- Mulualem Getachew

- Aug 10
- 4 min read

የሰንበት ዕይታ - 10
የትኛውም ሰዎች ይሄን አድርጉ ሲባሉ ደስ አይላቸውም። ሰዎች በራሳቸው መወሰን እንደሚችሉ እና ሙሉ ነጻነት እንዳላቸው ማመን ይፈልጋሉ። ልጆች እንኳ እንደሚገረፉ እያወቁ አታድርጉ የሚባሉትን ነገር ነው የሚያደርጉት፤ ይሄም የሰው ልጅ በባህሪው ይሄን አድርግ ወይም አታድርግ ሲባል ስለማይወድ ነው። ለራሱ የሚጠቅም እንኳ ቢሆን ከሚታዘዝ ይልቅ ነጻነቱን ይመርጣል።
የማስታወቂያ ሰዎች ይሄን የሰው ልጅ ባህሪ ጠንቅቀው የተገነዘቡ ናቸው። ለዚህ ነው ጥሩ ማስታወቂያ የሚሰሩ ሰዎች ፥ ሰዎች ያን ዕቃን ግዙ ሳይሆን የሚሏቸው በመግዛት የሚገኘውን ደስታ፣ እርካታ እና ጥቅም ነው የሚያሳዩአቸሁ።
ኢትዮጵያ እያለው የተማረ ሰው ቢዝነስ እንደማይችል ይነገር ነበር። በከፊል እውነት ነው። አሜሪካ ስመጣ ግን ፥ በተለይ ቢዝነስ ስኩል ስገባ የአሜሪካ ኢንቬስተሮች አንዳች ነገር ያለዕውቀት እንደማያደርጉ አየሁ። ለምሳሌ በአሜሪካ ውስጥ ከአንድ እስከ ሦስት ያሉ ባለሀብቶች ሁሉም የIQ መጠናቸው መቶ ሀምሳ ወይም ከዛ በላይ ነው፣ በጣም ምጡቆች ናቸው። ይሄን ለምን አነሳው? ምንም ነገር በእውቀት ሲሰራ የተለየ እና ዘላቂ ውጤት እንዳለው ለማሳየት ነው። ለምሳሌ ቢዝነስ የሰውን ስነ-ልቦና በአግባቡ ማወቅ እና ራስን መግዛት ይጠይቃል። ዴቪድ ኦግሊቪ የተባለ ታዋቂ አሜሪካዊ ጸሐፊ ያሳየውን የቢዝነስ ጥበብ እሱም “አሳይ እንጂ አትንገር - Show but don’t tell” የሚለውን እንይ።
ዴቪድ ከቢሮው ሲወጣ አንድ ዓይነ ስውር ለማኝ ሰው በሚመላለስበት መንገድ ላይ “ዓይነ ስውር ነኝ እርዱኝ - I am blind please help” የሚል በካርቶኒ የተጻፈ ማስታወቂያ ይዞ ቁጭ ብሏል። አንድም ሰው ገንዘብ የሰጠው የለም። ለብዙ ሰዓት እንደተቀመጠ ግን ያስታውቃል። ዴቪድ ዓይነስውሩን ተጠጋው እና “ገንዘብ አልሰጥህም ፥ ይሄ ሁሉ ሰው ግን ገንዘብ እይሰጠ እንዲያልፍ ማድረግ እችላለሁ ፥ ከፈቀድክልኝ” አለው። ዓይነስውሩም የሚያጣው ምንም ነገር ስለሌለ “እሺ” አለ ፥ ዴቪዲም የዓይነስውሩን “ዓይነ ስውር ነኝ እርዱኝ” የሚለውን በራሱ ጹሁፍ ለውጦ ሄደ። በጥቂት ደቂቃ ውስጥ ሰዎች ገንዘብ እና ሳንቲያቸውን ለዓይነስውሩ እየወረወሩ ፥ አንዳንዶቹም ከንፈራቸውን እየመጠጡ ያልፉ ጀመር።
ለማኙ በመደነቅ ፥ የሆነ ሰው ሲያልፍ “ወንድሜ እባክህ የተጻፈው ነገር ምን እንደሆነ ትነግረኛለህ?” አለው።
ሰውዬው ያነበበለትን ከመንገሬ በፊት፤ የመጀመሪያው ጹሁፍ ምን ስህተት እንዳለበት ላሳይ። “ዓይነ ስውር ነኝ እርዱኝ”። “ዓይነ ስውር ነኝ” የሚለው መረጃ ነው ፥ ሰዎች ዓይነ ስውር እንደሆነ እያዩ ነው ምንም የተለየ መረጃ አይሰጥም። ከሚያዩት በላይ የሚነግረው ምንም ነገር የለም። “እርዱኝ!” የሚለው ትዕዛዝ ወይም ማድረግ ያለባቸውን የሚነግር ነው። ሰዎች ደግሞ ይሄን አድርጉ ሲባሉ ደስ አይላቸውም። በራሳችን መወሰን እንችላለን ብለው ነው የሚያምኑት ፥ ሁሉም ሰው ለትዕዛዝ ያምጻል ፥ የእግዚአብሔር ትዕዛዝን የሚጥስ ሰው የሰውን ያከብራል ማለት ሞኝነት ነው።
ዴቪድ ኦግሊቪ ለዓይነ ስውር ለማኙ ምንድነው የጻፈው?
“በጋ (spring) ነው፤ እኔ ግን እዚህ ነኝ - “It is spring but I am here”)፣ በአሜሪካ ውስጥ ስፕሪግ ሰዎች እረፍት የሚወጡበት እና የሚዝናኑበት ወቅት ነው፣ በዚህ ወቅት ውጪ እየወጡ መዝናናት የሁሉም ሰው ናፍቆት ነው ምክንያቱም የበረዶ ዘመን ያለቀበት እና ሀሩር ፀሐይ የሚመጣበት መኃከል ነው ስፕሪንግ ያለው። ሰው ሁሉ በዚህ ሰዓት ምኞቱ መዝናናት ነው። ዴቪዲ በስድስት ቃላት የገለጸው ስለዚህ የሰዎች ምኞት ነው። ሁሉም ሰው በስፕሪንግ ደሀ መሆን እና አለመዝናናት አለመቻል እንዴት እንደሚያም ያውቀዋል ፥ ሁሉም ሰው ግን ዓይነስውር ሆኖ አያውቅም። ስለዚህ ዓይነስውር መሆን ምን እንደሆነ አይረዳም። ስለዚህ ለሁሉም ሰው ቅርብ በሆነ ነገር ነው ዴቪድ የሰውዬውን ሕመም የገለጸው። ሁለተኛው ሰዎች ምን ማድረግ እንዳለባቸው አይገልጽም። ያን ውሳኔ ለሰዎ ትቷል። ማሳየት እንጂ የጥሩ አስተዋዋቂ ተግባር ሰዎች ምን ማድረግ እንዳለባቸው መንገር አይደለም።
ስማርት ነጋዴ ልክ እንደ መርማሪ ፖሊስ ነው። የሞተ ሬሳ ጋር ቆሞ ፥ “ምን ቢፈጠር ነው ይሄ ሰውዬ የተገደለው?” ብሎ የሚጠይቅ ማለት ነው። ነጋዴም የመጨረሻውን መልስ ያውቃል። እሱም “እቃውን በሚፈልገው ትርፍ መሸጥ።” “ይሄን ዕቃ ለመሸጥ ምን መፍጠር አለብኝ ፥ ገዢዎቼ ውስጥ ምን ዓይነት ስሜት መቀስቀስ አለብኝ?” ብሎ የሚጠይቅ እና ለዛ ብዙ ነገሮችን የሚሞክር ማለት ነው።
ሰዎች እቃ የሚገዙት ወይም ሰርቪስ የሚጠቀሙት ለመደሰት ነው። ማንም ሰው ለማዘን ምንም ነገር አያደርግም። ደስታ ማለት በሆነ መጠን ከፍርሃት ነጻ መሆን ነው። ስለዚህ ሰዎች ምንድነው የሚፈሩት የሚለውን ማወቅ ያስፈልጋል። ሰዎች ተመሳሳይ ዕቃ ሆኖ ርካሹን ትተው ውዱን የሚገዙት ፥ ስለሚፈሩ ነው። ይሄ ርካሽ የሆነው እውነተኛ ስላልሆነ ነው ፥ ፌክ ስለሆነ ነው በሚል። ሰዎች ውድ እቃ ከመንገድ ላይ የማይገዙት ፥ በመንገድ ላይ የሚሸጠው ሰው ነገ እዛ ቦታ ላይ ስለማይገኝ ነው። የመንገድ ላይ ነጋዴ ደንበኛ መፍጠር የሚል ነገር አያስጨንቀውም። የሚያስጨንቀው እጁ ላይ ያለውን ዕቃ ሸጦ መገላገል ነው። ስለዚህ አጭበርብሮ ቢሆንም ይሸጣል። ሱቅ ያለው ሰው ግን (ቱሪስት ብቻ የሚሄዱበት ቦታ ካልሆነ) ስለነገ ስሙ ይጨነቃል። ደንበኞቹ ነገም ተመልሰው እሱ ጋር እንዲመጡ ይፈልጋል። ስለዚህ ትርፍና መታመንን አብሮ ነው የሚሸጠው። ስለዚህ የማስታወቂያ አንዱ ዓላማ መታመንን መፍጠር ነው።
ሌላኛው ሰዎች አንድን ነገር የሚያደርጉት በሁለት ነገሮች ግፊት ነው። የመጀመሪያው “በልምድ።” ሁለተኛው “ሌሎች ሰዎች ሲያደርጉ ስላየን።”
ሩዝ ሳይሆን እንጀራ በየቀኑ የምንበላው የእንጀራ ጥቅም ስለሚበልጥ አይደለም። በልምድ ከልጅነት ጀምሮ ስለምንበላ እንጂ። ስለዚህ ማስታወቂያ ሰዎች የምንሸጠውን ነገር እንዲለምዱ ማድረግ ፤ ለማስለመድ ደግሞ ከዚህ በፊት ከሚያደርጉት ነገር ጋር ማያያዝ ያስፈልጋል። አንዱ ልምድ የምንፈጥረው የምንሸጠውን ነገር በተደጋጋሚ በማስተዋወቅ ነው። የዛኔ ሰዎች የኛን እቃ ይለምዱታል።
ሁለተኛው ሌሎች ሰዎች ሲያደርጉት ስናይ ነው። ሰዎች ራሳችንን ምክንያታዊ አድርገን ማሰብ ደስ ይለናል። ያ ግን ውሸት ነው። ብዙ የምንሰራቸው ነገሮች ከምክንያት ጋር የሚጋጩ ናቸው። ብዙ ነገራችን “ሰዎችን ኮፒ” ማድረግ ነው። የምንቀናው ራሱ ከእኛ ከሚበልጠው ነገር ግን ከእኛ ብዙ ባልራቀ ሰው ነው፤ ከኛ በቅርብ ርቀት በሀብት በተለየው ሰው ነው። በቢልጌት አንቀናም። ምክንያቱም አንደርስበትም ብለን ስለምናስብ፤ ከእኛ በጣም ሩቅ ስለሆነ። ነገር ግን በጓደኛችን እንቀናለን። ምክንያቱም እሱ ከኛ ጋር አቻ ነው ብለን እናስባለን። ስማርት ነጋዴዎች ይሄን የሰው ባህሪ ጠንቅቀው ያውቃሉ። ስለዚህ የሚሸጡት ነገር በብዙ ሰዎች የተወደደ እንደሆነ ከማሳየት በተጨማሪ፣ የፉኩኩር መንፈሶችን በመቀስቀስ ስነ-ልቦና የተካኑ ናቸው። የሚሸጡት ነገር በብዙ ሰዎች የተወደደ እንደሆነ ያሳያሉ። ታዋቂ ሰዎች የነሱን ዕቃ ሲጠቀሙ ፥ የነሱን ዕቃ መጠቀም ፋሽን መሆኑን ለሰዎች በማሳየት ፥ ሌሎች ሰዎችም መከተለ እንዳለባቸው በጥበብ ያን ስሜት በሰው ልቡና ያሰርጻሉ።
በእንግሊዝ የማስታወቂያ ጂኒየስ የሚባለው ሮሪ ሰዘርላንድ እንዲህ ይላል “ሰዎችን ወደ ሬስቶራንት በማምጣት በሼፉ (ምግቡን በሚሰራው) እና ወለሉን በሚወለውለው ሰዎች መካከል ምንም ልዩነት የለም።” ወደ ሬስቶራንት ሰዎች የሚሄዱት በዋነኝነት ምግብ ለመብላት ቢሆንም ወለሉ ከቆሸሸ ግን ስለምግቡ ያላቸው ምልከታ ዜሮ ይገባል። እውነታው ግን በወለሉ እና በምግቡ መካከል ምንም ግንኙነት የለም። ወለሉ ሌላ ነገር ፥ ምግቡ ሌላ ነገር። የሰው አዕምሮ ግን እንደዚያ አያስብም። ወለሉ ከቆሸሸ ወዲያው ምግቡም ንጹህ አይደለም ብሎ ያስባል። ሊያስታውክ ሁሉ ይችላል።
ልክ እንደዛው ነጋዴዎች ሁሉ በሰዎች ዓዕምሮ ውስጥ ስለሚፈጥሩት ስዕል በጣም መጨነቅ አለባቸው። ለዚህም ሙያ ያላቸውን ሰዎች መጠየቅ፣ ዕይታ ላይ መስራት፣ ማስታወቂያ መስራት ብቻ ሳይሆን ፥ ያ ማስታወቂያ በሰዎች አዕምሮ ውስጥ ስለሚፈጥረው ምስል ማሰብ እና ጥሩ ምስል ከሳች ነገሮችን መጠቀም ወሳኝ የሚሆነው።
በዚህ ጹሁፍ በትንሹ ያሳየውት እንዴት ቢዝነስ የሰዎችን ስነ-ልቦና የማወቅ ጥበብ እና የአዕምሮ ውጤት መሆን እንዳለበት ነው። ይሄ ግን በቢዝነስ ብቻ ሳይሆን በየትኛውም የሕይወት ክፍላችን እና በተሰማራንበት መስክ መጠቀም ያለብን ብልሃት ነው። የሰዎችን ስነ-ልቦና ማጥናት እና ማወቅ በማንኛውም ተግባራችን ፊት-አውራሪ እንድንሆን የራሱ እገዛ ያደርጋል።








