top of page

የሰንበት ዕይታ - 6

ree

የአፍሪካ ልማት ባንክ ሁለት ከፍተኛ ኃላፊዎች በፋይናንስ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ ጠባቂዎች ታፍነው እንደተደበደቡ፣ ለዚህም ምክንያቱ ከ5.2 ሚሊዮን ዶላር በላይ ለባንኩ የኢትዮጵያ ባንክ በተጭበረበረ የባንክ አካውንት ማስገባቱ እና ያ በሚኒስትሩ እና በባንኩ የኢትዮጵያ ከፍተኛ ኃላፊዎች መካከል የተፈጠረ መካረር ለዚህ ድብደባ እና መታፈን እንደዳረጋቸው በማህበራዊ ሚዲያ ሲገለጽ ነበር። እ.ኤ.አ በኦክቶበር 30 2023 የአፍሪካ ልማት ባንክ ባወጣው መግለጫ ሁለት ከፍተኛ ኃላፊዎቹ ተደብድበው መታፈናቸውን ገልጾ፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉዳዩን ሲሰሙ ባደረጉት ፈጣን ጣልቃ ገብነት የታፈኑት ግለሶቦች መለቀቃቸውን ገልጿል። ነገር ግን ባንኩ በሰጠው መግለጫ ስለታፈኑበት ምክንያትም (ስለ 5.2 ሚሊዮን ዶላሩ) ሆነ በማህበራዊ ሚዲያ ስለተሰራጨው ዜና ከመታፈናቸው እና መደብደባቸው ውጪ ያለው ነገር የለም።



በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ ራሳቸው መኪና እየነዱ አህመድ ሽዴ እና ማሞ ምህረቱን አስከትለው የተደበደበው የባንኩ ኃላፊ ጋር እንደሄዱ እና በዚህም የአህመድ ሽዴ ጠባቂዎችን ደብዳቢዎቼ እነሱ ናቸው ብለው መለየታቸውን በማህበራዊ ሚዲያ ተገልጿል። ይሄን ግን በባንኩም መግለጫ አልተገለጸም፤ ታማኒነት ካላቸው የመረጃ ምንጮችም ማረጋገጥ አልቻልኩም። ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅም ጉዳት ቅነሳ (damage mitigation) በሚመስል መልኩ የራት ግብዣ ለተደብዳቢዎቹ አድርገዋል። ይሄ ሁሉ ግን ግለሰቦቹን ከሀገር ጥለው እንዳይወጡ አላደረጋቸውም።



በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ሚኒስትሮች በዚህ ደረጃ የሀገሪቷን አጠቃላይ ሉአላዊ ክብር እና ብሔራዊ ጥቅም የሚጎዳ ሥራዎችን የራሳቸውን ጠባቂ ተጠቅመው የሚያደርጉበት፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማያውቁበት ሁኔታ ይሄን የማድረግ ድፍረት ሚኒስትሮቹ ከገቡ ፥ ሀገሪቷ ያለችበትን ሥርዓት አልበኝነት የሚያሳይ ነው።



በዛሬ ጹሁፌ በጥቂቱ መዳሰስ የምፈልገው ኢትዮጵያ በዓብይ ዘመን የገባችበትን የዲፕሎማሲ ውድቀት እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መ/ቤትን ክሽፈት ነው።



ዓብይ ከሕወኃት የተረከበው የውጭ ጉዳይ መ/ቤት ኢትዮጵያን በጸጥታው ምክር ቤት ለአባልነት ያስመረጠ፣ በጎረቤት ሀገራትም ሆነ አጠቃላይ በአፍሪካ በብዙ መልኩ ዲፕሎማቲካዊ ተቀባይነቷ እየጨመረ የመጣ፣ በጸጥታ ጉዳይ፣ በስደት እና አከባቢያዊ ደህንነት (regional security) ፣ በኢኮኖሚ ልማት ከአፍሪካ የኢትዮጵያ ድምጽ የሚሰማበት ወቅት ነበር። በዓባይ ጉዳይ ከግብጽ እኩል ድምጻ የሚከበር ያደረጉ ዲፕሎማቶች ታይተዋል። በተለይ በኦሮሚያ እና በአማራ ክልል ከተቀሰቀሱት ሕዝባዊ ተቃውሞች በፊት የነበረው የሀገሪቷ ዲፕሎማሲያዊ ቁመና በብዙ መልኩ አመርቂ የሚባል ነበር። ይሄም ቢሆን ሀገራችን ካላት አቅም፣ ታሪካዊ ማንነቷ እና መድረስ ከምትችልበት ልዕልና አንጻር ሲነጻጸር በጣም ትንሽ ነበር። ነገር ግን ወደ ኋላ ተመልሰን ያለፈውን ስንገመግመው ግን፤ በብዙ መጠን የተለየ እና የሚደነቅ ነበር።



በውጭ ጉዳይ መ/ቤት ውስጥ ለብዙ ጊዜ ሰዎች በዲፕሎማሲ መስክ ይቀጠሩ የነበሩት ባላቸው አካዳሚያዊ ብቃት ወይም ፖለቲካው ቅርበት ነበር። በሕወኃት ዘመን ብዙ አካዳሚያዊ ብቃታቸውን ያስመዘገቡ ልጆች ቀጥታ ከዩኒቨርስቲዎችም ሆነ ከሌሎች መስሪያ ቤቶች በዝውውር መልክ ወደ ዲፕሎማሲው አገልግሎት ገብተዋል። በተመሳሳይ ለሕወኃት ባላቸው ታማኝነትም ይሄን ዘርፍ የተቀላቀሉ ሰዎች ነበሩ። የ1997ኑን ምርጫ ተከትሎ፤ ዲፕሎማሲውን በአካዳሚክ ብቃታቸው የተቀላቀሉ ሰዎች ለቅንጅት ባሳዩት ውግንና መስሪያቤቱ ጥልቅ የሆነ ግምገማ አድርጎ ቀላል የማይባሉ ዲፕሎማቶችን አባረረ። ከውጭም የተጠሩ ዲፕሎማቶች የሚገጥማቸውን ጠርጥረው ሳይመለሱ በዛው ከዱ።


ይሄ የ1997 ምርጭ ነው የውጭ ጉዳይን የዲፕሎማሲ መስክ በመጠኑም የቀየረው። ዛሬ ድረስ የካድሬው ቡድን የሚባለውን ስብስብ ወደ መስሪያ ቤቱ አስገባ። በበረከት ስምዖን መልማይነት ከየክልሉ ከዩኒቨርስቲ የተመረቁ እና በሰዓቱ ያላቸውን አካዳሚያዊ ብቃት በመጠራጠር ሥራ ላለማጣት ኢህአዴግን ተቀላቅለው የነበሩ ካድሬዎችን መስሪያ ቤቱ በዲፕሎማትነት አስገባቸው። እነዚህ የካድሬው ቡድኖች በ1997 የተባረሩትን እና የከዱትን ዲፕሎማቶች ለመተካት በዙር የገቡ ነበሩ። ይሄ የመስሪያ ቤቱን መልክ ቀየረው ፥ ምንአልባትም እስከወዲያኛው።


የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊን ሞት ተከቶሎ፤ ዶ/ር ቴዎድሮስ ወደ ሚኒስትርነት ሲመጣ ፥ ዲፕሎማሲው ገጥሞት የነበረው የሰው ኃይል ጥራት ኪሳራ ከፍተኛ የሚባል ነበር። የካድሬው ቡድን በአመዛኙ ኖት ቨርባል በእንግሊዘኛ መጻፍ የማይችል፣ ጆሮውን ቢቆርጡት እንግሊዘኛ የማይሰማ እና እምብዛም ‘critical thinking’ ችሎታ ያልነበረው ነበር (ከእነዚህ ውስጥ ጥቂት ብቃት ያላቸው ሰዎች ግን ነበሩ)። በዚህ ሰዓት ነው በአምባሳደር ብርሃነ ገብረክርስቶ አማካይነት (በሰዓቱ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የፖለቲካል ዘርፍ ስቴት ሚኒስትር የነበረ) አዳዲስ ዲፕሎማቶችን ለመመልመል ታቅዶ ወደ ሥራ ተገባ። በዚህም የዲፖሎማቲክ ማሰልጠኛ ተቋም ተቋቁሞ፣ በትምህርት ችሎታቸው ከ3.2 ጂፒኤ በላይ ያላቸው እና ሁለት ዙር ፈተና (አንድ የጹሁፍ አንድ የቃል) ተቀምጠው ማለፍ የቻሉ ወጣቶች ተቋሙን ተቀላቀሉ።


መስሪያ ቤቱ በካድሬው ቡድን እስከቴዎድሮስ መምጣት ድረስ ገጥሞት የነበረውን ከፍተኛ የሰው ኃይል ጥራት ክፍተት እነዚህ ወጣቶች በተወሰነ መጠንም ከአንድ ዓመት ስልጠና በኋላ ማስተንፈስ ቻሉ። ምንም እንኳ አብዛኞቹ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ፤ ጥቂቶች ደግሞ ከክልሎች ዩኒቨርስቲዎች ጥሩ ውጤት ያመጡ ልጆች ቢሆኑም፤ የሀገሪቱ የትምህርት ሥርዓት መላሸቅ ግን በአዲሶቹ ዲፕሎማቶች ጥራት ላይም የራሱ ጥላ ነበረው።



እነዚህ ዲፕሎማቶች ለመስሪያ ቤቱ እና ለሀገራችን ዲፕሎማሲ ውጤት ማምጣት በጀመሩበት የአራት እና አምስት ዓመታት ጊዜ ውስጥ ነው፤ የዓብይ መንግስት ሥልጣን የተረከበው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሥልጣን ላይ ከወጣ ቀን ጀምሮ ግልጽ ያደረገው ለውጭ ጉዳይ መ/ቤት በጎ ምልከታ እንደሌለው ነበር። ሰውዬውን በቅርብ ከሚያውቁ ሰዎች ጋር ስለዚህ ጉዳይ ማውራት ብችልም ምክንያቱ ግን ለእኔ ግልጽ አይደለም። አንድ ነገር ግን አውቃለው። ዓብይ አህመድ ሥርዓት እና ደንብ፣ ፕሮሲጀር ይጠየፋል። አንድን ነገር ለማድረግ ሥርዓት አለው፣ ሂደት አለው፣ ዘው ብለህ እንደፈቀድክ አታደርግም፣ ከአለባበስ እስከ ሰላምታ አሰጣጥህ፣ ከማንኛውም የሰውነት ቋንቋ እስከ መመገቢያ ጠረጴዛ ላይ ሹኪያ አቀማመጥህ ድረስ ትርጉም አለው የሚለውን የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤትን ደንብ እና ያን ዓይነት የሥርዓት አካሄድ ይጠየፋል። ነጮች እንደሚሉት ግለሰባዊ (personal) ነው የሚያደርገው። ለምሳሌ ጠቅላይ ሚንስትር መለስ ዜናዊ በፈረንሳይ ቤተመንስግት በተደረገለት ግብዣ ወቅት ምግቡን ቢጨርስም የሹኪያ አቀማመጡ ልክ ስላልነበረ አስተናጋጆቹ የመመገቢያ ሳህኑን ሳያነሱ ይቀራሉ፣ ይሄም ሁሉንም ሂደት ማስተጓገል ይጀምራል፣ ማለትም የሌሎች ሳህንም ሳይነሳ እና ወደ ውይይት ሳይገባ ደቂቃዎች ይነጉዳሉ። በዚህ ወቅት ነው የዛሬዋ ፕሬዝዳንት አምባሳደር ሳህለወርቅ ብድግ ብለው ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ይሄን ሲነግሯቸው ወዲያው ታርመው ሳህናቸው ሊነሳ እና ወደ ውይይት ሊገባ የተቻለው።



እነዚህን የመሰሉ ጥቃቅን ነገሮች በዲፕሎማሲ ትልቅ ውጤት አላቸው። ሀገሪቷ ሁሉ የራሱ ንብረት ነው የምትመስለው፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ ግን እነዚህ እንደተራ አላስፈላጊ ጉዳዮች ነው የሚያያቸው። ብድግ ብሎ ማቀፍ፣ ጺም ማሻሸት፣ ቀለበት ማድረግ፣ አጎንብሶ ማውራት፣ ቡና ማቅረብ ምንም ትርጉም ያለው አይመስለውም። ሲ ኤስ ሉዊስ ሰው ለሰውነት እንቅስቃሴው ትርጉም እንዳይሰጥ ማድረግ ትልቁ የሰይጣን ስትራቴጂ ነው ይላል። ምክንያቱም የሰው ነፍስ በሰውነቱ እንቅሳቃሴ የተወሰነች ናት። ያን ሰው ሲረሳ ነፍሱን ያደክማታል ይላል። ይሄን የሲ ኤስ ሉዊስ እዚህ ጋር ያነሳውት የኦክስፎርዱ ሊቅ ሉዊስ እንዴት የሰው አዕምሮ ከሰው ሰውነት ጋር የተያያዘ መሆኑን ካሳየበት በላይ ፥ የሺ ዘመን የዲፕሎማሲ ልምድን ያለምንም እውቀት እና ምርምር እንደተራ ኤቲኬት (etiquette) በመቁጠር ለማጥፋት መጣር ጥልቀት የሌላቸው ሰዎች ባህሪ መሆኑን ለማሳየትም ነው።



ዓብይ ወደ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ሲመጣ፤ የሲቪል ሰርቪስ ምሩቅ (የመመሪቂያ ወረቀቷን የሰራላት ባልደረባዬ ነው) የሆነችው እና በዘር ድልድል በካናዳ አምባሳደር ተደርጋ የተሾመችውን፣ ከዛም በከፍተኛ የአቅም ማነስ ክስ ከካናዳ አምባሳደርነት ተነስታ፣ ውጪ ጉዳይ መስሪያ ቤት በተራ ሠራተኝነት ሳይቀር አልቀበላት ብሎ፤ ኦሮሚያ ክልል የጸረ ሙስና ኮሚሽን ውስጥ የተቀጠረችውን አምባሳደር ብርቱካን አያኖ ዳዲን ውጪ ጉዳይ ስቴት ሚኒስትር አድርጎ ጉብ አደረጋት። የሷ ሹፌር የነበረው እንዳጫወተኝ ፥ በገዱ አድርጋቸው ጊዜ ቤተመንግስት ዓብይ ጋር ሳትሄድ የምትውልበት ቀናት ጥቂት ነበሩ። በተለይ በፕሮቴስታንት እምነት ምክንያት ከዓብይ ሚስት ዝናሽ ጋር የቀረበ ግንኙነት አላት። የተቀመጠችበ ዘርፍ የሰው ኃይል ሚኒስቴር ዴኤታ ቢሆንም (ምንም የዲፕሎማሲ፣ የፖለቲካል እና የኢኮኖሚ ጉዳዮች የማይመለከቷት ቢሆንም) ከሚኒስትር ደመቀ መኮንን በላይ ከዓብይ አህመድ ጋር የዞረችው እርሷ ነች። ይሄ ማለት የፖለቲካ ዘርፍ ሚኒስትሩ አምባሳደር ምስጋናው እያለ ማለት ነው። በቅርብ ወደ አንድ ዲፕሎማት ጓደኛዬ ደውዬ ስለደመቀ ስጠይቀው ከዚህ በፊት ያለኝን ነው የነገረኝ፤ ምን ባክህ “እሱ የብርቱካን ልጣጭ ነው።”



ዓብይ አህመድ መስሪያ ቤቱን ያዳከመበት መንገድ አንዱ ምንም ስለውጪ ጉዳይ እውቀትም ሆነ ልምድ፣ የሥራ ተጋላጭነትም የሌለውን ገዱ አዳርጋቸውን ከላይ አስቀምጦ ፥ ሌላ ከገዱ የባሰች ሴትዮን በሚኒስትር ቦታ አስፍሮ በውስጡ ያሉ ብቃት ያላቸው ዲፕሎማቶች እንዲማረሩ እና የውጭ ጉዳይ አገልግሎት በጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት ጥገኛ እንዲሆን ነበር። በርግጥ ገዱ አንዳርጋቸው የመ/ቤቱን ክብር ለማስጠበቅ፣ ከጠቅላይ ሚኒስቴር ጽ/ቤት የሚደርስበትን ጫና ተቋቁሞ፣ ብዙ ሙያተኞች ከውስጥ እንዲያድጉ ያደረገ ሰው ነበር። በዚህም ሙያተኞችን በመስማት እና ቦታ በመስጠቱ የሚያመሰግኑት ቀላል የማይባሉ ናቸው።



 በዚህ ወቅት የትግራይ ጦርነት መጣ። ቀላል የማይባሉ ብቃት ያላቸው የትግራይ ልጆች ደግሞ በዲፕሎማሲው መስክ ነበሩ። መንግስት እነዚህ ዲፕሎማቶች ተቋሙን ተጠቅመው ሕወኃትን እያገዙ እና የመንግስትን የዲፕሎማሲ አቅም እያዳከሙ እንደሆነ መረጃ ይደርሰዋል። በዚህም ዘዴ ተፈየደ። መንግስት ነጥሎ አንድን ብሔር ከሚያባር ፥ ሂድ አትበለው እንዲሄድ አድርገው የሚል ዘዴ። ማለትም ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ እ.ኤ.አ በጁላይ 5 2021 ዓ.ም. ፓርላማ ተገኝቶ አብዛኛው ኤምባሲ እንደሚዘጋ እና ዲፕሎማቶችም ከሀገራቸው ሆነው እንደሚያገለግሉ ለፓርላማው ገለጻ አደረገ።


ይሄን የሰሙ የትግራይ ተወላጆች የሆኑ ዲፕሎማቶች ወደ ሀገር ሳይመለሱ በዛው ቀሩ። ቀላል የማይባሉ የኦሮሞ ተወላጆች ሳይቀር ፥ ወደ ሀገር ቤት ተመልሶ ከሀገር ቤት የሚሰራ ዲፕሎማሲ አልታይ ስላላቸው በዛው ሳይመጡ ቀሩ። ነገር ግን መንግስት በዋነኝነት ይሄን ያደረገው ለማጥራት ስለነበረ፤ ወደ ሀገር ቤት የተጠሩት አብዛኛው ዲፕሎማቶች ተመልሰው ተመደቡ። ከጥቂቶች በቀር ብዙም ኤምባሲዎች ሳይዘጉ ቀሩ (ቆንስሎች በአብዛኛው ተዘግተዋል)።



በተለይ በዶ/ር ቴዎድሮስ ዘመን ተመልምለው በብቃታቸው የገቡ ወጣት ዲፕሎማቶች ወደ ሀገራቸው ሳይመለሱ ቀርተዋል። የእነዚህ ልጆች አንዱ ብቃት ማሳያ ቀላል የማይባሉ ወጣት ዲፕሎማቶች በአሜሪካ Ivy league ስኩሎች ሳይቀር (እንደ ኮሎምቢያ እና ኖተርዳም) ሙሉ ስኮላርሽፕ አግኝተው ዛሬ እየተማሩ ያሉ መኖራቸው ነው፤ አንዳንዶቹም ፕሮፌሽናል ሥራ ላይ ተቀጥረው ጥሩ ተከፋዮች ሆነው የሚሰሩ ሆነዋል። እነዚህን ነው ኢትዮጵያ ያጣችው። ከትግራይ ጦርነት በኋላ ያለው ዲፕሎማሲ አቅሙ የላሻቀ፣ በጠቅላይ ሚኒስትሩ በጎ ፍቃድ የሚመራ፣ በውጭ ጉዳይ ደግሞ ለብርቱካን አያኖ የማይሰግድ እና ወሬ የማያቀብል የዲፕሎማሲ ዕድገቱ አደጋው ውስጥ የገባበት፣ ተቋሙ ወጣት ብቃት ያላቸው ዲፕሎማቶች ገብተው ፍሬያቸው መታየት ሲጀምር ፥ ጨለማ ውስጥ ተመልሶ የገባበት ሆኗል።



በውጭ ጉዳይ በነበረኝ ቆይታ ሁሉንም ሊባል በሚችል ደረጃ ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ የሚኒስትር መስሪያቤቶችን ጎብኝቻለው፣ አይቻለው። በአንድ ወቅት ከአውስትራሊያ የመጣ እንግዳ ይዜ የኦሮሚያ ፕሬዝዳንት ቢሮ ውስጥ ስገባ፤ ጸሐፊዋ የቡና ሲኒዎችን በሳፋ አድርጋ የቢሮ ጠረጴዛ ላይ ታጥባለች። በቀጠሮ እንደመጣን ነግሬያት፣ በዚህ ሰዓት ይሄን ማድረጓ ለገጽታ ነውር እንደሆነ ስነግራት፣ ሳፋውን ይዛ የቢሮው መስኮት ላይ ራሷን በመጋረጃ ከልላ ማጠቧን ቀጠለች።

ይሄን የጠቀስኩት፣ በትዝብቴ ሁሉ ያየውት በሥርዓት በመስራት፣ ከቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመን ጀምሮ ሀገራቸውን በከፍተኛ ሙያዊ ብቃት ሲያገለግሎ የነበሩ እንደ ጋሽ ውሂብ ሙሉነህ ያሉ ድንቅ ሙያተኞችን የምታገኙበት፣ ስለኢትዮጵያ የትኛውም ድንበር እና የድንበር ውል ጥያቄ ሲኖራቹሁ በራቸውን አንኳኩታችሁ መጠየቅ ብቻ የሚጠበቅባችሁ ድንቅ ሰዎች የነበሩበት መስሪያ ቤት አላየውም። አልገጠመኝም።



ከልባቸው ሀገራቸውን የሚያገለግሉ፣ ከእውቀት ያልተነጠሉ ሰዎች ለብዙ ዘመን ሲሰሩ የምታገኙበት በኢትዮጵያ ውስጥ ውጭ ጉዳይ መ/ቤት ነው። እውነት ነው ዲፕሎማሲው የሚሰጠው የውጭ ምደባ ዕድል እና የውጭ ተጋላጭነት ከሌሎች ሚኒስትር መ/ቤቶች በላይ ሰዎች በዛ እንዲቆዩ አድርጓቸው ይሆናል። አሁን ባለው የኑሮ ውድነት ግን እነዚህ ብቃት ያላቸው ዲፕሎማቶች በየትም ሥፍራ ከዛ ያልተናነሰ ማግኘት ይችላሉ። በተለይ በሀገር ውስት በሚቆዩባቸው አራት ዓመታት የሚሰጣቸው ደሞዝ እና የኑሮ ድጎማ አሳፋሪ ብቻ ሳይሆን ክብረ ነክ ነው። ግን የእነሱን ሞራል በማላሸቅ ብቻ የበላይ መሆን የሚችሉ ሰዎችን ሚኒስትር አድርጎ መንግስት ስለሚሾም ፥ እነዚህን ኢንቴሌክቿል ካሊበራቸው ከፍ ያለ ዲፕሎማቶችን ከመ/ቤቱ ለቀው እንዳይሄዱ የሚደረግ ምንም ጥረት የለም።



ከዛ ይልቅ የሊሴ ተማሪ እና የፈረንሳይኛ ተናጋሪ የሆነችውን የኢትዮጵያ በፓሪስ አምባሰደር ማህሌትን ከአትዮጵያ ኤርፖርት ወደ ምደባዋ ፈረንሳይ በምትሄድበት ሰዓት በመመለስ እና ባልታወቀ ምክንያት መውጣት አትችይም ብሎ በማፈን ሌሎች የብልጽግና አባል ያልሆኑ ዲፕሎማቶቹ በከፍተኛ ፍርሃት እና ለነገ ማረፊያቸው በማሰብ ውስጥ እንዲጠመዱ አድርጓቸዋል።

አክሊሉ ሀብተወልድን፣ ዶ/ር ሚናሴን፣ ከተማ ይፍሩን፣ ኮነሬል ጎሹን የሚያህሉ ለሀገር የከበዱ ሰዎች መሪ የሆኑበት ፥ እነ እጓለ ገብረዮሐንስ (የከፍተኛ ትምህርት ዘይቤ መጽሐፍ ጸሐፊ)፣ ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ ዲፕሎማት ኦፊሰር ሆነው የሰሩበት ያ ተቋም ዛሬ ሀሳቧን በአግባቡ መግለጽ በማትችል በብርቲካን አያኖ ሲመራ ማየት ያስደነግጣል።


ዛሬ ድረስ በከፍተኛ ሙያዊ ብቃት ዲፕሎማት ሆኖ የሚያገለግል አንድ አለቃዬ የነገረኝ እና በሕወኃት ዘመን መ/ቤቱን የለቀቀ አዕምሮ ብሩህ የሆነ የሕግ ባለሙያ ዲፕሎማት የተናገረውን የጹሁፌ መዝጊያ ላድርግ።



ይሄ የሕግ ባለሙያ መልቀቂያ እንዳስገባ ሲሰማ፣ አለቃዬ እንዳይለቅ ይማጸነዋል። በዘረኝነቱ ምንም ብትማረር ለኢትዮጵያ ግን ታስፈልጋታለህ ሲል ተማጸነው። “ይሄውልኽ የጭልፊትን እንቁላል ወስደው ለዶሮ አሳቀፉት። ሁሉም ተፈለፈሉ። ሲያየው በቁመት፣ በጉልበት፣ በክንፍ ጥንካሬ ከጫጩቶቹ ይለያል። ወገኖቹ አልመስሉት አለው። አሻግሮ ሲያይ ደግሞ እሱን የሚመስሉ የጭልፊት ጫጩቶች ተመለከተ። እነዚያ ይበራሉ። እሱንም ይመስላሉ። ሲመለከት እነዚህ አይበሩም ፥ ድኩማን ናቸው። ከዛ አይ የኔ ቦታ ከጭልፊቶች እንጂ ከጫጩቶች አይደለም ብሎ ለቆ ሄደ” አለው። የኔም ቦታ ከጭልፊቶች እንጂ ከጫጩቶች አይደለም ብሎ መስሪያቤቱን እስከወዲያኛው ለቀቀ። አሁን ያለው የኢትዮጵያ ዲፕሎማሲ እና የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ጭልፊቶችን የታቀፈች ዶሮ ይመስላል።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 3 min read

የሰንበት ዕይታ - 11

ree

ሰዎች ስኬታማ ሕይወት ለመምራት ይፈልጋሉ ወይም ይጥራሉ። ብዙ ሰዎች ለተመሳሳይ ግብ በሚሮጡበት ዓለም ያን ግብ ማሳካት በጣም ከባድ ነው። ሳይንቲስቶች ችግር ሲገጥማቸው ፥ ከዛ ችግር ለመውጣት የሚጠቀሙበት ጥሩ ጥያቄ አላቸው። ይሄም “ምንድነው ለማሶገድ እየጣርኩ ያለውት?” የሚለውን ጥይቄ ነው። የምንሰራቸውን ሥራዎች ሁሉ ከማድረጋችን በፊት ይሄን ጥይቄ እንጠይቅ። “ምንድነው ግን ይሄን ሥራ በመስራት ለማሶገድ እየጣርኩኝ ያለውት?” ለምሳሌ ሀብታም ለመሆን እንፈልግ ይሆናል። ሀብታም ለመሆን የምንጥረው ምን ለማሶገድ ነው?


ብዙዎቻችን ዋነኛ ፍላጎታችን ድህነትን ማሶገድ ነው። ይሄ አስተሳሰብ የሚረዳን ሀብታም ላለመሆን እንቅፋት የሆኑብንን ቀላል ነገሮችን ያሶግድልናል። ድሀ ላለመሆን ቀላሉ ነገር ፥ “ከምታስገባው በላይ አለማውጣት ነው፣ ከፍተኛ ኢንተረስት ሬት ያላቸውን ብድሮች ማሶገድ ወይም ቶሎ ከፍሎ መገላገል፣ መቆጠብ መጀመር ነው”፥ እነዚህ ቀላል ነገሮች የመጀመሪያውን በሽታ ያሶግዳሉ። እሱም ድሀ መሆንን። ይሄን ጥይቄ በሌሎች ስራችንም ላይ እንጠይቅ። ለምሳሌ ለሰው በጣም ትለፊያለሽ ፥ በዚህም የራስሽን ጤና አደጋ ውስጥ ሁሉ ትከችያለሽ። “ምን ለማሶገድ ነው ይሄን ሁሉ የሆንሽው?” ምን አልባት ያ ሰው እንዳይቀየምሽ ወይም ያ ሰው እንዳይታዘብሽ ይሆናል ይሄን ሁሉ ክፍያ የከፈልሽው። ስለዚህ መቀየምን ለማሶገድ ራስን ጎድቶ የሆነ ነገር ከማድረግ ውጪ ያለ ሌላ አማራጭ የለም? በግልጽ ማውራት፣ ያለብሽን ፈተና ለዛ ሰው ማስረዳት የበለጠ እንዲወድሽ ሊያደርግ ሁሉ ይችላል። ብዙ ጊዜ ግን እኛ የምናደርገው ይሄን ነው፤ የሆነ ነገር ለማድረግ እናስባለን። ከዛ እሱን ለማድረግ የሚያስችሉ ነገሮችን እንሰራለን። ለምን ማድረግ እንደፈለግን ወይም ምን ለማስቀረት እየጣርን እንደሆነ አናስብም። ከዛ በዋናነት ደግሞ የምንፈልገውን ነገር ለማሳካት “ምን እንቅፋት ሊሆነን እንደሚችል” ፈጽሞ አንገምትም።



 ለምሳሌ ጥሩ እንቅልፍ ለመተኛት እናስባለን። ለዚህ የሚያስፈልገው ጥሩ አልጋ እና ወደ አልጋ መሄድ ላይ ብቻ ይሆናል የምናተኩረው። ጥሩ አሳቢ ስንሆን ግን ሦስተኛ ደረጃ እርከንን እናስባለን። “ጥሩ እንቅልፍ ላለመተኛት እንቅፋት የሚሆኑ ነገሮች ምንድናቸው?” የሚለውን። “ስልክ ይዞ ወደ አልጋ መሄድ፣ ከስልክ እና ከቲቪ የሚወጣው ብሉ ላይት፣ በማታ ፕሮቲን ያለበት ምግብ መብላት፣ እንቅስቃሴ አለማድረግ”፤ ስለጥሩ እንቅልፍ ስናስብ እነዚህ ነገሮች ቶሎ አዕምሮአችን ውስጥ አይመጡም። ምክንያቱም ብዙ ጊዜ የምናስበው አንድን ነገር ስለማሳካት ነው እንጂ ምን ነገሮች ያን ነገር ከማሳካት እንደሚያሰናክሉት አይደለም።



ቻርሊ መንገር አንድ የሚለው ጥሩ አባባል አለው። “ማወቅ የምፈልገው ብቸኛ ነገር የት እንደምሞት ነው፤ ስለዚህ እዛ ፈጽሞ አልሄድም።” ይሄ ነገሮችን ገልብጦ የማሰብ ዘይቤ የመነጨው ካርል ጉስቶቭ ጃኮብ ከተባለው የጀርመን የሒሳብ ሊቅ ነው። ጃኮብ ከባባድ የሆኑ የሒሳብ ጥያቄዎችን የፈታው በቀላል ስትራቴጂ ነው። “man muss immer umkehren” (invert, always invert) “ገልብጠው፣ ሁልጊዜ ገልብጠው” እንደማለት ነው። ጃኮብ የተገነዘበው ነገር ብዙ የሕይወት ውጣ ውረዶች የሚፈቱት ነገሮችን ከኋላ ወደፊት በመመልከት እንደሆነ ነው። ብዙ ችግሮች ከችግሩ ተነስተን ወደፊት (forward thinking) በማሰብ የሚፈቱ አይደሉም። መገልበጥ ይሻሉ።



ለምሳሌ በተቋማቹ ውስጥ የፈጠራን ክህሎት ማዳበር ትፈልጋላችሁ። ፈጠራን ለማዳበር ማድረግ ያለባችሁን ዘርዝራችሁ ታስባላችሁ። ወደፊት ማሰብ ማለት ነው። ግን ይሄን ጉዳይ ገልብጣችሁ እዩት። “ፈጠራን ለማቀጨጭ ወይም ለማዳከም ምን ምን ማድረግ አለብን?” ብላችሁ አስቡ እስቲ። ቢሳካላችሁ እነዚህ ፈጠራን የሚያቀጭጩ ተግባሮችን አለማድረግ ነው። በተመሳሳይ “ምንድነው ጥሩ ሕይወትን የሚሰጠን? የሚለውን ከማሰብ ይልቅ “ምንድነው መጥፎ ሕይወት እንዲኖረን የሚያደርገው?” የሚለውን አስቡ። እርግጠኛ ነኝ ብዙዎቻችን መጥፎ ሕይወት እንዲኖረን የሚያደርጉ ብዙ ሥራዎችን ዛሬ እየሰራን ነው። ማህበራዊ ሚዲያ ከተገቢው መጠን በላይ ከመጠቀም ጀምሮ።



በሕይወት ውስጥ ትልቅ ቦታ የሚያደርሰን ስማርት ወይም ብሩሕ አዕምሮ እንዲኖረን በመጣር አይደለም። ደደብ ነገሮችን ከመስራት በመቆጠብ ነው። ለምሳሌ “ኢትዮጵያን ከድህነት የሚያላቃት ምንድነው?” ብላችሁ ከምታስቡ “ኢትዮጵያን ድህ አድርጎ ሊያስቀራት የሚችለው ምንድነው?” ብላችሁ አስቡ። ይሄን ጥያቄ ሁላችን በቀላሉ እንመልሰዋለን። በእርስ-በርስ ጦርነት የሚታመስ ሀገር መቼም ቢሆን በልጽጎ አያቅም። አንድ ሀገር መጥቀስ የሚችል የለም። ሀገራትን ወደ ብልጽግና ለመምራት ግን መቶ አይነት እርስ በእርሱ የሚጋጩ የብልጽግና ንድፈ ሀሳቦችን እና ፍልስፍናዎችን ልታመጡ ትችላላቹ። አንዱን መርጣችሁ በሀገራችን በደንብ ልትተገብሩ ትችላላችሁ። ነገር ግን ሀገራትን ድሀ አድርጎ የሚያስቀርን ዋነኛ ድድብናን፣ ማለትም የእርስ በእርስ ጦርነትን እስካላቆምን ድረስ ብልጽግና የሕልም እንጀራ ነው። መቶ ጊዜ ስፖርት ብትሰራ፣ አጥንትህን የሚያዳክሙ ምግቦችን ከመመገብ እስካላቆምክ ወይም በሽታህን እስካልታከምክ ድረስ ስፖርት በመስራትህ ብቻ ጠንካራ አጥንት አይኖርህም። በተመሳሳይ “ምንድነው ጠንካራ ሀገር እንዲኖረኝ የሚያደርገው?” የሚለውን ትንታኔ ለጊዜው ገታ አድርግ እና “ምን ባደርግ ነው ደካም ሀገር የምፈጥረው?” ብለህ ጠይቅ። ከዛ እነዛን ነገሮች ከመስራት ተቆጠብ።



ይሄ አስተሳሰብ ነው ዋረን በፌትን ከግማሽ ምዕተ ዓመት በላይ የአሜሪካንን የቢዝነስ ኢምፓየር እንዲመራ ያስቻለው። ድድብናችንን ማስቀረት ካልቻልን፣ ማለትም የምንሞትበትን ቦታ አውቀን ወደ ዛ መሄድ እስካላቆምን ፥ ብልሃታችን ከመጥፋት አይታደገንም።

ይሄ ደካማ አስተሳሰብ ነው ደርግንም ሆነ ዐብይን የጦር ሠልፍ በማሳየት እንዲጠመዱ ያደረጋቸው። ድድብናን ማሶገድ ሳይሆን ፥ ጉልበትን ማጠንከር ይመስላቸዋል የአሸናፊነት ምስጢር። ፈጽሞ።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 5 min read

የሰንበት ዕይታ - 15

ree

በከተማችን ከ50 በላይ የሕግ ባለሙያዎች በሥሩ የሚያስተዳድር “Law Firm” እና የተለያዩ የሬስቶራንት ቢዝነሶች ያሉት አንጋፋ የሕግ ባለሙያ በየወሩ በርሱ ሕይወት ያስተዋለውን መንፈሳዊ ዕድገት እና ውጊያ አስመልክቶ ከ49 ለማይበልጡ የቅርብ ወዳጆቹ በሁለት ገጽ ሪፍሌክሽኑን ጽፎ በኢሜል ያሰራጫል። ከሁለት ወር በፊት ለዚህ ሰው ቅርብ በሆነ ወዳጄ አማካኝነት በዚህ የኢሜል ቡድን ውስጥ ለመካተትና የግለሰቡን ወርሃዊ ሪፍሌክሽን ለማግኘት ቻልኩ። አሁን የዚህን ግለሰብ ወራዊ ሪፍሌክሽን ስቀበል ሦስተኛዬ ነው። የግለሰቡን ስም ፈቃድ ስላላገኘው መጥቀስ አልችልም።

ወደ ዋናው ሃሳብ ሳልገባ በዚህ መግቢያ ላይ ግን ለአንባቢዎች ማስታወስ የምፈልገው አንድ ነገር አለ። በመንፈሳዊውም ሆነ አካዳሚያዊ ስመጥር አዋቂ በሆኑ ግለሰቦች መኃል በሕይወት ስለገጠማቸው መንፈሳዊም ሆነ ልዩ ልዩ ተግዳሮቶች ደብዳቤ መለዋወጥ በጣም የዳበረ ባህል መሆኑን። የስቶይክ ፍልስፍና ውስጥ ስመጥር ከሆኑት ኤፔክቲተስ፣ ሴኒካ፣ ማርከስ አሩሊየስ፣ ዳዮጄኒስ፤ እንዲሁም በክርስትና ደግሞ ቅዱስ ጳውሎስ፣ ቅዱስ አውግስጢን፣ ቅዱስ ባስሊዮስ፣ የኑሲሱ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ከቅርብ ሰዎቻቸው ጋር በደብዳቤ መወያየት፣ መከራከር እና ተግዳሮቶቻቸውን ማካፈል እጅግ የተለመደ ነገር ነበር። ያለ ሃሳብ ፍጭትና መሞራረድ ተጽዕኖ ፈጣሪ ቅዱሳንን ወይም ሀሳቢያንን ማግኘት የሚቻል አይመስልም።



በዚህ ወር ያካፈለንን ሀሳብ ተርጉሜ ላቅርብ። የዚህ ወር ርዕሱ “Trust” በሚል ነው። አማርኛው Trustንም faithንም እምነት ብሎ ነው የሚተረጉመው። ያ ግን ልክ አይመስለኝም። ለዚህ ጹሁፍ Trustን መደገፍ ብዬዋለሁ፣ faithን ደግም እምነት ብዬዋለሁ። መደገፍ ከዚህ በፊት ያለን ልምድ፣ እውቀት፣ ማስረጃ ይመረኮዛል። እምነት ግን ከዚህ በፊት ያለን እውቀት፣ ማስረጃ፣ ልምድ አይጠይቅም። በዚህም መደገፋችን ወደ እምነት ይወስደናል። በጥቂቱ ነገር ተደግፈን ስላየነው፣ ባላየነው ጉዳይ እናምነዋለን። በዚህም ተስፋ የምናደርገው ነገር በእምነት እውነት እንደሆነ እንቀበላለን። ማንም Trust የሌለው (ጠንካራTrust ወይም መደገፍ የሌለው) እምነት ሊኖረው አይችልም። ከአብርሃም (ዘፍጥረት 15) እስከ ጌዲዮን የሚነግሩን ሀቅ እንዲያምኑ መጀመሪያ መደገፍ እንዳለባቸው ነው። ስለዚህም መደገፋቸውን በማስረጃ እና በልምድ ካደረጉ በኋላ ያላዩትን ነገር እንደሚሆን አምነው ተቀበሉ። በተቃራኒው ከእምነት የወጡ ሰዎችን ስናይ ይሄ በእግዚአብሔር ላይ ያላቸው መደገፍ ወደ እምነት ያልወሰዳቸው ሰዎች ሆነው እናገኛለን። ማለትም ምንም ዓይነት ግለሰባዊ የመደገፍ ልምምድ የሌለው ሰው የጸና እምነት ሊኖረው አይችልም።



አንድ ጸሐፊ ስለ ዴማስ ጳውሎስን መክዳት ሲናገር፤ “ዴማስ ከቅዱስ ጳውሎስ ተሻግሮ ክርስቶስን ማየት ያልቻለ ተከታይ ነበር” ይላል። ቅዱስ ጳውሎስን ብቻ የሚያይ እና በዚያ የተወሰነ ሰው ክርስቲያን ሆኖ ለመጽናት ይቸገራል። ምክንያቱም ቅዱስ ጳውሎስ ሲታሰር፣ ሲገረፍ፣ ሲጋዝ፣ ሲወገር፣ ሲሰደድ ነው የሚያየው እንጂ እነዚህ መከራዎች ኃያል የሆነ ውሳጣዊ ደስታ እና ክርስቶስን የመምሰል እርካታ እንዳላቸው መመልከት አይችልም። ምክንያቱም ያ ደስታ ያ ግለሰብ እርሱም ከፈጣሪው ጋር በሚኖረው ግለሰባዊ ሕብረት ብቻ የሚገኝ ስለሆነ። ፊሊጶስ ናትናኤልን ያለው ይሄን ነው። “መጥተህ እይ!”፤ ቶማስ መጠራጠሩን ለሐዋርያት ሲናገር ፥ ሐዋርያት ምንም አላሉም። ለርሱም እነሱ ያዩትን እና የቀመሱትን ጌታን እንዲያይ እና እንዲቀምሰው ከመመኘት እና ከመጸለይ በቀር። ጌታዬ አምላኬ ማለት የምንችለው ስንቀምሰው ብቻ ነው። ይሄ ማንም የሚሰጠን አይደለም። በእርሱ ቸርነት እርሱን ያገኘች ነፍስ ብቻ ወደ እምነት ታድጋለች። ከመደገፍ (Trust) ወደ እምነት ትሸጋገራለች። በዚህ ወደ የሕግ ባለሙያው የመደገፍ (Trust) ሪፍሌክሽን ልሻገር። በዚህ ጹሁፍ በቅንፍ ውስጥ የማስቀምጣቸው የኔ ማብራሪያዎችን ነው።



ላለፉት ዓመታት እግዚአብሔር ፈቅዶልኝ ይሄን መንፈሳዊ ሪፍሌክሽን ማድረግ ከጀመርኩ ጀምሮ በመደገፍ (Trust) ጉዳይ በሁለት ዓመት አንዴ፣ አንዳንዴ ደግሞ በዓመት አንዴ ጽፌያለሁ። በመንፈሳዊ ሕይወት ዕድገት ውስጥ መደገፍ (trust) በጣም ትልቅ ትርጉም ያለው ጉዳይ ነው። በተለይ እንደ እኔ ላለ ሰው፣ ሁሉን ነገር መቆጣጠር ለሚፈልግ እና ራሴን እና በዙራዬ ያሉ ሰዎችን ለምሳሌ ሚስቴን፣ ልጆቼን ብቻ ለማምን ግለሰብ በእግዚአብሔር ላይ የመደገፍን (trust) ጉዳይ ዘወትር ራሴን ላስታውሰው ይገባል። በተለይ በከባድ ጊዜያት እግዚአብሔር ላይ መደገፍ በጣም ይከብደኛል፤ ነገሮችን በራሴ የምወጣ ይምስለኛል። “ለምንድነው በእግዚአብሔር የምደገፈው? ለምንድነው ችግሬን ለእግዚአብሔር አደራ ብዬ የምሰጠው?” የሚል ዓይነት ዝንባሌ ነው ያለኝ። እንደሚመስለኝ በዚህ ዓለም በእኔ ደረጃ ከፍተኛ ስኬት ላይ የደረሱ ሰዎች ፥ ልክ እንደኔው ችግራቸውን ለእግዚአብሔር የመተው እና በእርሱ የመደገፍ ከፍተኛ ተግዳሮት አለባቸው።



ስለ trust ብዙ ምሳሌዎችን መጥቀስ እችላለሁ። እንደ አባት ቶሎ ወደ አዕምሮዬ የሚመጣው ግን ልጆቼ ናቸው። ልጆቼን ማመን በጊዜ ሂደት ተምሬያለሁ። ልጆቼን ባምናቸውም የሆነ መከራ እና ችግር ውስጥ ራሳቸውን ይከታሉ የሚል ፍርሃት ስላለኝ ሁልጊዜ “check” አደርጋቸዋለሁ። ይሄን ፍጹም መታመን (trust) ትሉታላችሁ? በርግጥ ልጆቼን አምናቸዋለሁን? የፕሬዝዳንት ሬጋንን ታዋቂ ንግግር አስታውሳለሁ Trust but verify (እመን ግን አረጋግጥ)። የሚለውን። ይሄ የሚነግረኝ ጌታዬን እንደዛ በቅድመ ሁኔታ እንደማምነው ነው። አምነዋለሁ ግን ማረጋገጥ እፈልጋለሁ። ሁልጊዜ ቼክ አደርገዋለሁ። አንዳንዴ የራሴን መንገድ እጠቀማለሁ።



ክርስቲያኖች ግን እንዲህ አልተማርንም። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረን በፍጹም በርሱ ላይ እንድንደገፍ ነው። ይሄ የሚነገረኝ ሰው በእምነት ሲያድግ በእግዚአብሔር ላይ ያለው መደገፍም እየጨመረ እንደሚሄድ ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብን አስታውሱት። እምነት አለኝ የሚል ሥራ ግን የሌለው ሰው የሚያድን እምነት እንደሌለው ነው የነገረን (ያዕ 2፥14)። እምነት አለኝ ብሎ በእምነቱ ያልተደገፈ ሰው እምነቱ ከጌጥነት የተሻገረ ትርጉም የለውም።



ስለ መደገፍ (trust) ትክክለኛ ትርጉም ለማግኘት ብዙ ሞክሬያለሁ፣ ጥቂት የሚቀርብ ነገር ያገኘሁት “ጠንካራ መታመን፣ በዛ መታመን ላይ የተመሰረት ተግባር፣ መደገፍ” የሚል ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ከ150 ጊዜ በላይ መደገፍ (trust) ስለሚለው ቃል ተናግሯል። ስለእስራኤላውያን ማን ይረሳል፣ በአምላኩ በእግዚአብሔር ላይ ለመደገፍ ብዙ የተቸገረ ሕዝብ ነበር፣ ትንቢተ ኢሳይያስ፣ ትንቢተ ዳንኤል፣ ምሳሌ እነዚህ ሁሉ መደገፍ (trust) በሚል ቃል የተሞሉ አይደሉምን? የዮናስ መጽሐፍ በሙሉ በእግዚአብሔር ላይ መደገፍ ስለከበደው ነብይ አይደለምን? ነብዩ ነገሮችን ለእግዚአብሔር ሰጥቶ እንደታዘዘው መተግበር ከእርሱ እውቀት ጋር አልገጥም ብሎት ሲቸገር ነው የምናነበው!

በአዲስ ኪዳን ቅዱስ ጳውሎስ በእግዚአብሔር መታመን ስለሚያስገኘው ተስፋ እና ደስታ ጽፎልናል። (ሮሜ 15፥13)። በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 14፥1 ደግሞ ጌታችን ስለመታመን የሁልጊዜ ምርጤ የሆነውን ቃል ነግሮናል። “ልባችሁ አይታወክ” አለን ጌታችን። “ልባችሁ አይታወክ፤ በእግዚአብሔር እመኑ፥ በእኔም ደግሞ እመኑ።”



ታላቁ የመታመን ምሳሌ የትኛው እንደሆነ ታውቃላችሁ? የቃና ሠርግ ነው። የኢየሱስ እናት ማርያም “የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ አለቻቸው።”ድንግል ማርያም በኢየሱስ ላይ ምንም ጥርጣሬ የላትም። ምንም እንኳ ልጇን ያልተረዳችበት ጊዜ ቢኖርም። ታስታውሳላችሁ ጌታችን የ12 ዓመት ልጅ ሆኖ በመቅደስ ሲያስተምር፣ ከሦስት ቀን ፍለጋ በኋላ እናቱ ድንግል ማርያም እና ዮሴፍ ሲያገኙት የተሰማቸው ስሜት፤ መገረም ነበር፤ ከዛ በፊት ደግሞ የት እንዳለ ስላላወቁ የመጨነቅ ስሜት ወርሷቸው ነበር።



ምንድነው የድንግል ማርያም መታመን በቃናው ሠርግ ያመጣው? ወይን ብቻ መሰላችሁ፤ ከወይን ሁሉ የሚልቅ ወይን፣ ከብዛቱ የተትረፈረፈ፣ ከጥራቱ አቻ የሌለው ወይን የድንግል ማርያም በኢየሱስ መታመን ያመጣው ነው። “የሚላችሁን ሁሉ ስሙት” ነው ያለችው። (ድንግል ማርያም በቅዱስ ገብርኤል የቀረበላት ሠላምታ ግራ አጋብቷት ነበር፤ አንድ ቃል ግን ተናገረች ፥ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለም። በዚህ ዓለም የእግዚአብሔር ሥራ ግር ካላለን ገና ብዙ ነገር አልገባንም ማለት ነው። ማየት አልጀመርንም ማለት ነው። ብዙ፣ በጣም ብዙ የማንረዳው፣ ፈጽሞ የማይገባን ነገሮች አሉ። ግን ለእግዚአብሔር የሚሳነው፣ ለፍቅሩ የሚከብደው ነገር የለም። ይሄ ነው የእመቤታችን እምነት)። በእርሱ ስንደገፍ የምናገኘው ውጤት “ምንም አይልም “ይሁን” “0k” የሚያስብል ውጤት ሳይሆን ፥ እጅን አፍ ላይ የሚያስጭን፣ በዘርፉ ያሉ ባለሙያዎችን (የወይን ጠማቂውን) ጉድ የሚያስብል ነው። ባለሙያዎች ሳይቀር የሚደመሙበት ትሩፋት ነው የመደገፍ ውጤት።


(እግዚአብሔር እንዴት እንደሚሰራ በምልአት ማናችንም አናውቅም፤ ብዙ ጊዜ ያንንም እርሱ አያብራራም። ለኢዮብ መጨረሻ ላይ ሲገለጥለት ለምን እንደተፈተነ፣ ሰይጣን ስለጠየቀው ጥያቄ እና ለምን ያንን እንደፈቀደ ምንም ማብራሪያ አልሰጠውም። ይልቁስ ለኢዮብ ያለው እርሱ አንድን ቁራን የሚመግብ፣ ሰጎን የረሳቻቸውን ልጆቿን የሚያሳድግ እርሱ እግዚአብሔር እንደሆነ ነው የነገረው። ማለትም ለቁራዎች አይደለም፣ በግል ደረጃ ለቁራ የሚጨነቅ አምላክ የፍጥረቱ ሁሉ መደምደሚያ እና የእጆቹ ውብ ሥራ የሆነውን የሰው ልጅ ያውም ኢዮብን እንደምን ሊተወው እንደማይችል ነበር የነገረው። “እምነኝ እኔ የምሰራው ሁሌ ልክ ነው፣ ፍጹም አስብልሃለሁ” ነበር ያለው። ብዙ ጊዜ እግዚአብሔር የሚሰራው ነገር አይገባን ይሆናል፣ በርግጠኝነት ግን የምናውቀው ነገር እርሱ ልክ እንደሆነ ነው። የሆነ ሰው መጥቶ ሕጻናት ሲሞቱ የት ነው የሚገቡት አለኝ፤ አላውቅም አልኩት። አንድ ነገር ግን አውቃለሁ፤ የትም ይግቡ የትም ፥ እግዚአብሔር ልክ ነው።)

ስለዚህ ወንድሞች ሆይ በየቀኑ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ያለንን መደገፍ ለመጨመር እና ለማሳደግ አንሰራምን? በእምነት ቀስ እያልን ግን በየቀኑ እንደግ።



እስቲ እነዚህን ጥያቄዎች ራሳችሁን ጠይቁ፤


፩) ምንድን ናቸዉ በእግዚአብሔር እንዳልደገፍ እንቅፋት የሆኑኝ ምክንያቶች?

፪) በእግዚአብሔር ለመደገፍ ምን እርምጃዎችን (steps) ልውሰድ?

፫) በእግዚአብሔር ስደገፍ ከእርሱ ምን ልጠብቅ? ምንድነው ከእርሱ የምጠብቀው?

መልካሙን ሁሉ በክርስቶስ እመኝላችዋለሁ፤ አካባሪ ወዳጆ።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page