top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 2 min read
ree

ኖሕ መርከብን ለመገንባት 20 ዓመት ነበር የፈጀበት። 20 ዓመት መሉ ያን ግዙፍ መርከብ ሲገነባ ሰዎች ያሾፉበት ነበር ምክንያቱም ሰማዩ የጠራ ነበር ፥ አንዳች ዝናብ የሌለበት፣ ፀሐይ በሰዓቷ ትወጣለች በሰዓቷ ትገባለች፣ ቀኑ በሰዓቱ ነግቶ በሰዓቱ ይመሻል፣ ዓየሩ የመለወጥ ምልክት አያሳይም፤ ሁሉም ዑደቱን ጠብቆ ነበር የሚጓዘው። የማያቋርጠው ዝናብ መዝነብ እስከሚጀምር ኖሕ ነበር ሞኙ። ኖሕ ነበር ጊዜ አባካኙ፣ ኖሕ ነበር ያልገባው፣ ኖሕ ነበር ያለፈበት፣ ኖሕ ነበር ነቄ ያልነበረው፣ ኖሕ ነበር የሚሾፍበት፥ ያ ዝናብ እስኪጀምር።



 በሕይወትም እንደዛ ነው ፥ ፈተና እስከሚደርስ የማያጠኑ፣ ችግር እስከሚመጣ ገንዘብ የማጠራቀም ጥቅሙ የማይታያቸው፣ ብቸኛ እስከሚሆኑ ዝምድና የማይገነቡ፣ እድሜያቸው ጨምሮ በሽተኛ እስከሚሆኑ ስለሚበሉት ምግብ የማይጨነቁ፣ በዶክተር እስከሚነገራቸው ስፖርት የማይሰሩ ፥ የመከራ ዝናብ እስከሚዘንብ መርከብ የማይገነቡ ሰዎች ብዙ ነን። ዝናቡ አንዴ መዝነብ ከጀመረ ግን ሰርገኛ መጣ በርበሬ ቀንጥሱ ነው ፥ ፋይዳ የሌለው ሩጫ ፥ ትርጉም የሌለው ጭንቀት፣ ሰሚ የሌለው ዋይታ ብቻ ነው።



ከዓመታት በፊት ከአንድ ኢአማኒ ወዳጄ ጋር እንደቀልድ ስንወያይ በዚህ ምድር እንዴት በፍቃዳችን መከራ መቀበል እንዳለብን እና ያ ደግሞ ለሚመጣው ዓለም ዋስትናችን እንደሆነ ስነግረው ፥ “አንተ እኮ የቆጡን አወርድ ብላ የብብቷን እንደጣለችው እየሆንክ ነው፤ ገና ለገና ያን አገኝ ብለህ እጅህ ላይ ያለውን ደስታ አሳልፈ ትሰጣለህ” አለኝ። ፈተነኝ። ከባድ ምት ነበር። ነገር ግን በሕይወታችን ይሄን ወዳጄ ጨምሮ በየቀኑ የምናደርገው በፍቃዳችን የብብታችንን እየጣልን ተስፋ የምናደርገውን ለመያዝ አይደለም የምንዘረጋው?



ቀኑን መሉ እየተራገጠ እና እየቦረቀ ከሚውል (እጁ ላይ ያለውን የዛሬ ደስታ) ይልቅ ነገ መኖሩን እርግጠኛ ላሎነለት ዓለም አይደል እንዴ ተማሪ ዛሬ የሚጨነቀው? ስንቶቻችንስ ዛሬ እጃችን ላይ ያለው ገንዘብ ሊሰጠን የሚችለውን ደስታ ገታ አድርገን (ብብታችን ውስጥ ያለውን ትተን) ነገ ተጠራቅሞ አንድ ቁም ነገር ላይ ለማዋል ገንዘባችንን እናጠራቅም የለ። ይሄስ ተስፋ የምናደርገውን ነገር በዛሬ ስቃይ ለመያዝ መዘርጋት አይደለምን? ስንቶቻችን አይደለን ምራቃችንን እየዋጥን ለነገ ጤናችን ስንል ስንት አሁን ላይ የሚጥመንን ምግብ የምናሳልፈው። እነዚህስ ሁሉ ከተስፋ ውጪ ምን ዋስትና አላቸው? ብዙ ሰዎች ተጠንቅቀው የዛሬን ደስታ አሳልፈው ለነገ ያቆዩትን ሳይጠቀሙ ከመካከላችን እንደተለዩን እያየን እንኳ ፥ መቼ በነገ ተስፋ ቆርጠን እናውቃለን? መቼ የዛሬን ሕይወት በጥቂት ስቃይ ለነገ ከማስተላለፍ ተቆጥበን እናውቃለን? አባካኝ የሚባለው ሰው ሳይቀር በሆነ መጠን ለነገ የዛሬን ደስታ የሚገብርበት ንቃተ ሕሊና ቀርቶለታል።



በመኃል ይሄን የኑሮ እውነት ወደ መግለጽ የገባውት፤ የሰው ልጅ ለዚህ ዓለም የተፈጠረ እንዳልሆነ ተፈጥሮው ራሱ እንዴት እንደሚመሰክርበት ለማሳየት ነው። ሰው ከሃይማኖት የሚፈልገው የዕለት ሕይወቱን ከሚመራበት የምክንያት ሚዛን በላይ ስለሆነ እንጂ፤ የሰው ተፈጥሮ ራሱ ተስፋ ለምናደርገው ነገር ስቃይን ዛሬ በፈቃድ መቀበል ላይ የተመሰረተ ነው።



ወደ ቀደመው ነገር ልመለስ፤ ኖሕ እንዴት በጉብዝናው ወራት የመከራውን ወራት መርከብ እንደሰራ እና በጉብዝናቸው ሰዓት ያሾፉበትን ሰዎች እናያለን። ጠቢቡ ሰሎሞን እንዳለው የጭንቀት ቀን ሳይመጣ፣ ያ መጥፎ የምንለው ወራት ሳይደርስ፣ ሁሉም አልቃሽ፣ ሁሉም ራሱን የማዳን ሩጫ፣ ሁሉም የኩራዝ ጋዛቸው አልቆ ሊገዙ ወደ አደባባይ የመሮጣቸው ወራት ሳይመጣ ፥ የሕይወት መርከባችንን እንስራ። ትላንት መርከብ የሰሩ ሰዎች የዛሬ የመዓት መከራ ላይ ሲንሳፈፉ እያያችሁ ነው። ትላንት ዘረኝነትን የዘሩ፣ ሕዝብን የጨፈጨፉ፣ ሁሉን ማስተንፈስ ስለቻሉ ዘለዓለም የሚገዙ መስሏቸው ሁሉን ፈሪ ብለው ተዘልለው የተቀመጡ እንዴት እንደወደቁ እንዳያችሁ አትዘነጉትንም።



 ከአሁኑ የሕይወት መርከባችንን እንስራ ፥ የመከራ ዝናብ ሳይዘንብ የጥበብ እና የአስተዋዮች ኑሮ እንኑር። ዛሬ አስረስ ምቺው ካሉት ጋር ስላላልን ሞኝ ነን ፥ ነገ ግን እኛን ዛሬ ሞኝ ያሉን ሲጠፉ እኛ በመከራ ዝናብ ላይ እንሳፈፋለን። ዛሬን ሞኝ ለመባል የደፈረ ብቻ የነገ ብልሕ ይሆናል። ዝናቡ እስኪጀምር ሞኝ ሆነን መርከባችንን እንስራ።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 2 min read

የሰንበት ዕይታ - 12

ree

በዘፍጥረት ምዕራፍ 4 ላይ ያለ ታሪክ ነው። ምንድነው ይሄን ታሪክ ስታነቡ የሚደንቃችሁ? ለምን የቃየንል መሥዋዕት እግዚአብሔር እንዳልተቀበለው? ወይስ ለምን የአቤልን መሥዋዕት እንደተቀበለው?ወይስ ቃየን ላይ እግዚአብሔር ያደረገበት ምልክት ምን ይመስል ነበር?

አሁን አሁን በጣም መማር ያለብኝ ሥርዓት (discipline) የመጽሐፍ ቅዱስ ጸሐፊ ትኩረት እንዳናረግበት የፈለጉትን የታሪክ ክፍተቶች ትኩረት አለማድረግን ነው። ያልተሰጡንን የታሪክ ክፍተቶች ለመሙላት በጣርን ቁጥር፣ ከመጽሐፉ ዓላማ እየወጣን (distracted) መሆናችንን ማወቅ አለብን። እነዚህን ክፍተቶች ለመሙላት መጣር ለምርምር አስደሳች ይሆናል። እግዚአብሔር ግን እንዳናተኩርባቸው የፈለጋቸው ጉዳዮች ናቸው። ለምሳሌ ቃየን ያገባት ሴት ከየት መጣች? ከተማን ለመመሥረት የሚያስችል ሰዎች ከየት መጡ? የእነዚህን መልስ ማወቅ ያስደስት ይሆናል።


የዘፍጥረት ጸሐፊ (ሙሴ) ግን እየነገረን ያለው ይሄ የመጽሐፉ ትኩረት እንዳልሆነ ነው።

የቃየን እና የአቤልን ታሪክ ሳነብ ከሚመጡብኝ ጥያቄዎች አንዱ፣ ጸሐፊው እንድናተኩርበት ከፈለገው ታሪክ ውስጥ የሆነው ነው። ይህም የአቤልን ገዳይ ቃየንን እግዚአብሔር ወዲያው እንዳልገደለው። ያ ብቻ ሳይሆን ነፍሰ ገዳዩን ቃየንን ሌሎች ሰዎችም እንዳይገሉት እግዚአብሔር ምልክት እንዳደረገበት። ቃየንን የሚገድል ሰባት እጥፍ እንደሚበቀልበት ነው የነገረን።


እግዚአብሔር ክፋትን ወይም ክፉን ወዲያው ማጥፋት እንዳልፈለገ ከዚህ ታሪክ ማየታችን ብቻ ሳይሆን፣ የመጀመሪያው ሰማዕት የሃይማኖት ሰማዕት ነው። ማለትም ስለእምነቱ ነው የመጀመሪያ ሰው የተገደለው። በእምነቱ በተገደለ ሰው መገዳደል ወደ ምድር ገባ። በአምላኩ በመወደዱ ነው አቤል የተገደለው። የመጀመሪያውን ክፉ ነገር ከሰው የተቀበለው ሰው ስለጽድቁ ነው። በጣም ክፉ ስለሆነ ሳይሆን የመጀመሪያ ሰው የተገደለው፣ በጣም ጥሩ ስለሆነ ነው። ይልቁስ ነፍሰ ገዳዩን ሰው ሌሎች እንዳይገዱለት እግዚአብሔር ፈለገ። ለምን?



መጽሐፈ ኢዮብ ላይ የሰው ልጅ የመጨረሻውን ክፉ ነገር ይቀበላል። ያም ሰው ኢዮብ ነበር። ለምን ብላችሁ ስትጠይቁ፣ "በጣም ጥሩ ስለሆነ ነው" መልሱ። ክርስቲያኖች ይሄ የታሪክ ሂደት ለእናንተ አዲስ አይደለም። የሃይማኖታችን ራስ እኮ የተገደለው ንጹሁ ስለሆነ ነው።

ክፉስ ቃየን?


የእንክርዳዱን እና የስንዴውን ታሪክ ስንቶቻችን እናስታውሳለን? (ማቴ 13፥24)። ክፉም ደጉም አብረው እንዲቀጥሉ እግዚአብሔር ለምን ፈለገ? እግዚአብሔር እንክርዳዱን በኛ ሰዓት እንዳንነቅል የፈለገ እንደሆነ እየገለጸልን አይደለምን? በግለሰብ ተነሳስተን ክፉን በራሳችን ወስነን፣ እኛው እርምጃ እንዳንወስድ እያዘዘን አይደለምን? ይሄስ በጦርነት ከመሳተፍ፣ ለነጻነት ከመታገል ጋር እንደምን ታስታርቁታላችሁ? ከሞአብ እስከፍልስጤም የተዋጉት እስራኤሎችስ ከዚህ አንጻር እንዴት ይታያሉ?



አንድ ነገር ግን ግልጽ ነው። ክፉ ከደጉ ጋር አብረው መኖር እንደሚቀጥሉ። ይሄንንም የፈቀደ እግዚአብሔር መሆኑ። ክፉም በርሱ ቁጥጥር ሥር እንደሆነ። በበቀል ስሜት ክፉን ሰው መግደል እንደሌለብን፣ ይልቁስ ያን በቀል እግዚአብሔር በሰዓቱ እንደሚያደርግ ነው ይሄ ታሪክ የሚነግረን። "እንክርዳዱን ተውት፣ ቃየንን አትግደሉት" ነው የተባልነው፤ እግዚአብሔር በጊዜው የአቤልን ገዳይ ይበቀለዋል። የበቀል ጦርነት የሚባል ክርስቲያኖች የሚሳተፉበት ጦርነት የለም።

ክርስቲያኖች ከበቀል ውጪ ባለ ጦርነት ውስጥ መቼ እንደሚገቡ ከዚህ በፊት ጽፌያለው።

 
 
 

የሰንበት ዕይታ - 6

ree

የአፍሪካ ልማት ባንክ ሁለት ከፍተኛ ኃላፊዎች በፋይናንስ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ ጠባቂዎች ታፍነው እንደተደበደቡ፣ ለዚህም ምክንያቱ ከ5.2 ሚሊዮን ዶላር በላይ ለባንኩ የኢትዮጵያ ባንክ በተጭበረበረ የባንክ አካውንት ማስገባቱ እና ያ በሚኒስትሩ እና በባንኩ የኢትዮጵያ ከፍተኛ ኃላፊዎች መካከል የተፈጠረ መካረር ለዚህ ድብደባ እና መታፈን እንደዳረጋቸው በማህበራዊ ሚዲያ ሲገለጽ ነበር። እ.ኤ.አ በኦክቶበር 30 2023 የአፍሪካ ልማት ባንክ ባወጣው መግለጫ ሁለት ከፍተኛ ኃላፊዎቹ ተደብድበው መታፈናቸውን ገልጾ፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉዳዩን ሲሰሙ ባደረጉት ፈጣን ጣልቃ ገብነት የታፈኑት ግለሶቦች መለቀቃቸውን ገልጿል። ነገር ግን ባንኩ በሰጠው መግለጫ ስለታፈኑበት ምክንያትም (ስለ 5.2 ሚሊዮን ዶላሩ) ሆነ በማህበራዊ ሚዲያ ስለተሰራጨው ዜና ከመታፈናቸው እና መደብደባቸው ውጪ ያለው ነገር የለም።



በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ ራሳቸው መኪና እየነዱ አህመድ ሽዴ እና ማሞ ምህረቱን አስከትለው የተደበደበው የባንኩ ኃላፊ ጋር እንደሄዱ እና በዚህም የአህመድ ሽዴ ጠባቂዎችን ደብዳቢዎቼ እነሱ ናቸው ብለው መለየታቸውን በማህበራዊ ሚዲያ ተገልጿል። ይሄን ግን በባንኩም መግለጫ አልተገለጸም፤ ታማኒነት ካላቸው የመረጃ ምንጮችም ማረጋገጥ አልቻልኩም። ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅም ጉዳት ቅነሳ (damage mitigation) በሚመስል መልኩ የራት ግብዣ ለተደብዳቢዎቹ አድርገዋል። ይሄ ሁሉ ግን ግለሰቦቹን ከሀገር ጥለው እንዳይወጡ አላደረጋቸውም።



በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ሚኒስትሮች በዚህ ደረጃ የሀገሪቷን አጠቃላይ ሉአላዊ ክብር እና ብሔራዊ ጥቅም የሚጎዳ ሥራዎችን የራሳቸውን ጠባቂ ተጠቅመው የሚያደርጉበት፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማያውቁበት ሁኔታ ይሄን የማድረግ ድፍረት ሚኒስትሮቹ ከገቡ ፥ ሀገሪቷ ያለችበትን ሥርዓት አልበኝነት የሚያሳይ ነው።



በዛሬ ጹሁፌ በጥቂቱ መዳሰስ የምፈልገው ኢትዮጵያ በዓብይ ዘመን የገባችበትን የዲፕሎማሲ ውድቀት እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መ/ቤትን ክሽፈት ነው።



ዓብይ ከሕወኃት የተረከበው የውጭ ጉዳይ መ/ቤት ኢትዮጵያን በጸጥታው ምክር ቤት ለአባልነት ያስመረጠ፣ በጎረቤት ሀገራትም ሆነ አጠቃላይ በአፍሪካ በብዙ መልኩ ዲፕሎማቲካዊ ተቀባይነቷ እየጨመረ የመጣ፣ በጸጥታ ጉዳይ፣ በስደት እና አከባቢያዊ ደህንነት (regional security) ፣ በኢኮኖሚ ልማት ከአፍሪካ የኢትዮጵያ ድምጽ የሚሰማበት ወቅት ነበር። በዓባይ ጉዳይ ከግብጽ እኩል ድምጻ የሚከበር ያደረጉ ዲፕሎማቶች ታይተዋል። በተለይ በኦሮሚያ እና በአማራ ክልል ከተቀሰቀሱት ሕዝባዊ ተቃውሞች በፊት የነበረው የሀገሪቷ ዲፕሎማሲያዊ ቁመና በብዙ መልኩ አመርቂ የሚባል ነበር። ይሄም ቢሆን ሀገራችን ካላት አቅም፣ ታሪካዊ ማንነቷ እና መድረስ ከምትችልበት ልዕልና አንጻር ሲነጻጸር በጣም ትንሽ ነበር። ነገር ግን ወደ ኋላ ተመልሰን ያለፈውን ስንገመግመው ግን፤ በብዙ መጠን የተለየ እና የሚደነቅ ነበር።



በውጭ ጉዳይ መ/ቤት ውስጥ ለብዙ ጊዜ ሰዎች በዲፕሎማሲ መስክ ይቀጠሩ የነበሩት ባላቸው አካዳሚያዊ ብቃት ወይም ፖለቲካው ቅርበት ነበር። በሕወኃት ዘመን ብዙ አካዳሚያዊ ብቃታቸውን ያስመዘገቡ ልጆች ቀጥታ ከዩኒቨርስቲዎችም ሆነ ከሌሎች መስሪያ ቤቶች በዝውውር መልክ ወደ ዲፕሎማሲው አገልግሎት ገብተዋል። በተመሳሳይ ለሕወኃት ባላቸው ታማኝነትም ይሄን ዘርፍ የተቀላቀሉ ሰዎች ነበሩ። የ1997ኑን ምርጫ ተከትሎ፤ ዲፕሎማሲውን በአካዳሚክ ብቃታቸው የተቀላቀሉ ሰዎች ለቅንጅት ባሳዩት ውግንና መስሪያቤቱ ጥልቅ የሆነ ግምገማ አድርጎ ቀላል የማይባሉ ዲፕሎማቶችን አባረረ። ከውጭም የተጠሩ ዲፕሎማቶች የሚገጥማቸውን ጠርጥረው ሳይመለሱ በዛው ከዱ።


ይሄ የ1997 ምርጭ ነው የውጭ ጉዳይን የዲፕሎማሲ መስክ በመጠኑም የቀየረው። ዛሬ ድረስ የካድሬው ቡድን የሚባለውን ስብስብ ወደ መስሪያ ቤቱ አስገባ። በበረከት ስምዖን መልማይነት ከየክልሉ ከዩኒቨርስቲ የተመረቁ እና በሰዓቱ ያላቸውን አካዳሚያዊ ብቃት በመጠራጠር ሥራ ላለማጣት ኢህአዴግን ተቀላቅለው የነበሩ ካድሬዎችን መስሪያ ቤቱ በዲፕሎማትነት አስገባቸው። እነዚህ የካድሬው ቡድኖች በ1997 የተባረሩትን እና የከዱትን ዲፕሎማቶች ለመተካት በዙር የገቡ ነበሩ። ይሄ የመስሪያ ቤቱን መልክ ቀየረው ፥ ምንአልባትም እስከወዲያኛው።


የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊን ሞት ተከቶሎ፤ ዶ/ር ቴዎድሮስ ወደ ሚኒስትርነት ሲመጣ ፥ ዲፕሎማሲው ገጥሞት የነበረው የሰው ኃይል ጥራት ኪሳራ ከፍተኛ የሚባል ነበር። የካድሬው ቡድን በአመዛኙ ኖት ቨርባል በእንግሊዘኛ መጻፍ የማይችል፣ ጆሮውን ቢቆርጡት እንግሊዘኛ የማይሰማ እና እምብዛም ‘critical thinking’ ችሎታ ያልነበረው ነበር (ከእነዚህ ውስጥ ጥቂት ብቃት ያላቸው ሰዎች ግን ነበሩ)። በዚህ ሰዓት ነው በአምባሳደር ብርሃነ ገብረክርስቶ አማካይነት (በሰዓቱ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የፖለቲካል ዘርፍ ስቴት ሚኒስትር የነበረ) አዳዲስ ዲፕሎማቶችን ለመመልመል ታቅዶ ወደ ሥራ ተገባ። በዚህም የዲፖሎማቲክ ማሰልጠኛ ተቋም ተቋቁሞ፣ በትምህርት ችሎታቸው ከ3.2 ጂፒኤ በላይ ያላቸው እና ሁለት ዙር ፈተና (አንድ የጹሁፍ አንድ የቃል) ተቀምጠው ማለፍ የቻሉ ወጣቶች ተቋሙን ተቀላቀሉ።


መስሪያ ቤቱ በካድሬው ቡድን እስከቴዎድሮስ መምጣት ድረስ ገጥሞት የነበረውን ከፍተኛ የሰው ኃይል ጥራት ክፍተት እነዚህ ወጣቶች በተወሰነ መጠንም ከአንድ ዓመት ስልጠና በኋላ ማስተንፈስ ቻሉ። ምንም እንኳ አብዛኞቹ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ፤ ጥቂቶች ደግሞ ከክልሎች ዩኒቨርስቲዎች ጥሩ ውጤት ያመጡ ልጆች ቢሆኑም፤ የሀገሪቱ የትምህርት ሥርዓት መላሸቅ ግን በአዲሶቹ ዲፕሎማቶች ጥራት ላይም የራሱ ጥላ ነበረው።



እነዚህ ዲፕሎማቶች ለመስሪያ ቤቱ እና ለሀገራችን ዲፕሎማሲ ውጤት ማምጣት በጀመሩበት የአራት እና አምስት ዓመታት ጊዜ ውስጥ ነው፤ የዓብይ መንግስት ሥልጣን የተረከበው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሥልጣን ላይ ከወጣ ቀን ጀምሮ ግልጽ ያደረገው ለውጭ ጉዳይ መ/ቤት በጎ ምልከታ እንደሌለው ነበር። ሰውዬውን በቅርብ ከሚያውቁ ሰዎች ጋር ስለዚህ ጉዳይ ማውራት ብችልም ምክንያቱ ግን ለእኔ ግልጽ አይደለም። አንድ ነገር ግን አውቃለው። ዓብይ አህመድ ሥርዓት እና ደንብ፣ ፕሮሲጀር ይጠየፋል። አንድን ነገር ለማድረግ ሥርዓት አለው፣ ሂደት አለው፣ ዘው ብለህ እንደፈቀድክ አታደርግም፣ ከአለባበስ እስከ ሰላምታ አሰጣጥህ፣ ከማንኛውም የሰውነት ቋንቋ እስከ መመገቢያ ጠረጴዛ ላይ ሹኪያ አቀማመጥህ ድረስ ትርጉም አለው የሚለውን የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤትን ደንብ እና ያን ዓይነት የሥርዓት አካሄድ ይጠየፋል። ነጮች እንደሚሉት ግለሰባዊ (personal) ነው የሚያደርገው። ለምሳሌ ጠቅላይ ሚንስትር መለስ ዜናዊ በፈረንሳይ ቤተመንስግት በተደረገለት ግብዣ ወቅት ምግቡን ቢጨርስም የሹኪያ አቀማመጡ ልክ ስላልነበረ አስተናጋጆቹ የመመገቢያ ሳህኑን ሳያነሱ ይቀራሉ፣ ይሄም ሁሉንም ሂደት ማስተጓገል ይጀምራል፣ ማለትም የሌሎች ሳህንም ሳይነሳ እና ወደ ውይይት ሳይገባ ደቂቃዎች ይነጉዳሉ። በዚህ ወቅት ነው የዛሬዋ ፕሬዝዳንት አምባሳደር ሳህለወርቅ ብድግ ብለው ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ይሄን ሲነግሯቸው ወዲያው ታርመው ሳህናቸው ሊነሳ እና ወደ ውይይት ሊገባ የተቻለው።



እነዚህን የመሰሉ ጥቃቅን ነገሮች በዲፕሎማሲ ትልቅ ውጤት አላቸው። ሀገሪቷ ሁሉ የራሱ ንብረት ነው የምትመስለው፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ ግን እነዚህ እንደተራ አላስፈላጊ ጉዳዮች ነው የሚያያቸው። ብድግ ብሎ ማቀፍ፣ ጺም ማሻሸት፣ ቀለበት ማድረግ፣ አጎንብሶ ማውራት፣ ቡና ማቅረብ ምንም ትርጉም ያለው አይመስለውም። ሲ ኤስ ሉዊስ ሰው ለሰውነት እንቅስቃሴው ትርጉም እንዳይሰጥ ማድረግ ትልቁ የሰይጣን ስትራቴጂ ነው ይላል። ምክንያቱም የሰው ነፍስ በሰውነቱ እንቅሳቃሴ የተወሰነች ናት። ያን ሰው ሲረሳ ነፍሱን ያደክማታል ይላል። ይሄን የሲ ኤስ ሉዊስ እዚህ ጋር ያነሳውት የኦክስፎርዱ ሊቅ ሉዊስ እንዴት የሰው አዕምሮ ከሰው ሰውነት ጋር የተያያዘ መሆኑን ካሳየበት በላይ ፥ የሺ ዘመን የዲፕሎማሲ ልምድን ያለምንም እውቀት እና ምርምር እንደተራ ኤቲኬት (etiquette) በመቁጠር ለማጥፋት መጣር ጥልቀት የሌላቸው ሰዎች ባህሪ መሆኑን ለማሳየትም ነው።



ዓብይ ወደ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ሲመጣ፤ የሲቪል ሰርቪስ ምሩቅ (የመመሪቂያ ወረቀቷን የሰራላት ባልደረባዬ ነው) የሆነችው እና በዘር ድልድል በካናዳ አምባሳደር ተደርጋ የተሾመችውን፣ ከዛም በከፍተኛ የአቅም ማነስ ክስ ከካናዳ አምባሳደርነት ተነስታ፣ ውጪ ጉዳይ መስሪያ ቤት በተራ ሠራተኝነት ሳይቀር አልቀበላት ብሎ፤ ኦሮሚያ ክልል የጸረ ሙስና ኮሚሽን ውስጥ የተቀጠረችውን አምባሳደር ብርቱካን አያኖ ዳዲን ውጪ ጉዳይ ስቴት ሚኒስትር አድርጎ ጉብ አደረጋት። የሷ ሹፌር የነበረው እንዳጫወተኝ ፥ በገዱ አድርጋቸው ጊዜ ቤተመንግስት ዓብይ ጋር ሳትሄድ የምትውልበት ቀናት ጥቂት ነበሩ። በተለይ በፕሮቴስታንት እምነት ምክንያት ከዓብይ ሚስት ዝናሽ ጋር የቀረበ ግንኙነት አላት። የተቀመጠችበ ዘርፍ የሰው ኃይል ሚኒስቴር ዴኤታ ቢሆንም (ምንም የዲፕሎማሲ፣ የፖለቲካል እና የኢኮኖሚ ጉዳዮች የማይመለከቷት ቢሆንም) ከሚኒስትር ደመቀ መኮንን በላይ ከዓብይ አህመድ ጋር የዞረችው እርሷ ነች። ይሄ ማለት የፖለቲካ ዘርፍ ሚኒስትሩ አምባሳደር ምስጋናው እያለ ማለት ነው። በቅርብ ወደ አንድ ዲፕሎማት ጓደኛዬ ደውዬ ስለደመቀ ስጠይቀው ከዚህ በፊት ያለኝን ነው የነገረኝ፤ ምን ባክህ “እሱ የብርቱካን ልጣጭ ነው።”



ዓብይ አህመድ መስሪያ ቤቱን ያዳከመበት መንገድ አንዱ ምንም ስለውጪ ጉዳይ እውቀትም ሆነ ልምድ፣ የሥራ ተጋላጭነትም የሌለውን ገዱ አዳርጋቸውን ከላይ አስቀምጦ ፥ ሌላ ከገዱ የባሰች ሴትዮን በሚኒስትር ቦታ አስፍሮ በውስጡ ያሉ ብቃት ያላቸው ዲፕሎማቶች እንዲማረሩ እና የውጭ ጉዳይ አገልግሎት በጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት ጥገኛ እንዲሆን ነበር። በርግጥ ገዱ አንዳርጋቸው የመ/ቤቱን ክብር ለማስጠበቅ፣ ከጠቅላይ ሚኒስቴር ጽ/ቤት የሚደርስበትን ጫና ተቋቁሞ፣ ብዙ ሙያተኞች ከውስጥ እንዲያድጉ ያደረገ ሰው ነበር። በዚህም ሙያተኞችን በመስማት እና ቦታ በመስጠቱ የሚያመሰግኑት ቀላል የማይባሉ ናቸው።



 በዚህ ወቅት የትግራይ ጦርነት መጣ። ቀላል የማይባሉ ብቃት ያላቸው የትግራይ ልጆች ደግሞ በዲፕሎማሲው መስክ ነበሩ። መንግስት እነዚህ ዲፕሎማቶች ተቋሙን ተጠቅመው ሕወኃትን እያገዙ እና የመንግስትን የዲፕሎማሲ አቅም እያዳከሙ እንደሆነ መረጃ ይደርሰዋል። በዚህም ዘዴ ተፈየደ። መንግስት ነጥሎ አንድን ብሔር ከሚያባር ፥ ሂድ አትበለው እንዲሄድ አድርገው የሚል ዘዴ። ማለትም ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ እ.ኤ.አ በጁላይ 5 2021 ዓ.ም. ፓርላማ ተገኝቶ አብዛኛው ኤምባሲ እንደሚዘጋ እና ዲፕሎማቶችም ከሀገራቸው ሆነው እንደሚያገለግሉ ለፓርላማው ገለጻ አደረገ።


ይሄን የሰሙ የትግራይ ተወላጆች የሆኑ ዲፕሎማቶች ወደ ሀገር ሳይመለሱ በዛው ቀሩ። ቀላል የማይባሉ የኦሮሞ ተወላጆች ሳይቀር ፥ ወደ ሀገር ቤት ተመልሶ ከሀገር ቤት የሚሰራ ዲፕሎማሲ አልታይ ስላላቸው በዛው ሳይመጡ ቀሩ። ነገር ግን መንግስት በዋነኝነት ይሄን ያደረገው ለማጥራት ስለነበረ፤ ወደ ሀገር ቤት የተጠሩት አብዛኛው ዲፕሎማቶች ተመልሰው ተመደቡ። ከጥቂቶች በቀር ብዙም ኤምባሲዎች ሳይዘጉ ቀሩ (ቆንስሎች በአብዛኛው ተዘግተዋል)።



በተለይ በዶ/ር ቴዎድሮስ ዘመን ተመልምለው በብቃታቸው የገቡ ወጣት ዲፕሎማቶች ወደ ሀገራቸው ሳይመለሱ ቀርተዋል። የእነዚህ ልጆች አንዱ ብቃት ማሳያ ቀላል የማይባሉ ወጣት ዲፕሎማቶች በአሜሪካ Ivy league ስኩሎች ሳይቀር (እንደ ኮሎምቢያ እና ኖተርዳም) ሙሉ ስኮላርሽፕ አግኝተው ዛሬ እየተማሩ ያሉ መኖራቸው ነው፤ አንዳንዶቹም ፕሮፌሽናል ሥራ ላይ ተቀጥረው ጥሩ ተከፋዮች ሆነው የሚሰሩ ሆነዋል። እነዚህን ነው ኢትዮጵያ ያጣችው። ከትግራይ ጦርነት በኋላ ያለው ዲፕሎማሲ አቅሙ የላሻቀ፣ በጠቅላይ ሚኒስትሩ በጎ ፍቃድ የሚመራ፣ በውጭ ጉዳይ ደግሞ ለብርቱካን አያኖ የማይሰግድ እና ወሬ የማያቀብል የዲፕሎማሲ ዕድገቱ አደጋው ውስጥ የገባበት፣ ተቋሙ ወጣት ብቃት ያላቸው ዲፕሎማቶች ገብተው ፍሬያቸው መታየት ሲጀምር ፥ ጨለማ ውስጥ ተመልሶ የገባበት ሆኗል።



በውጭ ጉዳይ በነበረኝ ቆይታ ሁሉንም ሊባል በሚችል ደረጃ ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ የሚኒስትር መስሪያቤቶችን ጎብኝቻለው፣ አይቻለው። በአንድ ወቅት ከአውስትራሊያ የመጣ እንግዳ ይዜ የኦሮሚያ ፕሬዝዳንት ቢሮ ውስጥ ስገባ፤ ጸሐፊዋ የቡና ሲኒዎችን በሳፋ አድርጋ የቢሮ ጠረጴዛ ላይ ታጥባለች። በቀጠሮ እንደመጣን ነግሬያት፣ በዚህ ሰዓት ይሄን ማድረጓ ለገጽታ ነውር እንደሆነ ስነግራት፣ ሳፋውን ይዛ የቢሮው መስኮት ላይ ራሷን በመጋረጃ ከልላ ማጠቧን ቀጠለች።

ይሄን የጠቀስኩት፣ በትዝብቴ ሁሉ ያየውት በሥርዓት በመስራት፣ ከቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመን ጀምሮ ሀገራቸውን በከፍተኛ ሙያዊ ብቃት ሲያገለግሎ የነበሩ እንደ ጋሽ ውሂብ ሙሉነህ ያሉ ድንቅ ሙያተኞችን የምታገኙበት፣ ስለኢትዮጵያ የትኛውም ድንበር እና የድንበር ውል ጥያቄ ሲኖራቹሁ በራቸውን አንኳኩታችሁ መጠየቅ ብቻ የሚጠበቅባችሁ ድንቅ ሰዎች የነበሩበት መስሪያ ቤት አላየውም። አልገጠመኝም።



ከልባቸው ሀገራቸውን የሚያገለግሉ፣ ከእውቀት ያልተነጠሉ ሰዎች ለብዙ ዘመን ሲሰሩ የምታገኙበት በኢትዮጵያ ውስጥ ውጭ ጉዳይ መ/ቤት ነው። እውነት ነው ዲፕሎማሲው የሚሰጠው የውጭ ምደባ ዕድል እና የውጭ ተጋላጭነት ከሌሎች ሚኒስትር መ/ቤቶች በላይ ሰዎች በዛ እንዲቆዩ አድርጓቸው ይሆናል። አሁን ባለው የኑሮ ውድነት ግን እነዚህ ብቃት ያላቸው ዲፕሎማቶች በየትም ሥፍራ ከዛ ያልተናነሰ ማግኘት ይችላሉ። በተለይ በሀገር ውስት በሚቆዩባቸው አራት ዓመታት የሚሰጣቸው ደሞዝ እና የኑሮ ድጎማ አሳፋሪ ብቻ ሳይሆን ክብረ ነክ ነው። ግን የእነሱን ሞራል በማላሸቅ ብቻ የበላይ መሆን የሚችሉ ሰዎችን ሚኒስትር አድርጎ መንግስት ስለሚሾም ፥ እነዚህን ኢንቴሌክቿል ካሊበራቸው ከፍ ያለ ዲፕሎማቶችን ከመ/ቤቱ ለቀው እንዳይሄዱ የሚደረግ ምንም ጥረት የለም።



ከዛ ይልቅ የሊሴ ተማሪ እና የፈረንሳይኛ ተናጋሪ የሆነችውን የኢትዮጵያ በፓሪስ አምባሰደር ማህሌትን ከአትዮጵያ ኤርፖርት ወደ ምደባዋ ፈረንሳይ በምትሄድበት ሰዓት በመመለስ እና ባልታወቀ ምክንያት መውጣት አትችይም ብሎ በማፈን ሌሎች የብልጽግና አባል ያልሆኑ ዲፕሎማቶቹ በከፍተኛ ፍርሃት እና ለነገ ማረፊያቸው በማሰብ ውስጥ እንዲጠመዱ አድርጓቸዋል።

አክሊሉ ሀብተወልድን፣ ዶ/ር ሚናሴን፣ ከተማ ይፍሩን፣ ኮነሬል ጎሹን የሚያህሉ ለሀገር የከበዱ ሰዎች መሪ የሆኑበት ፥ እነ እጓለ ገብረዮሐንስ (የከፍተኛ ትምህርት ዘይቤ መጽሐፍ ጸሐፊ)፣ ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ ዲፕሎማት ኦፊሰር ሆነው የሰሩበት ያ ተቋም ዛሬ ሀሳቧን በአግባቡ መግለጽ በማትችል በብርቲካን አያኖ ሲመራ ማየት ያስደነግጣል።


ዛሬ ድረስ በከፍተኛ ሙያዊ ብቃት ዲፕሎማት ሆኖ የሚያገለግል አንድ አለቃዬ የነገረኝ እና በሕወኃት ዘመን መ/ቤቱን የለቀቀ አዕምሮ ብሩህ የሆነ የሕግ ባለሙያ ዲፕሎማት የተናገረውን የጹሁፌ መዝጊያ ላድርግ።



ይሄ የሕግ ባለሙያ መልቀቂያ እንዳስገባ ሲሰማ፣ አለቃዬ እንዳይለቅ ይማጸነዋል። በዘረኝነቱ ምንም ብትማረር ለኢትዮጵያ ግን ታስፈልጋታለህ ሲል ተማጸነው። “ይሄውልኽ የጭልፊትን እንቁላል ወስደው ለዶሮ አሳቀፉት። ሁሉም ተፈለፈሉ። ሲያየው በቁመት፣ በጉልበት፣ በክንፍ ጥንካሬ ከጫጩቶቹ ይለያል። ወገኖቹ አልመስሉት አለው። አሻግሮ ሲያይ ደግሞ እሱን የሚመስሉ የጭልፊት ጫጩቶች ተመለከተ። እነዚያ ይበራሉ። እሱንም ይመስላሉ። ሲመለከት እነዚህ አይበሩም ፥ ድኩማን ናቸው። ከዛ አይ የኔ ቦታ ከጭልፊቶች እንጂ ከጫጩቶች አይደለም ብሎ ለቆ ሄደ” አለው። የኔም ቦታ ከጭልፊቶች እንጂ ከጫጩቶች አይደለም ብሎ መስሪያቤቱን እስከወዲያኛው ለቀቀ። አሁን ያለው የኢትዮጵያ ዲፕሎማሲ እና የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ጭልፊቶችን የታቀፈች ዶሮ ይመስላል።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page