሰቀለ መፈክር ነበር። ሥራ ብቻውን የጥላቻ እና የትዕቢት ባርነት ውስጥ ጀርመኖችን ጨምሮ፣ ውድቀታቸውን አስከተለ እንጂ ነጻ አላወጣቸውም።



ጠቢበኛው ሰሎሞን ስለመንስኤ ሲናገር ከኛ ውጪ ባሉ ኩነቶች ማለትም በጊዜ እና በዕድል የሚወሰኑ እንደሆነ ተናግሯል። እዚህ ላይ የደረሰው ከብዙ ማሰብ በኋላ እንደሆነ ሲያሳይ “እኔም ተመለስሁ” ብሎ ይጀምራል። “እኔም ተመለስሁ፥ ከፀሐይ በታችም ሩጫ ለፈጣኖች፥ ሰልፍም ለኃያላን፥ እንጀራም ለጠቢባን፥ ባለጠግነትም ለአስተዋዮች፥ ሞገስም ለአዋቂዎች እንዳልሆነ አየሁ፤ ጊዜና እድል ግን ሁሉን ይገናኛቸዋል።” መክ 9፥11።


፪) ሁለተኛው ነቀፋ ቲዎሎጂ እና አይዶሎጂ ነው። የኢዮብ ወዳጆች ጠንካራ ቲዎሎጂ ነበራቸው። ያም ክፋት ስለሚሸነፍበት መንገድ ነው። የእነሱ መንገድ ብቻ ኢዮብን ከቁስሉ እንደሚፈውሰው ደሰኮሩ። እየተፈራረቁ የቁስሉ መድኅን እነሱን መስማት መሆኑን ነገሩት። ይሄ በሃይማኖት ሰዎች መካከል በጣም ጠንካራ ዝንባሌ ነው። ለሁሉም ነገር መፍትሔ አለን። ለሁሉም ነገር ስንዱ ነን። የሚገርመው ግን ክፋትን እግዚአብሔር እንዴት እንደሚያሸንፍ ከኛ የተሰወረ ጥበብ መሆኑ ነው። ክፋትን በመስቀሉ እንደሚረታ ለማንም የተሰወረ ነበር በብሉይ ኪዳን። መስቀል ነበር \ የእግዚአብሔር ጥበብ ፥ ክፋትን የረታበት። የሰው ልጆችን ቁስል የፈወሰበት። ያ ግን በድንግዝግዝ ተመለከቱት እንጂ ለአንዳቸውም አበው አልተገለጠላቸውም ነበር። ቲዎሎጂ በፍጥነት አይዶሎጂ ይሆናል፤ ለሁሉም ነገር መልስ አለኝ ብሎ ሲያስብ። ክፋት እና መጥፎ ነገሮች ለምንላቸው ሁሉ መልስ አለኝ ብሎ ሲገምት። ዝምታ እና ለእግዚአብሔር ዕድል እና ጊዜ መስጠት ብዙዎቻችን በየቀኑ መማር ያለቡን ጸጋዎች ናቸው። “ምነው ዝም ብላችሁ ብትኖሩ፦ ይህ ጥበብ በሆነላችሁ ነበር።” ኢዮ 13፥5።


 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page