
1. ለራሳችሁ ሥራ አስኪያጅ ተደርጋችሁ ብትሾሙ ምንድነው የምታደርጉት?
ራስሽን እንደ አንድ ለትርፍ እንደተቋቋመ ድርጅት ተመልከቺ። ስምሽ ምህረት ነው እንበል። ምህረት ለምትባት ትርፍ ማምጣት ግዴታዋ ለሆነ ድርጅት፤ የድርጅቱ ቦርድ ሥራ አስኪያጅ አድርጎ ሾመሽ። አሁን ሥራሽ የሚሆነው በመስሪያ ቤቱ ውስጥ የማይሰራን ነገር ማሶገድ ፥ ትርፍ ሊያመጡ የሚችሉ ነገሮችን ማብዛት ነው። መስሪያ ቤት ስለሚሆን ስሜት የለውም። ትርፍ እና ኪሳራን መለካት በጣም ቀላል ነው። ስለዚህ ውሳኔዎችሽ በሜትሪክስ የተለኩ ናቸው። በእኔ አስተዳደር ይሄን መስሪያ ቤት ትርፍ በትርፍ አደርገዋለሁ ብለሽ ተነሳሽ። ግን ደግሞ የረጅም ጊዜ ትርፍ እንጂ የምትፈልጊው ለጊዜው ብቻ ትርፍ አግኝተሽ የአንድ ዓመት ድርጅት ማድረግ አትፈልጊም። ስለዚህ ጠንካራ ሠራተኞችሽን ትንከባከቢያለሽ። ደካማ ሠራተኞሽን በቶሎ ትቀንሺያለሽ። እስቲ ራስሽን እንደዛ ብታስቢ ምንድነው ፈጥነሽ የምታሶግጂው? ምንድነው በብዛት የምታደርጊው? የቱ ነገሮች ናቸው ለረዥም ጊዜ ስኬትሽ ዋጋ ያላቸው?
2. ትኩረትን መጨመር
ልህቀት ማሶገድን ይፈልጋል።
ብዙ ሰዎች በሕይወት ውስጥ የማይገቡበት የቢዝነስ እና የፕሮፌሽን መዓት የለም። ራሳቸውን በሁሉም ዘርፍ መለጠጥ ይወዳሉ። ሁሉም ነገር ትኩረት የሚፈልግ ሲሆን ምንም ነገር ትኩረት አያገኝም። ስኬታችን እሺ ከምንለው ነገሮች በላይ እንቢ በምንላቸው ጉዳዮች የተወሰነ ነው። አስር ነገሮችን ዘርዝሩ። በጣም ለእናንተ ወሳኝ የሆኑ ጉዳዮች። ከዛ ውስጥ ሦስቱ ላይ ብቻ አተኩሩ። ሦስቱ ነገሮችን ብቻ ከዛ ውስጥ ለማተኮር ሞክሩ።
3. መዘውሩን አታቁሙት
ማስተላለፍ ሕልምን በጸጥታ የሚገድል ነው።
የምናስተላልፈው ሁሉንም ደረጃዎች አሁኑኑ መውጣት አለብን ብለን ስለምናስብ ነው። ሥራችንን ሁሉ በደረጃ እንክፈለው። አንድ ደረጃ ከዛ ደግሞ ሌላኛውን ደረጃ ለመውጣት እናስብ። ማራቶኑን ሥራ በአንድ እና በሁለት ኪሎ ሜትሮች ከፋፍሉት። ስኬት የሚጀምሩ ሰዎችን ነው የሚሸልመው የሚጠብቁ ሰዎች ሳይሆን።
4. የማንነት ሰርክል
አንተ በዙሪያ የከበቡህ ሰዎች አቭሬጅ ነህ። እኔ ሰዎችን የምለካው ከሚውሉበት አካባቢ በመነሳት ነው። እኛ ማለት ጊዜያችንን የምናሳልፍበት ነን። አካባቢህ ወደፊት መሆን የማትፈልገው ሰዎች ጥርቅም ካልሆነ በፍጥነት ያን ቦታ ለመልቀቅ ሞክር።
ጊዜዬን የምሰጣቸው ሰዎች እጅግ የማክብራቸው ወይም ሊታገዙ የሚችሉ ሰዎች ብቻ ናቸው። ጊዜዬን እንደማቃጠል የሚቆጨኝ ነገር የለም። አዕምሮዬን እና መንፈሴን የማያንጹ ቦታዎች እና ሰዎች ከእኔ ሕይወት ውስጥ በፍጥነት እንዲወጡ ነው የምፈልገው። በዚህ የሚመጣብኝን የወቀሳ ድንጋይ እንደ ሰማዕቱ እስጢፋኖስ በደስታ ነው የምቀበለው።
አስተውሉ፦ ምንም ጥቅም የሌላቸውን ወዳጅነቶች ማሶገድ የዕድገት ሀ ሁ ነው።
5. አታካብድ
ስኬታማ ሰዎች ነገሮችን ማቅለል የሚወዱ ናቸው። በርግጥ አንዳንድ ነገሮች መቅለል ከሚገባው በላይ አይቀሉም። ራሳችሁን ይሄን ጠይቁ፦ ሕይወትን በማክበድ ነው ወይስ በማቅለል ነው እየኖርኩት ያለውት? ለምሳሌ ሰው ምክር ሳይጠይቀን መምከር ሕይወትን በማክበድ መኖር ማለት ነው። ለዚህ ሰውዬ እኛ ጥቅም ነው ያልነውን ነገር እየጋትነው ነው! በተመሳሳይ በጣም ደክሞን ከባድ ውሳኔዎችን መወሰን ወይም ጠንካራ ውይይቶችን ከፍቅር አጋራችን ወይም ከወዳጆቻችን ጋር ማድረግ ሕይወትን በከባድ ሁኔታ መኖር ማለት ነው። በየቀኑ ቢያንስ ለሰላሳ ደቂቃ ስፖርት መስራት ቀላል ሕይወትን ለረዥም ዘመን ለመኖር መወሰን ነው። አምሽቶ መተኛት የነገውን ቀን መጥፎ በማድረግ ሕይወትን በነጋታው አክብዶ ለመኖር እንደመወሰን ነው።
እስቲ አንድ ነገር ዛሬ ብትቀይሩ ነገን የተሻለ ሊያደርግ የሚችለው ምንድነው?
6. የተግባር ዕቅድ
የጊዜ ገደብ የሌለው ዕቅድ ተራ ሕልም ነው።
ማስፈጸም የማይችል ሰው ሕልመኛ ነው። መፈጸም የሚችሉ ሁሉ የቻሉት ለተግባራቸው የጊዜ ገደብ ስላበጁለት ነው።
7. ማወቅ የምፈልገው የምሞትበትን ቦታ ነው ፥ ወደዚያ ላለመሄድ።
ሁላችንም የሆነ መጥፎ ዝንባሌ አለን። አንዳንድ ሰው ለገንዘብ በጣም ስሱ ልብ አለው። አንዳንድ ሰው ለሴሰኝነት። አንዳንድ ሰው ለክብሩ። አንዳንድ ሰው ለመጠጥ እና ለሱስ። እነዚህ ሰዎች ይሄን ደካማ ጎናቸውን በቶሎ ተረድተው፤ ገደብ ካላበጁለት የሚሞቱበት ቦታ ያ ነው። እንደ ቶሎስቶይ የመሬት ነጋዴ ፥ በቃኝ ማለት አቅቶት መሬት ለመሰብሰብ ሲዳክር ሞተ። አንዳንድ ሰዎች ገንዘብ ያለበት ቦታ ሁሉ ይገባሉ። ለጥቂት ትርፍ ብለው የሞት ቀጠና ውስጥ ይደንሳሉ። አንዳንድ ሰዎች ለክብራቸው ሲሉ የውርደት ሞት ይሞታሉ። አንዳንድ ሰዎች ሴሰኝነት ድካማቸው ስለሆነ፤ ሴቶች ይጫወቱባቸዋል። የት ነው የምሞተው ብሎ መጠየቅ ወሳኝ ነው። የቱ ነው ደካማ ጎኔ? ስሱ ብልቴ። ወደ ዛ እንዳልሄድ።
Kommentare