- Mulualem Getachew

- Aug 10
- 5 min read
የሰንበት ዕይታ - 15

በከተማችን ከ50 በላይ የሕግ ባለሙያዎች በሥሩ የሚያስተዳድር “Law Firm” እና የተለያዩ የሬስቶራንት ቢዝነሶች ያሉት አንጋፋ የሕግ ባለሙያ በየወሩ በርሱ ሕይወት ያስተዋለውን መንፈሳዊ ዕድገት እና ውጊያ አስመልክቶ ከ49 ለማይበልጡ የቅርብ ወዳጆቹ በሁለት ገጽ ሪፍሌክሽኑን ጽፎ በኢሜል ያሰራጫል። ከሁለት ወር በፊት ለዚህ ሰው ቅርብ በሆነ ወዳጄ አማካኝነት በዚህ የኢሜል ቡድን ውስጥ ለመካተትና የግለሰቡን ወርሃዊ ሪፍሌክሽን ለማግኘት ቻልኩ። አሁን የዚህን ግለሰብ ወራዊ ሪፍሌክሽን ስቀበል ሦስተኛዬ ነው። የግለሰቡን ስም ፈቃድ ስላላገኘው መጥቀስ አልችልም።
ወደ ዋናው ሃሳብ ሳልገባ በዚህ መግቢያ ላይ ግን ለአንባቢዎች ማስታወስ የምፈልገው አንድ ነገር አለ። በመንፈሳዊውም ሆነ አካዳሚያዊ ስመጥር አዋቂ በሆኑ ግለሰቦች መኃል በሕይወት ስለገጠማቸው መንፈሳዊም ሆነ ልዩ ልዩ ተግዳሮቶች ደብዳቤ መለዋወጥ በጣም የዳበረ ባህል መሆኑን። የስቶይክ ፍልስፍና ውስጥ ስመጥር ከሆኑት ኤፔክቲተስ፣ ሴኒካ፣ ማርከስ አሩሊየስ፣ ዳዮጄኒስ፤ እንዲሁም በክርስትና ደግሞ ቅዱስ ጳውሎስ፣ ቅዱስ አውግስጢን፣ ቅዱስ ባስሊዮስ፣ የኑሲሱ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ከቅርብ ሰዎቻቸው ጋር በደብዳቤ መወያየት፣ መከራከር እና ተግዳሮቶቻቸውን ማካፈል እጅግ የተለመደ ነገር ነበር። ያለ ሃሳብ ፍጭትና መሞራረድ ተጽዕኖ ፈጣሪ ቅዱሳንን ወይም ሀሳቢያንን ማግኘት የሚቻል አይመስልም።
በዚህ ወር ያካፈለንን ሀሳብ ተርጉሜ ላቅርብ። የዚህ ወር ርዕሱ “Trust” በሚል ነው። አማርኛው Trustንም faithንም እምነት ብሎ ነው የሚተረጉመው። ያ ግን ልክ አይመስለኝም። ለዚህ ጹሁፍ Trustን መደገፍ ብዬዋለሁ፣ faithን ደግም እምነት ብዬዋለሁ። መደገፍ ከዚህ በፊት ያለን ልምድ፣ እውቀት፣ ማስረጃ ይመረኮዛል። እምነት ግን ከዚህ በፊት ያለን እውቀት፣ ማስረጃ፣ ልምድ አይጠይቅም። በዚህም መደገፋችን ወደ እምነት ይወስደናል። በጥቂቱ ነገር ተደግፈን ስላየነው፣ ባላየነው ጉዳይ እናምነዋለን። በዚህም ተስፋ የምናደርገው ነገር በእምነት እውነት እንደሆነ እንቀበላለን። ማንም Trust የሌለው (ጠንካራTrust ወይም መደገፍ የሌለው) እምነት ሊኖረው አይችልም። ከአብርሃም (ዘፍጥረት 15) እስከ ጌዲዮን የሚነግሩን ሀቅ እንዲያምኑ መጀመሪያ መደገፍ እንዳለባቸው ነው። ስለዚህም መደገፋቸውን በማስረጃ እና በልምድ ካደረጉ በኋላ ያላዩትን ነገር እንደሚሆን አምነው ተቀበሉ። በተቃራኒው ከእምነት የወጡ ሰዎችን ስናይ ይሄ በእግዚአብሔር ላይ ያላቸው መደገፍ ወደ እምነት ያልወሰዳቸው ሰዎች ሆነው እናገኛለን። ማለትም ምንም ዓይነት ግለሰባዊ የመደገፍ ልምምድ የሌለው ሰው የጸና እምነት ሊኖረው አይችልም።
አንድ ጸሐፊ ስለ ዴማስ ጳውሎስን መክዳት ሲናገር፤ “ዴማስ ከቅዱስ ጳውሎስ ተሻግሮ ክርስቶስን ማየት ያልቻለ ተከታይ ነበር” ይላል። ቅዱስ ጳውሎስን ብቻ የሚያይ እና በዚያ የተወሰነ ሰው ክርስቲያን ሆኖ ለመጽናት ይቸገራል። ምክንያቱም ቅዱስ ጳውሎስ ሲታሰር፣ ሲገረፍ፣ ሲጋዝ፣ ሲወገር፣ ሲሰደድ ነው የሚያየው እንጂ እነዚህ መከራዎች ኃያል የሆነ ውሳጣዊ ደስታ እና ክርስቶስን የመምሰል እርካታ እንዳላቸው መመልከት አይችልም። ምክንያቱም ያ ደስታ ያ ግለሰብ እርሱም ከፈጣሪው ጋር በሚኖረው ግለሰባዊ ሕብረት ብቻ የሚገኝ ስለሆነ። ፊሊጶስ ናትናኤልን ያለው ይሄን ነው። “መጥተህ እይ!”፤ ቶማስ መጠራጠሩን ለሐዋርያት ሲናገር ፥ ሐዋርያት ምንም አላሉም። ለርሱም እነሱ ያዩትን እና የቀመሱትን ጌታን እንዲያይ እና እንዲቀምሰው ከመመኘት እና ከመጸለይ በቀር። ጌታዬ አምላኬ ማለት የምንችለው ስንቀምሰው ብቻ ነው። ይሄ ማንም የሚሰጠን አይደለም። በእርሱ ቸርነት እርሱን ያገኘች ነፍስ ብቻ ወደ እምነት ታድጋለች። ከመደገፍ (Trust) ወደ እምነት ትሸጋገራለች። በዚህ ወደ የሕግ ባለሙያው የመደገፍ (Trust) ሪፍሌክሽን ልሻገር። በዚህ ጹሁፍ በቅንፍ ውስጥ የማስቀምጣቸው የኔ ማብራሪያዎችን ነው።
ላለፉት ዓመታት እግዚአብሔር ፈቅዶልኝ ይሄን መንፈሳዊ ሪፍሌክሽን ማድረግ ከጀመርኩ ጀምሮ በመደገፍ (Trust) ጉዳይ በሁለት ዓመት አንዴ፣ አንዳንዴ ደግሞ በዓመት አንዴ ጽፌያለሁ። በመንፈሳዊ ሕይወት ዕድገት ውስጥ መደገፍ (trust) በጣም ትልቅ ትርጉም ያለው ጉዳይ ነው። በተለይ እንደ እኔ ላለ ሰው፣ ሁሉን ነገር መቆጣጠር ለሚፈልግ እና ራሴን እና በዙራዬ ያሉ ሰዎችን ለምሳሌ ሚስቴን፣ ልጆቼን ብቻ ለማምን ግለሰብ በእግዚአብሔር ላይ የመደገፍን (trust) ጉዳይ ዘወትር ራሴን ላስታውሰው ይገባል። በተለይ በከባድ ጊዜያት እግዚአብሔር ላይ መደገፍ በጣም ይከብደኛል፤ ነገሮችን በራሴ የምወጣ ይምስለኛል። “ለምንድነው በእግዚአብሔር የምደገፈው? ለምንድነው ችግሬን ለእግዚአብሔር አደራ ብዬ የምሰጠው?” የሚል ዓይነት ዝንባሌ ነው ያለኝ። እንደሚመስለኝ በዚህ ዓለም በእኔ ደረጃ ከፍተኛ ስኬት ላይ የደረሱ ሰዎች ፥ ልክ እንደኔው ችግራቸውን ለእግዚአብሔር የመተው እና በእርሱ የመደገፍ ከፍተኛ ተግዳሮት አለባቸው።
ስለ trust ብዙ ምሳሌዎችን መጥቀስ እችላለሁ። እንደ አባት ቶሎ ወደ አዕምሮዬ የሚመጣው ግን ልጆቼ ናቸው። ልጆቼን ማመን በጊዜ ሂደት ተምሬያለሁ። ልጆቼን ባምናቸውም የሆነ መከራ እና ችግር ውስጥ ራሳቸውን ይከታሉ የሚል ፍርሃት ስላለኝ ሁልጊዜ “check” አደርጋቸዋለሁ። ይሄን ፍጹም መታመን (trust) ትሉታላችሁ? በርግጥ ልጆቼን አምናቸዋለሁን? የፕሬዝዳንት ሬጋንን ታዋቂ ንግግር አስታውሳለሁ Trust but verify (እመን ግን አረጋግጥ)። የሚለውን። ይሄ የሚነግረኝ ጌታዬን እንደዛ በቅድመ ሁኔታ እንደማምነው ነው። አምነዋለሁ ግን ማረጋገጥ እፈልጋለሁ። ሁልጊዜ ቼክ አደርገዋለሁ። አንዳንዴ የራሴን መንገድ እጠቀማለሁ።
ክርስቲያኖች ግን እንዲህ አልተማርንም። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረን በፍጹም በርሱ ላይ እንድንደገፍ ነው። ይሄ የሚነገረኝ ሰው በእምነት ሲያድግ በእግዚአብሔር ላይ ያለው መደገፍም እየጨመረ እንደሚሄድ ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብን አስታውሱት። እምነት አለኝ የሚል ሥራ ግን የሌለው ሰው የሚያድን እምነት እንደሌለው ነው የነገረን (ያዕ 2፥14)። እምነት አለኝ ብሎ በእምነቱ ያልተደገፈ ሰው እምነቱ ከጌጥነት የተሻገረ ትርጉም የለውም።
ስለ መደገፍ (trust) ትክክለኛ ትርጉም ለማግኘት ብዙ ሞክሬያለሁ፣ ጥቂት የሚቀርብ ነገር ያገኘሁት “ጠንካራ መታመን፣ በዛ መታመን ላይ የተመሰረት ተግባር፣ መደገፍ” የሚል ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ከ150 ጊዜ በላይ መደገፍ (trust) ስለሚለው ቃል ተናግሯል። ስለእስራኤላውያን ማን ይረሳል፣ በአምላኩ በእግዚአብሔር ላይ ለመደገፍ ብዙ የተቸገረ ሕዝብ ነበር፣ ትንቢተ ኢሳይያስ፣ ትንቢተ ዳንኤል፣ ምሳሌ እነዚህ ሁሉ መደገፍ (trust) በሚል ቃል የተሞሉ አይደሉምን? የዮናስ መጽሐፍ በሙሉ በእግዚአብሔር ላይ መደገፍ ስለከበደው ነብይ አይደለምን? ነብዩ ነገሮችን ለእግዚአብሔር ሰጥቶ እንደታዘዘው መተግበር ከእርሱ እውቀት ጋር አልገጥም ብሎት ሲቸገር ነው የምናነበው!
በአዲስ ኪዳን ቅዱስ ጳውሎስ በእግዚአብሔር መታመን ስለሚያስገኘው ተስፋ እና ደስታ ጽፎልናል። (ሮሜ 15፥13)። በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 14፥1 ደግሞ ጌታችን ስለመታመን የሁልጊዜ ምርጤ የሆነውን ቃል ነግሮናል። “ልባችሁ አይታወክ” አለን ጌታችን። “ልባችሁ አይታወክ፤ በእግዚአብሔር እመኑ፥ በእኔም ደግሞ እመኑ።”
ታላቁ የመታመን ምሳሌ የትኛው እንደሆነ ታውቃላችሁ? የቃና ሠርግ ነው። የኢየሱስ እናት ማርያም “የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ አለቻቸው።”ድንግል ማርያም በኢየሱስ ላይ ምንም ጥርጣሬ የላትም። ምንም እንኳ ልጇን ያልተረዳችበት ጊዜ ቢኖርም። ታስታውሳላችሁ ጌታችን የ12 ዓመት ልጅ ሆኖ በመቅደስ ሲያስተምር፣ ከሦስት ቀን ፍለጋ በኋላ እናቱ ድንግል ማርያም እና ዮሴፍ ሲያገኙት የተሰማቸው ስሜት፤ መገረም ነበር፤ ከዛ በፊት ደግሞ የት እንዳለ ስላላወቁ የመጨነቅ ስሜት ወርሷቸው ነበር።
ምንድነው የድንግል ማርያም መታመን በቃናው ሠርግ ያመጣው? ወይን ብቻ መሰላችሁ፤ ከወይን ሁሉ የሚልቅ ወይን፣ ከብዛቱ የተትረፈረፈ፣ ከጥራቱ አቻ የሌለው ወይን የድንግል ማርያም በኢየሱስ መታመን ያመጣው ነው። “የሚላችሁን ሁሉ ስሙት” ነው ያለችው። (ድንግል ማርያም በቅዱስ ገብርኤል የቀረበላት ሠላምታ ግራ አጋብቷት ነበር፤ አንድ ቃል ግን ተናገረች ፥ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለም። በዚህ ዓለም የእግዚአብሔር ሥራ ግር ካላለን ገና ብዙ ነገር አልገባንም ማለት ነው። ማየት አልጀመርንም ማለት ነው። ብዙ፣ በጣም ብዙ የማንረዳው፣ ፈጽሞ የማይገባን ነገሮች አሉ። ግን ለእግዚአብሔር የሚሳነው፣ ለፍቅሩ የሚከብደው ነገር የለም። ይሄ ነው የእመቤታችን እምነት)። በእርሱ ስንደገፍ የምናገኘው ውጤት “ምንም አይልም “ይሁን” “0k” የሚያስብል ውጤት ሳይሆን ፥ እጅን አፍ ላይ የሚያስጭን፣ በዘርፉ ያሉ ባለሙያዎችን (የወይን ጠማቂውን) ጉድ የሚያስብል ነው። ባለሙያዎች ሳይቀር የሚደመሙበት ትሩፋት ነው የመደገፍ ውጤት።
(እግዚአብሔር እንዴት እንደሚሰራ በምልአት ማናችንም አናውቅም፤ ብዙ ጊዜ ያንንም እርሱ አያብራራም። ለኢዮብ መጨረሻ ላይ ሲገለጥለት ለምን እንደተፈተነ፣ ሰይጣን ስለጠየቀው ጥያቄ እና ለምን ያንን እንደፈቀደ ምንም ማብራሪያ አልሰጠውም። ይልቁስ ለኢዮብ ያለው እርሱ አንድን ቁራን የሚመግብ፣ ሰጎን የረሳቻቸውን ልጆቿን የሚያሳድግ እርሱ እግዚአብሔር እንደሆነ ነው የነገረው። ማለትም ለቁራዎች አይደለም፣ በግል ደረጃ ለቁራ የሚጨነቅ አምላክ የፍጥረቱ ሁሉ መደምደሚያ እና የእጆቹ ውብ ሥራ የሆነውን የሰው ልጅ ያውም ኢዮብን እንደምን ሊተወው እንደማይችል ነበር የነገረው። “እምነኝ እኔ የምሰራው ሁሌ ልክ ነው፣ ፍጹም አስብልሃለሁ” ነበር ያለው። ብዙ ጊዜ እግዚአብሔር የሚሰራው ነገር አይገባን ይሆናል፣ በርግጠኝነት ግን የምናውቀው ነገር እርሱ ልክ እንደሆነ ነው። የሆነ ሰው መጥቶ ሕጻናት ሲሞቱ የት ነው የሚገቡት አለኝ፤ አላውቅም አልኩት። አንድ ነገር ግን አውቃለሁ፤ የትም ይግቡ የትም ፥ እግዚአብሔር ልክ ነው።)
ስለዚህ ወንድሞች ሆይ በየቀኑ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ያለንን መደገፍ ለመጨመር እና ለማሳደግ አንሰራምን? በእምነት ቀስ እያልን ግን በየቀኑ እንደግ።
እስቲ እነዚህን ጥያቄዎች ራሳችሁን ጠይቁ፤
፩) ምንድን ናቸዉ በእግዚአብሔር እንዳልደገፍ እንቅፋት የሆኑኝ ምክንያቶች?
፪) በእግዚአብሔር ለመደገፍ ምን እርምጃዎችን (steps) ልውሰድ?
፫) በእግዚአብሔር ስደገፍ ከእርሱ ምን ልጠብቅ? ምንድነው ከእርሱ የምጠብቀው?
መልካሙን ሁሉ በክርስቶስ እመኝላችዋለሁ፤ አካባሪ ወዳጆ።







