የአዕምሮን ካርታ ማደስ
- Mulualem Getachew

- Aug 10
- 3 min read

የሰው ልጆች በሁሉም ወቅት የሚሰራ መመዘኛ የለንም። መመዘኛችን እና የሞራል እይታችን በደረስንበት የእይታ ጥራት እና አድማስ የሚወሰን ነው። ይሄ ማለት ዘመን እና ድንበር ተሻጋሪ የሞራል ልኬቶች (universal values) የሉንም አይደለም። ለምሳሌ ደግነትን የትኛውም ማህበረሰብ በየትኛውም ስፍራ እንደ ጥሩ እሴት ያከብረዋል። ጥያቄው በአንድ ወቅት ደግነት ተብሎ የሚወሰድ ጉዳይ በሌላ ጊዜ ክፋት ሊሆን ይችላል። ይሄ ተቀያያሪ የሆነ የይዘት ሁኔታዎች የሰው ልጅን የመመዘኛ ድክመት ነው የሚያሳየው። ይሄ ማለት ግን ጽንፎችን የሰው ልጅ አያውቃቸውም ማለት ላይሆን ይችላል። ለአንዱ ሙቀት የሆነ ለሌላው ኖርማል የዓየር ጸባይ ሊሆን ይችላል። ግን የትኛውም የሰው ልጅ ላይኖርበት የሚችል የሙቀት መጠን አለ። በሚዛን ደረጃ ጽንፎችን የማወቅ አቅም አለን ማለት ነው። ፍጹም ምቾትን እና ፍጹም የሆነ ስቃይን የማወቅ አቅምም እንደዚሁ። በፍጽምና መኃል ስላሉት ጉዳዮች ግን በትክክል የሚመዝን አዕምሮ የለንም።
ይሄን በሕመም እንየው። ከእግር በታች ሰውነታችን ሕመም ቢደርስበት፤ በዛ ቦታ ያለው የነርቭ ሥርዓታችን ለአዕምሮአችን መልዕክት ያስተላልፋል። መልዕቱን ተከትሎ አዕምሮአችን ያ ቦታ አደጋ ውስጥ እንዳለ በመግለጽ፤ እዛ ቦታ ላይ እብጭ፣ መቅላት እና ሕመም እንዲኖር ያደርጋል። አዕምሮአችን ያን የሚያስተላልፈው ያን ስፍራ ከመጠበቅ አንጻር ነው። ያ ሕመም ያለበትን አካል በመጠቀም የበለጠ እንዳንጎዳው ያሳብጠዋል ወይም ሕመም ያኖራል። የአዕምሮ ተቀዳሚ ሥራ እኛን ከአደጋ መከላከል ነው። ልክ ነኝ ወይም ልክ አይደለውም የሚለው የአዕምሮ ተቀዳሚ ተልዕኮ አይደለም። ተቀዳሚው ተልዕኮ መጠበቅ (protect) ወይም መከላከል ነው።
አንዳንድ ጊዜ ግን አዕምሮ የተሳሳተ ሲግናል ይልካል። ለምሳሌ Complex Regional Pain Syndrome (CRPS) የሚነግረን ምንም እንኳ የታመመው የሰውነት አካል ቢድንም አዕምሮ ግን እስካሁን እንዳልዳነ ሊቆጥረው ይችላል። ስለዚህ እነዛ የሕመም ምልክቶችን በመላክ እብጠት እና መቅላት፣ ሕመም እንዲቀጥል ሊያደርገው ይችላል። ይሄ መጀመሪያ ከደረሰው የሕመም ከባድነት የተነሳ፤ ሰውነታችን ቢድን እንኳ፤ አዕምሮአችን ግን ሕመሙ ላይ ቀርቷል። ከሰውነታችን ጋር አብሮ ራሱን አላሻሻለም። በዚህም የሕመም ሲግናል (ምልክት) በተከታታይ ይልካል።
ለዚህ አንዱ የሚደረገው አዕምሮ እነዛን የሕመም ሲግናሎች መላክ እንዲያቆም ማሰልጠን ነው። አዕምሮአችን በየዕለት ሕይወታችን የሚያደርገው ይሄንን ነው። እኛን የመጠበቅ ተልዕኮ ስላለው፤ ከዚህ በፊት ውሻ የነከሰው ሰው ፥ ለውሻ የሚኖረው ፍርሃት ወደር አይኖረውም። ሁሉም ሰው ውሻውን እየዳሰሰ እርሱ ግን ከዛ ውሻ ይሸሻል። አዕምሮ ይሄን ሰው በማንኛውም ሁኔታ መጠበቅ ስላለበት፤ ከዚህ በፊት በውሻ የደረሰበትን እንዳይረሳ በማድረግ ይጠብቀዋል። ምንአልባት ሰውዬው ለራሱ ማጽናኛ ቃሎችን ሁሉ ሊጠቀም ይችላል። “ውሻ አይወደኝም ወይም የውሻ መወደድ የለኝም” እና የመሳሰሉት እምነቶችን።
ይሄ ግን በግለሰብ ደረጃ ብቻ እንዳይመስላችሁ። በማህበረሰብ ደረጃም በወል አዕምሮ ውስጥም ተመሳሳይ እሳቤዎች አሉ። በፖሊሲም ሊሆን ይችላል። ለምሳሌ ከዚህ በፊት ይገዛ የነበረን ብሔር ሌሎች የማህበረሰብ አካላት ሊፈሩት እና “ከመጣብን የቀደመውን ይደግማል” በሚል ፍርሃት ሊያሳዱት ይችላሉ። ለምሳሌ በሴፕቴምበር አስራ አንድ የደረሰው የሽብር ጥቃት እንዴት በዓለም ላይ ያሉ ሙስሊም ያልሆኑ ማህበረሰቦችን እይታ እንደቀየረ ተመልከቱ። የጥቂት ሰዎች አውሬነት የብዙ ሰዎች ተደርጎ በፖሊሲ ደረጃ ምንም በዚህ ጉዳይ ላይ የሌሉ የእምነቱ ተከታዮች ለአሰቃቂ ጥቃት ተጋልጠዋል።
አሁን በአሜሪካ ውስጥ የምናየው የኢሚግሬሽን ፖሊሲም የዚህ ስሁት ሪያክሽን ውጤት ነው። ጥቂት ከሌሎች ሀገራት የመጡ ሰዎች በፈጸሙት ወንጀሎች ብዙ መልካም ማንነት ያላቸው ሰዎች በጅምላ ይፈረድባቸዋል። ለሁሉም ጥላቻ ይኖራቸዋል። “ለምን እንደዚህ ታደርጋላችሁ?” ሲባሉ፤ አንድ ሰነድ አልባ ስደተኛ የሆነ ቦታ እና ጊዜ ያደረገውን ወንጀል እንደ ምክንያት ይጠቅሳሉ። ይሄ የሲግናል ግራ መጋባት ነው። ብዙ ጊዜ ለዚህ የሚዳረጉ ሰዎች የተጋላጭነት መጠናቸው በጣም ጠባብ የሆኑ ናቸው።
በቅርብ አንዱ ከኢትዮጵያ ስለ ካቶሊክ ቤተክርስቲያን ለክርስትና መስፋፋት እንቅፋት እንደሆነች ጻፈ። ይሄ ሰው ምን አልባት ከአዲስ አበባ የዘለለ የሕይወት ተጋላጭነት የለው። ስለ ካቶሊክም የሰማው ከኢትዮጵያ ወጥተው በማያውቁ ሰዎች ከተጻፉ መጽሐፎች ይሆናል። አውሮፓ በየሀምሳ ሜትሩ ቤተክርስቲያንን የተከለች፣ በቢሊዮን የሚቆጠር አማኝ ያላት ቤተ እምነት እንደሆነች ምንም እውቀቱ የለውም።
አንድ ወዳጄ ስለነጮች ያለው አመለካከት በጣም ጠባብ ነው። የእኔ ጥያቄ የነበረው “ምን ያህል ነጭ የቅርብ ወዳጅ አሉህ? ወይም በበዓል ቀናቸው የምትሄድበት ነጮች አሉ? ወይም የሴት ጓደኛ ከነጮች ይዘህ ታውቃለህ? የሚል ነበር። መልሱም የሉኝም። አላውቅም ነበር።
ለComplex Regional Pain Syndrome (CRPS) የሚመከረው ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? የተጎዳውን የሰውነት ክፍል ለተለያዩ ቴምፕሬቸሮች፣ ንክኪ እና እንቅስቃሴ ማጋለጥ ነው። በዚህም አዕምሮ ቀስ እያለ ያ ቦታ መዳኑን ይማራል። ስለዚህ ቀስ እያለ የስህተት የሕመም ሲግናሎችን መላክ ያቆማል ማለት ነው።
ትግሬን ወይም አማራን ወይም ኦሮሞን የሚጠላ ሰው የምመክረው፣ ወጥቶ ከእነዚህ ብሔሮች ብዙ ወዳጆች እንዲያፈራ ነው። ቀስ እያለ ያለው አስተሳሰብ ፍጹም ከእውነት የተቃረነ እንደሆነ ይማራል። ለምሳሌ በወንድ የተደፈረች ሴት ሁሉም ወንዶች መጥፎ እንደሆኑ ልታስብ ትችላለች። ከዚህ ስሁት አስተሳሰብ ብቸኛ የሚያወጣት ራሷን ለሌሎች ወንዶች ስታጋልጥ ነው። ፍርሃትህን በመጋፈጥ ብቻ ነው የምታሸንፈው። ይሄም የአዕምሮ ካርታን (GPS/Map) ማደስ ይባላል። አዕምሮአችን የሆነ ቦታ ለመድረስ የሚያውቀው GPS (Map) አለው። ያ GPS (map) አሁን ላይ አይሰራም። ዓለም ተቀያይሯል። ቁስሎች ድነዋል። ግን አዕምሮአችን ያው የጥንቱ GPS (map) ላይ ነው። ያንን እንዲቀይር ማድረግ የሚቻለው ቦታዎቹ ላይ በመሄድ (exposing the brain) የተለወጠውን ነገር በግድ በማሳየት ነው። አለበለዚያ ግን ከእውነት የራቁ እና ለሕይወት እንቅፋት የሆኑ ውሳኔዎችን እየወሰንን እንቀጥላለን።






Comments