top of page
Search

ችግራችንን እንዴት እንፍታ?

  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 26, 2024
  • 2 min read

ree


ይሄ ከሳምንት የቀጠለ ነው። ባለፈው ሳምንት ችግራችንን እንዴት እንፍታ በሚል ርዕስ መወያየት ከጀመርን በኋላ፤ በግልበጣ አስተሳሰብ (reverse thinking) መሠረት ይሄን አጥርቶ ለመረዳት በተቀራኒው ማሰብ ጥቅም እንዳለው አውርቼያችሁ ነበር። ማለትም ችግራችንን እንዴት አለመፍታት እንዳለብን። የመጀመሪያው ፈጥነን ክርስቶስን ወይም ሃይማኖትን በችግራችን ውስጥ ማስረግ (smuggling Jesus) እንደሌለብን አወራን። ከዛ ደግሞ ጊዜን የችግር ፈቺ አድርጎ አለማቅረብ እና ኋላፊነትን ለገለልተኛ ጊዜ አለመስጠት እንደሚገባ ተነጋገርን። ለዛሬ ችግራችንን እንዴት መፍታት እንደሌለብን የምንነሳው ከዚህ ነው።


3) ፍላጎትን እና እውነትን (reality) መነጠል፤

 

በሕይወት በጣም ወሳኝ ነገር ቢኖር እውነትን እንዳለ መረዳት መቻል ነው። ለዚህ ትልቁ እንቅፋት ፍላጎት ነው። ፍላጎት ብዙ ጊዜ የስሜት ልጅ ነው። በአስተዳደግ፣ በዶግማ፣ በማህበረሰብ እና በፖሮፓጋንዳ እጆች ተኮትኩቶ የሚያድግ እና የፋፋ ነው። ፍላጎት እና እውነትን ማስታረቅ እጅግ ከባድ ነገር ነው። በርግጥ ሰዎች ፍላጎት ባይኖራቸው ለብዙ አስገራሚ ለውጦችም ባልተጋበዙ ነበር። ፍላጎት ነው የብዙ አስደናቂ ግኝቶች ሞተር። በተመሳሳይ ፍላጎት ነው የብዙ መጥፎ ውሳኔዎች ክብሪት። ሰዎችን ለመረዳት ከፈለግን በጥልቀት የገለጡትን እና ያልገለጡትን ፍላጎታቸውን መረዳት ያስፈልጋል። ራሳችንን ማወቅ ከፈለግንም የሚጋልበንን ፍላጎት የተባለ ፈረሰኛ ማንነቱን ማወቅ እና በጥልቀት መገንዘብ ግድ ይላል። ፍላጎት ነው የደስተኛ ሕይወትም ሆነ የሐዘን ደም ሥር።

 

አለመፈለግ አይቻልም። ምክንያቱም አለመፈለግ ራሱ ፍላጎት ነው። አለመፈለግን የሚፈልግ ራሱ አለመፈለግን በመፈለግ ፍላጎት ውስጥ ነው። ከፍላጎት ነጻ መሆን አይቻልም። ማወቅ ያለብን  እውነታን ለመገንዘብ ፍላጎት እንቅፋት እንደሆነ እና ፍላጎትን የሚያህል የእውነት ዕውርነት እንደሌለ መገንዘብ ብቻ ነው። ዓለምን እና በዙሪያችን ያሉትን ነገሮች ሁሉ የምናየው በፍላጎት መነጽር ነው። ይሄን መነጽር እንዳረገ የሚክድን ሰው ያህል አደገኛ ሰው የለም። እኔን ከጠየቃችሁኝ፤ ከዚህ ሰው ጋር በምንም ነገር ባልዋሃድ እና ባልጎዳኝ እመርጣለሁ። ላንተ ስል ነው፣ አንዳች ፍላጎት የለኝም፣ ፍላጎቴ ምንም ሳይሆን ያንተ ፍላጎት ነው ከሚለኝ ሰው ጋር ከመራቅ ውጪ ምርጫ የለኝም። በክህደት ውስጥ መጓዝ ማለት ይሄ ነው።

 

በዚህ የአስተሳሰብ ስሌት ውስጥ ያለ ሰው ራሱን ለመፈተሽ ዝግጁ ስላልሆነ፤ በሌሎች ላይ የሚያየውን ማናቸውምስሜቶች በፍርድ ዓይን ነው የሚመለከተው። ስለዚህ በፍጥነት “ይሄ ሰው መጥፎ ነው፣ ጥሩ ነው፣ ጻድቅ ነው፣ ሉሲፈርነው፣ ገገማ ነው፣ ተንኮለኛ ነው” እና መሰል ቃላቶችን ከፍርድ አዕምሮ አውጥቶ ይናገራል። በዚህም ሌሎችን መረዳት ይሳነዋል። መረዳት ከተሳነን ደግሞ ጥሩ መፍትሔ የመስጠት አቅም አይኖረንም።

 

መቼ መጥፎ ውሳኔ እንደምንሰጥ ታውቃላችሁ? መቼ ነው ከመኪና ጋር የምንጋጨው? ከኋላችን የሚመጣውን ወይም ከጎናችን የሚያልፈውን መኪና ካላየነው የመጋጨት ዕድላችን ከፍተኛ ነው። በተመሳሳይ ሌሎችን ካልተረዳን፣በዙሪያችን ያሉ ሰዎችን በጥልቀት ለመረዳት ካልጣርን፣ ይሄ ማለት ደግሞ ፍላጎታቸውን ካላወቅን ስህተት የመስራት ዕድላችን የትየለሌ ነው። ልክ እንደዛው በራሳችን ውስጥ የሚርመሰመሱ እና ለፈጣን ውሳኔ የሚዳርጉን የፍላጎት ወጠምሻዎችን ካላወቅናቸው፣ መሠረታቸውን ካልተረዳን ከራሳችን ጋር ግጭት ውስጥ የሚከቱን እልፍ ስህተቶችን በሕይወት መንገዳችን መፈጸማችን የማይቀር ነው። ይሄ ማለት ቀናችን እና ጊዜያችን ሁሉ “ለምን እንዲህ አደረኩኝ፣ ምናለ ያኔ እንዲህ አድርጌ ቢሆን ኖሮ፣ ምናለ ዝም ብል፣ ምናለ ያን ነገር ፈጽሜ ቢሆን፣ እጄን በቆረጠው ያኔ፣ ብረጋጋ ምናለ” በሚሉ እና በመሰል ቃላቶች የተሞላ ይሆናል።

 

 ይቀጥላል።

 
 
 

Comments


  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page